Monday, December 31, 2018

የከሸፈው ሙከራ ካላስተማረን ተዋሕዶ ተብለን ባንጠራ ይሻለናል!




የአቡነ ማርቆስን ጠልነት ተጠቅመው ያንሰራሩት ከመቃብር አፋፍም የወጡት ቅባቶች  ኩላዊት አሐቲ ቅድስት የኾች ቤተ ክርስቲያንን ለመከፋፈልና ምእመናንን ግራ ለማጋባት በጀት ተመድቦላቸው በስፋት እየሠሩ ናቸው፡፡  ውስጥ ለውስጥ እየሠሩት ያለውን ነገር አሁን አሁን ወደ ምእመናንም በመውረድ በአንዲት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን ውስጥ መከፋፈልን እየፈጠሩ ናቸው፡፡ በጀቱ የማን እንደኾነ የሚታወቅ ነው፡፡ ለዚህ የበጀት ምንጭ ኹለት ነገሮችን እጠረጥራለሁ፡፡
1ኛ. የተሐድሶ መናፍቃን ሴራ ይኾናል ብየ እገምታለሁ፡፡ ቅባቶች በመጽሐፎቻቸው ውስጥ ያሰፈሯቸው በርካታ ትምህርቶች ከመናፍቃኑ በቀጥታ የተቀዱ ናቸው፡፡ ከዚህ በፊት በዚህ  ዙሪያ ብዙ ነገሮችን ብያለሁ፡፡ ተሐድሶ መናፍቃን ሰርገው ለመግባት አመቺ ሖኖ ያገኙትን ሁሉ ከመጠቀም ወደ ኋላ አይሉም፡፡ ስለዚህም አንዲትን ቤተክርስቲያን ለተለያዩ ጎራዎች እንድትከፈል የማድረግ አጀንዳ አንግበዋል፡፡ በአንዱ እግዚአብሔር በአንዲት ጥምቀት አንድ ሃይማኖት እንጅ ሁለት ሃይማኖት ሊመሠረት እንደማይችል ለማንም የተገለጠ እውነት ነው፡፡
2ኛ. አሁን ያለው ያልተረጋጋ የመንግሥት ፖሊቲካዊ አሠራር ይመስለኛል፡፡ በየዩኒቨርሲቲዎቻችን በየከተሞቻችን እና በተለያዩ ድንበር ቦታዎች ላይ እስካሁን ድረስ በርካታ መከፋፈሎች ይስተዋላሉ፡፡ ይህ ሴራ የማን እንደኾነ በግልጥ የሚታወቅ ነው፡፡ ወደ ሃይማታዊ ተቋማትም በመግባት ይህንን ነገር በገንዘብ እየደገፉ እንደኾነ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ በክልል እንዳይስማማ በዞን እንዳይስማማ በወረዳ በቀበሌ እንዳይስማማ እንደሀገርም አንድ እንዳይኾን በሚፈለግበት በዚህ ወቅት እነዚህ መነሣታቸው በኩንታል ከሚታደለው የጥፋት ገንዘብ መካከል ተቋዳሽ መኾናቸውን ያሳያል፡፡
እነዚህ ከላይ የገለጥኳቸው ጉዳዮች ለእኔ መስለው የሚታዩኝ ናቸው እንጂ እውታው ግን በእያንዳንዳችሁ ሀሳብ ውስጥ ሊመላለስ እንደሚችል እገምታለሁ፡፡ ያም ኾነ ይህ ቤተክርስቲያናችን አሁን ባለው ኹኔታ ተደፍራለች ተጠቅታለች፡፡ ትራስ በትራስ ላይ እየደራረብክ ተኝተሃል ጠላት ደግሞ ጦሩን ሰብቆ ቤትህ ውስጥ ሰተት ብሎ ገብቷል፡፡ በዚህ ዙሪያ ላይ ለዘብተኛ አመለካከት ያላችሁ ወገኖች ወይ የጥፋቱን ሠራዊት ተከተሉ ወይ ቤተክርስቲያንን ነቅቶ ከጠላት ከሚከላለከለው ሠራዊተ እግዚአብሔር ጋር ተሰለፉ፡፡
የቅባቶች ፌስቡክ አካውንቶች ዛሬ ታኅሣሥ 22/2011 ዓ.ም በጥንታዊቷ ርእሰ ርኡሳን መርጡለ ማርያም ከተማ ውስጥ በምትገኘው ቅድስት አርሴማ ቤተክርስቲያን ውስጥ ስብሰባ እንደሚያካሂዱ ሲለፉ ሰንብተዋል፡፡ እኛም የሚኾነውን ነገር እየተከታተልን ነበር፡፡ ቅዳሜ ዕለት ታኅሣሥ 20/2011 ዓ.ም ለሞጣ፣ ለደብረ ወርቅ፣ ለጎንቻ አካባቢ የቅባት አማኞች ደብዳቤ ተበተነላቸው፡፡ ስብሰባቸውን ደግሞ መርጡለ ማርያም እንደሚያደርጉ አሳወቋቸው፡፡ ካልጠፋ ቦታ ካላጡት ገዳም ለምን መርጡለ ማርያም ተደረገ?  ብለን መጠየቅ አለብን፡፡ መርጡለ ማርያም ማካሄድ ያስፈለጋቸው፡-
1ኛ. መርጡለ ማርያም ገዳም የምትታወቀው በጥንታዊነቷ ነው፡፡ የኦሪት መሥዋእት ይሠዋባቸው ከነበሩ አምስት ቦታዎች መካከል አንዷ ናት፡፡ መርጡለ ማርያም ገዳም ውስጥ ከጥንት ጀምሮ የቅባት አማኞች ወደ ተዋሕዶ እየተመለሱ የልጅነት ጥምቀትን ያጠምቁባት የነበረች ቦታም ናት፡፡ እውነታቸውን ይኹን አይኹን ባላውቅም ዛሬም የተወሰኑ ቅልቅሎች ሊኖሩ ቢችሉም ጥምቀት እንደሚካሄድባት ነው ቅባቶች የጠቀሱት፡፡
2ኛ. የሚቃወመን የለም በሚል ነው፡፡ በእውነቱ ይህ አመለካከት የመርጡለ ማርያምን ሕዝብ በትክክል ካለመረዳት የመጣ ይኾናል ብየ አስባለሁ፡፡ ለእመነቱ ሲል የሚሞት ስንት ደገኛ ምእመን እንዳለ የሚያውቁ አልመሰለኝም፡፡
በዋናነት ጥንታዊነቷን ለስማቸውና ለሃይማኖታቸው መገለጫ ማድረግን ይሹ ስለነበር ነው መርጡለ ማርያምን ለስብሰባቸው የመረጡት፡፡ ጉባዔ ከለባት (የውሾች ጉባዔ) በመርጡለ ማርያም ከተማ እንዲደረግ በዚህ መልኩ ተወሰነ፡፡ የሚገርማችሁ ነገር መርጡለ ማርያም ከተማ ውስጥ ቢሮ ከፍተው በመሥራት ላይ እንደኾኑ መረጃው ሊኖራችሁ ይገባል፡፡
ዛሬ ታኅሣሥ 22/2011 ዓ.ም በቀጠሯቸው መሠረት ከየወረዳው በእልህና በትዕቢት የሚንቀሳቀሱ የቅባት አማኖች መርጡለ ማርያም ከተማ ወደምትገኘው ቅድስት አርሴማ ቤተክርስቲያን ተሰባሰቡ፡፡ ኾኖም ግን ወረዳ ቤተክህነቱም ሰበካ ጉባዔውም የሚያውቀው ነገር ስለሌለው ወደ ቤተክርስቲያኗ መግባት አልቻሉም ነበር፡፡ ሌሊቱን ሙሉ መፍትሔ ሲያፈላልጉ የነበሩት የመርጡለ ማርያም የስበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች እና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ቅባቶች ይሰበሰቡበታል ወደተባለው ቤተክርስቲያን ገስግሰው አቅንተዋል፡፡ የጸጥታ አካላትም በቦታው በመገኘት ከኹለቱም ወገን ከቅባትም ከተዋሕዶም ወደ ቤተክርስቲያኗ እንዳገቡ ያደርጋሉ፡፡ ቅባቶች በዚህ የተነሣ ከቤተክርስቲያኗ ራቅ ብለው አጀንዳቸውን መወያየት ጀመሩ፡፡ አሁን ላይ የመርጡለ ማርያም የተዋሕዶ አርበኞች ቤተክርስቲያኗን ከበው እየጠበቁ ናቸው፡፡ በእውነት ለእነዚህ ወንድሞቻችን ምን ይከፈላቸዋል? የቅባቶች ስብሰባ የከሸፈው ቤተክርስቲያን ከመደረጉ ነው እንጂ ውይይት ከማድረግ ማንም አላስቆማቸውም፡፡ ዳግም ጥምቀት እና ማኅበረ ቅዱሳን እየተወገዙ ያለበት ሰዓት ነው አሁን፡፡
በዚህ ላይ ለማኅበረ ቅዱሳንም እና ለዘብተኛ አመለካከት ላላቸው ሰዎች ኹሉ መልእክት ማስተላለፍ እፈልጋለሁ፡፡
1ኛ. ለማኅበረ ቅዱሳን
====================================================
ማኅበረ ቅዱሳን በመንግሥት፣ በተሐድሶ፣ በቅባት እና በሌሎችም እምነቶች በከፍተኛ ደረጃ የሚወቀስ የሚወገዝ ማኅበር ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን እንዲህ ያደርጋል ማኅበሩ እንዲህ ይሠራል እያሉ ሲያሸማቅቁት እየተመለከትን ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት ምሥራቅ ጎጃም ላይ ስላለው የቅባቶች እንቅስቃሴ ማኅበረ ቅዱሳን እንደ ማኅበር አቋም ይዞ እየታገለ ነው ለማለት እቸገራለሁ፡፡ አቡነ ማርቆስ በነበሩበት ሰዓት ይነሣ የነበረው ይህ ሃይማኖታዊ በደል ዛሬ ላይ ስሙን ለማንሣት እንኳ የተፈራበት ሁኔታ ነው ያለ፡፡ ስብከት ሲሰጥም ቅብዐት የሚለው መነሣት የለበትም እየተባለ ለስብከት የሚቆሙ ሊቃውንት ምን ያህል ቃላትን ለመምረጥ እንደሚጠነቀቁ ሳይ አዝናለሁ፡፡ ጥምቀት ጋር በተያያዘ ማኅበረ ቅዱሳን ማጥመቅ እንደማይችል ይታወቃል፡፡ ነገር ግን ማኅበረ ቅዱሳን እያጠመቀ ነው ተብሎ ስለተከሰሰ ብቻ ጥምቀቱ ላይ ለዘብተኛ መኾን እየታየ ነው፡፡ ቅብዐት ምንፍቅና ነው በቅብዐት ካህናት የተጠመቁም መጠመቅ አለባቸው ብሎ ደፍሮ ማስተማር ላይ ችግር አለ፡፡ ይህን ሳልጠቅስ ማለፍ አልፈልግም፡፡ እኛ ቅባት ብለን ስላልጠራን፣ ዳግም ጥምቀት ላይ ብዙም አይጫኑም ስለተባልን ከቅባቶች ስድብና ከሰሳ የምናመልጥ ከመሰለን ተሳስተናል፡፡ ግልጽ እንነጋገር ከተባለ እኔ ያለኝ አቋም እውነቱን እውነት ሐሰቱን ሐሰት እያልን መደራደር ባለብን ዙሪያ እየተደራደርን መደራደር በሌለብን ጉዳይ ደግሞ መደራደር ሳያስፈልግ በግልጽ መቀጠል ነው፡፡ አሁን በየግቢ ጉባዔው እያስተማርን ነው፡፡ ቅባቶች አምነው ተመለሱ እና ምን እናድርግ አሉ? መልሳችን ምንድን ነው የሚኾነው? ምሥራቅ ጎጃም ላይ ያለው የማኅበሩ እንቅስቃሴ በቀጥታ ሳይኾን በተዘዋዋሪ ኾኗል፡፡ ከተወገዘ ይወገዝ የተለመደ ነው፡፡ ከተለየም ይለይ የታወቀ ነው፡፡ እውነቱን መነጋገር ግን የግድ ነው፡፡ ሱቃችን እና ከፌያችን እንዳይዘጋ አይደለም እኮ የምንሠራው፡፡ ሥራችን የጠፉ በጎችን መፈለግ ነው አለቀ፡፡
እኛ ብንሸፍነው ብናሽሞነሙነው አንድ ቀን መፈንዳቱ የሚቀር እንዳይመስላችሁ፡፡ መንግሥት ላይ ያለውን አትመለከቱም እንዴ? ሽህ ዓመት ይገዙናል ብለን ራሳችንን ለስቃይና ለመከራ ስናስበው እኮ ነው ይችን ሰላም ያገኘናት፡፡ ሊገዙን ያሰቡት ሰዎችም ባላሰቡበት ጊዜ ነው ያ ሁሉ ነገር የገጠማቸው፡፡ ባሠሩበት እስር ቤት አንገታቸውን ደፍተው የታሠሩበት ጊዜው ለእነርሱ ስላልኾነ ነው፡፡ ስለዚህ ማኅበሩም ይህንን በአቋም መሄድ አለበት፡፡ ፍናፍንት በሆነ አስተሳሰብ መዝለቅ አይቻልም፡፡ ያውም የችግሩ ምንጭ ላይ ተቀምጠን፡፡ ከአባታችን ጋር ያለውን መልካም ግንኙነት የሚያሻክር መስሎ ከተሰማችሁ መጀመሪያ ግንኙነታችን ሃይማኖታዊ መኾን አለበት፡፡ ቅባቶች ይጠመቁ የሚሉ መጻሕፍትን በማባረር ቅብዐትን የሚያነሡ መጻሕፍትን በማስወገድ ግንኙነታችንን ማሳመር አንችልም፡፡ ነገ አባታችን ማኅበሩን ሰብስበው ዳግም ጥምቀት መፈጸም የለበትም እናንተም ስታስተምሩ ጥምቀት እንደማይገባ ተናገሩ ብለው አጀንዳ አስይዘው ፈርሙ ቢሉ የሚፈርም ይኖራል በእርግጠኝነት፡፡  የማኅበሩ ዓላማ ነፍሳትን ማዳን ነው፡፡ ያስተምራል ቀኖና ቤተክርስቲያን በሚያዝዘው መልኩ ሥርዓት ያስፈጽማል አለቀ፡፡ የማኅበሩ ሥራ መጻሕፍተ ቤተ ክርስቲያንን በሚገባ ማስተማር ነው፡፡ ሌላው ነገር ለአባቶች የሚተው ነው፡፡ በዚሁ አጋጣሚ ደብረ አሚን የተሰኘችው መጽሐፌ በማኅበሩ ሱቅ ለምን አትገባም እያላችሁ ለጠየቃችሁኝ ኹሉ መልሴ ይኼ ነው፡፡ መጽሐፍህ ቅባቶች ዳግም ይጠመቁ ይላል ይህን ማሰራጨት አንችልም የሚል ነው፡፡ ታዲያ መጠመቅ የለባቸውም ወይ? መልሱ ይገርመኛል፡፡ ለማንኛውም አቋም መያዝ ግድ ይለናል፡፡ በማንደራደርበት አንደራደር፡፡ የነቀርሳ በሽተኛ ሰው እባክህ ነቀርሳ የሚለውን ስም አትጥራ ሕክምና የሚባለውንም ነገር አታንሣ እያለ ቢኖር መጨረሻው በበሽታው መሞት እንጂ ከበሽታው ማገገም አይችልም፡፡ ስሙ አይጠራ ስላልን ብቻ በውስጣችን ያለውን ነቀርሳ ያስወገድን ከመሰለን ተሳስተናል፡፡ ገና ለገና ከአባ ዮሴፍ ጋር ተስማምተን እንድንኖር በሚል አመለካከት መንጋውን ማጣት የለብንም፤ ትክክለኛውን ትምህርትም መዘንጋት የለብንም፡፡
2ኛ. ለዘብተኛ አመለካከት ላላቸው
==============================
እነዚህ ሰዎች ቅባት ተዋሕዶ ተብሎ ልዩነቱ ሲነገር ለምን ልዩነታችንን እናሰፋለን ባዮች ናቸው፡፡ ታዲያ ለምንድን ነው ስለፕሮቴስታንት፣ ስለካቶሊክ የምንጽፈው የምናስተምረው? ቅባት ከእነዚህ የተለየ ነውን? ሁለት ጓደኛሞች ተኝተው ሳለ የአንዱን እግር ጅብ ይይዘዋል፡፡ ያንጊዜ ጓደኛው ፈርቶ አረ ምንድን ነው? ይለዋል ያ በጅብ የተያዘው ልጅም ተው ዝም በል የእኔን እግር ነው አለ የሚባል ተረት አለ፡፡ መርጡለ ማርያም ላይ ስብሰባ የተደረገው አባ ዐሥራት ላይ ሥልጠና ሲሰጡ ሲመረቁም ዝም ስላልን ነው፡፡ ዛሬ መርጡለ ማርያም ላይ ከሸፈ ያልነው የቅባቶች ጉባዔ ነገ የኾነ ቦታ ላይ ማንም ሳይጠይቃቸው ስብሰባቸውን እንደሚያካሂዱ እርግጠኛ ነኝ፡፡ እስከመቼ ነው ቆይ እንዲህ ስንጃጃል የምንኖረው? ቤተክርስቲያኒቱ እኮ የእኛ ናት፡፡ ማንም ሲፈነጭባት ዝም ማለታችን የጤና ነው? ስለዚህ ጉዳይ መጻፍም መናገርም ፖለቲካ የሚመስላቸው ነገር ግን ቤተክርስቲያን የሚመላለሱ ሰዎች አሉ፡፡ እስከመቼ ነው ቤታችንን እየለቀቅን የምንሄደው? እነርሱ ለአንድ ጉባዔ እስከ 600 ሺህ ብር ድረስ ወጭ እንደሚደረግላቸው እየሰማን ነው፡፡ በእውነት ይህ ገንዘብስ ከየት የመጣ ይኾን? አባ ማርቆስ እንዲነሡልን የተጋነውን ያህል አሁን መትጋት ያቃተን ለምንድን ነው? አባ ማርቆስ ጋር የግል ጠብ ያለን እስኪመስል ድረስ እርሳቸው ከሄዱ በኋላ ኹሉም ተሸፋፍኖ ነው ለጥ ያለው፡፡ የመርጡለ ማርያም ጥቃት ለዚህም ጥቃት ኾኖ ካልተሰማን ቤተክርስቲያን አንዲት ናት የምንለው የት ላይ ነው? በአጼ ሱስንዮስ ዘመነ መንግሥት ጎንደር በነበረው የእርስ በርስ ግድያ ላይ የጎጃም ገበሬዎች ሳይቀሩ ሰማእትነት አያምልጠን ብለው ጎንደር ላሄደው በሰማእትነት አርፈዋል፡፡  ታዲያ የእኛ ለዘብተኛ መኾን ምንድን ነው? በፍናፍንት ሃሳብስ እስከ መቼ ድረስ ነው የምንቀጥለው?
ይህን ዛሬ የከሸፈውን ሙከራ ቀላል አድርጋችሁ ከተመለከታችሁት ነገ ምን እንደሚመጣ ማሰብ አያዳግትም፡፡ በራሳችን በቤተክርስቲያን ውስጥ ወልድ ዋሕድ በተዋሕዶ ከበረ ብለን ለማስተማር እየተሸማቀቅን እስከመቼ ነው የምቀጥል? እስከ መቼ ድረስስ ዲማ እየሄድን ስቆርብና ስናስጠምቅ እንኖራለን? አስቡት እንጂ፡፡ ነገ ዲማ ላይስ ምን እንደሚፈጠር ምን እናውቃለን? ሥራ እንሥራ ካላችሁ እንደ ኮርኮች የራሳችንን አጥቢያዎች የራሳችንን አድባራት እና ገዳማት ነጻ እናውጣቸው፡፡ እዚሁ ባለንበት ቦታ ክርስትና እናስነሣ፣ ተክሊል እንፈጽም፣ ንስሐ እንፈጽም እንቁረብ፡፡ ይህ ጉዳይ ሰፊ ውይይት የሚጠይቅ ይመስለኛል፡፡ የዛሬው ጉዳይ ካላስተማረን የእኛ የስም ተዋሕዶነት አይጠቅመንም፡፡ ከታች በፎቶ በምታዩት መልኩ ነው የመርጡለ ማርያም የተዋሕዶ ልጆች ቅባቶችን ከቤተክርስቲያን ያባረሯቸው፡፡ ቅባቶችም ከዛፍ ሥር በምታዩት መልኩ እየተነጋገሩ ናቸው፡፡
==================
ታኅሣሥ 22/2011 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፤ ኢትዮጵያ






 



Wednesday, December 26, 2018

የነገው ገዳመ አስቄጥስ የዛሬው እነጋትራ ቅድስት ሃና አንድነት ገዳም!


==========================================================
ይህ ገዳም በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሥር ከሚገኙ በርካታ ጥንታውያን ገዳማት መካከል አንዱ ነው። አብርሃ ወአጽብሐ እንደመሠረቱት የሚነገርለት ይህ ጥንታዊ ቦታ በአዋበል ወረዳ ቤተክህነት ሥር የሚገኝ የአንድነት ገዳም ነው። ገዳሙ በእናታችን ጽዮን ጽላት የተቆረቆረ ቢኾንም ከዘመናት በኋላ 13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አሁን የምትገኘው የቅድስት ሃና ጽላት እንደገባች ይነገራል። በአጼ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥት በዚህ ገዳም 3000 መነኮሳት በላይ ይኖሩበት እንደነበር ምዕላድ በተባለው መጽሐፍ ላይ ተመዝግቦ ይገኝ እንደነበር ቦታውን ስንመለከት ተነግሮናል።
ቦታው እነታድራ በምትባል በንጉሥ ልጅ ይጠራ እንደነበር ከጊዜ በኋላ ግን እነጋትራ እየተባለ መጠራት ጀምሯል። ይህ የበረከት እና የጽሙና ቦታ ለጸሎት እና ለአርምሞ ምቹ ነው። ከደብረ ማርቆስ ከተማ 50 . በላይ የማይርቀው ይህ ቦታ የቦቅላ ከተባለች ከተማ ወደ ቁይ ስንሄድ እነጋትራ ትምህርት ቤት እንደደረስን ከቁይ መንገድ ተገንጥሎ ወደ ሰሜን አቅጣጫ ያለውን የጠጠር መንገድ ተከትሎ ቀጥታ በመሄድ ገዳሙ ላይ መድረስ ይቻላል።
 
ገዳሙን ለሚመለከቱም ኾኑ ተአምረኛ በኾነው ጠበል ለሚጠምቁ ሰዎች ወደ ገዳሙ ሲመጡ ምግብ ይዞ መሄድ ፈጽሞ የተወገዘ ነው። ለገዳሙም ኾነ በገዳሙ ውስጥ ለሚገኙ መነኮሳት 5 ሳንቲም ምጽዋት መስጠት ውጉዝ ነው። ቦታውን ለማየትም ይኹን ብዙ ጊዜ ተቀምጦ ከበረከቱ ለመካፈል የፈለገ ኹሉ 5 ሳንቲም ወጭ አይጠየቅም ቢሰጥ እንኳ የተወገዘ ነው።

ገዳሙን እያስተዳደሩት ያሉት አባ ገብረ ሥላሴ (በአካባቢው ምእመናን በጎ ስም የላቸውም) የግብጽ እና የኢየሩሳሌም ገዳማትን በሚገባ የተመለከቱ ናቸው። በገዳሙ እየተሠሩ ያሉ በርካታ የሴትና የወንድ መነኮሳት የጸሎት ቦታዎች በአባ ገብረ ሥላሴ መሐንዲስነት በሚገባ በሚያምር መልኩ እየተገነቡ እንደሚገኙ ተመልክተናል። አርቆ አሳቢው ገዳሚው አባ ገብረ ሥላሴ ዓላማቸው ግብጽ የሚገኘውን ገዳመ አስቄጥስ ጎጃም ላይ መትከል ነው። የግብጹ ገዳመ አስቄጥስ ዘመናዊውን እና ሃይማኖታዊውን ትምህርት በሚገባ ጎን ለጎን በገዳሙ ውስጥ እየተማሩ ዶክተር እና ኢንጅነር ኾነው ገዳማቸውን በምንኩስና ያገለግላሉ። ዘመናዊውን ዓለም የዋጁ በርካታ መነኮሳት ይገኙበታል ይህን እነጋትራንም እንደዚያ ማድረግ እፈልጋለሁ ይላሉ አስተዳዳሪው። ለዚህም ማሳያ የኾኑት በግንባታ ላይ ያሉት በሚያምር መልኩ የተጀመሩት 3 3 የኾኑ 15 በላይ የሚኾኑ የወንዶች እና 15 በላይ የሚኾኑ የሴቶች መኖሪያ ቤቶች ምስክሮች ናቸው። ወደፊት ለመሥራት ያቀዱት ከወጣኒነት ወደ ማእከላዊነት እና ፍጹምነት ሲደርሱ መነኮሳት የሚያርፉበትን ቦታ መሥራት ነው። አሁን በቦታው የሚገኙት መነኮሳትና መነኮሳዪያት የሚኖሩበት ቦታ እንዴት ደስ እንደሚያሰኝ የሚያውቀው ቦታውን ያየ ሰው ብቻ ነው።

አባ ገብረ ሥላሴ ዓላማቸው ኹሉንም የጉባዔ ቤት ማለትም የቅኔ፣ የመጻሕፍት፣ የቅዳሴ፣ የአቋቋም  መምህራንን ቀጥረው የተማሪዎችና የመምህራን መኖሪያ ቤቶችን እና መማሪያ ክፍሎችን ከዚህ በተጨማሪም የዘመናዊ ትምህርት መማሪያ ትምህርት ቤቶችን መገንባት በቦታው ነው። ምእመናንም ቦታውን ዘወትር እንዲመለከቱት ሕጻናትን ሊስቡ የሚችሉ ገዳማዊ ሕይወት በሕጻንነት አእምሯቸው እንዲቀረጽባቸው የሚያደርጉ ማረፊያ ክፍሎችንና የሚታዩ የሚዳሰሱ የሚቀመሱ ነገሮችን ማስቀመጥ ነው፡፡ የሚመጡ መምህራንን እና ተማሪዎችን እንዲሁም ምእመናንን እና ልጆቻቸውን ቀለባቸውን እየሰጠን ለቤተክርስቲያናችን መልካም ልጆችን ማፍራት ነው ይላሉ። እርሳቸውን መደገፍ ማለት ይበርቱ አይዞዎት ማለት ቤተክርቲያናችንን ከተቃጣባት ፍላጻ መታደግ ነው ብየ አምናለሁ። የገዳም ኑሮ የምንኩስና ሕይወት ገብቷቸው የሚኖሩ ናቸው።

አባ ገብረ ሥላሴ ማን እንደኾኑ በመጻፍ የገዳሙን ስም ማስረሳት ጥሩ እንዳልኾነ አውቃለሁ። ነገር ግን ቦታውን ያላዩ ወይም ደግሞ በዚያ ቦታ እንደዚያ ያለ ገዳም እንዲመሠረት የማይፈልጉ ሰዎች በርካታ የሐሰት እና የውንጀላ ወሬዎችን ሲያናፍሱ መመልከት የተለመደ ኾኗል። ይህን ቦታ እንዳይ ያደረገኝም ‹banteamlak zewdu› የተባለ ማንነቱ የማይታወቅ ሰው ፌስቡክ ላይ የገዳሙን አስተዳዳሪ በሐሰት ክስ ሲያብጠለጥላቸው ሳይ ጊዜ ነው። ቦታውን ሳላይ ማን እንደኾኑ ሳላረጋግጥ ቦታው እንዲህ ነው፤ እርሳቸውም እንዲህ ናቸው ብየ ውል የሌለውን የአሉ እና የፈጠራ ወሬ ማውራት ስለማልፈልግ ነው። ይህ ልጅ አባ ገብረ ሥላሴንአቶ ገብሬ› እያለም ሲጽፍ የነበረ እና ከጌታቸው አሰፋ ጋር እንደሚገናኙ ስልካቸውን ጠልፎ እንደሰማቸው አስመስሎ ጽፎ ተመልክቻለሁ። የሕወኃት ተላላኪ ናቸው፤ የአዜብ መስፍን ወንድም ናቸው፤ ከትግራይ የመጡ ናቸው፤ ምንም የቤተክርስቲያን ትምህርት እውቀት የላቸውም ወዘተ እያለም ብዙ ብዙ ነገር ብሏል። ይህ ሰው የጻፈው ኹሉ ውሸት እንደኾነ በሦስት ነገሮች አረጋግጫለሁ።

እርሱሼር አድርጉት› ብሎ ቀስቅሶ ኹሉም ሳያጣራ ሼር ሲያደርግለት ከዚህም አልፎ ኮፒ እያደረጉ ብዙዎች በራሳቸው የፌስቡክ ገጽ ላይ ሳያጣሩ ሲጽፉለት ሲያይ እርሱ ማንነቱን ሰውሮ ስሙን ኹሉ አጥፍቶ አሁን አካውንቱ ተፈልጎ አይገኝም። ወይ ስሙን ቀይሯል ወይ ለጊዜው አካውንቱን አጥፍቶታል። እውነት ተናግሮ ቢኾን ኖሮ አካውንቱን ማጥፋት ለምን አስፈለገው? ወይስ ደግሞ ብከሰስ ምን እመልሳለሁ ብሎ ይኾን?

ትናንት በ15/04/2011 ዓ.ም ማታ አባ ገብረ ሥላሴ እኛን እንግዶቻቸውን አግኝተው ደስ ብሏቸው ከእኛ ማረፊያ ቦታ ላይ መጥተው እስከ ሌሊቱ 6 ሰዓት ድረስ ብዙ ነገር እያወሩን ነበር። በዚያ እርሳቸው እኛን እያወሩን በነበረበት ሰዓት ይኸው ልጅ ‹›አሁን በዚህ ሰዓት ከጌታቸው አሰፋ ጋር እየተነጋገሩ ነበር ንግግራቸውን ጠልፌ ስሰማቸው ነበር፤ ወደ ፊት ድምጹን እልክላችኋለሁ› ብሎ ጽፎ ሳይ ለእርሱ አፈርኩለት። ከእኛ ጋር ቁጭ ብለው እያወሩን ሳሉከጌታቸው አሰፋ ጋር እየተነጋገሩ ነበር፤ ጠልፌ ሰማኋቸው› ብሎ ውሸት ያስጠላል። ሰውን ሽብር እየፈጠሩ አብያተ ክርስቲያናትን ማጥፋት የማን ሴራ ነው? እኛ ሼር የምናደርግ ሰዎችስ ይህን ውሸት ከፈጠረው ሰው በምን እንለያለን? ለምን አናረጋግጥም? አሉ ከማለት ይልቅ እንዲህ ነው ማለት አይበልጥምን? ቦታውን በትክክል በዓይን መመልከት እየኾነ ያለውና እየተባለ ያለው ምን ያህል እንደሚለያይ ማረጋገጥ አይቻልም ወይ?
 
ትናንት ታኅሣሥ 15/2011 ዓ.ም ምሽት 130 አካባቢ ላይ ነው ወደ ገዳሙ የገባን። ከገባንበት ሰዓት ጀምረው ያሳዩን ኹሉ ነገራቸው ገዳማዊነታቸውን ያሳያል። እስከ 6 ሰዓት ድረስ ስለገዳሙ ኹኔታ ብዙ ነገር ሲያወሩን አመሸን። እንደደከመን ሲያዩ ደህና እደሩ ብለውን ሄዱ። ጠዋት ላይ ገስግሰው ተነሥተው መልክአ ቅዱሳንን፤ መልክአ ሰማእታትን፤ መልክአ መላእክትን በቃላቸው ሞክሸ ጠልፎ ሰይወስዳቸው አሰምተው ሲጸልዩ ሰይጣን ምን ያህል እንደሚርድ አምላከ ቅዱሳን ይወቀው? መልክአ ጉባዔን በቃል መቱን ያለምንም መሳሳት ማድረስ መታደል ነው? አንድ የሕወኃት ሰላይ ይህን ሊያደርግ አይችልም። ይህን ያህል ትምህርት አይማርም። እርሳቸው እኮ ቅዳሴን አጠናቅቀው ተምረዋል፣ መጻሕፍትን አጥንተዋል፣ ቅኔ አዋቂ ናቸው። እነዚህን ትምህርቶች ለማዎቅ ስንት ዓመት ይፈጃል? እርሳቸው ይህን ገዳም ማስተዳደር ከጀመሩ 33 ዓመታት ተቆጥረዋል። ከ33 ዓመት በፊት ነው እነዚህን ትምህርቶች የተማሩ፡፡ ታዲያ የሕወኃት ሰላይ ለመኾን ቅዳሴ መማር፤ ቅኔ ማወቅ፤ መጻሕፍትን ማጥናት የግድ ነው ወይ? የሕወኃት ተላላኪ የኾነ ሰውስ ጉዳዩን ሲጨርስ አይሄድም ወይ? እርሳቸው ለተዋሕዶ ሃይማኖት ሲሉ ራሳቸውን አሳልፈው የሚሰጡ ናቸው፡፡ ገዳሙን ለማስከበር የማይኾኑት የማያደርጉት ነገር የለም፡፡ አለማወቅ ለሐሜት ይዳርጋል። አንድ የኔ ቢጤ አላዋቂ ቤተክርስቲያን ሄዶ ካህናት መቋሚያ ሲያነሡ ሲመለከት እየሮጠ አባቱ ላይ ይሄድና አባቴ ዛሬ ካህናት በመቋሚያ ተጫረሱ ይላል። እንዲያው መርጌታም የሉ እርሳቸው አይሻሉም ባይኾን? ይሉታል። እንዲያውም ዋናው የድብድቡ ጀማሪ እኮ እርሳቸው ናቸው አለ ይባላል። ቀረብ ብሎ የማያውቅ ሰው ከዚህ የተሻለ ነገር ሊል አይችልም።

ቤተክርስቲያናችን እንደዚህ ያሉ ነገሮች ሲመጡባት የምትመልሰው መልስመጥተህ እይ› የሚል ነው። ሄዶ ቦታውን ማየትና ማረጋገጥ መልካም ነው። በቃላት የማይገለጡ በርካታ ነገሮችን ታገኛላችሁ። ስለገነት ከመጻፍ፣ ከመናገር፣ ከማስተማር የተሻለው ነገር በጎ ነገር ሠርቶ ገነትን ማየት ብቻ ነው። ይህ ቦታ ትልቅ ተስፋ ያለው ቦታ ነው። አባ ገብረ ሥላሴ ማንም ይኹኑ ማን፣ ከየትም ይምጡ ከየት፣ ምግባራቸው ጥሩም ይኹን መጥፎ ቦታውን ብታዩት ምን ትኾናላችሁ? ቦታውን ብትረግጡት ትኮነኑ፣ ትረክሱ ይኾን? ገዳም ስትሄዱ የገዳሙን አስተዳዳሪ ብላችሁ ነው ወይ የምትሄዱ? አረ ቆም ብለን እናስብ። ምን አይነት አዚም ነው የተጠናወተን?

አባ ገብረ ሥላሴ ከትግራይ ነው የመጡ የሚለው ሲታይ አያሳፍርም ግን? ይህንን አምነህ የተቀበልክ ሰውስ አታፍርምን? እስኪ ታሪክ አገላብጥ አቡነ ተክለሃይማኖት የት ተወልደው ነው ዳሞት የመጡ? አቡነ አረጋዊ የት ተወልደው ነው ደብረ ዳሞ የመጡ? አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የት ተወልደው ነው ዝቋላ የመጡ? ባሕታዊ ገዳማዊ ሰው የሃይማኖት ሰው ሀገር አለው? ሀገሩንስ መጠየቅ አለበት? ከየት መጣህ መባልስ አለበት? እንኳን ከታቦተ ጽዮን መዲና ቀርቶ ከመሐመድ ሐገር ከዐረብስ ለምን አይመጡም? እኛ ምን አገባን? ይህንን አይተን ስለነበር እርሳቸውን ጠይቀናል። መጀመሪያ ይህ ጥያቄ መጠየቅ የማይገባው እንደኾነ እናውቃለን። ግን የሰውን አእምሮ ነጻ ለማድረግ መጠየቅ አስፈላጊ ስለነበር ጠይቀናል እርሳቸውም መልሰውልናል፡፡ ምንኩስናቸው ዋልድባ አብረንታንት ገዳም ነው። የተወለዱት ጎንደር ነው። ግን ጎንደር ተወለዱ ትግራይ ተወለዱ ለእኛ ምን አገባን? ወደዚህ ገዳምም ሳያስቡት እንደመጡ ቅድስት ሀና ቤተ ክርስቲያን መቅደስ ውስጥ ሳለሁ እጄን ማን እንደኾነ ሳላውቅ ታሥሬ ቀረሁ ይላሉ። ከዚያ ገዳም ወጥቼ ሄጀ ነበር ነገር ግን በደም ተመትቼ ከሞት ተርፌ ያየሁትን አይቼ ተመልሸ መጣሁም ብለውናል። ብታይዋቸው በነጻነት እኮ ነው የሚያናግሩ። እገሌ free ነው እኮ እንላለን አይደል? እንደርሳቸው ያለ ግን free ሰው ያለ አይመስለኝም፡፡ እብድ ነው የሚመስሏችሁ እኮ፡፡ ሰው ለጠየቃቸው ኹሉ መልሳቸው ጠያቂው ያላቸው ነው፡፡ ‹አባ ሽፍታ ነዎት ይባላል እውነት ነው?› ብትሏቸው ‹አዎ ልጄ እንደእኔ ያለ ወንበዴ እኮ የለም ነው› የሚሉ፡፡

የቤተ ክርስቲያን እውቀት የላቸውም የሚለው ክስ ግን ሄዶ በመጠየቅ አስተምሩኝ በማለት የሚፈታ መልስ ነው። ቅኔውንም፣ መጽሐፉንም፣ ቅዳሴውንም መጠየቅ ትችላላችሁ። እስኪ አረጋግጡ በሐሜት አትታመሱ። ቦታውን ያየ በተአምሩ የተደነቀ ሰው በጣም ይታዘባችኋል። ጠበሉን ተጠምቆ 1 ቀን እየተፈወሰበት ያለ ከዚህም በላይ ገና ቦታውን ሲረግጡ መንፈስ ርኩስ ለቆ የሚሄድበት ከኤድስ ጀምሮ ሌሎችንም ከባድ የሚባሉ በሽታዎችን በጥቂት ቀናት የሚገላገሉበት ተአምረኛ ቦታ ነው። አሁን አሁን እንዲያውም የገዳሙን እንጀራ ሲቀምሱ ያለባቸው ደዌ በሙሉ የሚጠፋበት ልዩ በረከት ያለበት ነውም ብለውናል፡፡


ገዳሙ እንዳይታወቅ በአስተዳዳሪው ላይ የተነዛው ወሬ ለምን መጣ? የሚለውን ለማረጋገጥም ሞክረናል። ጉዳዩ በበጀት የሚመራ የመናፍቃን እጅ ያለበት ነው። የአካባቢው ምእመናንንም እንዲነሡባቸው የተደረገው ይህን ቦታ እንደ ዲማ ሊያደርጉብን ነው በሚል ነው። ምእመናን የገዳሙን የእርሻ ቦታ መውረስ ይፈልጋሉ። ከዚህ በተጨማሪ 3000 በላይ የኾኑ ሀገር በቀል የጽድ ዛፎችን ቆርጠው ለግል ጥቅማቸው ማዋል ይፈልጋሉ። ከዚህ ኹሉ የበለጠው ግን አካባቢው ላይ የሚኖሩት ምእመናን አብዛኞቹ ቅብዐቶች መኾናቸው ነው። አባ ዐሥራት ገዳም እዚህ ደብረ ማርቆስ አጠገብ የቅብዐት ምንፍቅና እየተማሩ እያሠለጠኑ ሲያስመርቁ እያየን ተኝተናል። አንድ ተው ባይ እንኳ የለበትም። እንዲያውም ይህን ጉዳይ አታንሡት እየተባለ ያለበት ጊዜ ነው። ጅብ እግሩን እየበላው ጓደኛውንተው ዝም በል የእኔን እግር ነው የሚበላ› ያለውን ጅል ሰው የኾንበት ዘመን አሁን ነው። HIV የተያዘ ሰውተው እባካችሁ ኤድስ እያላችሁ አታውሩ ተውት ዝም በሉ ስሙን አትጥሩት› እያለ መድኃኒት ባይፈልግለት ውስጥ ለውስጥ ገዝግዞ ገዝግዞ ሚገድለው ራሱን በሽተኛውን እንጂ በሽታውን አይደለም። የእኛ ቤተክርስቲያን አሁን ላይ ጤንነቷ ያሰጋል። የእነጋትራ አካባቢ ሰዎችም አባ ገብረ ሥላሴ ላይ የሐሰት ወሬ እየዘሩ የሚገኙት ከዚህ የተነሣ እንደኾነ ተረድቻለሁ። አባ ገብረ ሥላሴ ለሃይማኖታቸው ምንም ድርድር የላቸውም አድር ባይነት አያውቁም። የፈውስ ጥምቀት ለመጠመቅ እንኳ ተዋሕዶ መኾኑን ማረጋገጥ አለባቸው፡፡ ተዋሕዶ ያልኾነን ሰው ለፈውስ ጥምቀት አያስገቡትም፡፡ ማንም ይሁን ማን ለማንም ይሁን ለማን አያጎበድዱም። ቅብዐት ምንፍቅና ነው ተጠመቅ እያሉ ያስተምራሉ። ይህን ጥምቀት የማይፈልጉ ሰዎች ናቸው እንግዲህ ይህን ሁሉ ውሸት የሚፈበርኩ። በእነዚህ የሀሰት ፋብሪካዎች አእምሯችሁን የቆለፋችሁ ሰዎች ሂዱና ቦታውን ተመልከቱትማ።

አርብ ታኅሣሥ 19/2011 ዓ.ም በቅዱስ ገብርኤል በዓል በገዳሙ ውስጥ በሚገኘው ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ውስጥ ቅዳሴ ይቀደሳል በዓሉም ይከበራልና እባካችሁ የበረከቱ ተካፋይ መኾን የሚፈልግ ኹሉ ይምጣና ቦታችንን አይቶልን ይሂድ በረከቱንም ይካፈለን ብለዋል። እስኪ ሄደን የማረጋገጥ ነገር ይኑረን። አሉ የሚባለውን በሽታ እናሰወግድ። እዚህ ላይ ብጽፈው በተቃራኒው ለቆሙ ሰዎች መረጃ ስለሚኾናቸው መጻፍ አልፈልግም እንጂ እንደ አባ ገብረ ሥላሴ ፈሊጥ አዋቂ መነኩሴ አላየሁም። በእውነት ነው የምላችሁ ፈሊጠኛ ናቸው።

ትናንት የለጠፈውን ዛሬ የሚያጠፋ ውሸታም የበተነውን የሀሰት ወሬ ወደ ጎን ጣሉትና እስኪ ቦታውን ተመልከቱ። እርሳቸው ምንም ይኹኑ ምን ቦታው ግን የእኛ ነው። እርሳቸው ሥጋ ለባሽ ናቸው በጎ ሊባሉ አይችሉም ግድ ነው። በታሪክ ደግሞ በጎ የተባለ መነኩሴ አላውቅም። አቡነ ተክለሃይማኖትን ተመልከቱ። አቡነ ተክለ አልፋን ተመልከቱ። ማንም እየተነሣ እኮ ነው የሚዘምትባቸው። ክርስቶስስ ምን እንደተባለ ጠፍቷችሁ ነው? አባ ገብረ ሥላሴ ሽፍታ ወንበዴ ናቸው ነው የሚባሉ። እርሳቸው ሽፍታ ወንበዴ እንደመባል የሚያስደስታቸው ስም የለም። ሊቃነ ጳጳሳት እየደወሉአሁንም ስምህ ሽፍታ እና ወንበዴ መባል ነው?› ብለው ይጠይቁኛል።አዎ› ስላቸውበርታ በዚያው ቆይ በጎ ሰው ነው ያሉህ ቀን ግን አንድ ቀን እንዳታድር› ይሉኛል ብለውናል። እርሳቸው ቦታውን እንዲለቁ ከፈለጋችሁ እሽ ብላችሁ ያቀዱትን ሥራ አግዟቸው። ያንን ሠርተው ከጨረሱ እርሳቸው ሌላ ዓላማ የላቸውም። ለመነኮስኩበት ለዋልድባ አፈር አብቃኝ እያሉ የሚጸልዩ አባት ናቸው፡፡ የሚደንቀኝ ነገር 5 ሳንቲም አምጡ የማይባልበት ቦታ ላይ፣ ዓመት ኹለት ዓመት ብትኖር ዝም ብለህ ብላ ጠጣ በሚባልበት ቦታ ላይ የምእመናን መነሣሣት ምንድን ነው? የአካባቢው ምእመናን የዘሩትን በማበላሸት ያጨዱትን በመስረቅ ላይ ናቸው ዛሬ ድረስ። ጎጃም ውስጥ ገዳም አይውጣ የተባለ ይመስላል እኮ። እኔ የማውቀው አንድ ቦታ አለ። ቦታ ገዳሙ ተፈቶ የቅዱሳኑን አጽም በማረሻ እያረሱ እያወጡ በዚያ ስንዱ ዘርተው የሚበሉ አሉ። ይህንንም ገዳም ልክ እንደዚያ ለማድረግ ነው የሚጣጣሩት። በርካታ መጻሕፍትን ምእመናን ዘርፈዋል የአብነት ትምህርት ቤቶችንም አቃጥለዋል። የዚህን ገዳም ታሪክ የያዘው ምእላድ የተባለውን መጽሐፍም አብረው አቃጥለውታል። ታዲያ ይህ ሲኾን እኛ ገዳሙን ማገዝ ሲገባን አሉ የሚሉ ሰዎችን ሼር እያደረግን ገዳሙ እንዲፈታ ባናደርግ መልካም ነው። ብዙ የሚባል ነገር አለ እኔ አልጽፈውም ሄዳችሁ አረጋግጡ። ቅዱሳት መካናትን የምንሳለመው የቃልኪዳን ቦታ በመኾናቸው እንጂ አስተዳዳሪዎችን ብለን አይደለም። ከአስተዳዳሪዎች በረከት የሚሻ እነርሱንም ጸልዩልን ይበል ካላመነባቸው ቦታውን ተሳልሞ ይመለስ በቃ። ምንም እኮ አውጡ አልተባልንም። በቪዲዮ የያዝነውን መረጃ ወደ ፊት እናቀርባለን።

19 የቅዱስ ገብርኤሉን ቅዳሴ ግን አስቡበት።

0911791828
ላይ ደውላችሁ ራሳቸውን አባ ገብረ ሥላሴን ማግኘት ትችላላችሁ። እስኪ አይዞዎት በሏቸው፡፡ ዓላማቸው የግብጹን ገዳመ አስቄጥስ በጎጃም መትከል ነው፡፡ ምእመናንም የተነሡባቸው ዲማን አመጣብን ብለው ነው፡፡ እውነታው ይኼው ነው!