Thursday, October 30, 2014

‹‹ስትሆን አለመሆን››

ሰላም ለሁላችሁ ይሁን፡፡ አንድ ጓደኛዬ ያጫወተኝን ጨዋታ ላካፍላችሁ ሳስብ ርእሱን ምን እንደምለው በጣም ብዙ ጊዜያትን ወስጄ ነበር፡፡ አሁን ከብዙ ድካም በኋላ ከላይ ያለውን ርእስ ሰጠሁት ፡፡ ርእሱ ምን ያህል ደረጃ እንዳለው ባላውቅም ‹‹ስትሆን አለመሆን›› በሚል ሰይሜዋለሁ፡፡ ወሬ አበዛሁባችሁ መሰለኝ… “አዎ አብዝተሃል” ይለኝ ነበር አንድ ወጣት እንዲህ የሚል ነገር ሳነሣበት፡፡ ነገር ስዘበዝብበት አይወድም ወይ ጉዴ በነገር ላይ ሌላ ነገር ደረብኩባችሁ በእርግጥ ርእሱም ‹‹ስትሆን አለመሆን›› ስለሚል መድረኩ ሲመቻችልኝ እንደ መድረኩ ሆኜ አልተገኘሁም፡፡ ነገሩ ከጓደኛዬ የተገኘ ነው፡፡ ጓደኛዬ በስእለት ይሁን በሹመት በወሬም ይሁን በሆነ አጋጣሚ ብቻ ‹‹ስልጣን›› ነገር አለችው፡፡ ብዙ ጊዜውን የሚያሳልፈው ተሸከርካሪ ወንበር ላይ ነው፡፡ ስልኩም አይቆጥርበትም መሰል የቢሮው ስልክ እንደ ሴቶች የጆሮ ጌጥ ከጆሮው ላይ ተጣብቆ ይውላል፡፡ ባለጉዳይ የሚያስተናግደው መስማት እንደተሣናቸው ወገኖቻችን በምልክት ብቻ ነው፡፡ አንድ ባለጉዳይ ባለፈው ትዝ አለኝ “ስልኩን ይጨርሳል ብዬ ወንበር ላይ ተቀምጬ ብጠብቀው! ብጠብቀው! አንዱን ሲጨርስ ሌላውን ሌላ ሲጨርስ ደግሞ ሌላውን እያለ እኔም ሲመሽብኝ ተስፋ ቆርጬ ከቢሮ ወጣሁና ጉዳዬን ስልክ ደውዬ አናገርኩት” ሲለኝ እንባ እስኪወጣኝ ድረስ ነው የሳቅሁት፡፡ በእርግጥ ጓደኛዬ ነው… ቢሆንም ግን በሰው ልጅ ላይ የሚፈጸም ታሪክ በመሆኑ ብዙም አልገረመኝም፡፡ እንዲህ አይነት ነገር በጣም ያበሳጨው የነበረ ሰው ሲበሳጭበት በነበረው ነገር ውስጥ ሲገባ በጣም ያሳዝናል፡፡ አንድ ቀን የዓመት ፈቃዱን ሊጠይቅ ወደ ቢሮ ጎራ ይላል፡፡ ከቢሮ ሲገባ ጉዳይ ያለው ሰው አልነበረም፡፡ ጉሮሮውን ሞረደና “የዓመት ፈቃድ ፈልጌ ነበር” አላቸው፡፡ አንዲት የማይመለከታት ሰራተኛ “አንተ ደግሞ ሰራተኛ ሆነህ ሞተህ የዓመት ፈቃድ ትጠይቃለህ?” አለችው፡፡ “ምን ለማለት ፈልገሽ ነው? እኔ ሠራተኛ አይደለሁም ማለት ነው? የምትሰሪልኝ ከሆነ በሥርዓት አስተናግጅኝ” በማለት ጮኸባት፡፡ ከዚያ ዚያ እየተንጎራደደች “በእርግጥ የዓመት ፈቃድ የምጽፍ እኔ አይደለሁም፡፡ እርሱ እስኪመጣ መጠበቅ ከፈለግህ ተቀምጠህ ጠብቀው አለችው፡፡” እርሱም በጣም ተናድዶ ወንበሩን ሳበና ተቀመጠ፡፡ ቢጠብቀው ቢጠብቀው በፍጹም ሊመጣለት አልቻለም፡፡ ልክ 11፡20 ሲሆን በጣም ተበሳጨና “ስልኩን ስጡኝ” አላቸው፡፡ አንዲት ስልኩን ሰጠችው ስልክ ሞከረለት፡፡ ስልኩ “ጥሪ አይቀበልም” ይላል፡፡ ከቅድሙ የባሰ አሁን ቅጥል እስኪል ድረስ ተናደደ፡፡ የቢሮውን በር በርግዶት ወጣ፡፡ ፊቱ በርበሬ መስሏል፤ ግንባሩ ተቋጥሯል፡፡ “ምን ሆነህ ነው?” አልኩት፡፡ “እባክህ የቢሯቸው ቢሮክራሲ በጣም ያናድዳል፡፡ እነዚህ ሰዎች ግን ድንጋዮች ናቸው ወይስ አስተናጋጅ ናቸው፡፡ የሰውን ጉዳይ ከምንም አይቆጥሩም እኮ፡፡ ይገርምሃል አንዲት ሰራተኛ ተብዬ በማያገባት ነገር ገብታ አንተ ደግሞ ሰራተኛ ሆነህ ሞተህ የዓመት ፈቃድ ስትል አታፍርም አለችኝ እኮ! ይች ደደብ ባልሠራላት እኔ አይደለሁም” አለኝ፡፡ “አይዞህ!!! ግን የሰውን ልጅ ያህል ፍጡር ደደብ ብለህ በመሳደብህ ቅር ብሎኛል፡፡ በእርግጥ የሰው ልጅ ወደኋላ ዞር ብሎ ያለፈ ተጋሪኩን ስለማያስታውስ ያናድድ ይሆናል፡፡ ግን ምንም ማድረግ አይቻልም ዘመኑ ነው እያልክ መቀመጥ ነው” አልኩት፡፡ “እንዴ ተው እንጅ ምን ዓይነት ጅልነት ነው የምታወራው? ዘመኑ ነው እያልክ እስከመቼ ድረስ ዝም ብለህ ትቀመጣለህ? እንደዚህ ዓይነቱን ሰው እኮ መንጥረን ማውጣት አለብን፡፡ ዘመኑ ድሮም ዘመን ነበር አሁንም ዘመን ነው እኛ ሰዎች ግን በየጊዜው እንደ እስስት እንለዋወጣለን፡፡ ብቻ ተወው የእኛ ጉድ እንዲህ በቀላሉ የሚነገር አይደለም” ብሎ በረዥሙ ተነፈሰ፡፡ “ይህ እኮ የሚያናድድ ነገር አይደለም፡፡ የሰው ልጅ እኮ ማግኘት የተመኘውን ነገር ሲያገኝ እንደ ድሮው አይሆንም አንተም ነገ ይህን ወንበር ብታገኘው ብትብስ እንጅ አትሻልም አልኩት፡፡ ድሮ ላይ የነገርኩት ነገር ዛሬ ላይ ሲፈጸም እኔ እንደ ነቢይ ትንቢት ተናጋሪ ሆኜ ራሴን አገኘሁት፡፡ ያ ድሮ ላይ ሲለው የነበረውን ነገር ዛሬ ራሱ ላይ ሲደገም በጣም ገረመኝ፡፡ ሰዎች ስለእርሱ ብዙ ነገር ሲሉኝ አንድ ቀን ስልክ ደወልኩለትና ተቀጣጠርን፡፡ በቀጠሯችን ተገናኘንና ከነገር ነገር ያን የድሯችንን ነገር ስናነሣ ስንጥል ብዙ ሰዓታትን አሳለፍን፡፡ እየተሳሳቅን “አንተስ ያው ሆነሃል አላሉ” አልኩት፡፡ “ተወው እባክህ?” አለኝ፡፡ “ግን ለምንድን ነው የሰው ልጅ ድሮ ሲበሳጭበት በነበረው ነገር ውስጥ ራሱ የሚወድቅ? አልኩት፡፡ እርሱም ብዙ ሳያስብ በሳቅ ፍርስ የሚያደርገውን ንግግር ነገረኛ!፡፡ “ምን መሰለህ የሰው ልጅ ድሮ በተጎዳበት ነገር ይጎዳበታል እንጅ አይጠቅምበትም፤ ሰው ድሮ በተበሳጨበት ነገር ያበሳጭበታል እንጅ አያስደስትበትም፤ ሰው ድሮ በታሰረበት ነገር ያስርበታል እንጅ አይፈታበትም፡፡ ድሮ ላይ እኔ እበሳጭ የነበረው እኮ እነርሱ ቦታ ላይ እኔ ስላልሆንኩ ነው፡፡ ዛሬ ግን እኔ በእነርሱ ቦታ ላይ ስላለው በራሴ ስለማልበሳጭ ሌሎች በእኔ መበሳጨት አለመበሳጨታቸው አይገባኝም፡፡ እኔ ጥሩ የሰራሁ እንጅ መጥፎ ነገር ያደረግሁ አይመስለኝም፡፡ ጠቅለል ሲል ‹‹ስትሆን አትሆንም›› ማለቴ ለመሆን የተመኘኸውን ነገር ስትሆን ድሮ እንደተመኘኸው አትሆንም፡፡ በእጅ የያዙት ወርቅ ከመዳብ ይቆጠራል ይሉ የለም፡፡ ተማሪ ሆነህ ሰራተኞችን ስታይ እንደእነርሱ መሆንን ትሻለህ፡፡ ነገር ግን አንተ ያንን የተመኘኸውን ስትሆን አትሰራበትም፡፡ ስንቱ ሰዎችን ሲኮንን በነበረበት ሃሳብ ገብቶ አይደል እንዴ ራሱ የሚሠራው፡፡ ሙስና የሚፈጽም ሰራተኛ ያየ ሰው ለምን ሙስና ይፈጽማል ብሎ ይደነፋል፡፡ ነገ በዚያ ሰው ቦታ ሲቀመጥ ግን የበለጠ ሙስና ሰሪ ራሱ ይሆናል፡፡ መሆን እና መናገር እኮ የሰማይ እና የምድርን ያህል ይራራቃሉ፡፡ ሰው የተባለ ፍጡር በአጠቃላይ “ሲሆን አይሆንም” --› ታማኝ አይሆንም ማለቴ ነው፡፡ የሚፈልገውን ነገር ሲያገኝ እንደሞፈልገው ሆኖ አይገኝም” አለኝ፡፡ እኔም በጣም ገረመኝና በሳቅ ተለያየን፡፡

Tuesday, October 7, 2014

ንቁም በበሕላዌነ / በያለንበት ጸንተን እንቁም/

ማተባችን መለያ ማኅተማችን ነው፡፡
በሥነ ፍጥረት ታሪክ ላይ የመጀመሪያዎቹ ፍጥረታት ላይ ማለትም በመላእክት ዘንድ የተፈጠረ ሽብር ነበር፡፡ የሽብሩ ቀስቃሽ የዚያን ጊዜ አኃዜ መንጦላእት የነበረው በክብር ስሙ ሳጥናኤል በውርደት ስሙ ደግሞ ዲያብሎስ ነበር፡፡ ዲያብሎስ ቀና ቢል ከእርሱ የበለጠ ፍጡር አጣ ፈጣሪም ተሰውሮበታልና ባለማስተዋል ዝቅ ብሎ ሲመለከት እልፍ አእላፋት መላእክትን ተመለከተ፡፡ ያን ጊዜ “አነ ፈጣሪሆሙ ለእሉ ፍጡራን” ብሎ አረፈው፡፡ ምን ማለት ነው “እነዚህን ሁሉ የፈጠርኳቸው እኔ ነኝ” አለ፡፡ ልብ በሉ ወገኖቼ በማእረግ ከሌሎች መብለጥ ወይም ከሌላው በስልጣን ከፍ ብሎ መገኘት ማለት መፍጠር ማለት አይደለም፡፡ ምናልባት ከአንተ በላይ ሌላ የሚበልጥህ ነገር ላይኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን ከአንተ በታች ያለውን ሁሉ የፈጠርከው አንተ አይደለህም፡፡ የሳጥናኤል ጉዳይ ግን ይህ ነበር፡፡ ከእርሱ በታች እልፍ አእላፋት መላእክት ስለተረበረቡ የእነዚያ ሁሉ ፈጣሪ እርሱ እንደሆነ አሰበ አስቦም ተናገረ ተናግሮም አሸበረ፡፡ በዚህ ሽብር መካከል እርሱን ተከትልው የሄዱ ነበሩ፡፡ ነገር ግን እርሱን የተጠራጠሩም ነበሩ፡፡ እርሱን መጠራጠር ብቻም አይደለም አምላክ አይደለም ብለው ያመኑ መላእክት ነበሩ፡፡ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል “ንቁም በበሕላዌነ / በያለንበት ጸንተን እንቁም/” በማለት መላእክትን አጽናናቸው፡፡ ሽብሩን ዲያብሎስ ቢፈጥረውም ቅሉ በቅዱስ ገብርኤል ከሽፎበታል ምንም እንኳ የተወሰኑ ተከታዮችን ይዞ ቢጠፋም፡፡ ወገኖቼ ከመቸውም በላይ በቅዱስ ገብርኤል ቃል የምንጽናናበት ዘመን ዛሬ ነው፡፡ ማንም ምንም ሊል ይችላል፡፡ ከእኔ በላይ ማንም የለም ብሎ የሚያስብ ሰው በርካታ ነገሮችን ሊናገርና ሽብርና ሁከትን ሊፈጥር ይችል ይሆናል፡፡ ነገር ግን ለሁሉም ጊዜ አለውና ቅዱስ ገብርኤል በያላችሁበት ጸንታችሁ ቁሙ ማንም አያስፈራችሁ የሚልበትን ሰዓት መጠበቅ አለብን፡፡ አንድ ፈራሽ በስባሽ ሰው ማተብህን አታስርም ስላለኝ ማተቤን አልበጥሰውም ይህን በሚገባ አውቀዋለሁ፡፡ ከእርሱ በላይ ሌላ አካል የሌለ የሚመስለው አእምሮ ቢስ ሁሉንም በእርሱ ቁጥጥር ሥር ማኖር ይፈልጋል፡፡ ነገር ግን ከእርሱ የበለጠ አካል ፈጣሪያችን የተሰቀለበትን መስቀል እናስረዋለን፡፡ በዚህም ብዙ ዘመናትን አሳልፈናል ወደፊትም እንዲሁ እናደርጋለን፡፡ የትምህርት ተቋማት ከዚህ ነጻ ናቸው ካሉንም ትምህርቱ እና ሥራው ይቀራል እንጅ ማተቡ መታሰሩ አይቀርም ፡፡ ማተብ ሌላ ጉዳይ ነው ትምህርት ደግሞ ሌላ ነው፡፡ ምንም ሊገናኙ የሚችሉ ጉዳዮች አይደሉም፡፡ ወገኖቼ ማንም ምንም ነገር ስለተናገረ ብቻ አትሸበሩ፡፡ ይህ ሽብር የተጀመረው በመላእክት ዘንድ ነው፡፡ አሁን ደግሞ በእኛ መካከል ተፈጠረ ይሁን እንጅ በያለንበት ጸንተን ልንቆም ያስፈልገናል፡፡ በያሉበት ጸንተው የቆሙት ፈጣሪያቸውን አግኝተውታል፡፡ እኛም እንዲሁ ጸንተን እንቆይ ፈጣሪያችንን እናገኘዋለን፡፡ አትጠራጠሩ ይህን ሃሳባ ያመጣው ሰው እንጦሮጦስ ይወርዳል ምክንያቱም ሃሳቡ ዲያብሎሳዊ ስለሆነ፡፡ በእርግጥ ዘመኑ ዘመናቸው ጊዜው ጊዜያቸው ነው ነገ ደግሞ የሌላ ዘመንና ጊዜ ነው፡፡ ስለዚህ ጸንተን እንቆይ፡፡ አንድ ተራ ሰው በተናገረው ተራ ወሬ ቦታ ሰጥታችሁ አትሸበሩ፡፡