Wednesday, August 26, 2015

ባማ

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በርካታ አማርኛ ያልሆኑ ቃላትን እናገኛለን፡፡ ለምሳሌ፡- አማኑኤል፣ ኤልሻዳይ፣ አዶናይ እና የመሳሰሉትን ማየት ይቻላል፡፡ አሁን እነዚህ አማርኛ ያልሆኑ ቃላት ከእብራውያን፣ ከሮማውያን ወይም ከግሪካውያን የተወሰዱ ናቸው፡፡ ከሌሎች መወሰዳቸው ችግር ባይሆንም በትክክል ትርጉሙን መረዳት አለመቻል ግን ትልቅ ስህተት ነው፡፡ አማርኛ ብቻ የሚናገር ሰው ላይ በጥሬው ማለት ሳይተረጎሙ የቀሩ ቃላትን ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እየመዘዝን መጠቀም ትልቅ ሊያስብለን የሚችል አይመስለኝም፡፡ በእርግጥ ትርጉሙን ካወቅንና ለማሳወቅ ጥረት ካደረግን እውነትም ትልቆች ልንባል እንችል ይሆናል፡፡ ነገር ግን አሁን እየተመለከትን ያለነው ነገር የዚህ ተቃራኒ ነው፡፡ እነዚህን መሰል ቃላት በባትሪ እየፈለግን ለመዝሙር ወይም ለስብከት ርእስነት ስንጠቀም እንስተዋላለን ትርጉማቸውና መዝሙሩ ወይም ስብከቱ ግን የማይገናኙ ነገሮች ናቸው፡፡ እኔ አሁን ማሳየት የምፈልገው ቃል ከላይ በርእሱ ላይ ያስቀመጥኩትን ቃል ይሆናል “ባማ”፡፡ ምናልባት ዘግይቼ ሊሆን ይችላል ለመጻፍ ያነሣሣኝ ግን በዩ ቲዩብ ላይ ኦርቶዶክስ መዝሙር ብየ ስፈልግ አንድ መዝሙር ስሰማ እጅግ በጣም ስለገረመኝ ነው፡፡ የመዝሙሩን ግጥሞች እና የአስተዋዋቂውን የባማ አተረጓጎም እንዲህ እንመልከተው፡፡ ማዳመጥ የሚፈልግ ደግሞ ይህንን ሊንክ ይጫን፡፡ https://www.youtube.com/watch?v=3fQzC6SfBpE
“ባማ የሚለው ቃል የእብራይስጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም ከፍታ ማለት ነው” ይላል አስተዋዋቂው፡፡ ከዛም ዘማሪዋ ይህንን ግጥም ትዘምረዋለች፡
ባማ በማ ነው ለሕይወቴ
ውበት ሰላም ነው ለቤቴ
ክብር የሆነኝ ከፍታ
እርሱ ነው የሞተልኝ ጌታ
መዳፌን አረሰረሰው
ጓዳዬን በረከት ሞላው
ሹመቴ ሆነኝ ከፍታ
ኢየሱስ የነፍሴ ጌታ
መቅረዜ ሆነኝ ብርሃን
ደህንነት ማረፊያ ዙፋን
ጠባቂ የነፍሴ እረኛ
ትጉህ ነው ከቶም አይተኛ
ከትቢያ ከወደቅሁበት
አነሣኝ መዳኔን ሽቶ
በፍቅር ምህረቱ በዝቶ
አዳነኝ ስለኔ ሞቶ
የጠላት ክንዱን አውርዶ
ቀኝ ሆነኝ በኃይሉ ወርዶ
ለክብሩ አንበረከካለሁ
ለስሙ እዘምራለሁ

በእውነት “ባማ” የሚለው ቃል አስተዋዋቂው እና ዘማሪዋ እንዳሉት ነውን? አረ ምን ነካህ በፍጹም እንደምትሉኝ አልጠራጠርም፡፡ ታዲያ ትክክለኛ ትርጉሙን በጋራ እንመልከተዋ፡፡ ሊቀ ሊቃውንት ያሬድ ሽፈራው 1997 ዓ.ም ባሳተሙት መጽሐፈ ግስ ወሰዋስው መርኆ መጻሕፍት ላይ ገጽ 322 ላይ እንዲህ ይተረጉሙታል፡፡ ባማ፡- በተራራ ላይ የተሠራ የጣዖት ቤት ካሉ በኋላ ለማስረጃነትም እንዲህ ይጽፋሉ “ምንት ውእቱ ባማ ዘተሐውሩ አንትሙ” ሕዝ 20÷29 ብለው ይደመድሙታል፡፡ ስለዚህ የባማ ትክክለኛ ትርጉሙ ከፍታ ማለት ሳይሆን ከፍታ ላይ የተሠራ የጣዖት ቤት ማለት ነው፡፡ ይህንን ከላይ ጀምረን መጽሐፉን እናንብበው፡፡ ሕዝ 20÷28-31 እነዲህ ይላል፡፡ እሰጣቸውም ዘንድ ወደማልኹላቸው ምድር ባገባኋቸው ጊዜ ከፍ ያለውን ኮረብታ ሁሉ ቅጠልማውን ዛፍ ሁሉ አዩ በዚያም መስዋእታቸውን ሠዉ በዚያም የሚያስቆጣኝን ቁርባናቸውን አቀረቡ፡፡ በዚያም ደግሞ ጣፋጩን ሽታቸውን አደረጉ በዚያም የመጠጥ ቁርባናቸውን አፈሰሱ፡፡ እኔም እናንተ ወደርሱ የምትሄዱበት ከፍታ ምንድር ነው? አልኋቸው፡፡ እስከዛሬም ድረስ ስሙ ባማ ተብሎ ተጠርቷል፡፡ ቁርባናችሁን ባቀረባችሁ ጊዜ እስከ ዛሬ ድረስ ልጆቻችሁንም በእሳት ባሳለፋችሁ ጊዜ እስከዛሬ ድረስ በጣዖቶቻችሁ ትረክሳላችሁን? የእስራኤል ቤት ሆይ ከእናንተስ ዘንድ እጠየቃለሁን? እኔ ሕያው ነኝና ከእናንተ ዘንድ አልጠየቅም ይላል ጌታ እግዚአብሔር፡፡” ምንም ሳልጨምር ምንም ሳልቀንስ ቃሉን እንዲህ ጻፍሁላችሁ፡፡ እንግዲህ የባማ ትክክለኛ ትርጉም ይኼው ነው፡፡
ሌላው ኪዳነወልድ ክፍሌ መጽሐፈ ሕዝቅኤልን ተርጉመው በ1917 ዓ.ም ባሳተሙት መጽሐፈ ሕዝቅኤል ከትርጓሜው ጋራ ገጽ 208 ላይ ግእዙን በአማርኛ እንዲህ ተርጉመውት እናገኛለን፡፡ “ወእቤሎሙ ምንት ውእቱ ባማ ዘተሐውሩ አንትሙ ህየ” እኔ አንድ ነኝ ስል አንድ ቦታ አሳይቻችሁ ነበር እናንተ የእኔን ትእዛዝ አፍርሳችሁ በየቦታው የሰራችሁት ጧት ማታ የምትሄዱበት ቤተ ጣዖት ምን ልዖል ነው ምን ልዕልና አለው አልኋቸው፡፡ “ወተሰምየ ስሙ ባማ እስከ ዛቲ ዕለት” ስሙ እስከዛሬ ድረስ ባማ ተባለ ባማ ማለት ልዑል ነዋኅ ማለት ነው ይላሉ፡፡ አሁንም እንደቅድሙ ሁሉ ባማ ማለት ልዑል ነዋኅ (ከፍታ) ማለት ነው፡፡ ከፍታነቱ ግን ከላይ ሲተረጉሙት ዘተሐውሩ የምትሄዱበት ቤተ ጣዖት ልዑል ነዋኅ ትልቅ ከፍታ ነው ብለውታል፡፡ ስለዚህ ባማ ማለት ከፍታ ላይ ያለ ጣዖት ማለት ነው፡፡ ባማ ማለት ከፍታ ብቻ ቢሆን ኖሮ ለምን ወደዚያ ቦታ ሄዳችሁ? መስዋእታችሁም የረከሰ ነው ባላላቸው ነበር፡፡ ስለዚህ ባማ ማለት ከፍታ ላይ የተሠራ ጣዖት ማለት ነው፡፡
ስለዚህ ቃላትን ዝም ብለን በሚመስለን እየተረጎምን የማይገባ ሥራ ባንሠራ እላለሁ፡፡ ምክንያም ኢየሱስ ክርስቶስን ባማ በማ ነህ ለሕይወቴ ማለት ምን ማለት ነው? በትክክለኛ ትርጉሙ ካየነው እኮ በጣም ከባድ ኑፋቄ ነው፡፡ “ኢየሱስ ክርስቶስ ለሕይወቴ ከፍታ ላይ የተሠራህ ጣዖት ነህ ማለት እኮ ነው” ሎቱ ስብሐት፡፡ እኔም እንዲህ በመጻፌ “አቤቱ ማረኝ ይቅር በለኝ ብዬ እጸልያለሁ” ማስተማር ስላለብን ነው፡፡ እባካችሁ ልብ እናድርግ እናስተውል፡፡

ፈጸምኩ

ዓለም ለበርባን ናት /ክፍል አራት/

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ተሐድሶ መናፍቃኑ ያሰባሰቧቸው የአፍ ደጋፊዎች በተለያዩ ማኅበራዊ መገናኛዎች እገሊት እገሌ ካጠመደባት ወጥመድ ነጻ ሆነች፣ እገሌን እንዲህ የሚባለው ማኅበር አስደበደበው ሃብት ብረቱን ዘረፈው እያለች ደጋፊዋን ትለቃቅማለች፡፡ እውነት በቤተክርስቲያን ያደገ ሰው ከኢየሱስ ክርስቶስ እንጅ ከበርባን ምን ሊማር ይችላል? በርባን እህቱን ሰጥቶ ከእስር ቤት ሊወጣ ይጥራል ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ ከኃጢአት ነጻ ሊያወጣ ከመስቀል ላይ ይሰቀላል፡፡ ምንም ኅብረት የላቸውም፡፡ የደጋፊ ብዛትና ቁጥር ለፖለቲካ ፓርቲዎች ካልሆነ በቀር ሃይማኖት ውስጥ ምን ቦታ አለው? ዘረኝነት በቤተክርስቲያናችን ውስጥ ምን ቦታ ሊኖረው ይችላል? በእውነት በተዋሕዶ እምነት ውስጥ ያለ ግለሰብ ወይም ማኅበር በግለሰቦች ላይ ወይም በማኅበራት ላይ ወጥመድ የሚያጠምደው ለምንድን ነው? ማንንስ ለማጥመድ ይሞክራል? የሚጠመደውስ ለምን እንደሚጠመድ ያውቃልን? መጠማመድ እዚህ ውስጥ ምን አገባው? መጥመድ መጠመድ ያለው በእርሻ ሥራ ላይ ብቻ ነው በእርግጥ እሱም ትራክተር እየተካው ስለሆነ መጥመድና መጠመድ አየቀረ ነው፡፡ ታዲያ እርሻ ላይ የቀረው መጠማመድ ቤተ ክርስቲያን እንዴት ብሎ ሊመጣ ቻለ? አንዳንዴ እንቆቅልሽ ነገር ይመስላል፡፡
በእርግጥ ዓለም ለበርባን ናት፡፡ በርባንን ትደግፈዋለች፣ ታሞግሰዋለች፣ ትሸልመዋለች፣ ታከብረዋለች፣ ታጨበጭበለታለች ግን ለምን? መልሱን መመለስ አትችልም፡፡ በርባን የወንበዴዎች አለቃ ነው ብለናል፡፡ ታዲያ አጨብጫቢዎችስ ምን ሊባሉ ይችላሉ? የወንበዴዎች አለቃ መሆኑን አምነው የሚያጨበጭቡ አሉ፣ወንበዴ መሆኑን ሳያውቁ ሰዎች ስላጨበጨቡለት ብቻ አብሮ አለ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ማጨብጨብ ደስ ስለሚላቸው ብቻ የሚያጨበጭቡለት ናቸው፡፡ የወንበዴነቱን አለቅነት አውቀው የሚያጨበጭቡ ሰዎች ሳያውቁ የሚያጨበጭቡለትን ሰዎች ቁጥር ለማብዛት ይጥራሉ፡፡ አሁን እያየን ያለው ነገር እርሱን ነው፡፡ ሃገር ውስጥ አልበቃ ብሏቸው እስከ ሃገር ውጭ ድረስ መስመራቸውን ዘርግተዋል፡፡ የማኅበራዊ ድረገጾች እና መገናኛዎችም እንደ ታንቡር ይደልቃሉ እንደ ደወልም ያቃጭላሉ፡፡ የዋሃንን ለማታለል ብዙ የበርባን ደጋፊዎች ብዙ ነገር ይጥራሉ ብዙ ሥራን ይሠራሉ፡፡
ጹሙ፣ ጸልዩ፣ ንስሐ ግቡ ብሎ ደፍሮ የማያስተምርና ደፍሮ የማይዘምር ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት የማይናገር ስለ ድንግል ዘላለማዊ ድንግልናና ክብር የማይናገር ምሥጢራትን ጠንቅቆ የማያስተምር መምህር እና ዘማሪ ለተዋሕዶ አይረባትም አይጠቅማትምም፡፡ መናፍቃን የሚናገሩትንና የሚያስተምትን የሚዘምሩትንና የሚናገሩትን ገልብጠው በቤታችን መጥተው ከመድረኮቿ ላይ ቆመው በነጭ ልብስ ተጎናጽፈው የሚለፈልፉ ተሐድሶ መናፍቃን በርባንን ፍቱልን የሚሉ ናቸው፡፡ ታዲያ ለእነዚህ ማጨብጨብ ማለት ምን ማለት ነው? ምንም ሊገባኝ አይችልም፡፡ አምላክ ልብ እንዲሰጣቸው ጸልዩ በማለት ፋንታ ማጨብጨብን ምን አመጣው? ቆም ብለን ልናስተውል ይገባል፡፡ ስለ እውነት ግን የትኛው መዝሙራቸውና ትምህርታቸው ነው የቤተክርስቲያናችን ጣዕምና ለዛ ያለው? ነገር ግን ዓለም ለበርባን ናትና ዛሬም ድረስ አጨብጫቢዋን ትፈልጋለች፡፡
ተፈጸመ