Monday, October 31, 2016

“እመ አምላክ ድንግል ማርያም”

© መልካሙ በየነ

ጥቅምት 21/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================
እመ አምላክ (የአምላክ እናት) ድንግል ማርያም፡፡ ይህ አገላለጽ ከእናታችን ከቅድስተ ቅዱሳን ከወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም ውጭ ለማንም ለማን የማይነገር ብቸኛ አገላለጽ ነው፡፡ እናትነትን ከድንግልና ጋራ አስተባብራ የምትገኝ ሴት ከድንግል ማርያም ውጭ በየትኛውም ዓለም ውስጥ አትገኝም፡፡ እም ወድንግል ቢሉ የአዳም ተስፋ ምክንያተ ድኅነታችን የገነት በር የተከፈተባት እናታችን ብቻ ናት፡፡ ይህ ነገር ከሰው ኅሊና በላይ ነው፡፡ አእምሯችን ምጡቅ ሥራችን ረቂቅ ነው የሚሉ ጠቢባን ሁሉ ይህንን ነገር ሊረዱት አይችሉም፡፡ ምክንያቱም እናት እና ድንግል ሲባል መስማት ለጆሮም እንግዳ ነውና፡፡ ሌሎች ሴቶች ድንግል ከተባሉ እናት፤ እናት ከተባሉም ድንግል መባል አይችሉም፡፡ በምንም ተአምር ይህንን ማስተባበር አይችሉም፡፡ ከዓለም መፈጠር በፊት በአምላክ ኅሊና ተስላ የነበረች ንጽሕት ዘር እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ይህንን አስተባብራ ከፍጥረታት ሁሉ ልቃ ተገኘች፡፡ አስቡት ይህንን ድንቅ ምሥጢር! ይህ ነገር እኮ ከእኛ ኅሊና በላይ ወደ ላይ ብንወጣ የማናገኘው፣ ወደ ታች እመቀ እመቃት ወደ ጥልቁ ብንወርድ የማንረዳው፣ ወደ ዓለም ዳርቻ ሁሉ ብንበርር የማንገነዘበው  ምጡቅ ነው፡፡ ለዚህም ነው የእናታችን ምስጋና የበዛለት አባ ኤፍሬም “ኦ ዝ ነገር” በማለት በአንክሮ የሚናገረው፡፡ እውነት ነው ነገሩ ይረቃል፣ ነገሩ ይደንቃል፣ ነገሩ ይከብዳል፣ ነገሩ ለመረዳት ያስቸግራል፣ ነገሩ እጹብ እጹብ ብቻ የሚባል ነው፡፡

ሴቶች ልጅ በመጽነሳቸው ደስ ይላቸዋል በመውለዳቸው ደግሞ አብልጠው ደስ ይላቸዋል፡፡ ከዚህ ሁሉ ደግሞ ወንድ ይወለድላችኋል ሲባሉ ደስ ይላቸዋል፡፡ አያችሁት የእናታችንን ደስታ! በመልአኩ ብሥራት ትጸንሻለሽ መባል ምንኛ ያስደስታል!!! ይህንንማ ሌሎች ሴቶችስ የሚያገኙት አይደለምን ቢሉ፡፡ ሌሎች ሴቶች ትወልዳላችሁ ቢባሉ ነቢይ ነው በዚያ ይደሰታሉ፡፡ ሌሎች ሴቶች ትወልዳላችሁ ቢባሉ ሐዋርያ ነው በዚያ ይደሰታሉ፡፡ ሌሎች ሴቶች ትወልዳላችሁ ቢባሉ ቅዱስ አባት ቅድስት እናትን ነው በዚያ ይደሰታሉ፡፡ ሌሎች ሴቶች ትወልዳላችሁ ቢባሉ ጳጳስ ሊቀጳጳስ ካህንን ነው በዚያ አብዝተው ይደሰታሉ፡፡ እናታችን ግን ትወልጃለሽ ብትባል የሰማይ እና የምድር ጌታን እርሷንም የፈጠራትን አምላክ ነው፡፡ ይህ ያስደስታል! በዚህም ላይ ድንግልናን ከእናትነት ጋራ ማስተባበር ምንኛ ያስደስት፡፡ ይህ ድንቅ ነገር የተደረገው ለእናታችን ለድንግል ማርያም ብቻ ነው፡፡ ፈጣሪን ጸንሶ መውለድ ምንኛ ረቂቅ ምሥጢር ነው? ይህ ረቂቅ ምሥጢር በድንግል ማርያም ሲደረግ ስናይ እናታችንን አብዝተን ወደድናት አብዝተንም አደነቅናት አብዝተንም ተስፋችን አልናት፡፡ አብዝተን ስንደነቅ አብዝተን ስንወዳት አብዝተን ተስፋችን ነሽ ስንላት ግን ቅንጣት ታህል የምንጨምርላት ነገር ኖሮ አይደለም ነገሩ ቢረቅብን ነው እንጅ፡፡ በእውነት በእናታችን ፍቅር ተነድፈን አፋችን ለዘለዓለም ድንግል እናቴ ድንግል እናቴ አማልጅኝ ሲል ቢኖር ምንኛ በታደልን! ከእናታችን ፍቅር ርቀው የሚኖሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ ፍቅሯ ጣዕሟ ባይገባቸው ነው፡፡ ቢገባቸውማ እናቴ ለማለት ቅጽበት ባልወሰደባቸውም ነበር፡፡ አምላካችን ፈጣሪያችን ከእናቱ ከእናታችን ከድንግል ማርያም ረድኤት በረከት ያሳትፈን፡፡


Friday, October 28, 2016

“ሳይሆኑ እንዲሆኑ መምከር”

© መልካሙ በየነ

ጥቅምት 18/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================

“መሆን ደስ ይላል መምሰል ግን ያስጠላል” ይሉኝ ነበር አንድ አባት፡፡ ለጊዜው ነገራቸው አልገባኝም ነበር እየቆየ በሕይወቴ ውስጥ ሳየው ግን ገባኝ፡፡ ብዙዎች ያውቁኛል፤ ምን ማወቅ ብቻ ያደንቁኛልም እንጅ፡፡ ያወቁኝ እና ያደነቁኝ ግን በማወቄ ሳይሆን በመታወቄ ነበር፡፡ ለመታወቅ ደግሞ መሆን ላያስፈልግ ይችላል፡፡ አረ ልክ ነው መምሰል ለመታወቅ በቂ ነው፡፡ አሁን ገና አንድ ነገር ትዝ አለኝ፡፡ ለመታወቅማ መምሰልም ላያስፈልግ ይችላል አሉ፡፡ አወ ልክ ነው፡፡ በዚያ ቀደምለት አንዱ ለመታወቅ ሲል ታዋቂዎችን ሲገርፍ ነበር አሉ፡፡ በታዋቂ ሰዎች ትክሻ ላይ ተንጠልጥለህ ታዋቂነትህን ለመጎናጸፍ በቻልከው መጠን በስድብ መወረፍ ነው አሉ፡፡ ታዋቂዎችን ካልተሳደብክ አትታወቅም፡፡ ብታመሰግናቸው ማንም አያውቅህም ምክንያቱም እልፍ ህዝብ ያመሰግናቸዋልና፡፡ ስለዚህ በቻልከው መጠን ብዙ ተከታይ ያላቸውን ሰዎች በስድብ ናዳ ትቀጠቅጣቸዋለህ ለጊዜው እብድ ሊሉህ ቢችሉም ከጊዜ በኋላ ግን ታዋቂ ትሆናለህ፡፡ ይሁዳ እንዲህ ስመ ገናና ሆኖ ዓለም ሁሉ ሲጠራው የሚውለው እኮ ጽድቅ ስለሰራ አይደለም ጌታውን ስለሸጠ እንጅ፡፡ በእርሱ ምትክ የተተካውን ሐዋርያ ማትያስን ማን ይጠራዋል? በዓለም ዘንድ የይሁዳን ያህል እውቅና ያገኘ አይመስለኝም፡፡ መንገድ ዳር ሄደህ ይሁዳ ማነው ብትል ጌታውን በ30 ብር የሸጠ ሰው ነው ይሉሃል፡፡ ማትያስ ማነው ብትል ግን ማንም አይመልስልህም፡፡ ይሁዳ ሁሉን አዋቂ በሆነው በሁሉም ዘንድ ስሙ በደረሰው አምላክ ላይ ስለተነሣሣ ነው ታዋቂ የሆነው፡፡ ዛሬም ይህንን ፈለግ ይዘው ሆነው ሳይሆን መስለው የሚኖሩ ሰዎች የራሳቸውን ታዋቂነት ለመጨመር ብቻ ያልተደረገውን ተደረገ እያሉ ያለማስረጃ አደባባይ ላይ በስድብ የሚቀጠቅጡ ሰዎች አሉ፡፡

እኔ አስመሳይ የለመለመ ዛፍ ነኝ፡፡ ቅጠል አለኝ ፍሬ ግን የለኝም፡፡ ለተራበ አጓጓለሁ ነገር ግን ከእኔ ፍሬን አያገኝብኝም፡፡ ምናልባት ለጥላነት ሊጠቀምብኝ ይችል ይሆናል፡፡ ብዙ ዛፎች የቅጠሌን ማማር ተመልክተው እንደአንተ እንድናምር ምን እናድርግ ይሉኛል፡፡ እኔም ፍሬ ያለኝ መስየ እንደ እኔ ቅጠላቸው እንዲያምር እመክራቸዋለሁ፡፡ ከዚህም በበለጠ እኔ ማፍራት ያልቻልኩትን ፍሬ እንዴት እንደሚያፈሩ ሁሉ እመክራቸዋለሁ፡፡ ያልሆንኩትን ሁኑ እያልኩ ስመክር ውስጤ ይረበሻል፡፡ አዋቂ አይደለሁም በዚህ መካሪነቴ ግን ብዙዎች ያውቁኛል፡፡ አልጾምም ሰዎች እንዲጾሙ ግን እመክራለሁ፡፡ አልሰግድም ሌሎች እዲሰግዱ ግን እመክራለሁ፡፡ አልጸልይም ሌሎች እንዲጸልዩ ግን አስተምራለሁ፡፡ አልመጸውትም ሌሎች እንዲመጸውቱ ግን እወተውታለሁ፡፡ አልቆርብም ሌሎች እንዲቆርቡ ግን አስተምራለሁ፡፡ ንስሐ ገብቼ አላውቅም ሌሎች እንዲገቡ ግን ሥርዓት አስተምራቸዋለሁ፡፡ እኔ እቅማለሁ አጨሳለሁ ሌሎች እንዳይቅሙ እንዳያጨሱ ግን አስተምራለሁ፡፡ እኔ ከመጠን በላይ እጠጣለሁ እሰክራለሁም ነገር ግን ሌሎች እንዳይሰክሩ አስተምራለሁ፡፡ አያችሁኝ ሳላችሁኝ! እኔ ማለት ነጠላየ በጣም የነጣ ልቡናየ በኃጢአት ብዛት የገረጣ ሰው ነኝ፡፡ የማስበው ኃጢአትን ነው፡፡ አፌ ይሰብካል ነጠላየ ይመሰክራል ውስጤ ማንነቴ ግን የሲዖልን ደጅ የሚያንኳኳ ነው፡፡ በአፌ እመርቃለሁ በልቤ እረግማለሁ፡፡ የእኔ ክርስትና ከነጠላ የዘለለ አይደለም፡፡ በልቤ የሸፈትኩ ወንበዴ ነኝ፡፡ በዝሙት አልጋ ውስጥ ተደብቄ እኖራለሁ፡፡ በዋዘኞች ወንበር ላይ ተቀምጨ አንቀላፋለሁ፡፡ ፍርዴ ደሃን ያስለቅሳል፤ እጀ ደምን ያፈሳል፡፡ እግሬ ለስርቆት ይገሰግሳል፤ ልቤ ኃጢአትን ያመላልሳል፡፡ በሰዎች ሃብትና ንብረት ዓይኔ ይቀላል፤ በወንድሜ ላይ እቀናለሁ በእህቴ ላይ አመነዝራለሁ፡፡ እናቴን እደበድባለሁ አባቴን እገድላለሁ፡፡ እንደዚህ ባደርግም ግን ስለ ጽድቅ እመክራለሁ፡፡ ምክንያቱም ታዋቂነትን ስለምሻ፡፡

ባልሆንኩበት ጠባይ ሌሎች እንዲሆኑ እመክራለሁ፡፡ እኔ ኃጢአተኛ ነኝ ስለጽድቅ እመክራለሁ፤ እኔ አልጾምም ጹሙ ብየ ግን እመክራለሁ፡፡ በጣም የሚገርሙኝ ግን እኔን ምከረን የሚሉኝ ሰዎች ናቸው፡፡ እኔ ለራሴ መቸ ሆንኩና ነው መካሪ የምሆነው? በእርግጥ የእኔን ድፍረት ተመልክተው እንደሚሆን እገምታለሁ፡፡ እኔ ከፈጣሪየ ጋር ሳልታረቅ ሰዎችን ታረቁ የምል ከንቱ ፍጥረት ነኝ፡፡ እናንተ ቅጠሌን አትመልከቱ ፍሬ አልባ ነኝና፡፡ እናንተ የምትሹ ፍሬ ማፍራትን ነው እኔ ግን ቅጠል ብቻ ነኝ፡፡ ታዲያ እኔ ያላፈራሁትን ፍሬ ታፈሩ ዘንድ እንዴት ልመክራችሁ እችላለሁ?


  

Friday, October 21, 2016

“አጽናኑ ሕዝቤን አጽናኑ” ኢሳ 40÷1

© መልካሙ በየነ

ጥቅምት 10/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================
በመጀመሪያ ይህንን እንደ ርእስነት እንድጠቀምበት በውስጥ መስመር ለላከልኝ ፀገየ ባዩ አመሰግናለሁ፡፡
“አጽናኑ ሕዝቤን አጽናኑ” ኢሳ 40÷1 ይህንን ቃል የተናገረው አምላካችን እግዚአብሔር ነው፡፡ ቃሉ የተነገረው በዘመኑ ለነበሩት የሕዝብ መሪዎች ለሆኑ ነቢያት እና ካህናት ቢሆንም ፍጻሜው ግን በዘመናችን ላሉ የሃይማኖት አባቶች ሁሉ ነው፡፡ እዚህ ላይ በዋናነት ሁለት ነገሮችን ማንሣት ተገቢ ነው ብየ አምናለሁ፡፡ የመጀመሪያው እግዚአብሔር ሕዝቤ የሚላቸው እነማንን ነው የሚለው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ማጽናናት ምንድን ነው የሚለው ጉዳይ ነው፡፡ እግዚአብሔር በመጀመሪያ ከፍጥረት ሁሉ አክብሮ እና አብልጦ ሲፈጥረን የመንግሥቱ ወራሾች የሥሙ ቀዳሾች እንድንሆን እንጅ በከንቱ እንድንጠፋበት አይደለም፡፡
የእግዚአብሔር ሕዝብ የሚባለው በእግዚአብሔር አምላክነት የሚያምንና በእግዚአብሔር ትእዛዝ የሚመራ ነው፡፡ ለዚህም ማስረጃችን እግዚአብሔር ሙሴን አሥነስቶ  እስራኤላውያንን ከግብጽ ባርነት ነጻ ሊወጣቸው በወደደ ጊዜ የግብጹን ፈርዖን “ህዝቤን ልቀቅ” ብሎታል፡፡ እነዚህ በግብጽ ባርነት ውስጥ አገዛዝ የከበዳቸው እስራኤላውያን በእግዚአብሔር አምላክነት የሚያምኑ እና በእግዚአብሔር ትእዛዝና ሥርዓት የሚመሩ ነበሩ፡፡ ለዚህም ነው እግዚአብሔር “ህዝቤ” የሚላቸው፡፡ ከዚህ በኋላ የነጻነት ጉዞውን በሙሴ መሪነት ጀመሩ፡፡ የኤርትራን ባህር ከፍሎ አሻገራቸው፡፡ አሁን ሲና ተራራ ላይ ደርሰዋል ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ቃል ለቃል ሊነጋገር ወደ ተራራው ወጥቷል፡፡ ሙሴ በጣም እንደዘገየባቸው ሲረዱ ሕዝበ እስራኤላውያን “ሙሴ አመሌ አመሌ ሲል እሳት አቃጥሎት ሞቶ እንደሆነ አናውቅማና አምላክ ሥራልን” ብለው ወንድሙ አሮንን አስቸገሩት፡፡ አሁን ህዝበ እስራኤላውያን አምላካቸው እግዚአብሔር እንደሆነ ዘንግተዋል፡፡ የሚገርመው ነገር “አምላክ ሥራልን” ማለታቸው ነው፡፡ እግዚአብሔር ባህረ ኤርትራን ከፍሎ አሻግሮ፣ መና ከደመና እያወረደ መግቦ ውኃ ከጭንጫ እያፈለቀ አጠጥቶ፣ ዋዕየ ፀሐይን በደመና ከልሎ እየመራቸው ለዚህ ደርሰዋል እነርሱ ግን ይህንን ሁሉ ውለታ ዘነጉ፡፡ አሮንም ከግብጽ ስትወጡ ይዛችሁት የመጣችሁትን  ንብረታችሁን ሰብስቡ አላቸው፡፡ ለገንዘባቸው ቀናዒ ናቸውና አንሰጥህም ይሉኛል ጊዜ አገኛለሁ እስከዚያ ድረስም ወንድሜ ይመጣልኛል አርፋቸዋለሁ ብሎ ነበር፡፡ እነርሱ ግን ወዲያውኑ ገንዘባቸውን ሰብስበው “አምላክ ሥራልን” አሉት፡፡ አርሱም ጉድጓድ አስምሶ እሳት አስነድዶ ወርቅ ብራቸውን ከዚያ ላይ ጣለው የጥጃ ምስል ሆኖ ወጣላቸው፡፡ አምላካችን ይኼ ነው ብለው ዘፈኑለት ሰገዱለት መስዋእት ሰውለት፡፡ በዚህ ጊዜ  እግዚአብሔር “ሙሴ ህዝብህ በደለኝ” አለው፡፡  ቅድም “ህዝቤ” ያላቸውን አሁን “ህዝብህ” አለው ጠብ ተጀመረ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ህዝብነት ዝም ብሎ የሚኖር የባሕርያችን አይደለም ማለት ነው፡፡ ጠቅለል ሲል ህዝብ ማለት በእግዚአብሔር የሚያምን፣ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ የሚጠብቅ፣ በእግዚአብሔር ሥርዓት የሚኖር ማለት ነው፡፡

ሁለተኛው ጉዳይ “ማጽናናት” የሚለው ነው፡፡ ይህ ህዝብ ያዝናል፣ ይተክዛል፣ ይራባል፣ ይጠማል፣ ይሰደዳል፣ ይገደላል፣ ሃብት ንብረቱ ይዘረፋል፣ በበሽታ ይሰቃያል፣ ይታሰራል፣ ይንገላታል ወዘተ፡፡ በዚህ ጊዜ እንባውን አባሽ፣ መካሪ፣ አይዞህ ባይ ይሻል፡፡ ማጽናናት ሃዘንን ማስረሳት ነው፡፡ ማጽናናት ችግሩን መፍታት ነው፡፡ ማጽናናት አይዞህ አለንልህ ብቻህን አይደለህም ብሎ ከጎኑ መቆም ነው፡፡ ማጽናናት ሲራብ ማብላት ሲጠማ ማጠጣት ሲታረዝ ማልበስ ነው፡፡ ማጽናናት የጠፋበትን ሃብትና ንብረት መተካት ነው፡፡ ማጽናናት ማለት የሚያድርበትን የሚያርፍበትን ጎጆ መቀለስ ነው፡፡ ማጽናናት ማለት ከኃጢአት ባርነት መመለስ ነው፡፡ ማጽናናት ማለት ንስሐን ማስተማር ነው፡፡ ማጽናናት ማለት የተስፋ ቆራጭነትን ስሜት ማጥፋት ነው፡፡ ማጽናናት ማለት ተስፋን ማለምለም ነው፡፡

እግዚአብሔር “አጽናኑ ሕዝቤን አጽናኑ” ኢሳ 40÷1 ሲል ከላይ በተመለከትነው መልኩ ነው፡፡ እነዚህ የእግዚአብሔር ህዝቦች በሥጋቸውም በነፍሳቸውም እግዚአብሔርን ሲያመልኩ እንዲኖሩ፣ በፍቅር በደስታ ምድርን እንዲሞሏት፣ መከራ ጭንቀታቸውን እንዲረሱ፣ ኃጢአታቸውን ትተው ወደ ጽድቅ እንዲመለሱ አድርጉ ማለቱ ነው፡፡


አባቶቻችን ዛሬም እኛ ከሃዘናችን፣ ከመከራችን፣ ከስቃያችን ሁሉ እንድንጽናና ምክራችሁ ትምህርታችሁ ያስፈልገናል፡፡ ማጽናናት እንደማስለቀስ እንደማሳዘን ቀላል አይደለም፡፡ ልቡ የተሰበረን ህዝብ አጽናኑ፣ የእኛ ተስፋ ነገ ብቻ ነው፡፡ ነገ አዲስ ቀን ነው ነገ ይችን ምድር ተሰናብተን ለዘለዓለም የምንሄድበት ቀን ነው፡፡ ነገ እንደ ሥራችን ገነት ወይም ሲዖል የምንገባበት ነው፡፡ ዕድሜ ዘመናችንን በምድር ላይ አናሳልፍም፡፡ እርስ በርሳችን አንጠላላ፣ እርስ በርሳችን አንገዳደል፣ አርስ በርሳችን አንወቃቀስ፣ እርስ በርሳችን ቂም በቀል አንያዝ ሁላችንም ነገ ከመቃብር በታች ነን፡፡ ይች ምድር አትጥበበን ነገ ጥለናት የምንሄድ ሰዎች ነን፡፡ ሁላችን በፍቅር እንተያይ፡፡ አባቶቻችን ካህናት፣ ጳጳሳት ሆይ “አጽናኑ ሕዝቤን አጽናኑ” ይላል እግዚአብሔር፡፡ ሃዘናችንን አስረሱን፣ ኃጢአት በደላችንን በንሥሐ እጠቡት፣ ፍቅር ማጣታችንን በፍቅር ግዙት፣ መገዳደላችንን ደም መፋሰሳችንን በመስቀላችሁ ሰላም አቁሙት፣ እናንተ የመጽናናት መንገድን ምሩን እኛም እስከ ገነት ድረስ እንከተላችሁ፡፡ ያለእናንተ እኛ ምንድን ነን? ያለእናንተ ማን ሊያጽናናን ይችላል? ያለ እናንተ ማን ሊደርስልን ይችላል? ለሞቱት እረፍትን እና ምሕረትን ላሉት ፍቅር አንድነትን ከፈጣሪ ዘንድ ለምኑልን፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር ለዘለዓለም እንድንኖር እርዱን፡፡ ይህን ካላደረጋችሁ ግን በኃጢአት ወድቀን  “ህዝቤ” ያለንን “ህዝብህ” ብሎ ለጠላት አሳልፎ ይሰጠናል፡፡ ለጠላት “ህዝብህ” ከመባላችን በፊት እናንተ ከፈጣሪያችን ጋር አገናኙን አጽናኑን፡፡ አጽናኙ መንፈስ እስኪመጣልንም ድረስ በኢየሩሳሌም እንጠብቃለን፡፡ “አጽናኑ ሕዝቤን አጽናኑ” ኢሳ 40÷1

Saturday, October 15, 2016

“ሁለት ክብደት በአንድ ሚዛን”

© መልካሙ በየነ

ጥቅምት 5/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================
ሰውየው መዛኝ ነው፡፡ የሚገርመኝ ግን እርሱ ራሱ የተመዘነ አይመስለኝም፡፡ በእርግጥ በእኛ አገር እንዲህ ዓይነቱ አሠራር የተለመደ ብቻ ሳይሆን የተዋሐደ ነው፡፡ ሳትመዘን መመዘን ትችላለህ ያ ማለት እኮ ሳትማር ማስተማር ትችላለህ፣ ሳትሰለጥን ታሰለጥናለህ ማለት ነው፡፡ ሳይመዘን የሚመዝነው  ሰውየ “ሚዛን በ 50 ሚዛን በ 50” እያለ ይጮኸል፡፡ ይህን ጩኸቱን የሰማ ሰው ዳግም በዚያ በኩል የሚያልፍ አይመስለኝም፡፡ ሰውየው ከሚጮኸው በላይ የምትጮኽ መሣሪያ ከሚዛኑ አጠገብ አለች፡፡ እርሷ ታዲያ መጮኋን አታቋርም ትላዝናለች፡፡
መዛኙ “ሚዛን በ 50 ሚዛን በ 50” እያለ ይጮኸል፡፡ አንድ ኩንታል ሊሞላው ጥቂት ኪሎዎች የሚቀረው ሰውየ ራሱን ሊመዝን ተጠጋ፡፡ ባለሚዛኑ 50ዋ እንዳትቀርበት እንጅ ሰውየውን መመዘን አልፈለገም፡፡ ሚዛኑን የሚሰብርበት ነው የመሰለው፡፡ ሆኖም ግን መዛኝ ነውና የውስጡን ስሜት ዋጥ አድርጎ የሰማይ ስባሪ የሚያህለውን ሰውየ ወደ ሚዛኑ እንዲወጣ ጠቆመው፡፡ መዛኙ አሁንም “ሚዛን በ 50 ሚዛን በ 50” እያለ ይጮኸል፡፡ አንድ ቀጫጫ ሰው የመዛኙን ጩኸት ሰምቶ ሊመዘን ቀረበ፡፡ የሰማይ ስባሪ የሚያህለው ሰውየ ሚዛኗ ላይ እንደቆመ ነው፡፡ ጎንበስ ብሎ ማነበብ ስላልቻለ “ስንት ኪሎ ነኝ” ብሎ መዛኙን ጠየቀው፡፡ መዛኙም “ሚዛን በ 50 ሚዛን በ 50” ነህ አለው፡፡ ሰውየው ተናደደ፡፡ እኔ ግን በመዛኙ አልፈረድኩበትም ምክንያቱም አፉ “ሚዛን በ 50 ሚዛን በ 50” ከማለት ውጭ ሌላ አልለመደለትምና ነው፡፡ ልማድ ክፉ ነው በጣም ክፉ በሽታ ነው፡፡ እንዲያውም ሰው ተጣልቶ ሲሳደብም “ሚዛን በ 50 ሚዛን በ 50” የሚል ነው የሚመስለኝ፡፡ ልማድ በሽታ ነው ሲባል ብዙ ነገር ትዝ ይለኛል፡፡ ሲጋራ ማጨስ ልማድ የሆነባቸው ሰዎች ሲጋራ ካላገኙ ያዛጋሉ፡፡ የሚገርመው ነገር የሲጋራ ጢስ ሆድ የሚሞላ አለመሆኑ ነው፡፡ ሰው ጢስ ቀረብኝ ብሎ ሲያዛጋ ስታዩ “አይ ልማድ” ማለታችሁ አይቀርም፡፡ ጫት የሚቆረጥሙትንም እንዲሁ ነው የምታዘባቸው፡፡ ፍየሎቻችን የናቁትን ቅጠል ሰዎች ሲያመነዥኩ ሳይ “አይ ልማድ፤ ልማድ እኮ ክፉ በሽታ ነው” እላለሁ፡፡ ወደ ነገሬ ልመለስና ሰውየው 96 ኪሎ ነው፡፡ ሚዛኗ ሰውየውን የፈራችው ትመስላለች 96ን ጽፋ ትርገበገባለች፡፡ መዛኙ 96 ኪሎ ነህ አለው፡፡ ተመዛኙ ሰውየም ከሚዛኗ ከመቅጽበት ወርዶ 50 ሳንቲሙን ወርውሮለት ሄደ፡፡
ቀጭኑ ተመዛኝ ወደሚዛኑ ወጣ፡፡ መዛኙ “ሚዛን በ 50 ሚዛን በ 50”  እያለ ደጋግሞ ይጮኸል፡፡ ቀጫጫው ሚዛኗ ላይ የወጣው በአንድ እግሩ ነው፡፡ ቀጫጫው በአንድ እግሩ እንደቆመ “መዛኝ ስንት ኪሎ ነኝ” አለው፡፡ መዛኙም 45 ኪሎ ነህ አለው፡፡ ከሚዛኗ ወረደ እና 15 ሳንቲም ወረወረለት፡፡ መዛኙ ግራ ገባው “ምንድን ነው ይኼ” አለው ተመዛኙን፡፡ ተመዛኙም “የቅድሙ ትልቁ ሰውየ 96 ኪሎውን በ50 ሳንቲም ተመዝኖ እኔ 45 ኪሎውን ለዚያውም በ1 እግሬ ቆሜ ተመዝኘ 15 ሳንቲም አነሰህ” አለ፡፡ መዛኙ በጣም ተበሳጨና “ቀጫጫ በል 354 ሳንቲም ጨምር” አለው፡፡ ተመዛኙም ያልሰማ መስሎ ትቶት ሊሄድ ሲል መዛኙ አንቆ ያዘው፡፡ ተመዛኙ “በአንድ እግሬ ቆሜ 45 ኪሎ ለተለካሁት እና በ2 እግሩ ቆሞ 96 ኪሎ ለተለካ ሰው እኩል ታስከፍላለህ እንዴ” አለው፡፡ መዛኙም “ስትፈልግ ተኝተህም መመዘን ትችል ነበር እርሱ ያንተ ሂሳብ ነው የእኔ ሂሳብ ደግሞ 50 ሳንቲም ነው” አለው፡፡ ተመዛኙም ነገሩ ስለከረረበት ተጨማሪውን 35 ሳንቲም ወርውሮለት ሄደ፡፡
በአንድ ሚዛን ሁለት ክብደት ሲመዘን ሳይ ገረመኝ፡፡ እንዳትስቁብኝ ግን ሚዛን እንኳን ይህን ሌላስ ይመዝን አይደል እንዴ ምን ያስገርምሃል እንዳትሉኝ፡፡ በሁለት እግሩ ቆሞ የተመዘነ እና በአንድ እግሩ ቆሞ የተመዘነ ሰው እኩል ሂሳብ መክፈላቸው በጣም ያስገርማል እንጅ፡፡ በአንድ ሚዛን ስለተመዘኑ ብቻ እኩል ክፍያ መክፈላቸው ያስገርማል፡፡ በዚህ ህግ መሠረት ሳይሆን ይቀራል ፍርድ የሚፈረደው፡፡ በአንድ ዓይነት ወንጀል ሳይሆን በአንድ ዳኛ ስለተዳኙ ብቻ እኩል መቀጣታቸው አያስገርምም፡፡ በሬ የሰረቀ እና መርፌ የሰረቀ ሰው እኩል ሲፈረድባቸው አይደንቅም፡፡ በእርግጥ ይኼ ሰማያዊ ፍርድ ስላልሆነ ፍትሐዊ ይሆናል ማለት አይቻልም፡፡ በሥራ ቅጥርስ ገጥሟችሁ አያውቅም፡፡ በአንድ ተቋም ስለተማራችሁ ብቻ እኩል የምትቀጠሩበት ጉዳይ አይገርማችሁም፡፡ 5 ዓመት 3 ዓመት ወይም 2 ዓመት የተማረ ሰው በአንድ ተቋም ስለተማሩ ብቻ እኩል ደመወዝ ሲከፈላቸው ይገርመኛል፡፡ ቢያንስ እኮ ያጠናኸው የትምህርት መስክ እና ያስመዘገብከው ውጤት ግምት ውስጥ መግባት ነበረባቸው፡፡ ግን የለም!

በአንድ ሚዛን ተመዘን እንጅ የግድ እኩል ትከፍላለህ፡፡ በአንድ ዳኛ ተዳኝ እንጅ እኩል ይፈረድብሃል፣ በአንድ ሃኪም ታከም እንጅ አንድ አይነት መድኃኒት ይታዘዝልሃል፣ በአንድ ተቋም ተማር እንጅ እኩል ትቀጠራለህ፣ በአንድ መምህር ተማር እንጅ እኩል ውጤት ታገኛለህ፡፡ ይኼ የተለመደ ሆኗል፡፡  በእርግጥ አንድ ሚዛን ሁለት ክብደት መለካቱን ስመለከት ከዚህም ባለፈ ያየሁት ነገር አለ፡፡ ሁለት ሰዎች በአንድ ህግ እኩል ሳይሆኑ ሲቀሩ ታያለህ፡፡ ለምሳሌ ለእኔ የሚሰራ ህግ ላንተ ላይሰራ ይችላል፡፡ እኔ በተዳኘሁበት ህግ አንተ ላትዳኝ ትችላለህ፡፡ ሰው የገደለ ወንጀለኛ በሙሉ አንድ ዓይነት ፍርድ አይጠብቃቸውም፡፡ አንዳንዱ መግደልን እንደመብትም የተሰጠው ይመስላል፡፡ አንዳንዱ ደግሞ እድሜ ልኩን እስር ቤት ይጣላል አንዳንዱም ከ10 ዓመት በኋላ ይወጣል ብቻ ይለኛኛል፡፡ በአንድ ወንጀል እኩል አለመዳኘት እንደዚህ ነው፡፡ አንድ ሚዛን ሁለት ክብደት እንደለካው ማለት ነው፡፡ ብቻ ብዙ ነገር አለ እናንተም ጨምሩበት!!!!

Wednesday, October 5, 2016

የሚጠት ወይስ የምጽአት ዋዜማ?

© መልካሙ በየነ

መስከረም 25/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================
“ሚጠት” መመለስ ነው “ምጽአት” ደግሞ መምጣት ነው፡፡ መከራ፣ ስቃይ፣  እንግልት፣ ረሃብ፣ ጥም፣ እርዛት፣ ሰሚ ማጣት  ያሰድዳል፡፡ መሰደድ ፍርሐት አይደለም፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል  አረጋዊው ዮሴፍን ልጇን ኢየሱስ ክርስቶስን እና  እናቱ ድንግል ማርያምን ይዘህ ወደ ግብጽ ሂድ ብሎታል፡፡ አምላክ ሁሉን ማድረግ ይችላል፤ ንጉሡ ሔሮድስን በተቀመጠበት ዙፋን ላይ ጸጥ ማድረግ ይችላል፤ 14 እልፍ የቤተልሄም ሕጻናት እንዳይሞቱ ማድረግ ይችላል ግን መከራ ሲመጣባችሁ ፈተና ሲገጥማችሁ ክፉ ንጉሥ ሲነሣባችሁ እኔ ያደረግሁትን አድርጉ ለማለት አርአያነቱን ለማሣየት ተሰደደ፡፡ አሁን ወደ ግብጽ እየተሰደዱ ናቸው፡፡ የስደታቸው ምክንያት ደግሞ የክፉው ንጉሥ የሔሮድስ አሰቃቂ ግድያ ነው፡፡ ለዚህ ነው መሰደድ ፍርሐት አይደለም ያልኩት፡፡ ሕጻኑ ያለጊዜው ደሙ አይፈስም ስለዚህ ነው መሰደድን የመረጠው፡፡ ሆኖም ግን ጊዜው በደረሰ ጊዜ ደሙ የሚፈስበት ቀን ሲደርስ ራሱ በፈቃዱ ለገዳዮቹ እጁን ሰጥቷል፡፡ እዚህ ላይ የምንገነዘበው ነገር ለሚገድሉት እጁን ሰጠ እንጅ ልግደላችሁ አላለም፡፡ ለዚህ ነው ክርስትና ውስጥ እንሞታለን እንጅ አንገድልም እንደማለን እንጅ አናደማም እንቆስላለን እንጅ አናቆስልም የምንለው፡፡ ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና በዚህ በዘመነ ሄሮድስ ሁለት ምርጫዎች ብቻ ናቸው ያሉት፡፡ የመጀመሪያው በንጉሡ እጅ መሞት ሌላኛው ደግሞ መሰደድ ናቸው፡፡ እንግዲህ ሁለተኛው ምርጫ ነው ለአረጋዊው ዮሴፍ የተነገረው እርሱም እንደተነገረው ወደ ግብጽ ተሰደደ፡፡ ከዚያም ምን ቢገዙ፣ ምን ቢነዱ፣ ምን ቢጨክኑ ከሞት እጅ ማምለጥ አይቻልምና ይህ ጨካኝ ንጉሥ ሔሮድስ ሞተ ያን ጊዜ “ተመየጢ ተመየጢ ተመየጢ ሱላማጢስ” ተባለች፡፡ አወ አሁን በቤተልሔም መገደል የለም፣ ያ ጨካኙ ንጉሥ ከመቃብር በታች ነው፡፡ ስለዚህ ወደ ቤተልሄም መመለስ አለባቸው “ሚጠት” ማለት ይህ ነው፡፡ ሰው የሚሰደደው አገሩን ጠልቶ አይደለም ችግር ሆኖበት እንጅ፤ ስለዚህ ያ ችግር ሲፈታ መመለሱ አይቀርም፡፡ የንጉሡ ሞት ለሚጠት ዋዜማ ነበር፡፡
እስራኤላውያንም በግብጽ የባርነት ታሪክ ውስጥ ብዙ እንደተቸገሩ እናውቃለን፡፡ ዛሬ “የግብጽ ፒራሚድ” እያልን ግብጽን የምናነሣት ያኔ ድሮ እስራኤላውያን ራሳቸውን እንደ እባብ እየተቀጠቀጡ ባቦኩት ጭቃና ሲሚንቶ የተገነባ ነው፡፡ ራሄል የመውለጃዋ ቀን ደረሰ ነገር ግን ማንም ሊያሳርፋት አልቻለም ነበር፡፡ ምጧ ደረሰ ጭቃ እያቦካች ነው፡፡ አሁንም እየተደበደበች ምጧን ዋጥ አድርጋ ጭቃ ታቦካ ጀመረች፡፡ አልቻለችም እዛው ጭቃው ላይ ወለደች፡፡ ከዚያም ልጆችሽን ከጭቃው ጋር እርገጫቸው ደማቸው ጭቃችንን ያጠነክርልናልና ተባለች፡፡ አስቡት ይህን ግፍ፡፡ ይህ ግፍ ለእስራኤላውያን “ሚጠት” ዋዜማ ነበር፡፡ እንባዋን ወደ ሰማየ ሰማያት ረጨች አምላክ እንባዋን ተቀበለ ድንቅ መሪ የሆነውን ሙሴ አዘጋጀ ከዚያም ግብጽን ዳግም ባሪያ ሆነው ላይኖሩባት ተሰናብተው ወደ ርስት ሀገራቸው ተመለሱ፡፡ ይህ የእስራኤላውያን ሚጠት ነው፡፡
በተመሳሳይ ወደ ፋርስ ባቢሎን በባርነት በተሰደዱ ጊዜ ኤርምያስ ሳይቀር አብሮ ተሰዷል፡፡ በዚህ ወቅት ሀገሪቱ ተፈታለች ሰው የሚባል ፍጡር ጠፍቶባታል፡፡ ይህ የሚሆነው ለ70 ዓመታት ያህል ነበር፡፡ ከዚህ ጥፋት በእግዚአብሔር ጥበብ የተሠወሩት የኤርምያስ ደቀመዛሙርት ባሮክና አቤሜሌክ ብቻ ናቸው፡፡ ሌላው ህዝብ ግን የአገሩን ጥፋት በዓይኑ ተመልክቷል፤በባርነት ተሰዷል፡፡ አቤሜሌክ ለድውያን የሚቀባ መድኃኒት ሊያመጣ ተላከ ባሮክም መቃብረ ነገሥትን እንዲጠብቅ ተደረገ፡፡ የሚገርመኝ የአቤሜሌክ ጉዳይ ነው፡፡ መድኃኒቷን ቆርጦ ሲመጣ ደከመውና ከጥላ ሥር አረፍ አለ በዚያው 66 ዓመት ተኛ ሲነቃ እንቅልፉ በደንብ አልለቀቀውም ነበር፡፡ ተነሥቶ መንገዱን ሊቀጥል ሲል መንገዱ ሁሉ ጠፋበት አገሪቱ ጠፍታለች ሰው አይኖርባትም በኋላ ግን መልአኩ ከባሮክ ጋር አገናኝቶታል፡፡ ከዚያም መድኃኒቷን ለኤርምያስ በንስር አሞራ ላኩለት፡፡ ያኔ ለሚጠት ዋዜማ ነበር 4 ዓመት ብቻ ነበር የቀራቸው፡፡
አገራችን እንግዳ ተቀባይ፣ በማንም ወራሪ ጠላት ያልተንበረከከች የጀግኖች መፍለቂያ፣ የፍቅር አገር ናት፡፡ ለራበው የሚያበላ፣ ለጠማው የሚያጠጣ፣ ለበረደው የሚያለብስ፣ ለጠላት እጁን የማይሰጥ፣ ለማንም የውጭ ኃይል የማይንበረከክ ጀግና የሚፈልቅባት ቅድስና የማይጠፋባት፣ ጥበብ የሚመነጭባት፣ ጠላት የሚያፍርባት፣ በገንዘብና በብልጭልጭ ነገር የማይታለል ህዝብ ያላት አገር ናት፡፡  ዘመናዊ መሣሪያ ታጥቆ የመጣውን የጣሊያን ጦር በቆራጥ የአገር ፍቅር እንዴት እንዳንቀጠቀጠ ህዝባችንን አይተናል፡፡ ዛሬ ወንድም ወንድሙን ገድሎ ጀግና ተብሎ ማዕርግ እንደሚጨመርለት ያለ ወኔ አይደለም የጥንቱ ጀግንነት፡፡ ዛሬ  እንደ ሔሮድስ፣ እንደ ሂትለር እጃችን በደም ጨቅይቷል፡፡ ወንዞቻችን ደም እያጎረፉ ናቸው፣ ሴቶቻችን ተገዳዮችን እያረገዙ ናቸው፣ የቻሉት ስደትን መርጠው እየተሰደዱ ናቸው ያልቻሉትም በአገራችን መቃብራችንን አድርግልን ብለው ፈጣሪያቸውን እየተማጸኑ ናቸው፡፡ ይህ ዘመን ለሀገራችን ከባድ የሀዘን፣ የዋይታ፣ የለቅሶ፣ የስቃይ ዘመን እየሆነ ነው፡፡ ታዲያ “ሚጠት” ነው ወይስ “ምጽአት” ነው እየቀረበን ያለው፡፡
“ምጽአት” የጌታ ለዘላለም ፍርድ ወደዚህ ዓለም መምጣት ነው፡፡ የምጽአት ዋዜማዎች በርካቶች ናቸው ከእነዚህ ውስጥ ግን በማቴ 24 ላይ “ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣሉ” ይላል፡፡ ዛሬ በእኛ ላይም እንደዚያ እየሆነ ነው፡፡ ጦርን የጦርንም ወሬ በርቀት ሳይሆን በቅርበት እየሰማን ነው፤ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ እየተነሣ ነው፡፡ ለአገራችን አስከፊ የሚሆነው ህዝብ በህዝብ ላይ ከተነሣ ብቻ ነው፡፡ መንግሥት በመንግሥት ላይ፤ መንግሥት በሕዝብ ላይ ቢነሣ ምንም ማለት አይደለም፡፡ ምክንያቱም የሚያመጣው ተጽእኖ ከባድ አይሆንም ህዝብ የሌለው መንግሥት ምንም ሊያደርግ ስለማይቻለው፡፡ ህዝብ በህዝብ ላይ ከተነሣ ግን ተጽእኖው ከበድ ያለ ይሆናል፡፡ ህዝብ በህዝብ ላይ ከተነሣ ቋንቋ፣ ቀለም፣ ዘር፣ ጎሳ፣ ጎጥ፣ የደም ዓይነት ሁሉ የጥላቻ ምንጭ ይሆናል፡፡ ይህ ደግሞ መንግሥትንም እንዳይቆም ያደርገዋል ሀገርንም ያፈራርሳል፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣሉ” የሚለው ቃል የምጽአት ዋዜማ ነው፡፡ አገራችንን እንደቀደመ ክብሯ ለማስቀጠል ካስፈለገን ህዝብ በህዝብ ላይ መነሣት የለበትም፡፡ በዘር፣ በጎሳ፣ በብሄር፣ በቋንቋ አንከፋፈል አንድ እንሁን፡፡ መከፋፈል ካለብን ወድደን ባመጣነው ነገር ብቻ እንጅ ተፈጥሮ በቸረን ነገር ሊሆን አይገባውም፡፡ ከሆነ ዘር፣ ከሆነ ብሄር፣ ከሆነ እምነት፣ ከሆነ ቋንቋ ተናጋሪ በሆነ ብሔር የተፈጠርነው ፈልገን አይደለም ይህ የፈጣሪ ሥራ ብቻ ነው፡፡ አገራችን ደግሞ በህብረ ብሔሯ ዓለምን የምታስቀና ናት፡፡ ስለዚህ ይህን ህብረ ብሔር አንድ ማድረግ ካልቻልን መለያየታችን ሞታችንን ያፋጥነዋል፡፡

ለዚህ ነው አሁን በአገራችን እየተፈጸመ ባለው ግድያ የእናቶች ለቅሶ ከፍ ብሎ ሲሰማ ሳስተውል ዋዜማነቱ ወደ ቀደመ ክብራችን ወደ ቀደመ ኃያልነታችን ወደ ቀደመ አልደፈርም ባይነታችን ወደ ቀደመ ጀግንነታችን ልንመለስ ይሆን ወይስ ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣሉ” እንዳለው ምጽአት ቀርቦ ይሆን ብየ እንዳስብ የተገደድኩት፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን ወይ ለ “ሚጠት” ወይ ለ “ምጽአት” ዋዜማ መሆኑ አያጠራጥርም፡፡ አምላከ ቅዱሳን ለአገራችን ሰላምን እንዲሰጥልን ሁላችንም እንጸልይ መፍትሔው ከፈጣሪ ብቻ ነው፡፡ አሁን ደግሞ የፈቃድ ጾም ቢሆንም ነገ መስከረም 26 ጀምሮ የጽጌ ጾም ይጀመራል እስኪ ለዚሁ ዓላማ ብለን ዘንድሮ እንጹመው ሱባኤ እንያዝ፡፡ ሌላው እምነትም በራሱ ለዚሁ ብሎ በእምነት ሥርዓቱ የሚገባውን ያድርግ፡፡