Tuesday, June 30, 2015

ሲስቅ የሚኖረው ስቆ የተነሣ ፎቶ ብቻ ነው

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

አንድ በጣም የምወደው የልብ የምለው ጓደኛየ በሌሊት ስልክ ደወለልኝ። ከእንቅልፍ እንጅ ከስራ ስላላደናቀፈኝ ብዙም አልተበሳጨውበትም ነበር። በእንቅልፍ የተወረሩ ዓይኖቼን እያሻሸሁ ስልኩን አንስቼ "ምን ነካህ?" አልኩት። "ሰላምታ አይቀድምም?" የሚል መልስ ብስጭት በተቀላቀለበት አነጋገር መለሰልኝ። "ኧረ በሚገባ ይቀድማል ያለ ወትሮህ በዚህ ሰዓት ስትደውል ጊዜ ምን ሆነህ ነው ብየ እኮ ነው" አልኩት። " ነገ እኔ ጋር መምጣት አለብህ ከዛ ውጭ የእኔ እና የአንተ ጓደኝነት ያከትምለታል"አለኝ። በጣም አስጨነቀኝ " ምን ነካህ? ምን ገጠመህ? የእኔስ አንተ ጋር መምጣት ምን ፋይዳ ሊኖረው ይችላል?" አልኩት። " ትመጣለህ ወይስ አትመጣም ይህንን ብቻ መልስልኝ" አለኝ። " እንዴ ምን ነካህ ተረጋጋ እንጅ እኔንም በሌሊት አታስጩኸኝ። በኪራይ ቤት እንደምኖር አስብ እዚህ ጎረቤት የተኛ ሰው አለ ነገ አቤቱታ እንዳያቀርብብኝ ረጋ ብለህ አናግረኝ። ቆይ የገጠመህ ነገር ምንድን ነው? አልኩት ድምጼ የተኛ ጎረቤቴን እንዳይረብሽ እየቀነስኩ። " በኔ የደረሰ አይድረስብህ ጉድ ሆንኩልህ" አለኝ። " እንዴ አሞሃል ልበል ምን ሆነህ ነው እኔን ጨምረህ የምታስጨንቀኝ። ሰዓትህን አይተሃል? ከሌሊቱ 8:00 ሰዓት ነው እኮ። በዚህ ሌሊት ስልክ ሳናግር የመጀመሪያየ ነው። ማንም ቢሆን በዚህ ሰዓት ደውሎ አናግሬ አላውቅም። ዛሬ አንተ ሆነህብኝ እኮ ነው ዶሮ ሰልጥኖ መጮህ ባቆመበት ሰዓት የምጮኸው። ከነገርከኝ ንገረኝ ከዛ ውጭ ስልኩን ልዘጋው ነው" አልኩት። " ጉድ ሆንኩልህ ነው የምልህ። ፍቅረኛዬ ..." ንግግሩን አቋርጦ አለቀሰ። ይበልጥ አስጨነቀኝ "ምን ሆነች ታዲያ" አልኩት። " ከዳችኝ" ብሎ ይበልጥ አለቀሰ። " ታዲያ በዚህ ዘመን  መክዳት መከዳት ብርቅ ነው እንዴ? መከዳት ባንተ አልተጀመረም እኮ ተው እንጅ ራስህን አረጋጋ" አልኩት። እርሱ ግን ፍቅራቸው ጣራ በነካበት ጊዜ የተነሡትን ፎቶ አቅፎ ያነባል። "አይዞህ በቃ መኪና ካገኘሁ ጠዋት እመጣለሁ" አልኩትና ስልኩን ዘጋሁት። እንዳይነጋ የለም ሌሊቱ ነጋና ሻንጣዬን ይዤ ወደ መናኸሪያ ከነፍኩ። የመኪና ረዳቶች የተሰማሩባቸውን ቦታዎች እየጮሁ ይጠራሉ። እነርሱ የሚጮሁት የሚጠቅመው ማንበብ ለማይችል እንጅ ማንበብ ለሚችል ሰው ጫጫታው ጆሮ ያስይዛል። እኔም ጆሮዬን አፍኜ የምሄድበት ቦታ የተጻፈበትን መኪና ሳስተናብር አንድ ትልቅ መልእክት የተጻፈበት መኪና ተመለከትኩ "ሲስቅ የሚኖረው ስቆ የተነሣ ፎቶ ብቻ ነው" ይላል። " እውነቱን ነው ሰው ዛሬን በደስታ ቢስቅ ነገን በመከራ ያለቅሰዋል። ሰው ዛሬን በጥጋብ ቢስቅ ነገን በረሃብ ያለቅሳል። በአጠቃላይ ሰው ሁል ጊዜ በደስታ ሲስቅ አይኖርም አንድ ቀን ሃዘን አለበት። ዛሬስ ስራዬን ፈትቼ የምሄድበት ጉዳይ እርሱው አይደል እንዴ። በእነዚያ በፍቅራቸው በሳቅ በጨዋታቸው አገር ይቀናባቸው  በነበሩት ፍቅረኛሞች መካከል መከዳዳት! በዚህ ምክንያት ማልቀስ!" በጣም ገረመኝ። "መኪና ውስጥ ሳልገባ ትኬት ሳልቆርጥ እንኳን አየሁት" አልኩ በልቤ። ስልክ ደወልኩለት "በቃ ቀረሁ አልመጣም" አልኩት። "ለምን? የእኛ ጓደኝነት እስከዚህ ነበር እንዴ?" አለኝ። "ተወው እባክህ ሁል ጊዜ ደስታ ሁል ጊዜ ሳቅ ሁል ጊዜ ጥጋብ ጥሩ አይደለም። ኑሮ ጣዕም የሚኖረው በፍቅር መካከል መኮራረፍ፣ በደስታ መካከል ማዘን፣ በጥጋብ መካከል ረሃብ ሲኖር ነው። አንተ የምትሻው ሁል ጊዜ መሳቅን ብቻ ነው መሰል ሲስቅ የሚኖረው ስቆ የተነሣ ፎቶ ብቻ ነው ሲባል አልሰማህም እንዴ።  እንደዚህ የሚል አንድ መኪና ላይ የተጻፈ ጥቅስ አይቼ ነው ወደ አንተ ልመጣ የነበረውን ጉዞ የሰረዝኩት። ለማንኛውም ሁልጊዜ ደስተኛ ለመሆን የምትፈልግ ከሆነ ደስተኛ ሆነህ ፎቶ ተነሥ እኔ ቀርቻለሁ ደህና ሁን" ብየ ስልኩን ለመጨረሻ ጊዜ ዘጋሁት።

Monday, June 29, 2015

መሞት ብርቅ አይደለም (ክፍል አራት)

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ስለ ሞት አይነቶች በተከታታይ ክፍሎች ተመልክተናል በዚህ ክፍል ደግሞ መሞት ብርቅ እንዳልሆነ እናያለን።

ብዙዎቻችን ኑሮ አልሰምርልን ሲል፣ ገንዘብ ሲጠፋብን፣ የምንወደው ሰው ሲከዳን፣ የምንወደው ሰው ሲሞትብን፣ የፈተና ውጤት አልመጣ ሲለን፣ ከስራ ስንባረር፣ ከሰው ስንጣላ ወዘተ ተስፋ እንቆርጣለን። ተስፋ መቁረጥም ብቻ አይደለም ለመሞት እንመኛለን። ሰይጣን ይህንን ክፍተት ተጠቅሞ ራሳችንን በምን ልናጠፋ እንደምንችል የሞት መንገዶችን ያማርጠናል። ራስህን በመርዝ አጥፋ የሚል መንፈስ ሹክ ይልሃል። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ለምን ታንቀህ አትሞትም ይልሃል። ትምሽ ቆይቶ ደግሞ ለምን ኤሌክትሪክ ገመድ ጨብጠህ አንዴ አትገላገልም ይልሃል። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ሌላ መንፈስ ለምን ራስህን ወደ ገደል ወርውረህ አትገላገልም ይልሃል። ሌላው መንፈስ ደግሞ ይመጣል ለምን ራስህን ውኃ ውስጥ አጥልቀህ አትገድልም ይልሃል። ብቻ ተስፋ መቁረጥህን ያየ መንፈስ ሁሉ የምትሞትበትን ምርጫ በገፍ ያቀርብልሃል። ብልጥ መሆንን የሚጠይቀው ያን ጊዜ ነው። ሞኞች የሚሞቱት ሞት መነሻው ይህ ተስፋ የመቁረጥ ተስፋ የማጣት ሂደት ነው። ሰይጣን መንግሥተ ሰማያት ስትገባ ማየት አይወድም። ለዚህም ነው የሞት አማራጭ የሚያቀርብልህ። ተስፋ በማስቆረጥ በቁምህ እንድትሞት ካግባባህ በኋላ ራስህን እንድታጠፋ ይጋብዝሃል። ጫቱን በገፍ፣ሲጋራውን በገፍ፣ ዝሙቱን በገፍ ያቀርብልሃል። አንተ እጅህን ወደዚያ ከጨመርህ ያንጊዜ ወደ ሞት መስመር መግባትህን ልትዘነጋ አይገባውም። ሰይጣን የሞት አማራጭ ሲያቀርብልህ መሞት ብርቅ አይደለም መርዝ አልጠጣም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ራሴን አላንቅም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ራሴን ወደ ገደል አልወረውርም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ኤሌክትሪክ አልጨብጥም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ጫት አልቅምም፣ ሲጋራ አላጨስም፣ ዝሙት አልፈጽምም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ራሴን ውኃ ውስጥ አልገድልም በለው፡፡ ለእኔ ብርቄ መሞት አይደለም ለኔ ብርቄ በህይወት መኖር ነው በለው። ሞት ብርቅ አይደለም እኔ የምፈልገው ብርቅ የሆነውን እንጅ የረከሰውን አይደለም በለው። ወንድሜ ሆይ መሞት ብርቅ አይደለም። ዛሬ ራስህን ልትገድል እድሉ አለህ ነገር ግን ብርቅ አይደለም። ብርቁ ነገር ንስሐ መግባት ነው። ብርቁ ነገር ሥጋ ወደሙን መቀበል ነው። ብርቁ ነገር ከኃጢአት መራቅ ነው። ብርቁ ነገር በእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ መሄድ ነው። ብርቁ ነገር ራስን መግደል ሳይሆን ራስን ማዳን ነው። ስለዚህ ሰይጣንን መሞት ብርቅ አይደለምና ለአንተ አንገዛም እንበለው። በቤተ ክርስቲያን ፊት ቆመን እንካደው። ርኩስ መንፈስ ሲገፋፋህ ቆም ብለን አስብ። 

Sunday, June 28, 2015

መሞት ብርቅ አይደለም (ክፍል ሦስት)

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
በክፍል ሁለት ሁሉን አቀፍ ሞት እና የሞኞች ሞት በሚል ማብራሪያ መስጠታችን ይታወቃል፡፡ ነገር ግን የሞኞች ሞት በራሱ በሁለት የሚከፈል በመሆኑ በዚህ ክፍል እነዚህን በዝርዝር እንመለከታለን፡፡ መልካም ንባብ፡፡
          ሀ.የቁም ሞት
ሰው ነፍስና ሥጋው ሳይለይ የሚሞተው ሞት ነው፡፡ አንድ ሰው ከእግዚአብሔርተለይቶ የኃጢአትን መንገድ ተከትሎ የሚጓዝ ከሆነ በቁሙ ሞቷል ይባላል፡፡“እንደቆመ የሚመስለው እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ” 1ኛ ቆሮ10፥12 እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ ሕይወት ያለው የሚመስለው ሁሉ ሕይወት ያለውአይምሰለው፡፡ መንቀሳቀስ ብቻውን በሕይት የመኖር መገለጫ አይደለም፡፡ ተንቀሳቃሽ የሆነ ነገር ግን በሥራ የሞተ ብዙ ነው፡፡ የቁም ሞትንየሞተ ሰው በሥጋ ከሞተ ሰው የሚለየው መንቀሳቀሱ፣ መናገሩ፣ መማር የሚችል በንስሓ ሊመለስ የሚችል መሆኑ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ተለይቶ በረከሰ ሥራ በኃጢአት ተዘፍቆ ለሰይጣን ተገዝቶ መብላት፣ መጠጣት፣ መስከር፣ መደነስ፣ መዳራት፣ መስረቅ፣ መግደል፣ መዋሸት ወዘተ… የዕለት ከዕለት ተግባሩ ያደረገ ሰው የሞተ ነው፡፡ ማስቀደስ ያቆመ ሰው፣ መጾም፣ መጸለይ፣ መስገድ፣ መመጽወት፣ የረሳ ሰው የሞተ ነው፡፡ንስሓ መግባት፣ መቁረብ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ የተወ ሰው የሞተ ነው፡፡ አባትና እናቱን የማያከብር፣ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የማይጠብቅ፣ አምላክነቱንም የሚጠራጠር፣ቅዱሳንን አማላጆቼ ብሎ የማይቀበል፣ ድንግል ማርያምን ወላዲተ አምላክ ብሎ የማያምን ሰው የሞተ ነው፡፡ የልጅነት ጥምቀት ያልተጠመቀ፣ በአህዛባዊ ግብር የሚኖር በምንፍቅና ዕድሜ የሚቆጥር፣ በክህደት የሚኖር ሰው ሁሉ የሞተ ነው፡፡ ከእነዚህ ሁሉ በንሥሓ በመመለስ እግዚአብሔርን አምነን በጽድቅ መመላለስ ከቻልን የሞኞችን ሞት ሳንሞት መኖር እንችላለን፡፡ ሞኞች ሲጋራ በማጤስ፣ ጫት በመቃም፣ ቡና በመጨለጥ ወዘተ… ሞተዋል፡፡እነዚህን በመተው ደግሞ ሕይወት የሚኖሩ አሉ፡፡ከምድር በላይ ከሰማይ በታች ለሰው ልጆች ያለአድልዎ እኩልየሆነ ነገር ተሰጥቶናል፡፡ ይህን የተሰጠንን ነገር በአግባቡ የመጠቀምና ያለመጠቀም ጉዳይ ነው የሞኞችን ሞት የፈጠረው፡፡ ስለዚህ ብልጥ በመሆን ማለትም ኃጢአትን ባለመሥራት፣ በእግዚአብሔር ትእዛዛት በመመራት፣ በአባቶቻችን ሥርዓት በመጽናት፣ ንስሓ በመግባት፣ ሥጋን ለነፍስ በማስገዛት የቁምን ሞት ማምለጥ ይቻላል፡፡ ሞኝ ሆነህ ነፍስህን ረስተህ ለሥጋህ ብቻ የምትኖር ከሆነ ግን ሁሉም የሞት አይነቶች በተራ ማስተናገድህ አይቀርም፡፡
ለ. የነፍስ ሞት

አስፈሪው የሞት አይነት ይህ ነው፡፡ለሞኞች ይህ ሦስተኛ ሞት ነው፡፡ ይህ ሞት የዘላለም ሞት ነው፡፡ ሥጋ ወደ መቃብር ነፍስ ወደ ሲኦል በትንሣኤ ጊዜ ደግሞ ሥጋ ከመቃብር ተነሥቶ ነፍስ ከሲኦል መጥታ ከሥጋ ጋር ተዋሕዳ ወደ ገሐነም የሚገቡበት ለዘላለም ከዲያብሎስ ጋር የሚኖሩት ኑሮ የዘላለም ሞት /የነፍስ ሞት/ ይባላል፡፡የቁም ሞት የሞተ ሰው በንስሓ ካልተመለሰ የነፍስ ሞት ያገኘዋል፡፡ በዳግም ምጽአት ጊዜ በእንባ ብንታጠብ ንስሓ ብንገባ ማንም የሚቀበለን የለም፡፡“እናንተ ርጉማንለሰይጣንና ለመላእክቱ ወደ ተዘጋጀ ወደ ዘላለም እሳት ከእኔ ሂዱ፡፡” ማቴ 25፥41የሚለው ዘላለማዊ ፍርድ ከተፈረደብን የትም ማምለጥ አንችልም፡፡ ወገኖቼ ይህን ሞት ፍሩ፡፡ የሥጋ ሞትማ ለሁሉም ነው፡፡ ደግሞም ከምድር የስቃይ ኑሮ የምንገላገልበት ትልቅ እረፍት ነው፡፡እረፍት የሚሆነው ግን እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ ለተጓዘ ነው፡፡የነፍስ ሞት ቆሻሻቸውን ላላስወገዱ ሞኞች የተሰራ ነው፡፡ በእድፍ /በኃጢአት/ እንደ ተጨማለቁ መንግሥተ ሰማያት መግባት አይቻልም፡፡ ስለሆነም የገሐነም ፍርድ ይፈረድበታል፡፡ በአጠቃላይ በቁሙ የሞተ ሰው ንስሓ እስካልገባ ድረስ የነፍስ ሞት አይቀርለትም፡፡ ሞኞች ሦስት ጊዜ ይሞታሉ ብልጦች ግን አንድ ጊዜ ብቻ፡፡ ስለዚህ በሞኝነት ከምንሞታቸው ሁለት ሞቶች ልንቆጠብ ይገባል፡፡ ምክንያቱም የቁም ሞትና የነፍስ ሞት ራሳችን በራሳችን ላይ የምንወስናቸው ሞቶች ናቸው፡፡ የሥጋ ሞት ግን ሁሉን አቀፍ ሁሉን የሚጎበኝ ስለሆነ ፈቀድንም አልፈቀድንምአይቀርልንም፡፡ እኛ ልንቆጠብ የሚያስፈልገው ፈቅደን ከምናመጣቸው ሞቶች ነው፡፡

Saturday, June 27, 2015

መሞት ብርቅ አይደለም (ክፍል ሁለት)

በክፍል አንድ ስለሞት ትርጉም አይተናል በዚህ ክፍል ደግሞ ስለ ሞት አይነቶች ዝርዝር ማብራሪያ እንሰጣለን፡፡ መልካም ንባብ
1.    ሁሉን አቀፍ ሞት
ይህ የሞት አይነት ለፍጡራን ሁሉ እኩል የተሰጠ ነው፡፡ እንስሳት፣ ዕፅዋት፣ ሁሉም ይሞታሉ፡፡ የሰው ልጅም እንዲሁ ይሞታል፡፡ ይህን ሞት የሥጋ ሞት ብለን የምንጠራው ነው፡፡የነፍስ ከሥጋ መለየት ማለት ነው፡፡ ውሎ ውሎ ከቤት ኖሮ ኖሮ ከሞት የሚባልለት ይህ ነው፡፡ ማንኛውም ፍጡር የሆነ ሁሉ የሚጎነጨው ጽዋእ ነው፡፡ እንኳን ፍጡራን አምላካችን ክርስቶስም ስለኃጢአታችንና በደላችን ለሞት ተላልፎ ተሰጥቷል፡፡1ኛ ቆሮ15፥4አምላክ የሞተውን ሞት ሁሉም ፍጡር ይቀምሰው ዘንድ ግዴታ አለበት፡፡ አሁን በብሔረ ሕያዋን የሚኖሩ ቅዱሳን እነ ሄኖክ፣ እነ ዕዝራ፣ እነ ኤልያስወዘተ… በዓለም ፍጻሜ ስለክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትመስክረው በሰማዕትነት ያርፋሉ እንጅ ሞትን ሳይቀምሷት አይቀሩም፡፡ይህን ሞት ልንፈራውና ልንሸሸው አይገባም፡፡“ ሥጋንየሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ” ማቴ 10፥28እንዲል የሥጋን ሞት መፍራት አይገባም፡፡ ብንፈራውስ ብንሸሸውስ አይቀርልን ነገሩ ነው እንጅ፡፡ ደግሞም እኮ አላስተውል ብለን እንጅ ሁልጊዜ በትክሻችን ይዘነው የምንዞረው እርሱን ነው፡፡ ሰው ሥጋው ከነፍሱተለየ ማለት በስብሶ አፈር ትቢያ ሆኖ ይቀራል ማለት አይደለም፡፡ የሰው ልጅ “ዋይ” እያለ ወደ ዓለም እንደመጣ “ዋይ” እያሉ ያሸኙታል፡፡ እንደገል ቀጥቅጠው እንደ ሰም አቅልጠው የገዙ ነገሥታት እንዲሁም በወርቅና በዕንቊ ያሸበረቁት ከመጋረጃ ወጥተው ታይተው የማይታወቁ ንግሥታት በአሸበረቀና በተዋበ በዕንቊበተጌጠ ባማረ ቤት ይኖሩ የነበሩት ባለጠጋዎች ዛሬ ከመቃብር በታች ሥጋቸው ፈርሶ አጥንታቸው በስብሶ ትንሣኤን ይጠባበቃል፡፡ሞት ሲመጣ አሜን ብሎ ተቀብሎ እንሂድ ሲል አብሮ መሔድ ነው ቀጠሮ የለውም ተዘጋጅቶ መጠበቅ ብቻ ነው፡፡ ይህ አይነቱ ሞት ሊያስጨንቀን የሚገባ አይደለም የሚያስጨንቀንና የሚያስፈራንስ ሞት የነፍስ ሞት ነው፡፡“ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሐነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ፡፡” ማቴ10፥28ማለቱ ለዚህ ነው፡፡
2.   የሞኞች ሞት

ይህኛው የሞት አይነት ሁሉን የሚያቅፍ /ሁሉን አቀፍ/ አይደለም፡፡ ሞኞች ብቻ የሚሞቱት የሞት አይነት ነው፡፡ በውስጡ የቁም ሞትንና የነፍስ ሞትን ይይዛል፡፡ ዝርዝር መረጃውን በክፍል ሦስት ይጠብቁን፡፡
©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

Friday, June 26, 2015

መሞት ብርቅ አይደለም (ክፍል አንድ)

© መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

የዚህን ትምህርት ዋና መልእክት የምንጀምረው በድርሳነ ሚካኤል ዘመስከረም ከቁጥር 23-27 ያለውን ስለሞት የተጻፈ መልእክት በማስቀደም ይሆናል፡፡ ጽሑፉ እንዲህ ይላል፡-“እንግዲህ በስንፍና ነፍሱን ያጠፋ ወዮለት ወዮታ አለበት፡፡ በዚህ ዓለም በሕይወተ ሥጋ ሣለ ይቅርታ ካላደረገ በጎ ሥራ ካልሠራ ምን ይጠቅመዋል? ምን ይረባዋል?የሚሞትበትን ቀን አያውቅም፡፡ገንዘቡም ከእርሱ ጋር አብሮት አይሔድም ነፍሱም ድንገት ተመንጥቃ ትለየውና መላእክት በሐፀ እሳት እየነደፉ በመፍራትና በመንቀጥቀጥ በሰማያዊው ንጉሥ ቅድመ እግዚአብሔር ደርሳ ራቁቷን ትቆማለች፡፡ ይህች ምድራዊት ዓለም ሳታዋርደን ሳታስንቀን በፊት እኛ እናዋርዳት እናሳጣት ከእርሷ ተፈጥረን ሁላችንም ወደ እርሷ ተመልሰን እንሔዳለንና አላፊ ጠፊ ስለሆነች የተናቀች ሰነፍ ናት፡፡ እንደ ተውሶ ልብስም ፈጥና ታረጃለች፡፡እንደ ጥላም ታልፋለች፡፡ በዚህ ዓለም የተደሰታችሁበት ሁሉ ከንቱ ነው፡፡ ቋሚነት የለውም፡፡ መግቢያችንና ማደሪያችን በዚያ ነውና እስከዘላለሙ ድረስ፡፡ ወንድሞቼ ሆይ ያች የመከራ ቀን ከመድረሷ አስቀድሞ ስለራሳችሁ አልቅሱ፡፡ ወዳጆቼ ሆያ እስኪ ልብ አድርጋችሁ አስተውሉ፡፡ የቀደሙ አባቶቻችን ነገሥታቱ መኳንንቱ መሳፍንቱ የተከበሩት ሽማግሌዎች ሕጻናትና ዋጋው ብዙ የሆነ ነጭ ሐር የለበሱ በወርቅና በብር ጌጥ የተሸቆጠቆጡ የሴት ወይዘሮዎች ሁሉ ወዴት አሉ?እናንተም እንደ እነርሱ ትሞታላችሁ የዚህን ዓለም ሀብትና ንብረት ትታችሁ ትሔዳላችሁ፡፡ ወዳጆቼ ሆይ አላፊ ጠፊ የሚሆን የዚህን ዓለም ሃብት ከመውደዳችሁ በስተቀር እስከዛሬ አላስተዋላችሁምና፡፡ ወንድሞቼ ሆይ እናንተስ ገሐነማዊ ፍርድ ያለበትን ሰማያዊ ሞት ፍሩ እንጅ የዚህን ዓለም ሞት አትፍሩ፡፡”ከዚህ እንደምንረዳው ሞት ንጉሥ አይል ሎሌ፣ ካሕን አይል ምእመን፣ መምህር አይል ተማሪ፣ አዋቂ አይል ሕጻን፣ ሃብታም አይል ድሃ፣ ሴት አይል ወንድ ለሁሉም እንደየተራውጊዜውን ጠብቆዕጣው ይወጣል፡፡ ሞትን ማን አመጣው ቢሉ የሰው ልጅ ነው፡፡ “ስለዚህ ምክንያት ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፡፡” ሮሜ5፥12እንዳለ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ ይህስ እንዴት ነው ቢሉ አዳም በገነት ላይ አዛዥ እና ገዥ ሆኖ በተፈጠረ ጊዜ ሦስት ዕፅዋት ነበሩ፡፡ እንዲበላው የታዘዘ፣ እንዳይበላው የታዘዘ እና እንዲበላውም እንዳይበላውም ያልታዘዘው ማለት ነው፡፡“ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ ከእርሱ በበላህቀን የሞት ሞትን ትሞታለህ” ዘፍ2፥17እንዳለ፡፡ ይህችን አትብሉ የተባሏትን ዛፍ ሳይበሉቢጠብቋት ኖሮ ከሺህ ዘመን በኋላ ብላም አትብላም ተብሎ ያልታዘዘውን ዕፀ ሕይወት በልተው ታድሰው መንግሥተ ሰማያት ይገቡ ነበር፡፡ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ በሉ ሞትንም ወደ ዓለም አመጡ፡፡ዘፍ3፥6ለዚህም ነው ሞትን የሰው ልጅ አመጣው የምንል፡፡ ሞት በተለያየ መልኩ ተከፍሎ ሊታይ ይችላል፡፡ እነዚህም፡-
1. ሁሉን አቀፍ ሞት
2. የሞኞች ሞት በማለት መክፈል ይቻላል፡፡
ለእያንዳንዳቸው የሞት አይነቶች ዝርዝር ማብራሪያ በክፍል ሁለት ይጠብቁን፡

Thursday, June 25, 2015

ቸርነቱን ለኃጢአት አትጠቀምበት

ወንድሜ ሆይ ኮልታፋ በሆነው አንደበቴ ላይ የአሮንን አንደበት ተክቼ ልመክርህ ነው፡፡ በእርግጥ ልመክርህ አይደለም ልንመካከር ልንማማር ነው እንጅ፡፡ አምላክ ለምን ፈጠረኝ ብለህ አስበህ ታውቃለህ? አምላክ ሥነ ፍጥረትን በየወገኑ ሲፈጥር ምክንያት አለው፡፡ እንድንማርባቸው የተፈጠሩ አሉ፣ እንድንመገባቸው የተፈጠሩ አሉ፣ እንድንገለገልባቸው የተፈጠሩ አሉ፣ ፈጣሪን እንድናውቅበትም የተፈጠሩ አሉ፡፡ የምድር ጠቢባን ምንም ያህል ቢራቀቁ ካለው ነገር ነው እንጅ ከራሳቸው አንቅተው የሚፈጥሩት ነገር የለም፡፡ አምላክ ግን ካለመኖር ወደ መኖር አምጥቶ ሥነ ፍጥረትን ፈጥሯል፡፡ ሰውን ግን አልቆ ፈጠረው ለምን ፈጠረው? እግዚአብሔር አንድነቱ ሶስትነቱን ሳይጠቀልለው፣ ሦስትነቱም አንድነቱን ሳይከፋፍለው የገዛ ባሕርይው ባሕርይውን እያመሰገነ ክብሩ በራሱ እንደቀረ ባየ ጊዜ ክብሩን የሚወርስ ስሙን የሚቀድስ ሰውና መላእክትን ፈጠረ፡፡ ፍጠረን ሳንለው ስለፈጠረንም ቸርነቱን አብዝቶልን በምሕረቱ ሁሌም ይጠብቀናል፡፡ እንደውም ለኃጢአታችን ከሳ ሆኖ በመስቀል ሞት ራሱን አሳልፎ ሰጥቶ ፍቅር ማለት እንዲህ ጠላትን አብዝቶ መውደድ ነው ብሎ ፍቅርን በተግባር ተረጎመልን፡፡ በደሙ ፈሳሽነትም 5 ሺ ከ 5 መቶ ዘመን ተዘግታ የነበረችውን ገነት ከፍቶ ነፍሳትን ከባርነት ቀንበር አሳርፎ በዚያ አኖራቸው፡፡ የአምላክ ትእግስት እና ቸርነት መጠን የለውም ስንበድለው ይክሰናል፣ ኃጢአት ስንሰራ ወዲያውኑ አይቀጣንም ነጻ ፈቃዳችንን ሊሽርብን አይሻም፡፡
የእኛ ችግር ምንድን ነው? ቸርነቱን ሲያበዛልን ጻድቅ የሆንን ይመስለናል፡፡ ትልቁ ውድቀታችን ያን ጊዜ ይጀምራል፡፡ ዛሬን በሰላም ውለህ ነገን በተስፋ የምትጠብቀው ቸርነቱ ስለጠበቀህ ነው፡፡ በልተህ የምትጠግብ፣ ጠጥተህ የምትረካ፣ ለብሰህ የምትደምቅ የአምላክ ቸርነቱ ስለጠበቀህ ነው፡፡ እንደ ዮሴፍ በስደት ሳለህ ሞገስ የሚሰጥህ ቸርነቱ ስለጠበቀህ ነው፡፡ ጸሎት የምታደርሰው እስከ ምሽት የምትጾመው ቸርነቱ ስላበረታህ ነው፡፡ እስከምትደክም የምትሰግደው፣ ያለህን ሁሉ የምትመጸውተው ቸርነቱ ስላበረታህ ነው፡፡ ያዘኑትን የምታረጋጋው፣ የደከሙትን የምታበረታው፣ የተጣሉትን የምታስታርቀው ቸርነቱ ስለበዛልህ ነው፡፡ የሰራኸው የሚባረክልህ ቸርነቱ ስለበዛልህ ነው፡፡ በኃጢአትህ ብዛት ዛሬ ያላጠፋህ ቸርነቱ ስለሚከለክለው ነው፡፡
ሰነፍ በልቡ እግዚአብሔር የለም ይላል፡፡ እውነቱን ነው ሰነፍ የአምላኩን ቸርነት አይረዳም፡፡ እንዲያውም ትላልቅ ኃጢአትን እየሰራ አምላኩ ሲታገሰው “እውነት ፈጣሪ ካለ ለምን እኔን አላጠፋኝም?” ይላል፡፡ የአምላክ ትእግስትና ቸርነት እንደ ሰው ትእግስትና ቸርነት የሚመስለው ሰው አለ፡፡ ያ ሰው ኃጢአት በየጊዜው እየሰራ በሰላም ሲኖር እግዚአብሔር እንደሌለ አድርጎ ይቆጥራል፡፡ እግዚአብሔርን እንደ ሰው ቆጥረነው ካልሆነ በቀር ስንበድለው ዝም ቢለን ትእግስቱንና ቸርነቱን እያደነቅን ልናመሰግነው እንጅ እንደሌለ ልንቆጥረው አይገባም፡፡ የትእግስቱ ብዛትማ ሲሰቅሉት ምንም አላላቸውም እኮ እንደውም ጎኑን የወጋው ለንጊኖስ አንድ ዓይና ነበርና ደሙ ነጥቦ ቢነካው ዓይኑ በርቶለታል፡፡ በእውነት በጦር የሚወጉትን ዓይን ማብራት እንዴት ያለ ቸርነት ነው ብለን ማድነቅ ሲገባን እግዚአብሔር ስለሌለ ነው ልንል አይገባም፡፡ የጠፋውን ዓይን ማን አበራለት ልንል ነው ታዲያ?

እግዚአብሔር እንዲህ በቸርነት ጥላው ከልሎ ዘመናትን ሲያሻግረን ልናመሰግነው ይገባል እንጅ ቸርነቱን ለኃጢአት ሥራ ልንጠቀምበት አይገባም፡፡ ትናንት ንስሐ ካልገባን ዛሬ ንስሐ እንድንገባ ነው ቸርነቱ የሚጠብቀን፡፡ ነገር ግን አምላክ የሰጠንን ቸርነት በአግባቡ ካልተጠቀምንበት ፍዳው ለራሳችን ነው፡፡ ስለዚህ ቸርነቱን ለኃጢአት ሥራ ልናውለው አይገባንም፡፡ አምላካችን ቸርነቱን ዛሬም ይላክልን፡፡

Wednesday, June 24, 2015

የመጨረሻው ዘመን መጀመሪያ /ክፍል አራት/

በተከታታይ ሶስት ክፍሎች ስለመጨረሻው ዘመን የማቴወስ ወንጌል ምእራፍ 24 ን ከአንድምታ ትርጉሙ ጋር ተመልክተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ በተከታታይ ያየናቸውን እናጠቃልላቸዋለን፡፡ ሰው ሁሉ ዛሬ እየተጨነቀ ያለበት በርካታ ጉዳይ አለ፡፡ እነዚህ ጉዳዮች ደግሞ ከዘመኑ መጨረሻነት ጋር የተያያዙ ናቸው፡፡ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ሥር ተሰግስገው ወተቷን የጠቧትን እናታቸውን ጡቷን የሚነክሱ ተሃድሶ መናፍቃን የዘመኑ መጨረሻነትን አርጅዎች ናቸው፡፡ ዛሬ በየ መንገዱ ኢየሱስን ተቀበሉ እያሉ ህዝቡን መከራ የሚያበሉ መናፍቃን መኖራቸው ዘመኑን ለመጨረሳችን አርጅዎች ናቸው፡፡ ዛሬ በተለያዩ ክፍለ ዓለማት ኢየሱስ ነኝ እያሉ የተነሡት በእኛም ሃገር ሳይቀር ድንግል ማርያም ነኝ ብላ የተነሣችው ዘመኑ ማለቁን አስረጅዎች ናቸው፡፡ ዛሬ እኮ ማታ በሰላም እደር ብለህ የሸኘኸውን ጓደኛ ነገ ሞተ ተብለህ እየገረመህ ልትቀብር የምትሄድበት ጊዜ ነው፡፡ መንግሥት በመንግሥት ላይ ህዝብም በሕዝብ ላይ ይነሣል የተባለውስ ቢሆን ስንቱ አገር ነው ዛሬ ድረስ የሰላም እንቅልፍ ያጣው? የአንዲት አገር መንግሥትም እንዲሁ በሌላው አገር መንግሥት ላይ እየተነሣ ያለበት ዘመን ነው፡፡ የሰው ልጅ ሞቱ እጅግ የበዛበት ነው፡፡ ድሮ ሕመም ብቻ ይገድለው የነበረው ሰው ዛሬ ባልታወቀ ነገር ሁሉ ሞቶ ይገኛል ሬሳው ወድቆ የአራዊት መጫዎቻ ይሆናል፡፡ ግፍ መከራ ስደት እንግልት ሆኗል፡፡ ዘመኑ ቀርቧልና ንስሐ ግቡ የሚለው የእውነት አዋጅ ዛሬ ላይ ሊታወጅ የሚገባው ነው፡፡ በእርግጥ ሁሌም ቢሆን ቤተክርስቲያናችን ይህንን ስታውጅ ኖራለች ዛሬም ታውጃለች ወደፊትም ዘመኑ እስከተፈጸመ ድረስ ታውጃለች፡፡ የአሁኑ ችግር የእኛው ነው፡፡ መስማት መስማት አሁንም መእማት በመስማት ብቻ ጆሯችን ሰባ ሥራ ግን ያው ባዶ፡፡ ቅዱስ ዳዊት አቤቱ ንጹሕ ልብን ፍጠርልኝ ማለቱ የድሮውን ልቤን አስወግደህ አዲስ ልብ እንደገና ፍጠርልኝ ማለቱ አይደለም ልቤን አስተዋይ ጥበበኛ ብልህ አዋቂ አድርግልኝ ሲል ነው፡፡ ስለዚህ ዘመኑ ቀርቧልና ንስሐ ልንገባ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ማለት ግን በሰው ልብ ዘንድ ሽብር  እና ጭንቀትን መፍጠር ማለት አይደለም፡፡ ይህ ሁሉ ሊሆን ግድ ነው ብሏል እኮ ታዲያ የቃሉ ባለቤት ይዋሸናል? በፍጹም ውሸት የለበትም አምላክ የተናገረውን አያስቀርም ሁሉም ጊዜውን ጠብቆ ይደርሳል፡፡ በርካታ መከራ ወደፊትም ይመጣል የግድም ይሆናል ያንን መከራ ግን እንዳንሰቀቅ እንዳንፈራ አምላካችን ብርታቱን እንዲሰጠን መለመን አለብን፡፡ ፎቅ በፎቅ ላይ ስንቆልል፣ ሃብት በሃብት ላይ ስንደርብ ባልታወቀ ሰዓት ባልተጠበቀ ቀን ሞት መጥቶ እንዳይጠራን እንጸልይ፡፡ አቤቱ በዘመኔ እኩሌታ አትውሰደኝ ብለህ ፈጣሪያችንን እንማጸነው፡፡ የዘመን እኩሌታ ማለት ንስሐ ሳንገባ ፍሬ ሳናፈራ ኃጢአት ስንሰራ ባለንበት ወቅት አትውሰደኝ ማለት ነው፡፡ ዕድሜ የሚሰጠን ለንስሐ ነው እድሜ ብቻ ስንቆጥር የምንውል ከሆነ ግን ችግር አለብን፡፡ እኔ ዛሬ የተወለድኩበትን ቀን ሰኔ 17 ን ለ27 ዓመት ያህል አከበርኩ በዚህ 27 ዓመት እድሜዬ ላይ እልፍ አእላፋት ጊዜ አምላኬን በድያለሁ ነገር ግን የእድሜዬን ያህል እንኳ 27 ጊዜ ማለት ነው ንስሐ አልገባሁም ታዲያ እድሜዬ ምን ፈየደልኝ፡፡ በዓለም ብዙ ዓመት የኖረ ሰው ተብዬ ሪከርድ አላስመዘግብ ነገር ማቱሳላ 969 ዓመት ኖሮ ሪከርዱን ይዞታል፡፡ ታዲያ ዛሬ ብሞት ነገ ብሞት ንስሐ ካልገባሁ ምኑ ያስፈራኛል? አመጣጣችን እዚህ መሬት ላይ ብዙ ዘመን ለመኖር ሳይሆን ባለን ዘመን ሁሉ የሚጠቅም የጽድቅ ሥራ እንድንሠራ ነው፡፡ ስለዚህ መከራውን ታግሰን ልንኖር ያስፈልጋል ዋጋችን የሚበዛው እሱን ማድረግ ስንችል ብቻ ነውና፡


Tuesday, June 23, 2015

የመጨረሻው ዘመን መጀመሪያ /ክፍል ሦስት/

በተከታታይ ሁለት ክፍሎች ውስጥ የዓለምን ፍጻሜ አስመልክተን በማቴዎስ ወንጌል ምእራፍ 24 ባለው መነሻነት የዓለም ፍጻሜ የምጥ መጀመሪያ ምልክቶችንና እነዚያን ምልክቶች ስንመለከት ምን አይነት ጥንቃቄ ልንወስድ ይገባናል የሚሉትን ዓበይት ነጥቦት ተመልክተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ ፍጻሜው ሊደርስ ጥቂት ሲቀረው ምን ይከሰታል የሚለውን እንመለከታለን፡፡
1ኛ. “ለአሕዛብ ሁሉ ምሥክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል በዚያም ጊዜ መጨረሻው ይመጣል” ጌትነቱን የምትናገር ወንጌል በአራቱ ማእዘን ትነገራለች በእስላም ቤት ሳትቀር፡፡ ይህ የሚሆንበት ታሪክ አለው በአገራችን ቴዎድሮስ በአገራቸው ዮሐንስ የሚባል ይነግሣል የእኛም ሄዶ የእነርሱም መጥቶ በእስክንድርያ ሦስት ቀን ይዋጋሉ አራቱ ሊቃነ ጳጳሳት የክርስቲያን ደም ለምን ይፈሳል፤ መሥዋእት ሰውተን በመሥዋእቱ ምልክት በታየለት ሃይማኖት ይጽና ይሏቸዋል ሁሉም በያሉበት መሥዋእት ያቀርባሉ፡፡ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በሰዋው “እኔ ክርስቶስ ነኝ” ብሎ በርግብ አምሳል ወርዶ ይመሰክራል ከዚህ በኋላ በሃይማኖት አንድ ይሆናሉ በግቢ ይገናናሉ፡፡ ገድለ ፊቅጦርና ራእየ ሲኖዳ እንደሚለው፡፡
2ኛ. “በዚያን ጊዜ ከዓለም መጀመሪያ ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ ያልሆነ እንገዲህም ከቶ የማይሆን ታላቅ መከራ ይሆናል” በክፍል አንድ ከተመለከትናቸው መከራዎች ሁሉ የሚከፋው መከራ መቼም መቼ  ሊሆን የማይችል ከባድ መከራ ይሆናል፡፡ ዓለም ከተፈጠረች ጀምሮ የሌለ ወደፊትም የማይኖር ጸዋትወ መከራ አለ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ቀኖች ክፉ እንደመሆናቸው ስለተመረጡት ሲባል ያጠሩ ባይሆኑ ኖሮ ሥጋ የለበሰ ሁሉ ባልዳነም ነበር፡፡ ስለተመረጡት ሲል እግዚአብሔር ከቀኑ አራት ከሌሊቱ አራት በድምሩ ስምንት ሰዓታትን ያነሣለትና አንድ ሙሉ ቀን የሚባለው 16 ሰዓታት ብቻ ይሆናሉ፡፡

3ኛ. “መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምእራብ እንደሚታይ የሰው ልጅ አመጣጡ እንዲሁ ይሆናልና” በበረሃ አለ ቢሏችሁ አትመኑ፣ በዚህ አለ በዚያ የለም ቢሏችሁ አትመኑ፣ ወዲህ ይመጣል ወዲያ ይሄዳል ቢሏችሁ አትመኑ መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ መእራብ እንደሚታይ ሁሉ የእግዚአብሔርም አመጣጡ እንዲሁ ነው፡፡ ለአንዱ የሚታይ ለአንዱ የማይታይ ሆኖ ሳይሆን ለሁሉም የሚታይ ሆኖ ነውና ተጠበቁ ሀሰተኞችን አትመኑ፡፡

4ኛ. “ከዚያች ወራትም መከራ በኋላ ወዲያው ፀሐይ ይጨልማል ጨረቃም ብርሃንዋን አትሰጥም ክዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ” ይህ ሁሉ መከራ ከተደረገ በኋላ ፀሐይ ያልፋል ጨረቃም ብርሃኗን አትሰጥም ክዋክብትም ያልፋሉ ይወድቃሉ አድማስ ድንዑን ይለቃል፡፡ በዕለተ አርብ በሠሩት ኃጢአት እንደተፈረደባቸው ለማጠየቅ በእለተ አርብ የተደረገው ይደረጋል፡፡
5ኛ. “በዚያን ጊዜም የሰው ልጅ ምልክት በሰማይ ይታያል”  የተወጋ ጎኑ፣ የተቸነከረ እጁን ሳያጠፋ ለሁሉ እያሳየ ይመጣል፡፡ አባ ጳኩሚስ ሲሰግድ ወዙ ወርዶ መሬቱን ጭቃ አደረገው ወዲያውም ጌታ ተገለጠለት አንተን አገኝ ብየ እንዲህ እደክማለሁ አለው፡፡ ጌታም በዕለተ አርብ እንደተሰቀለ ሆኖ ጎኑን እንደተወጋ ደሙን እንዳፈሰሰ ሆኖ ታይቶታል እንደዚሁም በመጨረሻው ዘመን እንዲህ ሆኖ በክብሩ ይታያል፡፡
6ኛ. “ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም” ይህ ሁሉ መከራ ቢሆንም ቅሉ ቤተ አይሁድ አታልፍም እንደማታልፍ እነግራችኋለሁ፡፡
7ኛ. “ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም” እኔ እለፍ ያልሁት ያልፋል እኔ አትለፍ ያልሁት አያልፍም አንድም ህጌን የጠበቀ አያልፍም ህጌን ያልጠበቀ ግን ያልፋል

8ኛ. “እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል” ፈጽሞ ይህን ሁሉ መከራ እና ስቃይ ታግሶ በሃይማኖትና በምግባር የተገኘ እርሱ ከሞት፣ ከፍዳ፣ ከመከራ ነፍስ ይድናል፡፡ እሰከ እለተ ሞቱ ድረስ መከራውን ታግሶ የጸና መከራውን ሳይሰቀቅ የተቀበለ ከፍዳ የሚድን እርሱ ነው፡፡ ስለዚህ እስከ መጨረሻው ድረስ መጽናት ያስፈልጋል መከራ ሊያሰቅቀን አይገባም፡፡ 

Monday, June 22, 2015

የመጨረሻው ዘመን መጀመሪያ /ክፍል ሁለት/

የዓለምን ፍጻሜ ምልክቶች በክፍል አንድ ውስጥ ተመልክተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ የምንመለከተው ዓለም ከማለፏ በፊት ልንወስደው የሚገባውን ጥንቃቄ ይሆናል፡፡ ማቴዎስ ወንጌል ምእራፍ 24 ላይ ነን ዛሬም፡፡
1ኛ. “እንግዲህ በነቢዩ በዳንኤል  የተባለውን የጥፋትን ርኩሰት በተቀደሰችው ስፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል”  በቅዱስ ቦታ የሚቆም ማለት ለቤተመቅደስ አንባቢነት የሚሾም ያስተውል የተነገረውን ቤተመቅደስ በሚፈርስበት ጊዜ የሚሆን የጥጦስን ጣኦቱን ያያችሁ እንደሆነ ያንጊዜ ፍጻሜው ይመጣል ማለት የአይሁድ ጥፋት ይሆናል፡፡
2ኛ. “በዚያን ጊዜ በይሁዳ ያሉት ወደ ተራራዎች ይሽሹ” በሃይማኖት ያሉ ረድኤተ እግዚአብሔርን ጥግ ያድርጉ
3ኛ. “በሰገነትም ያለ በቤቱ ያለውን ሊወስድ አይውረድ” ነፍስ ያለውም ወደ ትህትና አይወርድም ሥጋዊ ሥራን ይሠራ ዘንድ
4ኛ. “በእርሻም ያለ ልብሱን ይወስድ ዘንድ ወደ ኋላው አይመለስ”የመነነም ዓለማዊ ሥራን ይሠራ ዘንድ ወደ ዓለም አይመለስ
5ኛ. “በዚያችም ወራት ለርጉዞችና ለሚያጠቡ ወዮላቸው” ይህ ማስጠንቀቂያ ነው፡፡ ኃጢአትን በሐልዮ ፀንሰው በነቢብ ወልደው በገቢር ለሚያሳድጉ ሰዎች ወዮላቸው የሚል ማስጠንቀቂያ መከራ አለባቸውና፡፡ አንድም  ምእመናንን በትምህርት ጸንሰው በትምህርት ወልደው በትምህርት የሚያሳድጉ መምህራን ወዮላቸው መከራ ሥጋ አለባቸውና፡፡
6ኛ. “ነገር ግን ሽሽታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ” ክረምት ላዩ ውኃ ታቹ ውኃ ነው አያሻግርም፤ ሰንበትም  እለተ እረፍት ነው መንገድ የሚያሳይ አይገኝም አንድም ሦስት ወር ክረምት ለማረፍ ዘጠኝ ወር በጋ የሚሰራ አለ አንድ ቀን ሰንበትንም ለማረፍ ስድስት ቀን የሚደክም አለ፡፡ አርፍባታለሁ ባለበት ስደት ሲመጣ ያሰቅቃል ተስፋ ያስቆርጣልና ነው፡፡ አንድም በሃይማኖት ብቻ ሳላችሁ ምግባር ሳትሠሩ ሞት እንዳይታዘዝባችሁ ለምኑ፡፡  ክረምት ወርኃ ልምላሜ ነው ፍሬ የለውም ሰንበትም እለተ ጽርአት (እረፍት) ናትና በጽርአት  ሳላችሁ፡ በእረፍት ሥራ በማትሠሩበት ምግባር በማትፈጽሙበት ሲል ነው፡፡
7ኛ. “በዚያን ጊዜ ማንም እነሆ ክርስቶስ ከዚህ አለ ቢላችሁ አትመኑ” ክርስቶስ ከወዲህ አለ ከወዲያ የለም ከወዲህ ወዲያ ይሄዳል ወዲህ ይመጣል ቢሏችሁ አትመኑ እንዲህ አይሆንምና፡፡ በበረሃ ነው ቢሏችሁም በእልፍኝ ነው ቢሏችሁም አትመኑ፡፡
8ኛ. “ምሳሌውንም ከበለስ ተማሩ ጫፍዋ ሲለሰልስ ቅጠሏም ሲያቆጠቁጥ ያን ጊዜ በጋ እንደቀረበ እወቁ”  የጥጦስን በቅጠል፣ የሐሳዊ መሲሕን በአበባ፤ የምጽአትን በፍሬ መሰለው፡፡ አንድም እንደ ቅጠሉ ሐሳዊ መሲሕ ነግሦላቸው ቤተ አይሁድ ደስ ብሏቸዋልና፡፡ እንደ አበባው የምእመናን መከራቸው እንደ ፍሬው ሞታቸው፡፡ አንድም እንደ ፍሬው ሞታቸው እንደ አበባ ክብራቸው ፡፡ አንድም ቅጠል አይለወጥም እንደ አበባው የአይሁድ መከራቸው እንደ ፍሬው ሞታቸው፡፡ አንድም እንደ አበባው ሞታቸው እንደ ፍሬው ፍዳቸው፡፡
9ኛ.  “እንዲሁ እናንተ ደግሞ ይህን ሁሉ ስታዩ በደጅ እንደ ቀረበ እወቁ” ከደጅ የቆመ ፈጥኖ እንዲገባ እንዲሁ የዓለም መፈጸምም ፈጥኖ እንዲሆን እወቁ

10ኛ. “ጌታችሁ በምን ሰዓት እንዲመጣ አታውቁምና እንግዲህ ንቁ” በኖኅ ዘመን ጊዜ ዓለም  በጥፋት ውኃ ለመጥፋት 120 ዘመን ተሰጣቸው፡፡ እነርሱም አገቡ ተጋቡ፤ ወለዱ ተዋለዱ፤ በሉ ጠጡ ፤ጠገቡ ረኩ፤ ጨፈሩ ደለቁ ዳንኪራ ረገጡ፤ የእግዚአብሔር ፍርድ ቀን ቀድማ መጣች ዓለምም በንፍር ውኃ ጠፋች፡፡ አንድም የሚመጣበት ቀን ያለማሳወቁ ምስጢር ይህ ነው፡፡ ሰብአ ትካት 120 ዘመን ቢሰጣቸው መቶውን ጨፍረን 20ውን ንስሐ እንገባበታለን ብለው በድለዋልና፡፡  የጥፋት ውኃ መጥቶም ውኃው እስከ አንገታቸው ደርሶ ይዘፍኑ እንደነበር ሊጠፉ መሆናቸውን አላወቁም፡፡ ጌታ ግን የሚመጣበትን ቀን ሰወረ፡፡ ስለዚህም ሁልጊዜ የተዘጋጃችሁ ሁኑ ብሎ አስተማረን፡፡ ንስሐ ገብታችሁ፣ በንጽሕና ሆናችሁ፣ ሥጋና ደሙን ተቀብላችሁ፣ በፍቅር በትህትና ሆናችሁ ጠብቁ፡፡ ሌባ መቼ እንደሚመጣባችሁ እንደማታውቁ ሁሉ የእኔም አመጣጥ እንዲሁ ነው፡፡ ሌባ መቼ እንደሚመጣ ብታውቁ ያንን ሰዓት ነቅታችሁ ትጠብቁ ነበር ነገር ግን የሌባው መምጫ ስለማይታወቅ ሁል ጊዜ ነቅታችሁ ጠብቁ፡፡ አመጣጡ መምጣቱን በማታስቡበት ሰዓት ነውና፡፡

Friday, June 19, 2015

የመጨረሻው ዘመን መጀመሪያ /ክፍል አንድ/

ሴኮንድ አድጋ ደቂቃ ስታክል ደቂቃም ታድግና ሰዓትን ታክላለች፡፡ የሰዓትም እድገት እንዲሁ ይገዝፍና ቀንን መፍጠር ይጀምራል፡፡ ቀንም ብርሃንንና ጨለማን እያፈራረቀ ወራትን ይመሰርታል፤ ወራትም እንዲሁ ዓመታትን፤ ዓመታትም ዓመታትን እየፈጠሩ የማያልቅ የሚመስለን ዘመን ይቆጠራል፡፡ ዘመኑም ዘመኑን እየተካ ያልፋል፡፡እስኪ ዛሬ ላይ ቆመን ዓለም የተፈጠረችበትን ዘመን ወደ ኋላ ዞር ብለን እናስብ እዩትላችሁ ድፍን 7507 ዓመት ኖራለች፡፡ ዓመተዓለም ማለት እርሱ ነው እንግዲህ እኛ የምንፈራው ስምንት ሽህ ስንት ዓመት ቀረው ይሆን?
በማቴዎስ ወንጌል ምእራፍ 24 ላይ እንደምናነበው ሐዋርያት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን “ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድን ነው? አሉት፡፡ ይህ ጥያቄ ዓለም የምትጠፋበት የመጨረሻው ዘመን መቼ እንደሆነ ለማዎቅ የሚረዳ ነው፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ የመለሰላቸው መልስ በትክክል ዓለም በዚህን ቀን፣ በዚህን ወር በዚህን ዓመት ትጠፋለች የሚል አይደለም የዓለምን መጨረሻ የመጀመሪያ ምእራፎች ነበር የነገራቸው፡፡ የዓለም መጨረሻ የመጀመሪያ ምእራፎች ምንድን ናቸው ብለን ስንመለከት የሚከተለውን መልስ እናገኛለን፡፡ “1ኛ. እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ 2ኛ. ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ 3ኛ. ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣሉ 4ኛ. ራብም ቸነፈርም የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል 5ኛ. ለመከራ አሳልፈው ይሰጧችኋል ይገድሏችሁማል 6ኛ. ስለስሜ በአህዛብ ሁሉ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ 7ኛ. እርስበእርሳቸው አሳልፈው ይሰጣጣሉ እርስ በእርሳቸውም ይጣላሉ 8ኛ. ብዙ ሃሰተኞች ነቢያት ይነሣሉ 9ኛ. የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች፡፡
ከላይ የተመለከትናቸው 9 ዋና ዋና ነገሮች የምጥ ጣር መጀመሪያዎች ናቸው ተብለዋል፡፡ ይህም ማለት ዋናው ምጥ ከመምጣቱ አስቀድመው የምጡን መድረስ የሚያሳዩ ነገሮች ናቸው ማለት ነው፡፡ ምጡ የዓለም ፍጻሜ ሲሆን የዓለም ፍጻሜ ከመሆኑ አስቀድሞ ግን እነዚህ ዘጠኝ ዓበይት ነገሮች ይከሰታሉ፡፡ ይህም ሊሆን ግድ ነው ይለናል፡፡ እነዚህ ሁሉ ነገሮች በመፈጸም ላይ ያሉ ወይም ደግሞ ወደፊት ሊፈጸሙ የሚችሉ ናቸው፡፡ እነዚህ ሳይፈጸሙ ግን ዓለም አትጠፋም ምክንያቱም የዓለም ፍጻሜ መጀመሪያዎች እነዚህ ናቸውና፡፡ እነዚህ ምልክቶች እኮ በቃ ተፈጽመው አልፈዋል ወይም እየተፈጸሙ ናቸው ታዲያ ዓለም መቼ ትጠፋለች የሚለውን ቁርጥ ያለ ጊዜ ንገረን እንደማትሉኝ ተስፋ አደርጋለሁ ምክንያቱም ሐዋርያት ራሳቸው በደብረ ዘይት ተራራ ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብለው ጠይቀውት ነበር ነገር ግን  መልስ አላገኙበትም፡፡ መልሱ ይህ ነው “ከበለስ ተማሩ ጫፍዋ ሲለመልም ቅጠሏም ሲያቆጠቁጥ ያን ጊዜ በጋ እንደቀረበ ታወቃላችሁ እንዲሁ እናንተ ደግሞ ይህን ሁሉ ስታዩ በደጅ እንደቀረበ እወቁ” ታዲያ አሁን ዓለም መቼ ትጠፋለች የሚል ጥያቄ ብትጠየቁ  በራሳችሁ መልስ ልትሰጡ የምትችሉት ነገር ቢኖር አሁን በደጅ ቀርቧል የሚል ብቻ ነው፡፡ ለምን? ካልን ደግሞ “ስለዚያች ቀንና ስለዚያች ሰዓት ግን ከአባት በቀር የሰማይ መላእክትም ቢሆን የሚያውቅ የለም” ብሎናልና አምላካችን፡፡ ያች ቀን ያች ሰዓት የተባለችው የዓለም መጨረሻ የምትሆንባት ቀንና ሰዓት ናት፡፡ ያች ቀን ደግሞ ሥጋ ለባሽ ከሆነ ሁሉ የተሰወረች ናት፤ ከሥጋ ለባሽም ብቻ ሳይሆን ከሰማይ መላእክትም እንዲሁ ናት፡፡ በአምላክ ልብ ብቻ ታስባ ያለች ናት እንጅ፡፡ ሊቃውንቱ የዓለም መጨረሻ ዘመኑ ዘመነ ዮሐንስ፣ ወሩ ወርኀ መጋቢት፣ እለቱ እለተ ሰንበት (እሁድ)፣ ሰዓቱ መንፈቀ ሌሊት (ሌሊት ስድስት ሰዓት) ነው ቢሉም የትኛው ዘመነ ዮሐንስ፣ የትኛው መጋቢት ወር፣ ከመጋቢት ውስጥም የትኛዋ ሰንበት የትኛዋ መንፈቀ ሌሊት እንደሆነች ማንም አያውቃትም ከአምላክ በቀር፡፡

ለምን ቀኒቱንና ሰዓቲቱን ሰወረብን? እግዚአብሔር አምላክ የዓለምን ፍጻሜ ምጦች እንጅ ቀንና ሰዓቱን አልተናገረም፡፡ ምክንያቱም 1ኛ. ሰው በባህርዩ የሚኖረው ነገን ተስፋ አድርጎ ነው፡፡ ሞት እንዳለበት ያውቃል ነገር ግን የሚሞትበትን ቀን ስለማያውቅ በተስፋ ነገን እያቀደ ይኖራል፡፡ የዛሬን ፀሐይ እየሞቀ የነገን ፀሐይ ለመሞቅ ተስፋ ያደርጋል፡፡ የሞትህ ቀን ተነግራህ ቢሆን ኖሮ ነገን ተስፋ ማድረግ እንዴት ይቻልህ ነበር? አምላክ ለእኛ ምን ያህል እንደሚያስብልን አስተውሉ! ከሰዓታት በኋላ ልንሞት እንችላለን ነገር ግን እግዚአብሔር እንጅ እኛ አናውቅም፡፡ የዓለምም መጨረሻ እንዲሁ ቢነገረን ኖሮ ይህን ያህል ዓመት ቀረን እያልን ስናዝን እንውል እናድር ነበር፡፡ አዲስ ዘመን መለጫን አስቡት እንዴት እንደምንጓጓለት! ወር ቀረው፣ ሳምንት ቀረው 3 ቀን ቀረው እያልን የምንጠባበቀው መስከረም 1 ዘመን ስለሚለወጥ ነው፡፡ ይህ ቀን ደግሞ ለማንም ግልፅ ቀን ነው፡፡ ያንን ቀን የምንሞትበት ቀን እንደሆነ አድርጋችሁ ቁጠሩት ይህን ያህል ቀን ቀረችብኝ እያልን ሥራ ፈቶች ሆነን አልነበረም? ታዲያ አምላክ ውስጣችንን እያወቀ ዓለም በዚህን ወር፣ ቀን ፣ ዓመት ታልፋለች ብሎ እንዴት ይንገረን?

Tuesday, June 16, 2015

ንስሓ

ንስሓ ማለት መጸጸት፣ መቆርቆር፣ ኃጢአትን ስለሠሩ ማዘን፣ ማልቀስ፣ መቆጨት ነው፡፡ የበጎ ሥራ ጠላት ዲያብሎስ የሰው ልጅ መንግሥተ ሰማያትን እንዳይወርስ ክፉ መርዙን እየረጨ ከንስሓ መንገድ ያርቀናል፡፡ ኃጢአትን በኃጢአት ላይ ደርቦ ደራርቦ ያሠራህና ራስህን እንደ ሰው መቁጠር እስኪያቅትህ ድረስ ያስጨንቅሃል፡፡ ንስሓ ለመግባት ስትፈልግ “ይህን ያህል ኃጢአት እንዴት ነው ለንስሓ አባትህ የምትነግራቸው? የሚያሳፍር ኃጢአትም ሠርተሃል፡፡ ስለዚህ አሁን ተወውና ስታረጅ አንድ ጊዜ ትገላገላለህ” ይልሃል፡፡ የዕድሜ ዘመንህንም ረዘም አድርጎ ያሳይሃል፡፡ አንተም ትታለላለህ “ኃጢአቴን በሙሉ አንድ ጊዜ በሙሉ ልገላገለው” እያልህ ኃጢአትን ማጠራቀም ትጀምራለህ፡፡ እግዚአብሔር በሞት የሚጠራህ መቼ እንደሆነ ታውቃለህ? በፍጹም አታውቅም ጠላት ግን ሽህ ዘመን የምትኖር አስመስሎ ያሳይሃል፡፡ጠላት አሁንም ይቀርብና “የሠራኸው ኃጢአት በጣም ከባድ ነው፡፡ ለንስሓ አባትህ ከነገራካቸው በኋላ ለሌላ ሰው ቢነግሩብህሳ” ይልሃል፡፡ አንተ ግን አትስማው ለቅዱስ ጴጥሮስ የተሰጠው የማሰርና የመፍታት ስልጣን ለንስሓ አባቴም ተሰጥቷቸዋል በለው፡፡ /ማቴ 17፥19/ ዲያብሎስ ግን አሁንም ሌላ ወሬ ይጀምራል፡፡ “ንስሓ አባት ምናምን እያልክ ለምን ጊዜ ትፈጃለህ? ዝም ብለህ ወደ አምላክህ ቀርበህ ይቅር በለኝ ብትለው ይቅር ይልህ የለምን?” ይልሃል፡፡ አንተ ግን ምክሩን አትቀበል በኃጢአት ማሰሪያ እንደታሰርክ ወደ ክርስቶስ ብትቀርብ “ራስህን ለካህን አሳይ” ይልሃል እንጅ አይቀበልህም፡፡ “ክርስቶስ ወደ አንዲት መንደር ሲገባ በሩቁ የቆሙ አሥር ለምጻሞች ተገናኙት እነርሱም እየጮኹ ኢየሱስ ሆይ አቤቱ ማረን አሉ፡፡ አይቶም ሂዱ ራሳችሁን ለካህናት አሳዩ አላቸው”፡፡ /ሉቃ17፥12-14/ ስለዚህ የንስሓ አባት የግድ አስፈላጊ እንደሆነ ልትረዳ ያስፈልጋል፡፡ ንስሓ ሳትገባ መንግሥተ ሰማያት መግባት አትችልም፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ” እያለ ይሰብክ የነበረው ለዚህ ነው፡፡ /ማቴ3፥1-2/ በንስሓ መመለስ ኃጢአትን ሁሉ እንዳይታስብ (እንዲሰረይ) ግዱፍ እነዲሆን ያደርጋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ይላል “ሕመምተኞች እንጅ ባለጤናዎች ባለመድኃኒት አያስፈልጋቸውም ነገር ግን ሄዳችሁ ምሕረትን እወዳለሁ መሥዋዕትንም አይደለም ያለው ምን እንደሆነ ተማሩ ኃጢአተኞችን ወደ ንስሓ እንጅ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁምና” /ማቴ 9፥12-13/ ስለዚህ ንስሓ መግባት ተገቢ ነው ማለት ነው፡፡ ክርስቶስ ወደ ምድር የወረደ ኃጥአንን በንስሓ ለመጥራት እንጅ ለጻድቃን አይደለምና፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ የለበሰ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅ፣ ለያዕቆብ አይደለም ኃጢአትን ላደረጉ ኃጥአን ነው እንጅ፡፡ ንስሓ ኃጢአተኛን ንጹሕና ጻድቅ የሚያደርግ ልዩ ምስጢር ነው፡፡ “በደላቸውን እምራቸዋለሁና ኃጢአታቸውንም ከእንግዲህ ወዲህ አላስብምና” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ /ኤር31፥34/ ጠላት ያንተን ይቅር መባል አይወድምና ከዚህ ምሥጢር እንድትርቅለት በርካታ መሰናክሎችን ያስቀምጥብሃል፡፡ ኃጢአት ስትሠራ እነደ ማር ይጥምሃል፡፡ በኃጢአት ላይ ኃጢአት በበደል ላይ በደል ትደራርባለህ፡፡ የኃጢአት ካባ ሙቀት ይሆንሃል፤ የጽድቅ ሥራ ይቀዘቅዝሃል፡፡ ከዚህም የተነሣ ኃጢአት ባሪያው ያደርግሃል አንተም ትሆንለታለህ፡፡ የታሰርክበትን ሰንሰለት ለመፍታት ስታስብ እንቅልፍህ ይመጣል፡፡ ዕድሜህ እንደዋዛ በከንቱ ትሮጣለች፡፡ እንደ ኖኅ ዘመን ሰዎች የእግዚአብሔር ቁጣ ሳታስበው መጥቶ ንፍር ውኃ ቢዘንብብህ የት ትገባለህ? /ዘፍ6 እና ዘፍ 7 በሙሉ ተመልከት/ የሞትህ ቀን መቼ እንደሆነ አታውቅምና ንስሓ ገብተህ ተዘጋጅተህ መኖር ተገቢ ነው፡፡ ሙሽራው ሲመጣ ዘይት ፍለጋ ልትሄድ አይገባም ዘይትህን ከመብራት ጋር ይዘህ መጠበቅ እንጅ፡፡/ማቴ25፥1-ፍጻ/ የጠላትን ምክር አትቀበል እርሱ ጥሩ ምክር አይመክርህምና፡፡ እናታችን ሔዋን የጠላትን ምክር በመቀበሏ ስትጎዳ እንጅ ስትጠቀም አላየናትም፡፡ ስለዚህ ለጠላት ጆሮ ሰጥተህ አትስማው፡፡ንስሓ አትግባ እያለ የሚያስጨንቅህ ወደ ዘላለም ቅጣት ሊጥልህ እንጅ የዘላለም ሕይወትን እንድታገኝ አይደለም፡፡ የቀደመው እባብ አሁንም ንስሓ አይጠቅምም እያለ የሚጨቀጭቅህ ከሆነ የጥጦስን (ፈያታዊ ዘየማን) ታሪክ ዘርዝረህ ንገረው፡፡ ጥጦስ ቀማኛ ሽፍታ ወንበዴ ነበር፡፡ በዕለተ አርብ በኢየሱስ ክርስቶስ ቀኝ በኩል ተሰቀለ፡፡ ሰባቱን ተአምራት በዓይኑ ተመለከተ፡፡ የተሰቀለው ክርስቶስ አምላክ እንደሆነም አመነና “ጌታ ሆይ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ” የሚል ታላቅ ልመና ለመነ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም በንስሓ ተቀበለውና “እውነት እልሃለሁ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ” አለው፡፡ ይህ ወንበዴም አዳምን ተቀድሞ በክርስቶስ ደመ ማኅተም ለ5500 ዘመናት ያህል ተዘግታ የነበረችን ገነት ከፍቶ ገባ፡፡ /ሉቃ 23፥39-43/ ስለዚህ ንስሓ ቆሻሻን ሁሉ እንዲህ የሚያጠራ ሳሙና ነው እታጠብበታለሁ በለው፡፡ የኅሊናን ሸክም የሚያራግፍ ኃጢአትን ሁሉ የሚደመስስ ልዩ መድኃኒት ነውና በየሰዓቱ ውሰደው ንስሓን፡፡

Saturday, June 13, 2015

የሞተውን ለመቅበር ያልሞተውን መግደል

አንድ ቀን ሂድ ሂድ የሚል መንፈስ ያዘኝና መጓዝ በለመደው እግሬ እከንፍ ጀመር፡፡ በእርግጥ ክንፍ እንደሌለኝ አምናለሁ ነገር ግን በላይ በሰማይ ከሚበርሩት አእዋፋት እኩል የምበር ይመስለኛል፡፡ ዳሩ ግን አርሱ ፈጣሪ ቢያውቀው እንጅ ማን ሊያውቅ ይችላል? እኔም በመንፈሴ አይደለሁምና፡፡ ነገር ግን ከሰውነቴ አልወጣሁም፡፡ ለዚያም ነው አንድ ሽማግሌ በምሬት ሲናገሩት የነበረውን ምርር የሚል ንግግር የሰማሁ፡፡ ምሬቱ ለእሳቸው ብቻ ሳይሆን ለእኔም ነበር፡፡
ሽማግሌው ሌሊት የሰሙት የእድር ጥሩንባ የቀሰቀሳቸው ይመስላሉ፡፡ “እንቅልፍ አጣን እኮ እናንተ! ቀን ከሌሊት ጥሩንባ ብቻ፡፡ የእድር ጥሩንባ ነፊዎች እገሌ ሞተ ለማለት ጥሩንባ፣የቀበሌ ልማት ቡድኖች  እርከን ሥራ ውጡ ለማለት ጥሩንባ፤ ቀበሌ ስብሰባ አለ ለማለት ጥሩንባ፤ ምርጫ ለመምረጥ ጥሩንባ፤ ሰላማዊ ሰልፍ ውጡ ለማለት ጥሩንባ፣ መኪናዎች መንገድ ልቀቁልኝ ለማለት ጥሩንባ፣አምቡላንሶች  በሽተኛ ይዣለሁ ለማለት ጥሩንባ፣ ጋዜጠኞች ልማቱን ለማብሠር ጥሩንባ ብቻ ሁሉም ጥሩንባ ሆነብን እኮ፡፡ አረ መቼ ነው ከዚህ ድምጽ ጆሮዬ ነጻ የሚሆነው? እስከመቼ ድረስ ነው እንድንሰማቸው ብቻ የሚፈልጉትን ሁሉ የምንሰማቸው?” አሉ፡፡ ሽማግሌው  በሁሉ ነገር በጣም የተበሳጩ ይመስላሉ፡፡ እሳቸው ሲናገሩ ስሰማ እኔም  ውስጤ ትንሽ ተሰማው፡፡ እርግጥ ነው መናገረን ይናገሩ ግን ግድ ስሙኝ የሚሉ ሰዎች ሊኖሩ አይገባም አልኩ በውስጤ፡፡ እሳቸው ግን በነጩ እንደያዘው የሃምሌ ዝናብ በቀላሉ ከምሬታቸው የሚያባሩ አይመስሉም፡፡ ቀጠሉ “የትናንትናን ታሪክ ደፍጣጭ ምኑ ይደመጣል? የበሬ ወለደን ንግግር ማን ይሰማል? ዜና እና የጉዞ ማስታወሻ የተቀላቀለበትን ጋዜጠኛ ማን ይሰማል? አሉባልታ አይሉት ምክር፣ ማስጠንቀቂያ አይሉት ማስፈራሪያ፣ መግለጫ አይሉት ማላገጫ የመሰለውን ትርኪምርኪ ማን ያዳምጣል? ያለፈውን ታሪክ ለመቅበር የዛሬውን ታሪክ የሚገለውን ማን ይከተላል? በሽተኛውን ለማዳን ሲል ያልታመመውን የሚያሳምም ሃኪምን ማን ይቀርበዋል? ዘንዶ የሚወጣበትን ጉድጓድ ዓሣ ይኖርበታል ብሎ ማን እጁን ይሰዳል?” አሉ ሽማግሌው፡፡ ውስጤ ነደደ ተንቦገቦገ፡፡ ግን የትኛው እስር ቤት ሊገቡ ፈልገው ነው እንዲህ ዘራፍ የሚሉት? ስል አሰብኩ፡፡ እስር ቤቶች እንደ አሸን በዝተው እንደተራበ አንበሳ አፋቸውን ከፍተው ሊውጡ በተዘጋጁበት ወቅት እንዲህ አይነት ንግግር  የምሬታቸው ደረጃ ራሳቸውን እንዳሳታቸው ማሳያ መሰለኝ፡፡

ሽማግሌው በዚህ አላበቁም “በዚያ በቀደምለት ማናቸው አያ! እኒያ ትልቁ ባለሥልጣን የሞቱ ጊዜ ትልልቅ የተባሉት የጦር መሪዎች አስከሬናቸውን ይዘው ወደ መቃብር ሊያውርዷቸው ሲሉ የአገራችን ሰው በሕይወት ሳሉ በቴሌቪዥን እንጅ በአካል አይተዋቸው ስለማያውቁ ቢያንስ ሬሳቸው ያለበትን ሳጥን እንመልከት ብለው ሲጠጉ በፖሊሶች ዱላ እንደ እባብ ራስ ራሳቸውን ተቀጠቀጡ፡፡ በሕይወት ሳሉስ ጠባቂ የተመደበላቸው ለህዝብ ቅን ስለማያስቡ ሰው ይገለኛል ብለው ፈርተው ወይም ሰግተው ሊሆን ይችላል፡፡ ለህዝብ የሚያስቡ ከሆነ ማንን ፈርተው ነው ታዲያ ጠባቂ የሚያቆሙት? እሽ እሱስ ይቅር ከሞቱ በኋላ ሬሳቸውን የሚሰርቅ ሰው አለ እንዴ ያን ያህል በግድ ሃዘን እንዲወጣ የተቀሰቀሰውን ሰው በዱላ የሚቀጠቅጡት? የሞተውን ለመቅበር ያልሞቱትን መግደል ምን አይነት ግፍ ነው? የሞተው እኮ ከዚህ በኋላ አገሪቱን ላይመራ አንዴ የተሰናበተ ነው? ሊቀብሩ የመጡት ግን እድል አላቸው እድሉን ማን ይሰጣቸዋል እንጅ? ታዲያ በቁሙ ባናየው ቢያንስ ከሞተ በኋላ አስከሬኑን እንመልከት ያለውን ህዝብ በዱላ! የሞተውን ማን ይገለዋልና ነው ግን እንዲህ የተደረገው?” አሉ፡፡  እኔ አሁን ዋና መልእክታቸው ገባኝ እውነታቸውን ነው የተናገሩት፡፡ ገንዘብ ሞልቶት ሁሉ ኖሮት የዓለም ቁጥር አንድ ባለሃብት ለመባል ሲል የስንቱን ምስኪን ኪስ ይዳስሳል መሰላችሁ፡፡ ሰው የሚበላው ሞልቶት ሁሉ ተርፎት የዳቦ ሽራፊ የቀረችውን ደሃ ተካፍሎ ሊበላበት ሲጠጋ አይገርምም ትላላችሁ? የድሮ ታሪክን ለማጥፋት ሲባል ስንት የዛሬ ታሪክ ተጨፈለቀ መሰላችሁ? በሽተኛውን ለማዳን ሲሉ ስንቱን ጤነኞች በሽተኞች አደረጉ መሰላችሁ? የምትለውን ሳይሆን የሚሉትን ብቻ እንድትሰማቸው በየቀኑ ስብሰባ የሚጠሩህ ስንት ናቸው? አረ ተውት ስንቱ ስንቱ ስንቱ ጉድ ይነገራል?????? ናርምም አለ ሊቁ ነገሩ ቢረቅበት፡፡

Thursday, June 4, 2015

የማታውቀውን አትንካ

ሊቃውንቱ የሰውን ልጅ በዐራት ወገን ይከፍሉታል፡፡ ማወቁን የሚያውቅ፣ ማውቁን የማያውቅ፣ አለማወቁን የሚያውቅ፣ አለማወቁም የማያውቅ በማለት፡፡ በእነዚህ ዐራት ሰዎች ዙሪያ ጥቂት ነገር እንነጋገር፡፡
ማወቁን የሚያውቅ፡- እንደዚህ ዓይነቱ ሰው አዋቂ፣ ብልህ፣ አስተዋይ፣ ጠቢብ ከመሆኑም ባለፈ አዋቂ፣ ብልህ፣ አስተዋይ፣ ጠቢብ መሆኑን በሚገባ የሚያውቅ ዓይነት ነው፡፡ ይህ ሰው መሥራትን ብቻ ሳይሆን እንዴት እንደሚሰራ፣ ለምን እንደሚሰራ፣ መቼ እንደሚሰራ፣ ለማን እንደሚሰራ በሚገባ ያውቃል፡፡ ሁሉን ከማወቁ የተነሣም ራሱን ዝቅ አድርጎ በትህትና የሚኖር ዓይነት ነው፡፡ የሚገጥመውን ፈተና ለማለፍ ብዙ አይቸገርም፣ የሚመጣበትን መከራ አይሰቀቅም፣ የሚደርስበትን ችግር ሁሉ ከችግር አይቆጥርም ምክንያቱም ማወቁን ስለሚያውቅ፡፡ እውቀቱ ዋጋ እንዳለው ከራሱ የሕይወት ውጣ ውረድ ጋርም እንዴት ማዛመድ እንደሚችል በሚገባ ያውቃል፡፡ አዲስ የስልጣኔ ማዕበል አያናጋውም፤ አዲስ አስተሳሰብ አይነጥቀውም፣ አዲስ ትምህርት አያታልለውም፣ አዲስ አለባበስ አያስደነግጠውም፣ አዲስ ርዕዮተ ዓለም አይደንቀውም፣ አዲስ ነገር አያሳስበውም፣ በሚነፍስበት አይነፍስም፣ ሌላው በሚነዳበት ሁሉ አይነዳም፣ ሌላው ስላደረገ ብቻ አያደርግም ምክንያቱም ማወቁን ስለሚያውቅ፡፡ ከሥራ በፊት ለምን? የሚለውን ይመልሳል፤ ከመስራቱ በፊት ከሥራው ምን እንደሚጠብቅ ውጤቱን ቀድሞ ይተነብያል፡፡ ይህ ዓይነቱን ሰው ብንቀርበው ያስተምረናል፤ መጽሓፋችን ይሆናል፤ ጉድፋችንንም የምንመለከትበት መስታወት ይሆነናል፡፡
ማወቁን የማያውቅ፡- እንደዚህ ዓይነቱ ሰው አዋቂ፣ ብልህ፣ አስተዋይ፣ ጠቢብ ይሁን እንጅ እንደዚህ መሆኑን አያውቅም፡፡ በመሆኑም ከእርሱ ማወቅ ይልቅ የሌሎች እውቀት ይገዛዋል፤ እንሂድ ባሉት መንገድ ሁሉ ይሄዳል፤ በነፈሰበት ሁሉ ይነፍሳል፤ ሌሎች በተጓዙበት ተከትሎ ይጓዛል፤ ሌሎች በፈሰሱበት ይፈስሳል፡፡ ሥራን የመሥራት ችሎታ አለው ነገር ግን ለምን እንደሚሰራ፣ የሥራው ውጤትም ምን ሊሆን እንደሚችል አያውቅም፡፡ እንደዚህ አይነቱን ሰው ብትቀርበው የእውቀቱን ፍሬ ልትመገብ አትችልም ምክንያቱም ማወቁን ስለማያውቅ ለአንተ ለማሳወቅ የሚችልበትን ጥበብ አያውቅም፡፡ ስለዚህ ይህንን ሰው መቅረብ ጊዜን ከማባከን ውጭ ምንም ሊጠቅመን የሚችል አይደለም፡፡ ከእርሱ ለመማር ከምትቀርብ ይልቅ ማወቁን ብትነግረው ይበልጥ ተጠቃሚ ታደርገዋለህ፡፡ ይህ ሰው የሚጎድለው እውቀት ሳይሆን እውቀቱን እንዴት በተግባር መቀየር መቻል ብቻ ነው፡፡ አንተ ከጀመርክለት ፈሩን ካስያዝከው እርሱ በሚደንቅና በሚገርም ጥበብ ይፈጽመዋል፡፡ ስለዚህ በምክር እውቀቱን እንዲጠቀምበት ማድረግ ተገቢ ነው፡፡
አለማወቁን የሚያውቅ፡- እንደዚህ አይነቱ ሰው አዋቂ፣ ብልህ፣ አስተዋይ፣ ጠቢብ አይደለም፡፡ አዋቂ፣ ብልህ፣ አስተዋይ፣ ጠቢብ አለመሆኑን በሚገባ የተረዳ ነው፡፡ ሥራ መሥራት ይፈልጋል ነገር ግን እንደማያውቅ ስለሚያውቅ አይሰራም፡፡ ምክንያቱም ቢሰራም የስራው ውጤት ጥሩ እንደማይሆን በሚገባ የሚያውቅ ነው፡፡ ይህ ሰው ስራ ከመስራቱ በፊት ሌሎችን ያማክራል ምክንያቱም አለማወቁን ስለሚያውቅ፡፡ ይህ ሰው ተመራማሪ ነው እንደመጀመሪያው ያለ ሰው ነው ልዩነቱ እውቀት ብቻ ነው፡፡ ሌሎች በነፈሱበት አይነፍስም፣ ሌሎች በተጓዙበት አይጓዝም ምክያቱም አለማወቁን ስለሚያውቅ ከብዙ ሰዎች ጋር መመካከርን ይመርጣል፡፡ የተቀበለውን በርካታ ምክር አመዛዝኖ የራሱን ውሳኔ መስጠት የሚችልበት ችሎታ አለው፡፡ ይህ ሰው ለሌሎች መትረፍ የሚችል እውቀት አይኑረው እንጅ ራሱን የሚጥል አይነት አይደለም፡፡ ምክንያቱም አለማወቁን ስለሚያውቅ አለማወቁን ተጠቅመው ሊጥሉት የሚመጡትን ሁሉ ከሌሎች ጋር በመመካከር ይፈታልና፡፡ ይህ ሰው ሌሎችን ሳያማክር የሚነካው ነገር አይኖርም፡፡ ይህ ሰው ቅንነት፣ ትህትና አለው ስለዚህ በማስተማር አዋቂ ማድረግ የሚቻል ነው፡፡
አለማወቁን የማያውቅ፡-እንደዚህ አይነቱ ሰው አዋቂ፣ ብልህ፣ አስተዋይ፣ ጠቢብ አይደለም፡፡ አዋቂ፣ ብልህ፣ አስተዋይ፣ ጠቢብ አለመሆኑንም አያውቅም፡፡ ይህ ሰው ለራሱም ሆነ ለሌላ ሰው በሚተርፍ ችግር ውስጥ የሚገባ ነው፡፡ ያየውን ሁሉ ማድረግ ይፈልጋል ነገር ግን ካደረገው በኋላ ሊመጣ የሚችለውን ጉዳት አያውቅም፡፡ ሰው ሲሮጥ ካየ ይሮጣል ለምን እንደሚሮጥ ግን አያውቅም፤ ሰው ሲዘል ካየ ይዘላል ለምን እንደሚዘል ግን አያውቅም፤ ሰው ሲሄድ ካየ ይሔዳል የት ሊደርስ እንደሚችል ግን አያውቅም፡፡ እንደዚህ አይነቱ ሰው ድክመቱን በምላሱ መሸፈን ይፈልጋል፤ እንደዚህ አይነቱ ሰው ግብዝነቱ ይጎላል፤ እንደዚህ አይነቱ ሰው ለሌሎች መሰናክል የሚሆን ነው፡፡ ይህንን ሰው ብትከተሉት መጨረሻቹህ ገደል መግባት ነው፡፡ ምክንያቱም ገደሉንም ሆነ ገደሉን እንዴት ማለፍ እንደሚቻል የሚያውቅ ስላልሆነ፡፡ ስለዚህ አትከተለው፡፡
አሁን አሁን በ FACEBOOK አጠቃቀም ላይ የአንዳንድ ሰዎች ሥራ የዚህ የሁለተኛው ሰው አይነት ነው፡፡ ታግ (TAG) ማድረግ ያውቃሉ ምን ታግ እንዳደረጉ፣ በማን ታግ እንዳደረጉ፣ ለምን ታግ እንዳደረጉ፣ መቼ ታግ እንዳደረጉ ግን አያውቁም፡፡ ሼር (SHARE) ማድረግ ይችላሉ (ያውቃሉ) ነገር ግን ምን፣ ለማን፣ መቼ፣ እንዴት ሼር እንዳደረጉ ግን አያውቁም፡፡ ለዚህ ነው የዝሙት ፎቶዎችን እና ቪዲዮዎችን በሌሎች PROFILE ላይ ሲፈልጉ ሼር ሲፈልጉ ደግሞ ታግ የሚያደርጉት፡፡ ሼር እና ታግ ማድረግ ብቻውን ማዎቅ አይደለም፤ ምክንያቱም ለማን ሼር ማድረግ እንዳለብን፣ ለማን ምን ሼር ማድረግ እንዳለብን፣ ለምን ሼር ማድረግ እንዳስፈለገም ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ የግድ ሼር ማድረግ አለብኝ ያለ ሰው ግን አዋቂ የሚባለው ለራሱ ብቻ ሼር ማድረግ ከቻለ ነው፡፡ ከዚያ ውጭ ግን ማወቁን የማያውቅ ሰው ነው እንዲህ አይነቱን ተግባር የሚፈጽመው፡፡ በዚሁ አጋጣሚ ግን በእኔ PRIFILE ላይ ሼር የሚደረጉ የዝሙት ፎቶዎችና ቪዲዮዎች የእኔ እንዳልሆኑ እያሳወቅሁ ሼር የተደረጉብኝን ነገሮች ግን ወዲያውኑ የማጠፋቸው መሆኑን እገልጻለሁ፡፡ እንዲህ አይነት ተግባር ላይ የተሰማራችሁ ግለሰቦች ግን ከዚህ ተግባራችሁ ተቆጠቡ፡፡ በብዛት ሼር ያደረጋችሁብኝ ልጆች ለምን እንዳደረጋችሁ፣ መቼ እንዳደረጋችሁ፣ ለማን እንዳደረጋችሁ እንዳደረጋችሁ ራሱ የማታውቁ እንደሆነ በግል ተረድቼያለሁ፡፡ ስለዚህም የመጨረሻ መልእክቴ “የማታውቀውን አትነካካ” የሚል ነው፡፡


Wednesday, June 3, 2015

ይከራያል

በትንሽ ከተማ በኪራይ ቤት የሚኖር አንድ ሰው ነበር፡፡ ይህ ሰው የተከራየው ትልቅ መኖሪያ ቤት ነው፡፡ በዚህ ቤት ባለቤቱን፣ ልጆቹን፣ ከብቶቹን ይዞ ነበር የሚኖረው፡፡ ሰው ግን እጅግ አብዝቶ ያስመርረዋል፡፡ ሰውየው ማንበብና መጻፍ አይችልም፡፡ ማንበብ እና መጻፍ አለመቻሉ ነው ለዚህ ሁሉ ስቃይ የዳረገው፡፡ ኪራይ የሚፈልግ ሰው ሁሉ የተከራየውን ቤት እያንኳኳ “ስንት ነው የሚከራየው” ይለዋል፡፡ ሰውየው ይህንን ጥያቄ እጅግ በጣም ሰልችቶታል፡፡ ነጋ ጠባ ሰው ሁሉ እያንኳኳ “ስንት ነው ኪራዩ” ይለዋል፡፡ እርሱም በጣም ሰለቸና አንድ ቀን “እንዴ ሰው ሁሉ ምን ነካው? እኔ  ተከራይቼ እያያችሁ እንዴት አይነት ጥያቄ ነው የምትጠይቁኝ? ቤቱ እኮ የእኔ አይደለም የተከራየሁት እንጅ፡፡ ቆዩ ግን ለምንድን ነው እንዲህ በላየ ላይ ኪራይ ምናምን የምትሉት? ሰው እንደው ትንሽ ይሉኝታ የሚባል ነገር የለውም ልበል ሆ ወይ ጉድ ነገር፡፡ ግሩም እኮ ነው የእናንተ ደግሞ! እሽ ግን ይከራያል ብላችሁ ልትደረቡብኝ ነው እንዴ?” አለ በቁጣ ገንፍሎ፡፡ ሰውየው ቤቱን ሲከራይ አብሮ የተከራየውን ጽሑፍ አላወቀም፡፡ አላፊ አግዳሚው ግን ያንን ጽሑፍ እየተመለከተ ነበር “ኪራይ ስንት ነው?” የሚለው፡፡ከቤት በር ላይ የቤቱ ባለቤት ቤቱ ከመከራየቱ በፊት “ይከራያል” ብሎ በቆርቆሮ ቀለም በጉልህ ጽፎበት ነበር፡፡ ሰውየው ይህንን ቤት ሲከራይ ይህንን ጽሑፍ አላነበበውም ምክንያቱም ማንበብ ስለማይችል፤ የቤቱ ባለቤትም ቤቱ ከተከራየ በኋላ የተጻፈውን አላጠፋውም፡፡ ለዚህ ነው ሰው ሁሉ ቤቱን እያንኳኳ “ስንት ነው ኪራይ” በማለት ሰውየውን ልቡን ያወለቀው፡፡ ቤቱን ከነጽሑፉ ስለተከራየው ይህ ሰው በጣም ተቸገረ፡፡

ዛሬ ዛሬ ከዚህ ሰው በከፋ ችግር ውስጥ ያለን በርካታ ሰዎች አለን፡፡ ከግለሰብ እስከ ቡድን፣ ከነጠላ እስከ  ማኅበራት፣ከተማሪ እሰከ አስተማሪ፣  ከቀበሌ እስከ ፌዴራል፣ ከክልል እስከ አገር ድረስ ሳናውቅ በምንከራያቸው ነገሮች በጣም ስቃይ ጸንቶብናል፡፡ አንድ ሰው ባለማዎቅ ከልብሱ ጋር በሚገዛው ጽሑፍ ይሸማቀቃል፡፡ አንዲት እርጉዝ ሴት “I AM VIRGIN” የሚል ልብስ ለብሳ ስትሄድ ሰው ቢስቅባት ሳቁን ከማስተናገድ ውጭ የለበሰችው ልብስ ላይ የተጻፈውን ነገር አትረዳውም፡፡ አንዱ ደግሞ ያገኘው ሰው ሁሉ ባገኘው ነገር ይመታዋል፡፡ ለምን እንደሚመቱት ግን አያውቅም፡፡ ለካስ “KICK ME” የሚል ጽሑፍ ከልብሱ ላይ ተጽፏል፡፡ ሳናውቅ በምንሰራቸው ሥራ፤ ሳንረዳ በምንገለብጠው ነገር ሁሉ ተጠቂዎች ራሳችን ነን፡፡ ቆዩ እንጅ ግን የማናውቀውን የምንሠራ እና የምንገለብጥ እኛ ኢትዮጵያውያን ብቻ ነን እንዴ? ሰው የማያውቀውን እያደረገ በመከራ ይኖራል፤ መንግሥት የማያውቀውን ሕግ እየገለበጠ አገዛዝ ያከፋብናል፡፡ ተማሪው መልስ መሆን አለመሆኑን ሳይረዳ ከጓደኛው ይኮርጃል (ይሰርቃል)፤ አረ አንዳንዱስ ከነ ስሙም የሚኮርጅ አለ አሉ፡፡ የማናውቀውን ስንሠራ ትንሽ ኃፍረት የማይሰማን ግን ለምንድን ነው? አገርን ያህል ነገር በተቀዳ ፖሊሲ፣ በተኮረጀ እቅድ፣ ይጥቀም አይጥቀም በማይታወቅ አስተሳሰብ ስናስተዳድር ትንሽ አይሰቀጥጠንም፡፡ አይጥና ዝንጀሮ ለላብራቶሪ ምርመራ እንደሚጠቀሙባቸው ሁሉ እኛን ኢትዮጵያውያንንም የፖሊሲ፣ የስታራቴጅ፣ የአመለካከት፣ የአስተሳሰብ መፈተኛ ቤተሙከራዎች ያደረጉን በርካቶች ናቸው፡፡ ለማንኛውም ቢያንስ በራሳችን መፍታት የምንችላቸውን ቀላል ነገሮች መፍታት የተሻለ ስለሆነ ሥራን ከመስራታችን በፊት ጥቅሙን፣ ለምን እንደምንሰራው፣ መቼ እንደምንሠራው፣ እንዴት እንደምንሠራው ማወቅ ያስፈልጋል፡፡