Friday, January 29, 2016

“ፍቅረ ኦርጋን”


© በመልካሙ በየነ
ጥር 18/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ዛሬስ ደግሞ ምኖች መጡና አረፉታ! እነ “ብጹእ ወቅዱስ አቡነ” መልከጼዴቅ እነ “ቀሲስ” መላኩ ተረፈ ፍቅረ ኦርጋን አንገበገባቸው አንሰፈሰፋቸውሳ፡፡ አንድ ሞኝ የተከለውን ሃምሳ ሊቃውንት አይነቅሉትም አለ የአገሬ ሰው፡፡ እናንተ ሰነፎች! እናንተ ጅሎች! እናንተ ሞኞች! ዛሬ ለመትከል የምትሯሯጡትን ምንፍቅና ሀምሳ ሊቃውንት ለመንቀል በሚያስቸግራቸው ሁኔታ ልታደርጉት ነው የተነሣችሁ፡፡ እየቀላቀላችሁ ትውልዱን ልትነጥቁት የበግ ለምድ የለበሳችሁ ተኩላዎች እባካችሁ ታገሱ ወደ ልባችሁ ተመለሱ፡፡ እንዴ! ምን ሆናችሁ? ምን ነካችሁ? የክርስቶስን ጥምቀት ልብ በሉት እንጅ፡፡ ጌታ ነው ወይስ ባሪያው ዮሐንስ ነው ወደ መጠመቂያ ቦታው የሄደው? መጠመቅ የፈለገው ነው ወይስ ማጥመቅ የፈለገው ነው ወደ መጠመቂያው የወረደው? ረስታችሁታል መሰለኝ፡፡ አቡኑም ቀሲሱም ረሳችሁት? እሽ ልመልስላችሁ ጌታ መጠመቅ ፈለገ ወደሚያጠምቀው ባሪያው ወደ ዮሐንስ ሔደ፡፡ ከዚህ እንደምንረዳው መጠመቅ የሚፈልግ ሰው ነው ወደ መጠመቂያ ቦታው መሔድ ያለበት አይደል፡፡ ስለዚህ እንደዚያ ከሆነ ፍቅረ ኦርጋን ያቃጠለው ሰው ኦርጋን ወደሚገኝበት ቦታ መሄድ መብቱ ነው፡፡ ነገር ግን እርሱ ፍቅረ ኦርጋን ስላደረበት ሌሎችንም ፍቅረ ኦርጋን እንዲያድርባቸው ማስገደድ አይችልም፡፡ መብቱም አይደለም፡፡
በ1970ዎቹ አካባቢ የወጡ የመዝሙር ካሴቶች ለምሳሌ ሊቀ መዘምራን ኪነ ጥበብ ወ/ቂርቆስ ቁጥር1 እና 2 እንዲሁም ሌሎች ኦርጋንን ተጠቅመው መዝሙር አሳትመዋል፡፡ አሁን እነዚህ ፍቅረ ኦርጋን ያንገበገባቸው ሰዎች እንደማሳመኛ የሚጠቀሙት ይህንን የሊቀ መዘምራን ኪነ ጥበብን እንደቸርነትህ የሚለውን በኦርጋን የተሠራውን መዝሙር ነው፡፡ በሆነ ዘመን የሆነ ጅል የተከለውና ሊቃውንት ለመንቀል አልመቻቸው ብሎ የቆየው በኋላ ግን ጊዜው ሲደርስ የነቀሉት አረም ነው ኦርጋን፡፡ ታዲያ የዚያን ዘመን የነበሩትን ጳጳሳት እንደማስረጃ ልንጠቀምባቸውና የአሁኑን ሥርዓተ ቤተ-ክርስቲያን ልንጥስበት አንችልም፡፡ ያ ዘመን በቃ ከነችግሩ ከነኃጢአቱ ከነቆሻሻው ተጥሏል፡፡ አዲስ አዋጅ አዲስ ሥርዓት ተሠርቷል፡፡ ኦርጋንን መጠቀም አይቻልም ተብሎ የእኛ የሆኑት መሰንቆ፣ በገና፣ ጸናጽል፣ መቋሚያ፣ እንቢልታ፣ ከበሮ ተለይተው ልንጠቀምባቸው ሥርዓት ተሠራልን፡፡ ይህ የሆነው እኮ የዛሬ ስንት እና ስንት ዓመት ነው፡፡ ታዲያ እስከዛሬ የት ነበርን? ዳንስ ያማራችሁ ጭፈራ ያማራችሁ ዛሬ ነው እንዴ? ወይስ ደግሞ ብቻችንን ከምንጨፍር ብቻችንን ከምንደንስ ልጆቻችንን ይዘናቸው እንጥፋ ነው?
ሌላው በጣም የሚገርመኝ ነገር አርጋኖንን እና ኦርጋንን በማቀላቀል በሕዝቡ ዘንድ ብዥታን ለመፍጠር የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ነው፡፡ “ሊበሏት ያሏትን አሞራ ጅግራ ናት ይሏታል” ነው የሚባለው አይደል፡፡ አርጋኖን ማለት እኮ ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ብቻ የምንጠቀምባቸው ከብረት ከእንጨት ወይም ከነሐስ የተሠሩ መሣሪያዎችን እንደ ጸናጽል እንደ እንዚራ ያሉትን የሚያጠቃልል ነው፡፡ በሌላ በኩል አርጋኖን ማለት አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እመቤታችንን ያመሰገነበት የምስጋና መጽሐፍ ነው መጽሐፈ አርጋኖን እንዲል፡፡ ሌላም አርጋኖን ማለት የበገና ሰላምታ የበገና ድርድር ማለት ነው፡፡ ነገር ግን እነ “አቡነ” መልከጼዴቅ እና እነ “ቀሲስ” መላኩ ተረፈ ፍቅረ ኦርጋናቸውን በአርጋኖን ስም ለውጠው ብቅ ብለዋል፡፡ “አቡኑ” ወይም “ቀሲሱ” በነካ እጃችሁ በተናገረ አፋችሁ እዛው ጨርሱት መቼም አንዴ ከስራችኋል አርጋኖን አትበሉ ኦርጋን በሉ፡፡ አርጋኖኑን እኛው እናመስግንበት ኦርጋኑን ግን እናንተው እንደጀመራችሁ ጠቅልላችሁ ውሰዱልን አንፈልገውም፡፡ እኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ለራሷ ብቻ ሳይሆን ለዓለምም የተረፈ ምርጥ ምርጥ ልብን የሚመስጡ ንዋያት አሏት፡፡ እኛ መሰንቆው ይበቃናል፣ እኛ ጸናጽሉ ይበቃናል፣ እኛ ከበሮው ይበቃናን፣ እኛ በገናው ይበቃናል፣ እኛ መቋሚያው ይበቃናል፣ እኛ እንዚራው እንቢልታው ይበቃናል፣ እኛ የእኛ የሆነው ብቻ ይበቃናል ይህ አልበቃው ያለ ሰው ግን እዛው ከለመደው ባዶ አዳራሽ ገብቶ ይደንስ ይጨፍር መቼስ ምን እናደርገዋለን፡፡ ያላወቀውን እናሳውቃለን አዋቂ ነኝ ያለውን ግን ምን እናደርገዋለን፡፡ ሰው በስተርጅና ዳንስ ጭፈራ እንዴት ይመኛል? ያውም ጳጳሱ አቡነ አቡነ የምንላቸው ያውም ቀሲሱ ይፍቱኝ ይባርኩኝ የምንላቸው፡፡
ለዚህ ትቅልድ ግን መልእክቴ አርጋኖን ስንል የሙዚቃ መሣሪያ የሚለው የእነ አቡኑ እና የእነ ቀሲሱ አመለካከት እንዳይሸረሽራችሁ ነው፡፡ እነርሱ ኦርጋን ለማለት ፈልገው ነው ሳያውቁት አርጋኖን ያሉት፡፡ አርጋኖንን የእመቤታችን ፍቅሯ ጣዕሟ ውዳሴዋ የሚበልጥበት ክርስቲያን ገዝቶ የሚጸልየው መጽሐፍ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን እናመሰግነዋለን መጽሐፈ አርጋኖንን እንጸልይበት ዘንድ ከእናታችን ከእመብርሃን ረድኤትን በረከትን እናገኝ ዘንድ ስለረዳን፡፡ ዛሬ ፍቅረ ኦርጋን ያደረባቸው ሰዎች አርጋኖን እያሉ ስሙን ለመቀላቀል ቢፈልጉም እኛ ግን አባቶቻችን መምህራን አባቶቻችን ሊቃውንት እንዳስተማሩን እነዳሳዩን እንጓዛለን እንመራለን፡፡

Wednesday, January 27, 2016

“ዋናው አድሮ መገኘቱ ነው”

© በመልካሙ በየነ
ጥር 17/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ሰው ነህና መቼም ፈተና ይገጥምሃል፤ ደካማ ነህና ደግሞ አምላክህን ታማርራለህ፡፡ የፈጠረህ አምላክ ነገ ላንተ ያዘጋጀልህን ነገር ሳታውቅ በዛሬው ነገር ላይ ብቻ ጭንቅላትህ እስኪፈነዳ ድረስ ትጨነቃለህ፡፡ ነገር ግን ነገ ሌላ ቀን ነው በእውነት ነገ ሌላ ነው፡፡ ሰው መሆናችን ከሌላው ፍጥረት የሚለየን ነገን ተስፋ በማድረግ መኖራችን ነው፡፡ እንስሳትን ተመልከት ነገን ተስፋ አያደርጉም ምክንያቱም አእምሮ የላቸውምና ነው፡፡ ዓለም በፈተና የተሞላች ናት ሰው ደግሞ በዚህች ዓለም ውስጥ ሲኖር የግድ የፈተናው ተቋዳሽ መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡ አንተ የምትጨነቀው ብታገኘው ስለሚጎዳህ ነገር ሁሉ ነው፡፡ ፈጣሪ ደግሞ የለመንከውን ሁሉ የማይሰጥህ እንዳትጠፋበት፣ እንዳትሞትበት፣ እንዳትጎዳበት ነው፡፡ ወደፊት የሚመጣውን የሚያውቀው ፈጣሪ ብቻ ነው ነገን ማን ያውቃል? አንተ ነቢይ አይደለህም፤ ያለፈውንና የሚመጣውን አትመለከትም፤ ታዲያ ዛሬ ላይ ሆነህ ስለዛሬ ብቻ ስለምን ትጨነቃለህ? ስለምንስ ፈጣሪህን ታማርራለህ? በእውነት አምላካችን እኮ እኛ ስለእኛ ከምንጨነቅበት የበለጠ ያስብልናል፡፡ የምንተነፍሰው አየር የማን ነው? የምንጠጣው ውኃ የማን ነው? የምንሞቀው ጸሐይ የማን ነው? የምናይበት ዓይናችን፣ የምንሔድበት እግራችን፣ የምንዳስስበት እጃችን፣ የምንሰማበት ጆሯችን፣ የምናሸትበት አፍንጫችን …የማን ነው? እስኪ አስቡት እኛ ለእኛነታችን ምን አስተዋጽኦ አበርክተናል? ምንም!
አንተ የበላይህን እያየህ የበታችህን ሳትመለከት የቤትህን መጉደል እየተመለከትህ ትጨነቃለህ፡፡ አንተ በኪራይ ቤት ስለምትኖር ሌሎች የራሳቸውን ቤት ስለሠሩ እኔስ መቼ ይሆን ቤት የምሠራው? እያልክ ራስህን ትጠይቃለህ፡፡ ግን መልስ የለህም ምክንያም የጠየቅኸው ጥያቄ መልስ የሚያገኘው በፈጣሪ ስለሆነ፡፡ ከአንተ በታች የሚከራዩበት ገንዘብ አጥተው ሜዳ ላይ የቀን ጸሐይ የሌሊት ቁር የሚፈራረቅባቸውን ወገኖችህን አላስታወስክም፡፡ አንተ የበላይህን እየተመለከትህ በቀን 3 እና 4 ጊዜ የተለያየ ይዘት ያለውን ምግብ እንዴት እና መቼ መቼ ልመገብ እያልክ ትጨነቃለህ፡፡ ነገር ግን በቀን አንድ ጊዜ እንኳ የሚመገቡት አጥተው መንገድ ዳር የወደቁ ወገኖችህን ረስተሃል፡፡ አንተ የቱን “ፋሽን” ልብስ ልልበስ የቱ ያምርብኛል እያልክ ትጨነቃለህ ነገር ግን ወገኖችህ የሚቀይሩት ልብስ አጥተው የተባይ መጫወቻ ሆነዋል፡፡ ሰው መሆን ማለት እንዲህ ለሌሎች አለማሰብ ከሆነ ከሆነ ሰው አለመሆን መቶ እጥፍ ይሻላል፡፡ የሚገርመው ነገር አንድ ቀን እኩል እንሆናታለን እኮ፡፡ በላህ፣ ጠጣህ፣ ለበስክ፣ አጌጥህ፣ አማረብህ፣ ወፈርህ፣ ቀላህ … ከዚያስ? ወገኖቻችን ደግሞ ተራቡ፣ ተጠሙ፣ ታረዙ፣ አዳፋ ሆኑ፣ ለእይታ አላምር አሉ፣ ከሱ፣ ቀጨጩ፣ ጠቆሩ፣ ሥጋቸው ከአጥንታቸው ጋር ተጣበቀ… ከዚያስ?
ከዚያማ እነሱም በችግር ይኖራሉ እኛም በድሎት በምቾት በቅንጦት እንኖራለን፡፡ ነገር ግን እኛ በደም ብዛት እንሰቃያለን እነሱ ጤና! እኛ በስኳር ህመም ሺህ ሆስፒታል እንንከራተታለን እነርሱ ጤና ! እኛ በልብ በሽታ በብርድ ህመም እንሰቃያለን እነርሱ ጤና! እኛ በኩላሊት በጨጓራ በሽታ እንቃጠላለን እነርሱ ጤና! ታዲያ መጨነቃችን ምን ለውጥ አመጣልን? ምንም!!!! “ዋናው አድሮ መገኘቱ ነው” የምላት አባባሌ ደስ ትለኛለች፡፡ ስትራብ የጠገቡትን አታስብ፣ ስትታረዝ የለበሱትን አታስብ፣ ስትጠማ የረኩትን የጠጡትን አታስብ፣ ስትታመም ጤነኞችን አታስብ ምክንያቱም ጥቅም የለውም፡፡ ምናልባት ተስፋ የምናደርገውን ነገር ለመጠበቅ ካልሆነ በቀር ምንም አይረባንም፡፡ ነገር ግን ይህንን እያሰብን ተስፋ ይኖረናል ብየ አልገምትም ምኞት ግን ሊኖረን ይችል ይሆናል፡፡ እኔ እኮ እገሌን ብሆን? እንዲህ አደርግ ነበር እያልን በምኞት ባሕር ልንሰጥም እንችል ይሆናል፡፡ ምኞት ደግሞ ተስፋ አይደለምና አይጠቅመንም፡፡ እሱ በላ እኔ ተራብኩ ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ እሱ ጠጣ እኔ ተጠማሁ ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ እሱ ለበሰ እኔ ታረዝኩ ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ እኔ ጠቆርሁ ገረጣሁ እሱ ቀላ ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ እኔ ጎዳና ወድቄ አደርሁ እሱ በሚያምር አልጋ ላይ ተኝቶ አደረ ግን እኩል አድረን ተገኘን፣ እኔ ገንዘብ የለኝም እሱ ደግሞ ሁሉ ሞልቶታል ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ እኔ ከውሻ ጋር ተሻምቼ ተመገብኩ እሱ ደግሞ በጠረንጴዛ ዙሪያ በክብር ተቀምጦ ተመገበ ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ እኔ ባሪያ ሆኘ እየተንገላታሁ እሱ ደግሞ ጌታ ሆኖ እያንገላታ ኖርን ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ እኔ በስደት እጨነቃለሁ እሱ ግን ከቪላ ቤቱ ሰገነት ላይ ይንፈላሰሳል ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ እኔ በልመና የሰው ፊት ይገርፈኛል እሱ ግን ገንዘብን ይጫወትበታል ግን እኩል አድረን ተገኘን፤  እኔ ደመወዜ ከወር እስከ ወር አላደርስ ብሎኝ እጨነቃለሁ እሱ ግን ለ50 ዓመቱ የሚያቅድበት ገንዘብ አለው ግን እኩል አድረን ተገኘን፤ በቃ በሥጋ ደረጃ እኩል ነን፡፡ ዓላማችን ተስፋ የምናደርጋትን ነገ አድሮ በመገኘት ማየት ነው፡፡ ፈጣሪህን ለማመስገን ምክንያት አትሻ፡፡ ዛሬ ሳይኖርህም አመስግነው ነገ ሲኖርህም አመስግነው፡፡ ዛሬ ታመህም አመስግነው ነገ ስትድንም አመስግነው፡፡ ዛሬ ተርበህም አመስግነው ነገ ስትጠግብም አመስግነው፡፡ ዛሬ ስትታረዝም አመስግነው ነገ ስትለብስም አመስግነው፡፡ ዛሬ መንገድ ዳር ወድቀህም አመስግነው ነገም ቤት ስትሠራም አመስግነው፡፡ ዛሬ ታስረህም አመስግነው ነገ ስትፈታም አመስግነው፡፡ ስለሁሉ ነገር ስላደረገልህም ስላላደረገልህም ስለሚያደርግልህም ሁሉ አመስግነው፡፡ ምስጋና ገንዘቡ የሆነ አምላክ አንተን እንዲረዳህ አመስግነው፡፡

በሥጋዊ አረዳድ ትልቁ ነገር አድሮ መገኘቱ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ብዙ ዘመንን በችግር ከማሳለፍ አንድ ቀን ደስ ብሎኝ በልቼ ጠጥቼ ገንዘብ አግኝቼ ብሞት ይሻለኛል ይላሉ፡፡ እኔ ግን አልስማማበትም ምክንያቱም አምላክ ለሁሉ ነገር ጊዜ አለው፡፡ ዛሬ እኔ ድሃ እንድሆን ያደረገበት የራሱ ምክንያት አለው፡፡ እኔ እንድራብ እንድጠማ ያደረገበት የራሱ ምክንያት አለው፡፡ ምናልባት ገንዘቡን ቢሰጠኝና ብጠፋበትስ? ምናልባትስ ምግብ ሰጥቶኝ እስክጠግብ በልቼ አምላኬን ረስቼ ብጠፋበትስ? የራሱ ጊዜ አለው በቃ ያንን ጊዜ በትእግስት መጠበቅ ብቻ ነው፡፡ ጊዜው ሲደርስ በ3 ብር ሎተሪ ሚሊየነር ያደርግሃል ምን ይሳነዋል፡፡ ነገር ግን ቁም ነገራችን ይህ ገንዘብ መሰብሰቡ አይደለም በሕይወት መኖሩ በቃለ እግዚአብሔር መመራቱ ነው፡፡ ሁላችንም አድረን እንገኛለን ነገር ግን ለተለያዩ ዓላማዎች ነው አድረን የተገኘነው፡፡ ሰአታቱን ለመቆም፣ ኪዳኑን ለማድረስ፣ ቅዳሴውን ለማስቀደስ፣ ለመቁረብ ለማስቆረብ፣ ለጽድቅ ሥራ አድሮ የሚገኝ አለ ለኃጢአት ሥራውም አድሮ የሚገኝ አለ፡፡ ስለዚህ ስለገንዘቡ ስለምግቡ ሳይሆን ስለንስሐው ስለጽድቁ ነገር ዋናው ነገር አድሮ መገኘቱ ነው፡፡

Friday, January 22, 2016

ፍቅረ ሰብእ/ ሰውን መውደድ/



© በመልካሙ በየነ
ጥር 13/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
በኦሪት ሕግ “ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ” /ዘሌ19÷18/ በማለት ሰውን መውደድ ጥሩ ክርስቲያዊ ሥነምግባር ከመሆኑም ባለፈ የሌሎች ሕግጋት ሁሉ ጉልላት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ አንተ ራስህን በምትወደው መውደድ እንዲሁ ባልንጀራህን ውደድ፡፡ ከዚህ ውጭ ምንም ምን ብትሠራ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ አትችልም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “ከሁሉ በፊት እርስ በእርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ” /1ኛ ጴጥ4÷8/ በማለት ባልንጀራን መውደድ ከሁሉ ሕግጋት መቅደም እንዳለበት ያስገነዝባል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ይህን መዋደድ ልንቀናበት እንደሚገባ ሲያስረዳ “… ነገር ግን የሚበልጠውን የጸጋ ሥጦታ በብርቱ ፈለጉ” ይላል፡፡ ከሌሎች የጸጋ ሥጦታዎች የሚበልጠው የጸጋ ሥጦታ ፍቅር ነው፡፡ በሰዎችና በመላእክት ልሳን ከመናገር፣ ድሆችን ከመመገብ፣ ሥጋችንን ለእሳት መቃጠል አሳልፈን ከመስጠት ሁሉ የሚበልጠው ጸጋ ፍቅር ነው፡፡ ፍቅር ካለ አነዚህን ሁሉ ለመሥራት እንችላለን ነገር ግን እነዚህ ጸጋዎች ፍቅርን ማምጣት አይችሉም፡፡ ፍቅር በቃል የሚገለጽ ጸጋ አይደለም በተግባር እንጅ፡፡ አንተም ፍቅርን በተግባር እንጅ በሽንገላ ቃላት አትግለጽ፡፡ ነቢዩ ዳዊት እንዲህ ይላል “በአፋቸው ይባርካሉ በልባቸው ይረግማሉ” /መዝ61÷4/ እነዚህን ሰዎች በግብር አትምሰላቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች በፍቅር ቃላት በአፋቸው ይባርካሉ ነገር ግን በልባቸው የሚረግሙ ናቸው፡፡ ፍቅራቸው ግብዝነት የተሞላበት የሽንገላ ነው፡፡ እነዚህ በአፋቸው የሚባርኩት ሰዎች ፍቅራቸው ጊዜያዊ፣ ወረተኛ፣ የሚሻር፣ የሚለወጥ ነው፡፡ ገንዘብ ስታገኝ ያንዣብብልሃል ስታጣ ደግሞ ነፋስ እንደተመለከተ ደመና ተገፎ ይሄዳል፡፡ አንተ ግን ሰውን ስትወድድ ያለምንም ነገር ውደደው፡፡ ሰውን ለመውደድ ምክንያት የምታደርገው  ቁሳዊ ወይም ሌላ ነገር አትሻ፡፡ ሰውን ሰው በመሆኑ የእግዚአብሔር ክቡር ፍጥረት መሆኑን ብቻ አስበህ ከወደድከው ያን ጊዜ ከእግዚአብሔር ጋር ለመሆንህ ትልቅ ምስክር አገኘህ ማለት ነው፡፡ ፍጹም ፍቅር ጠላትን ይወድዳል፡፡ ምክንያቱም  ወንጌል “በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላታችሁን ውደዱ”/ማቴ5÷44-45/ ይለናልና፡፡ የሰው ልጅ የመጨረሻ ተስፋው ርስት መንግሥተ ሰማያትን ወርሶ ከመላእክት ጋር “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ” እያለ ለዘላለም ማመስገን ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ለሰማይ አባታችን ልጆች መሆን ያስፈልገናል፡፡ ልጆች ለመሆን ደግሞ ጠላትን መውደድ ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ ይህ ፍጹም ፍቅር ቀዳሜ ሰማእት ቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ አንዲህ በተግባር ተተረጎመ፡፡ “… እስጢፋኖስም ፡- ጌታ ኢየሱስ ሆይ ነፍሴን ተቀበል ብሎ ሲጠራ ይወግሩት ነበር፡፡ ተንበርክኮም ጌታ ሆይ ይህን ኃጢአት አትቁጠርባቸው ብሎ በታላቅ ድምጽ ጮኸ” /የሐዋ7÷60/ የፍቅር ባለቤት የእግዚአብሔር ቅዱስ ሰማእት የሆነው ሊቀ ዲያቆን  እስጢፋኖስ ድንጋይ አንሥተው ለወገሩትና ለሞት አሳልፈው ለሰጡት ሰዎች ኃጢአታቸውን እንዳይቆጥርባቸው አምላኩን ለመነላቸው፡፡ እውነተኛ ፍጹም ፍቅር እግዚአብሔርንም በዙፋኑ ቁጭ እንዳለ የሚያሳይ ይህ የቅዱስ እስጢፋኖስ ፍቅር ነው፡፡ እናትና አባቶቻችንን ስለወለዱን ብሎም ስላሳደጉን፣ ጓደኞቻችን ውለታ ስለዋሉልን ወይም የልባችንን መነጋገር ስለምንችል እንወዳቸዋለን ነገር ግን ሊወግሩን ድንጋይ በእጃቸው የያዙትን ሰዎች እንወዳቸዋለንን? የዚህ መልስ አዎ መሆን ከቻለ ፍጹም ፍቅር ማለት እርሱ ነው፡፡ ከዜሮ ወይም ከምንም ተነሥተን መውደድ ከቻልን ለመውደዳችንም ምንም ምን ምክንያት የሌለን ከሆነ እውነተኛ ፍቅር ያንጊዜ አለን እንላለን፡፡ ይህ ፍቅር እግዚአብሔርን የሚያሳይ ነው፡፡ /የሐዋ7÷56/ ሰውን መውደድ ስትጀምር አንተን ሌሎች እንዲወዱህ እግዚአብሔር ጸጋውን ያድልሃል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር የሚገኘው በፍቅር መካከል ነውና፡፡ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ሲሆን ሰዎች ከትቢያ አንሥተው ከከበረ ዙፋን ላይ ያስቀምጡሃል፡፡  በግብጽ በግዞት ውስጥ የነበረው ዮሴፍ በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስ በማግኘቱ በግብጽ ምድር ሁሉ ላይ ፈርዖን ሹመት ሰጠው፡፡ ፈርዖን ቀለበቱን ከእጁ አውጥቶ በዮሴፍ እጅ ላይ አደረገው ነጭ የተልባ እግር ልብስም አለበሰው፣ በአንገቱም የወርቅ ዝርግፍ አደረገለት፤ በቤቱ ላይም ሁሉ አሰለጠነው፡፡ ሕዝቡም ሁሉ እንዲታዘዝለት አዋጅ አስነገረ፡፡ /ዘፍ 41÷37-45/ እግዚአብሔር  አብሮህ ሲሆን የጨካኞችን ልብ ያራራልህና የመወደድ ካባ አልብሶ ለሹመት ይመርጥሃል፡፡ ፍቅር በቃላት ከምንገልጸው በላይ ትልቅ ኃይል ነው፡፡ ፍቅር ዛሬ በተቃራኒ ጾታዎች መካከል የሚደረገው ድራማ መሰል ጨዋታ አይደለም፡፡ አንዱ አንዲቷን በአለባበሷ፣ በሃብቷ፣ በውበቷ ወይም በሌላ ነገር ደልሎ ሥጋዊ ፈቃዱን የሚፈጽምበትን ድለላ አይደለም፡፡ ይህ አይነቱ ፍቅር ሶምሶን የከፈለውን ከባድ ዋጋ የሚያስከፍል ነው፡፡ ኃያሉ ሶምሶን በደሊላ ፍቅር በመውደቁ ኃይሉ በምን ሊደክም እንደሚችል ትልቁን ምሥጢር አሳልፎ ሰጣት፡፡ በዚህም የተነሣ ፍልስጥኤማውያን ጸጉሩን ላጭተው፣ ኃይሉን አድክመው አይኑን አወጡት፣ በሰንሰለትም አሰሩት፣ በግዞትም ውስጥ እህል ያስፈጩት ነበር፡፡ /መሳ16÷1-31/ አንተ ግን ከእንደዚህ አይነቱ ፍቅር ልትርቅ ያስፈልጋል፡፡ ይህ አይነቱ ፍቅር የልብ ሳይሆን የአፍ መውደድ ነው፡፡ ፍቅር ራስህን አሳልፈህ የምትሰጥበት እንጂ ሌሎችን የምታጠምድበት ወጥመድ አይደለም፡፡

Friday, January 15, 2016

ሐሰተኛ ሰላም



© በመልካሙ በየነ
ጥር 06/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ይህ ሰላም በውሸት የሚገኝ ምናባዊ ሰላም ነው፡፡ሰላም አለመኖሩ እየታወቀ “ሰላም አለ” እየተባለ የሚነገርለት ነው፡፡ “ሰላም ሳይኖር ሰላም እያሉ ሕዝቤን አታልለዋልና” /ሕዝ13÷10/ ሐሰተኛነት ባሪያ ያደረጋቸው ሰዎች ሰላም በሌለበት መካከል “ሰላም አለ” እያሉ ሕዝቡን ያታልላሉ፡፡ ይህ እነርሱ አለ የሚሉት ሰላም የውሸትነው፡፡ እነዚህ ሰዎችን ነቢዩ ኤርምያስ “ሰላም ሳይሆን ሰላም ሰላም ይላሉ” /ኤር 6÷14/ በማለት ይገልጻል፡፡ እንዲህ አይነቱ ሰላም ምናባዊ ነው፤ የሚታይ፣ የሚዳሰስ፣ የሚጨበጥ  አይደለም፡፡ መዳብን ወርቅ በስሱ ቀብተው ያብረቀርቁታል በወርቅ ዋጋም ይሸጡታል፤ ገዥዎች ለጊዜው ወርቅ የገዙ ይመስላቸዋል፡፡ የተወሰነ ጊዜ ከተጠቀሙበት በኋላ ማንነቱን ይገልጥላቸዋል፡፡ የወርቁና የመዳቡ ጓደኝነት ጊዜያዊ ነው፡፡ የዚያን ጊዜ ወርቅ ሳይሆን መዳብ እንደገዙ ይረዳሉ፤ እጅግም ያዝናሉ ይተክማል፡፡ ይህ ውሸተኛ ሰላም እንዲህ ያለ ነው፡፡ ለጊዜው ሰላም ይመስለናል እንጨብጠዋለን ከጨበጥነው በኋላ ግን መርዝ ያለበት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ሰው ኃጢአትን የሚሠራው ሰላም አገኝበት መስሎት ነው፡፡ በኋላ ግን ኅሊናው መሸከም የማይችለውን ዕዳ ያሸክመውና ሰላሙን ያጣል፡፡ እንቁላል ላይ ላዩን ሲያዩት ጠንካራ ወድቆ የማይሰበር ይመስላል፡፡ ነገር ግን ያ ጠንካራ የመሰለው ቅርፊት በውስጡ ፈሳሽ የያዘ ነው፡፡ ውሸተኛ ሰላም እንዲህ አይነት ነው፡፡ ንጉሥ አክዓብና ኤልዛቤል የናቡቴን ርስት ለመውረስ ናቡቴን መግደል በቂ ሰላም የሚፈጥርላቸው መስሏቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ናቡቴን በመግደላቸው ሰላማቸውን አጡ፡፡/1ኛነገ20÷1-17/ ይህ አይነቱ ሰላም በማር የተለወሰ መርዝ ነው፡፡ ስትበላው ማር ስለሆነ ሊጣፍጥህ ቢችልም መርዝ ስላለበት ደግሞ በስተጀርባው ሞት ያመጣል፡፡ ከሰዎች እና ከዓለም የምታገኘው ሰላም እንዲህ ያለ ሰላም ነው፡፡ ቃየን መልከ መልካሟን ሉድ ለማግባትና በሰላም ለመኖር ነበር ወንድሙ አቤልን የገደለው፡፡ ነገር ግን በፊት ያሰበውን ሰላም ማግኘት አልቻለም፡፡ በአንጻሩ በምድር ላይ ኮብላይና ተቅበዝባዥ ሆነ፡፡ ሰው የሰውን ልጅ ሲገድል ማንም ሳያውቅበት በሰላም ለመኖር አስቦ ነው፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሔር የሚሠወር ነገር የለምና ያንን ኃጢአት መፈጸሙ ታውቆ ወደ ወኅኒ ቤት ሲወርድ ሰላሙ ይደፈርሳል፡፡ ያፈሰሰው ደም ኅሊናውን ያስጨንቀዋል፤ በእግዚአብሔር ፊትም ይከስሰዋል፡፡ በፊት ያሰበውን ሰላም ሳይሆን ጭንቀትን ይለብሳል፡፡ በዘመኑ የነበረው ንጉስ ሔሮድስ የወንድሙ ፊሊጶስን ሚስት ሄሮድያዳን ለአንተ አልተፈቀደችም ይለው የነበረውን መጥምቁ ዮሐንስን ወደ እስር ቤት አወረደው፡፡ ሄሮድያዳና ሔሮድስ ተጋብተዋል፤ በዚህም መካከል የሚመጣባቸውን ነገር አይቀበሉም፡፡ በንጉሡ የልደት በዓል የሄሮድያዳ ልጅ ዘፈነችለት ሽልማትም እንደሚሰጣት ቃል ገባላት፡፡ ለእናቷ አማከረቻት እናቷም ሰላም የነሣኝ ዮሐንስ የሚሉት ነቢይ ነውና አንገቱን ቆርጦ ይስጥሽ አለቻት፡፡ ለጊዜው ቢያዝንም ቃል ገብቶላታልና በወኅኒ ቤት ውስጥ የዮሐንስን አንገት አስቆረጠው፡፡ /ማቴ13÷1-12/ የዮሐንስን አንገት መቁረጥ ሰላም የሚፈጥርላቸው መስሏቸው ነበር፡፡ ነገር ግን የዮሐንስ አንገት ክንፍ አውጥታ እየበረረች ለ 15 ዓመታት ያህል ያንኑ የቀደመውን ትምህርቷን ማስተማር ቀጠለች፡፡ ሄሮድያዳና ሔሮድስ የጠበቁትን ሰላም ማግኘት አልቻሉም ውሸተኛ ሰላም ነበርና፡፡ሰላም ስለፈለግናት ብቻ የምትመጣልን አይደለችም፡፡ ሰላምበከበረ ዕንቁ በብዙ ዋጋ በሚከፈል ገንዘብ ልትገዛት አትችልም፡፡ምናልባትለዛሬ ብቻ ደስታ የምትፈጥርልህን ሰላም ትገዛ  ይሆናል ለነገ የሚተርፍህ ሰላም ግን አታገኝም፡፡ ሰላምን ያይደለ ሰላም የመመስል ነገር ታጠራቅም ይሆናል እንጅ በሽብርና በጭንቀት መካከል የመ፣ያስፈራህን የዕረፍት ሰላም አታገኝም፡፡ ዲያብሎስ በእጁ ሲያስገባህ የሰላምን ትርጉም ያሳጣሃል፡፡ በወንጌል የተጻፈልን የጠፋው ልጅ ታሪክ ይህንን ያሳያል፡፡ ታናሹ ልጅ በምቾት፣ በሰላምና በደስታ ይኖርበት ከነበረው ከአባቱ ቤት መውጣት ፈለገ፡፡ አባቱም ለልጁ የሚደርሰውን ገንዘብ ሰጠው፡፡ በአባቱ ቤት የነበረው ሰላም ለጊዜው ተሠውሮበታልና  ሰላም በዓለም የሚገኝ ስለመሰለው ገንዘቡን ተካፍሎ ወደ ሩቅ አገር ኮበለለ፡፡ ዓለም በብልጭልጭ ጊዜያዊ ሰላሟ አቅፋ ተቀበለችው፡፡ ከሰሜን ወደ ደቡብ፣ ከደቡብ ወደ ሰሜን፤ ከምሥራቅ ወደ ምዕራብ፣ ከምዕራብ ወደ ምሥራቅ ዞረ ተንከራተተ በእጁ የነበረውን ገንዘብ አባከነ በእጁ ምንም ምን አልተረፈውም ነበር፡፡ በዚህ ሁሉ ውጣ ውረድ መካከል ሰላምን ማግኘት አልተቻለውም፡፡ እንዲያውም ገንዘቡ ባለቀበት ጊዜ አገሪቱ ውስጥ ጽኑ ረሃብ በመነሣቱ እጅግ አብዝቶ ይጨነቅ ነበር፡፡ በአባቱ ቤት ሳለ ከምንም ያልቆጠረው ሰላም ከጥሩ የአባትነት ፍቅርና እንክብካቤ ጋር ትዝ ሲለው ይባስ ያለቅስ ነበር፡፡ ረሃብ ሲጸናበት በዚያች አገር ካለ ከአንድ ሰው ጋር ተዳበለ፡፡ የሚበላው በማጣቱ እጅግ ተራበ እሪያዎች ከሚበሉት አሰር ሊጠግብ ተመኘ ነገር ግን ያንን የእሪያዎች ትራፊ እንኳ የሚሰጠው አልነበረም፡፡ ረሃቡ እጅግ ከመጠን በላይ ሲያስጨንቀው የአባቱ ቤት ታወሰው፡፡ /ሉቃ 15÷11-24/ ገንዘብ ስላለን ብቻ ሰላምን መግዛት እንደማንችል ታሪኩ ያስረዳናል፡፡ ዓለምም ሰላም የምትሰጠን ገንዘባችን እስከሚያልቅ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ገንዘባችንን ከጨረሰች በኋላ ግን እንደማይጠቅም ነገር ከውጭ ጥላ መሳቂያ ታደርገናለች፡፡  ዲያብሎስ ዓይንህን ሲያጨልምብህ ሰላ ምን እንደሆነ አትረዳውም፡፡ ለባልንጀራህ “ሰላም ነው?” በሚል ጥያቄ ሰላምታ ታቀርባለህ እርሱም “ሰላም ነው” ብሎ ይመልስልሃል ነገር ግን አንተ የጠየቅኸው እርሱም የመለሰልህ ሰላም እውነተኛ ሰላም አይደለም፡፡ ለዚህም ነው ነቢዩ ዳዊት “ክፋትም በልባቸው እያለ ከባልንጀራቸው ጋር ሰላም ከሚናገሩት ጋር አትጣለኝ” /መዝ 27÷3/ በማለት የገለጸው፡፡ በልብህ ውስጥ ሰላም ሳይኖር አንተ ግን በአፍህ ብቻ “ሰላም ነው” እንድትል ትገደዳለህ፡፡ ፈጣሪህን እንዳታመሰግን ሰላምህን ያሳጣህ ጠላት “ሰላም ነው” በሚል ጥያቄና መልስ ሰላምታ እንድታቀርብ ያስገድድሃል፡፡ ሰላም ስትኖረው የምታገኘው ስትቀምሰው የምታውቀው እንጅ ስለተናገርከው “ሰላም ነው” ስላልህ ብቻ የምትጎናጸፈውና የምትደርበው ካባ አይደለም፡፡ ቁጥሩ ከ12ቱ ነቢያት መካከል አንዱ የነበረው ይሁዳ “ሰላም ለአንተ ይሁን” ብሎ አምላን ስሞ አሳልፎ ሲሰጥ በውስጡ ሰላም የለም ነበር፡፡ /ማቴ 26÷49/ ኢየሱስ ክርስቶስ ከተያዘ በኋላ በመጀመሪያ እንዳሰበው ሊሆንለት ባለመቻሉ በውስጡ ሳይኖር በአፉ ብቻ “ሰላም” ይል የነበረው የውሸት ሰላም አእምሮውን ነሣው፡፡ ንጹሕ ደም አሳልፎ በመስጠቱም መበደሉን ተረድቶ ገንዘቡን በቤተመቅደስ ጥሎ ታንቆ ሞተ፡፡ /ማቴ 27÷3-5/ ነገሮች ሁሉ ይሁዳ መጀመሪያ እንዳሰባቸው ሊሆኑለት አልቻሉምና የመጨረሻ ዕጣ ፈንታው የዘላለም ሞት ሆነበት፡፡ ስለዚህ አምላክህን ያችን ገንዘብ የማይገዛትን የከበረች እውነተኛ ሰላም ይሰጥህ ዘንድ ተማጸነው፡፡

Tuesday, January 5, 2016

አሻንጉሊት አፍቃሪነታችን ለምን?



© በመልካሙ በየነ
ታህሳስ 26/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ዓላትን ተንተርሰው የሚመጡ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ድሮ ድሮ አባቶቻችን ለዘመን መለወጫ “እንቁ ጣጣሽ” የሚል ስም ያወጡት በዓሉ ብዙ ጣጣ ስለነበረበት ነው ይባላል፡፡ ስለ በዓሉ ክብር ሲባል በጉ፣ ዶሮው፣ ዳቦው፣ጠላው፣ ጠጁ ሁሉም መዘጋጀት ያስፈልገዋል፡፡ ያንን ሁሉ ለማሟላት ደግሞ ገንዘብ ይጠይቃል ስለዚህ ያን ገንዘብ ማግኘት ከባድ ስለሆነ “ጣጣሽ” አሏት፡፡ እኔን የሚቆጨኝ አባቶቻችን ዛሬ ተነሥተው እኛን አለማየታቸው ብቻ ነው፡፡ እኛ በጉ፣ ዶሮው፣ ጠላው፣ ዳቦው፣ ጠጁ ምናችን ነው? ለእኛ እኮ ለዘመናዊዎቹ በዓል ክብር የሚኖረው በዚህ አይደለም በአሻንጉሊቶቹ ነው፡፡ አሻንጉሊቶችን ደርድረን በቀላሉ በዓሉን እንሸውደዋለን እናታልለዋለን የምን ወጭ የምን ጣጣ ነው፡፡ እንደውም አባቶቻችን ለደቂቃ ተነሥተው ቢመለከቱን ባህላችን ባህላቸውን መስሎ ስለማያገኙት “እንቁ ጣጣሽ” ን “እንቁ አሻንጉሊት”፣ “ገና”ንም “አሻንጉሊትና” ፋሲካን ወይም ትንሣኤንም “ኢስተር አሻንጉሊት” ብለው ስም ያወጡልን ነበር፡፡ ለቅጽበት ቢነሡ “በእውነት ልጆቻችን ኢትዮጵያ ውስጥ ነበርን የቀበሩን?” ማለታቸውም የማይቀር ነው፡፡ ግን ለምን ለአሻንጉሊት ክብርን መስጠት አስፈለገን?
ዛሬ እኮ ሱቆች የተሞሉት ቤቶች ያሸበረቁት በአሻንጉሊቶች ብዛት ነው፡፡ እኔ “ለምን በፍቅረ አሻንጉሊት ተነደፍን” የሚለውን ጥያቄ የምመልስበት የራሴ እይታና አስተሳሰብ አለኝ፡፡ እኔ የምገምተው ለምሳሌ ሕጻናትን የሚመስሉ አሻንጉሊቶችን ታቅፈው የሚያድሩ ሴቶች አሉ ወንዶችም እንዲሁ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ባልና ሚስትም በመካከላቸው እንደ ሕጻን ሕጻናትን ሊተኩ ከሚችሉ አሻንጉሊቶች መርጠው  ሊያስተኙ ይችላሉ፡፡ በዚህ ዘመን ልጅ ለመታቀፍ ልጅ ለማሳደግ ከባድ የሆነባቸው ሰዎች አሻንጉሊት ታቅፈው ኑሮን ይሸውዱታል ያታልሉታል፡፡ ሕጻንን ለማሳደግ ለቁም ነገር ለማብቃት 9 ወር ማርገዝን ከዚያም አምጦ መውለድን ከዚያም ማልበስን መንከባከብን ማብላት ማጠጣትን ይጠይቃል፡፡ አሻንጉሊት ግን ራበኝ አብሉኝ ጠማኝ አጠጡኝ በረደኝ አልብሱኝ ብሎ አያለቅስብንም፡፡ ለዚህ ይመስለኛል ፍቅረ አሻንጉሊት ያንገበገበን፡፡ እናት አባቶቻችን ስንት ደክመው ስንቱን ወጥተው ስንቱን ወርደው ሳይማሩ አስተምረው ሳይለብሱ አልብሰው ለቁም ነገር ያደረሱን ወልዳችሁ ሳሙ ዘርታችሁ ቃሙ፣ ዓይናችሁን በዓይናችሁ ለማየት ያብቃችሁ  ብለው የመረቁን በስህተት ነበር ለካ፡፡ ምክንያቱም እኛ እየሳምን ያለነው የወለድነውን ልጅ ሳይሆን የገዛነውን አሻንጉሊት ነዋ፡፡ ምክንያቱም እኛ ዓይናችንን በዓይናችን አይተናል የምንለው አሻንጉሊት ታቅፈን ቁም መስታወት ፊት ለፊት ቆመን አምሮብኛል አላማረብኝም እያልን የምንለውን ነዋ፡፡ ውጮቹን ምዕራባውያኑን እንመስላለን ብለን ራሳችንን መሆን አቃተን፡፡ እነርሱ የራሳቸው አስተሳሰብ፣ የራሳቸው አመለካከት፣ የራሳቸው ባህል፣ የራሳቸው የሆነ ነገር አላቸው ከአሻንጉሊቶች ጋርም የተዛመደ ነገር ሊኖራቸው ይችላል እኛ ደግሞ የራሳችን የሆነ ከእነርሱ ጋር የማያዛምደን ዓለምን የሚያስደንቅና የሚያስደምም ባህል አለን፡፡ የእነርሱን አለባበስ የእነርሱን ባህል የእነርሱን አመጋገብ የእነርሱን አነጋገር ወዘተ ሙሉ በሙሉ እኛን በሚመስልና እኛን በሚመጥን መልኩ አለመውሰዳችን ጥፋታችንን ያጎላዋል፡፡
ሌላው የሚገርመኝ ነገር “የገና ዛፍ” የሚባለው አሻንጉሊት ዛፍ ነው፡፡ በመጀመሪያ ይህንን ስም ያወጣለት ሰው ማነው? ምክንያቱም ገና የሚባለውን የምናውቀው እኛ ኢትዮጵያውያን ብቻ ነን፡፡ በእኛ የባህል ታሪክ ውስጥ  በዓላትን የምናከብረው በጉን፣ ዶሮውን፣ እንቁላሉን፣ ጠላውን፣ ጠጁን ወዘተ በማድረግ ራሳችን በሠራነው ራሳችን በጋገርነው ራሳችን ባረድነው ራሳችን በጠመቅነው ራሳችን በደፋነው ነገር ብቻ ነው፡፡ በዓላትን ያለው ለሌለው አካፍሎ በአንድ መሶብ ልጅ አዋቂው ከብቦ እየተመገበ አፈር ስሆን ብሉ አፈር ስሆን ጠጡ በሚሉት እናቶቻችን አጅ ጉርሻም እየተቀበልን ነው ያደግነው፡፡ ታዲያ ዛሬ “የገና ዛፍ” የሚባል አሻንጉሊት አቁመን “መልካም ገና” መባባላችን ትርጉሙ ምንድን ነው? በእውነት ባህል ያለው ሰው ታሪክ ያለው ሰው እምነት ያለው ሰው አፍሪካ ምድር ቅድስቲቱ አገር ኢትዮጵያ ውስጥ የተወለደ ሰው መሶብን በአሻንጉሊት መለወጡ ምን ያህል ያሳምማል? በእርግጥ አብሉኝ አጠጡኝ ማዳበሪያ ጨምሩልኝ ስለማይለን ሊሆን ይችላል፡፡ ፈረንጆቹ “የገና ዛፍን” የሚጠቀሙበት የራሳቸው የሆነ ምክንያት አላቸው እኛ ግን ምንም ምክንያት የለንም፡፡ እነርሱ በደጉ ዘመን የነበረው አምላካቸው በክፉ ዘመን ድርቅ ሲሆን ሁሉም ዛፎች ሲደርቁ ጽድ ግን በበጋም ስለማይደርቅ አምላካቸው በዚያ ተሸሽጎ ደጉ ዘመን እስኪመጣ ጠብቆ ደጉ ዘመን ሲመጣ ከዚያ ከተሸሸገበት ዛፍ ይወጣል ብለው ያምናሉ፡፡ ለዚያም ባለውለታቸው ምስጋና ያቀርባሉ፡፡ ለዚህም ነው “የገና ዛፎች” ከጽድ ዛፍ ጋር ተመሳስለው የተሠሩት፡፡ አምላካቸውን ደብቆ ላቆየላቸው ባለውለታቸው ክብር ሰጥተው በመብራቶች አሸብርቀው በዓላትን ያከብሩበታል እንዲያውም ያመልኩበታልም፡፡ እኛ ደግሞ በክፉ ዘመን የሚሸሸግ በደጉ ዘመን እንደ መስቀል ወፍ ብቅ የሚል አምላክ የለንም፡፡ ደግ ዘመን ክፉ ዘመን ሁሉም የሚሆነው በእግዚአብሔር ነው ብለን የምናምን ክርስቲያኖች ነን፡፡ ታዲያ እንዲህ ከሆነ በኢትዮጵያውያን ዘንድ “የገና ዛፍ” ትርጉሙ ምን ሊሆን ይችላል? ምንም ትርጉም የለውም ምናልባት አምልኮ ባዕድ ካልተጠናወተን በስተቀር፡፡ ዛፍ አምላኪነት የተጠናወታቸው ሰዎች ግን በዓላትን ምክንያት ማድረግ አይጠበቅባቸውም፡፡ ሁልጊዜም ሊወድቁለት ሊሰግዱለት ሊገዙለት ያስፈልጋል፡፡ ስለ ገና ዛፍ ምንነትና የት መጣነት ይህንን ሊንክ ተጭነው ያንብቡ፡፡
www.dw.com/am/የገና-ዛፍ-እና-የገና-አባት-ታሪክ/a-16481554  ወይም ይህንን
lemabesufekad.blogspot.com/2014/12/blog-post_24.html?m=1

ይቅርታ አድርጉልኝ እንጅ አሻንጉሊትን የሚጠቀመው ማኅበረሰብ በብዛት ሰነፍ ነው፡፡ አንድን ሕጻን እና አንድን ዛፍ ከማሳደግ ይልቅ ምንም የማያስቸግሩትን አሻንጉሊቶች መግዛት መታቀፍና ማቆም ይቀናዋል፡፡ ግን ባህላችን አለመሆኑን መረዳት ያስፈልገናል፡፡ ምን ችግር አለው እኔ የምፈልገው ጌጥነቱን እንጅ አላመልከው ልንል አያስፈልግም፡፡ “ፍቅረ አሻንጉሊት” ለመጨመሩ ብዙ ማሳያዎችን እየተመለከትን ነው፡፡ ሴቶችም ሆኑ ወንዶች የሚገዟቸውን ልብሶች ቅድሚያ የሚለብሱት አሻንጉሊቶች ናቸው፡፡ ልብስ ከሚሸጥባቸው ሱቆች ጎራ በሉና ይህንን አረጋግጡ፡፡ አዳዲስ ዘመናዊ “ፋሽን” የሚባሉ ነገሮችን ቅድሚያ የምናያቸው አሻንጉሊቶች ለብሰዋቸው ነው፡፡ ግን ስለ እውነት እንነጋገር እስኪ አንዱ የለበሰውን ልብስ እንድንለብስ ቢሰጠን እንለብሰዋለን? የእህቶቻችንን የወንድሞቻችንን ልብስ ለመልበስ እንኳ አንፈልግም ምክንያቱም ያ “የማንም ልባሽ” ነዋ፡፡ ታዲያ ላንተ ታዲያ ላንች ከእህትህ ከወንድምህ ከእህትሽ ከወንድምሽ አሻንጉሊት በልጦብህ/ሽ ነው የአሻንጉሊት ልባሽ የምትለብሰው/ የምትለብሽው፡፡ አቤት ጉድ!!!! ፍቅራችንን መተሳሰባችንንም ለካ አሻንጉሊት ተሻምቶብናል፡፡