Wednesday, October 21, 2015

የእግር ስንፍና

ሰነፍ እግር የሚገሰግሰው ለኃጢአት ሥራ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሂድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ የሚለውን የዳዊት መዝሙር አይወድም፡፡/መዝ121÷1/ ሰነፍ እግር በክፉዎችና በኃጢአተኞች ምክር ይጓዛል፤ የበደልንም ጫማ ይጫማል፡፡ የሚገሰግሰውም ወደ ሰዶምና ገሞራ ከተማ ነው፡፡ ለክርክር እና ለሙግት ይቸኩላል፡፡ እግዚአብሔር ከሚጠላቸው ስድስት ነገሮች መካካል አንዱ ወደ ክፉ የሚሮጥን እግር ነው፡፡/ምሳ6÷18/ ሰነፍ እግር የሚረግጠውን አያስተውልም፤ የት ለመድረስ እንደሚፈጥንም አያውቅም፡፡ሰነፍ እግር ቀራንዮ ድረስ የሚሄደው በክርስቶስ ምራቁን ሊተፋ አልያም ሊሳለቅ ነው፤ በመስቀሉ አጠገብም የሚቆመው በልብሱ ዕጣ ለመጣጣል ነው፡፡ ሰነፍ እግር እንደ ቃየን እግር የሚቅበዘበዝ ይሆናል፡፡ በባዶ ሜዳ በድንጋጤ የሚሮጥ መድረሻውን የማያውቅ ተንከራታች ይሆናል፡፡ ሰነፍ እግር ለጸሎት መቆምን አብዝቶ ይጠላል፡፡ ሰነፍ እግር ከምጽዋት ይልቅ ስርቆት፣ ከስግደት ይልቅ ክፋት፣ ከጸሎት ይልቅ ትዕቢት፣ ለነፍሴ ከማለት ይልቅ ለኪሴ፣ ንስሓ ከመግባት ይልቅ ኃጢአት መሥራት፣ ከልጅነት ይልቅ ባርነት፣ ከሕይወት ይልቅ ሞት ይመርጣል፡፡ የሚጓዘውም በኃጢአተኞች መንገድ ነው፡፡ የሚሮጠውም ከነዓን ለመግባት ሳይሆን በእስራኤላውያን ላይ አደጋ ለመጣል ነው፡፡ የእስራኤላውያን እግር ባሕረ ኤርትራን በደረቅ ሲሻገረው እርሱ ግን በኤርትራ ባሕር ውስጥ ይሰጥማል፡፡ ሰነፍ እግር ናቡከደነጾር ላቆመው ምስል ይንበረከካል፤ ጥበበኛ እግር ግን ሠለስቱ ደቂቅን ይከተላል፡፡ ሰነፍ እግር በጦርነት መካከል ይቆማል፤ ብልህ እግር ግን ሰላምን ይፈልጋል፡፡ ሰነፍ እግር ድንግል ማርያምን የሚከተላት በግብጽ በረሓ ለማሳደድ ነው፡፡ ሰነፍ እግር እስጢፋኖስ ሲወገር ድንጋይ ያመላልሳል፤ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሲፈጭ ደብረ ይድራስ ሊበትነው ይቸኩላል፡፡ ወንድሜ አንተ ግን እግርህን ጠብቅ፤ ስንፍና በእግርህ ዘንድ እንዳይመጣ ነቅተህ ጠብቅ፡፡ የጽድቅን ጫማ እንዲጫማ ወደ ጽድቅ ገበያ ውሰደው፡፡ ጉዞው እንደ ዮሐንስ ያለ ጉዞ እስከ ቀራንዮ ተራራ ድረስ የሚጸና ይሆን ዘንድ አበርታው፡፡ እንደ ማርያም መግደላዊት እሾኹን እንቅፋቱን ሌሊቱን የሮማን ወታደር ሳይፈራ የጌታን መቃብር የሚመለከት አድርገው፡፡ ትንሣኤውን ለዓለም ሁሉ የሚያበሥር እግር እንዲሆን ምከረው፡፡ የሐዋርያትን እግር እንዲከተል አሰልጥነው፡፡ እስከ ዓለም ዳርቻ ድረስ ወንጌልን ለመስበክ የሚዞር ጠንካራ እግር ይሆንልህ ዘንድ ምከረው፡፡ መጥፎ ነገር ለማርዳት ሳይሆን ጥሩውን ነገር ለማብሠር አፍጥነው፡፡ እግርህ የምሥራች የሚናገር ያማረ እንዲሆን ጸሎትህ አይቋረጥ፡፡ እንደ አረጋዊው ዮሴፍ ልጅ ሰውን ለማስደንገጥ አይፍጠን፡፡ ወደ ግብጽ በተሰደደች ጊዜ ይህ ወልደ ዮሴፍ እየሮጠ ደረሰባቸውና እዚህ ተቀምጣችኋልን የሔሮድስ ወታደሮች መጥተዋልና ተነሡ ባላቸው ጊዜ እመቤታችን እጅግ ደነገጠች ዕንባዋንም አፈሰሰች፡፡ ይህን ያህል በረሀ የተንከራተትሁ ከሞት ላላተርፍህ ነውን ብላ አለቀሰች፡፡ ሕጻኑ ኢየሱስ ክርስቶስም አመጣጥህ መልካም ነበር ነገር ግን እናቴን አስደንግጠሃታልና በፍርድ ቀን አስነሥቼ እስክፈርድብህ ድረስ ድንጋይ ተንተርሰህ ተኛ አለው በዚያው ድንጋይ ሆኖ ቀረ፡፡ ይህ እግር አስደንጋጭ እግር ነው በመሆኑም ተገቢውን ቅጣት አገኘ፡፡ አንተ ግን ከእንደዚህ አይነቱ እግር የተለየ እግር ሊኖርህ ይገባል፡፡

© በመልካሙ በየነ
ጥቅምት 10/2008 ዓ.ም

ደብረማረቆስ፣ ኢትዮጵያ

Wednesday, October 14, 2015

ስሞት እንዳትቀብሩኝ

“… ሰው ነኝ! አዎ ሰው ነኝ! ሰውስ ብላችሁ ሰው መሰልኳችሁ! ዓለምን የዞርኩ፣ ዓለምን ያጣጣምኩ፣ ሁሉን የቀመስኩ፣ ሁሉ ያልቀረኝ፣ ሁሉን የሠራሁ፣ በነፈሰበት የነፈስኩ፣ በወረደበት የወረድኩ፣ በዘነበበት የዘነብኩ፣ በበረሩበት የበረርኩ ሁሉን የሆንኩ ሰው ነኝ፡፡ ያኔ ገና “ሀ” ብዬ ራሴን ለማይገባ ሱስ እጄን ሳነሣ ተው ባይ አጣሁ፤ እኔም በዛው ገፋሁበትና በጫት የጀመርኩት ሱስ በሲጋራ፣ በሲሻ እና በመጠጥ አጎለመስኩት፡፡ በፊት በፊት የሰፈር ጓደኞቼ የነበሩት ትምህርት ቤት የመማር ዕድል ሲያገኙ እኔ ግን ወላጆቼ ማስተማር ስላልቻሉ ነበር ወደ ጎዳና የወጣሁት፡፡ በእርግጥ ጎዳና መውጣቴ ለሱስ ዳረገኝ የሚል ጸጸት የለብኝም ምክንያቱም ትልልቅ የሚባሉት አገራችን በብዙ ዋጋ ውጭ አገር ድረስ ልካ ያስተማረቻቸው የአገር መከታና አለኝታ ይሆናሉ የተባሉ “ምሁራን” ሳይቀሩ የሱስ ተጠቂዎች ናቸው፡፡ የዩኒቨርሲቲ ምሁራን፣ የአገራችን ትልልቅ ዲፕሎማቶች እንዲሁም የሚኒሰትር መስሪያ ቤት ተጠሪዎች ሁሉ ሱስ አጥቅቷቸው እንደኔ ሆነው ሳያቸው እጽናናለሁ፡፡ ሲጋራው ጫቱ ሁሉም አይቀራቸውም እኔ የጎዳና ተዳዳሪው እና እነርሱ አንድ እኩል የሚያደርገን ነገር ሱስ ብቻ ነው፡፡
ዛሬ እነዚያ የሰፈሬ ልጆች ትልልቅ ሰዎች ሆነው ትልልቅ ከሚባሉ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ ናቸው፡፡ እኔ ደግሞ በሱስ ብዙ ዘመናትን ያሳለፍኩ ከንቱ ሰው እንደሆንኩ አስባለሁ፡፡ ይህ ከንቱነቴ ይበልጥ የሚያስለቅሰኝ የእኔ እኩዮች የሰፈሬ ልጆች ሲያገኙኝ ሰላም ለማለት ተጠይፈውኝ እንደማያውቁኝ ሲያልፉኝ ነው፡፡ በጣም አለቅሳለሁ በጣምም አነባለሁ እጅግም አዝናለሁ እንዴት የሰፈሬ ልጆች ይጠየፉኛል? ቢያንስ አብረን አፈር ፈጭተን ጭቃ አቡክተን አኩኩሎሽ ተጫውተን ያደግነውን እንዴት ይዘነጉታል? ወይስ የእኔ በሱስ መውደቅ የእነርሱን ክብር የሚነካ መስሎ ታይቷቸው ይሆን? ይህን ሳመላልስ ኅሊናዬ በጣም ይደማል እጅግ አዝናለሁ፡፡ ለነገሩ ልክ ናቸው እንደእኔ ያለ ከንቱ እንደነርሱ ላለ ትልቅ ሰው ጓደኛ መሆን ክብራቸውን የሚነካ ሊሆን ይችል ይሆናል፡፡
እኔ ከዚያ ሱስ መውጣት አልቻልኩም በእርግጥ እንድወጣም የሚመክረኝ ሰው የለኝም፡፡ በጣም የምበሳጨውም በዚህ ነው፡፡ ሰው ሕይወቴን ለመቀየር ባይጥር ምክር መለገስ ምን ይከብደዋል? ምን ወጭ ያስወጣዋል? እኔ በኃጢአት ባሕር እንደምዋኝ በኃጢአት ማዕበል እንደምናጥ አውቀዋለሁ፡፡ ዛሬ ከአንዷ ነገ ደግሞ ከሌላኛዋ ጋር፤ ብቻ ካገኘዋት ጋር ሁሉ አንሶላ ተጋፍፌያለሁ፡፡ ያ በሽታም ሳይኖርብኝ አይቀርም ስላልተመረመርኩ ነው እንጅ፡፡ በጣም ጎስቁያለሁ ከውሻ ጋር እየተሻማሁ እመገባለሁ ዞሮ ያየኝ ሰው አለመኖሩ ውስጤን ያሳዝነዋል፡፡ መንግሥትስ ቢሆን ምን አረገልኝ? ተው ጫት አትቃም፣ ሲጋራ አታጭስ፣ ዝሙት አትፈጽም በማለት ፈንታ በጥቃቅን በምናምን አደራጀሁ እያለ አይደል እንዴ ሴቶችን የሚቀያይርልን፡፡ ዝሙት አትፈጽም ብሎ ከመምከር ይልቅ ኮንዶም ተጠቀሙ እያለ ነው ማስታወቂያ የሚሰራልን፡፡ ዛሬ ሴተኛ አዳሪዎች ስንት ናቸው? እንደእኔ ካገኛት ጋር የሚተኛው ወንድስ ስንት ነው? ጫት መቃሚያ ቤቶች የሚዘጉት እኮ ግብር አልከፍል ሲሉ እንጅ ወጣቱን ሱሰኛ ስላደረጉት አይደለም፡፡ ታዲያ እንደዚህ አይነት መንግሥት ባለበት አገር ላይ እኔ ራሴን ማዳን ካልቻልኩ በቀር ማን ዞሮ ያየኛል? የሰውን ኅሊና ከመገንባት ይልቅ ሕንጻ መገንባት ላይ ትኩረት ባደረገች አገር ውስጥ ከሱስ ነጻ መሆን ይከብዳል፡፡

አብሮ አደጎቼ ሆይ! ዛሬ እንዲህ ስጎሰቁል፣ መካሪ ሳጣ፣ አይዞህ ባይ ረዳት ሲርቀኝ፣ ሰው የመሆን ህልሜ ሲዳፈን አይታችሁ ጨከናችሁ አይደል? ተውት ለእኔስ እግዚአብሔር አለኝ እመብርሃን ወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም እናቴ አለችኝ፡፡ ዛሬ እና ነገ የእኔን ማንነት አንድ ሆኖ አታዩትም፡፡ ያንን ሱሰኛ ጓደኛችሁን ዳግም በዚያ ሁኔታ ላታዩት እስከወዲያኛው ይሰናበታል፡፡ ይኼው በቃ! ማል ካላችሁኝ ማልሁላችሁ ሲጋራዬን ሰባብሬ፣ ጫቴን አሽቀንጥሬ፣ ዝሙቴን መዳራቴን ሁሉ ትቼ ንስሐ ገብቼ ከአምላኬ ጋር ታርቄ ልኖር ወስኛለሁ፡፡ በቃ አለቀ! ታሪኬን እቀይራለሁ ሲጋራ ማጨሴን ጫት መቆርጠሜን ዳግም ላልመለስባቸው ላልደርስባቸውም ወረወርኳቸው፡፡ ነገር ግን ሰው ስሆን ያኔ ሰው ሆኜ ስሞት ያኔ እንዳትቀብሩኝ ምክንያቱም በቁሜ ቀብራችሁኝ ስለነበር፡፡ ያን ያህል አይዞህ ባይ ባጣሁበት፣ ከውሻ ጋር ተሻምቼ በተመገብኩበት ማደሪያ አጥቼ ግድግዳ ተደግፌ በማነጋሁበት ሌሊት፣ በሲጋራ ሳንባዬ በነደደ ሰዓት ልባችሁን አጨክናችሁብኝ አልነበር? ሰላም እንዳትሉኝ ተጠየፋችሁኝ አይደል? በእርግጥ አልቀየማችሁም ነገር ግን ስሞት እንዳትቀብሩኝ እናዘዝላችኋለሁ፡፡ የሰው ልጅ ትልቁ ሰውነት በቁም መረዳዳት ብቻ ነው ሲሞቱ አልቅሶ መቅበር አይደለም ስለዚህ በቁሜ ስሞት ለቀበራችሁኝ አብሮ አደጎቼ ሁሉ ከእግዚአብሔር ጋር ሆኜ ስሞት ለቅሶ ደረሱ ለመባል ያህል ቀብሬ ላይ መጥታችሁ እንዳትቀብሩኝ፡፡ እንዳታለቅሱልኝ፡፡ አደራ በሰማይ አደራ በምድር፡፡ አበቃሁ…”

Monday, October 12, 2015

ፍርሐት


©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
…ሌላው ከእግዚአብሔር እንድንርቅ ምክንያት የሆነው ፍርሐት ነው፡፡ ዓላውያን ነገሥታት፣ ከሐድያንና መናፍቃን ሲነሡ ስለ እግዚአብሔር አምላክነት ለመመስከር ፍርሐት አለ፡፡ እነዚህ ሊገድሉህ ቢችሉ እንኳን ሥጋህን እንጅ ነፍስህን ሊገድሏት አይችሉም፡፡ እነዚህን መፍራት እንደማይገባም በወንጌል እንዲህ ተገልጿል “ሥጋህንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ” /ማቴ10÷28/ አንተ መፍራት ያለብህ ገሃነም ሊያስገባህ የሚችልውን ኃጢአት ነው፡፡ ሰው ቢዝትብህም፣ ቢያስፈራራህም፣ ቢያስጨንቅህም ፍርሐት ከእግዚአብሔር ሊያርቅህ አይገባውም፡፡ መግደላዊት ማርያም ሴት ሳለች ሴትነቷ ከእግዚአብሔር ፍቅር የሚያርቅ ፍርሐት አላመጣባትም፡፡ የኢየሱስ ክርስቶስን መቃብር ይጠብቁ የነበሩትን የታጠቁ ወታደሮች ከምንም አልቆጠረቻቸውም ፍርሐት የለባትም ነበርና፡፡ በማለዳ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ሄደች ሌሊቱ አላስፈራትም፡፡/ማቴ28÷1-10/ ሌሎች ፍርሐት ሲያርቃቸው እርሷ ግን ትንሣኤውን ለማየት የመጀመሪያ ሆነች፡፡ ሰለስቱ ደቂቅን የሚነድደው እሳት 49 ክንድ ያህል ከፍ ከፍ ሲል አላስፈራቸውም፡፡ የናቡከደነጾር ንጉሥ መሆን አላሸበራቸውም፡፡ እግዚአብሔር ብቻ አምላክ እንደሆነ መሰከሩ፡፡ ከፊታቸው የሚነድደው እሳት ወላፈኑ ልባቸውን አላስደነገጠውም፡፡ ንጉሥ ናቡከደነጾር ላቆመው ምስል እንዲሰግዱ በብዙ ነገሮች አስፈራራቸው፡፡ እነርሱ ግን ምንም አይነት ፍርሐት የለባቸውም ነበር፡፡ ንጉሥ ሆይ አንተ ላቆምከው ምስል በፍጹም አንሰግድም አንተንም እኛንም ዓለምን በፈጠረ እግዚአብሔር እናመልካለንና አሉት፡፡ በዚህም የተነሣ ወደ እቶኑ እጃቸውን ታስረው ተጣሉ ቅዱስ ገብርዔል መጥቶ እሳቱን እንደ ውኃ አቀዘቀዘላቸው በእሳቱ መካከልም እየተመላለሱ እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡/ዳን3÷1-ፍጻ/ እነዚህን ሕጻናት የሚነድደው እሳት አላስፈራቸውም፡፡ እግዚአብሔር እንደሚያድናቸው ፍጹም እምነት ነበራቸው፡፡ እግዚአብሔር ፈቃዱ ሆኖ ከእሳቱ ባያወጣን ማለትም ሰማእትነትን እንድንቀበል ቢተወን እንኳን አንተ ላቆምከው ምስል አንሰግድም ብላው ፍጹም እምነታቸውን አሳዩ፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ የሚቆረጥበት ስለት የሚፈጭበት ወፍጮ ሲቀርብለት አልፈራም በእግዚአብሔር ጸና እንጅ፡፡ ንጉሡ ዱድያኖስ እስኪያፍርና እስኪፈራ ድረስ እየሞተ እየተነሣ ስለ እግዚአብሔር አምላክነት መሰከረ፡፡ ንጉሡ እጅግ ተጨነቀ፤ ገደልኩት አረፍኩት ሲል ተነሥቶ ይመጣበታል፡፡ አሁንም እኔን ከሞት ባስነሳ አንተንም በፈጠረ ዓለምን ሁሉ ካለመኖር ወደ መኖር ባመጣ አምላክ በእግዚአብሔር እመን እያለ ይገስጸዋል፡፡ንጉሡ ግን መስማትን እንቢ አለ፡፡ይህን የተቀደሰ ምስክርነት ለመጠበቅ አንተም የፍርሐትን ጫማ አውልቀህ ልትጥል ያስፈልጋል፡፡ እስከመጨረሻው ድረስ ፍርሐትን አርቀህ ከተከተልህ የድል አክሊልን ትቀዳጃለህ፡፡ ሐዋርያው ዮሐንስን ልብ በል፡፡ ሌሎች ሐዋርያት ፈርተው ሲሸሹ እርሱ ግን እስከ ቀራንዮ ድረስ ፍርሐቱን አስወግዶ ተከተለው፡፡ በመስቀሉ አጠገብ በመገኘቱም ድንግል ማርያምን የምታህል እውነተኛ ቅድስት እናትእነኋት እናትህ ተብሎ ከአምላኩ ለመቀበል በቅቷል፡፡/ዮሐ19÷27/ አንተም እንደዚህ ባለው ጭንቅ ቀን እንኳን ሳይቀር ልትታመን ያስፈልጋል፡፡ በሰላም እና በደስታ ጊዜ ሁሉም ተከታይ ነው በመከራ ጊዜ ግን ሁሉ አይደለም፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ምግቡን እያበረከተ ሲመግብ ይመገብ የነበረው ያ ሁሉ ሕዝብ እስከ ቀራንዮ ድረስ መስቀሉን ተሸክሞ ሲወድቅ ሲነሣ ሊያሳርፈው የተከተለ አልነበረም፡፡ ፍርሐትን ከልብህ አውጥተህ ወዲያ ጣለው፡፡ ያየኸውን ሁሉ ፈርተህ ከእግዚአብሔር ርቀህ ልትኖር አትውደድ፡፡ የእግዚአብሔርን ቃል ያለ ፍርሐት ልትመሰክር አደራ አለብህ፡፡ ልምን ይህን ትናገራለህ? የሚልህ ቢነሣ ለእግዚአብሔር የሚገባ ስለሆነ ተናገርሁ ብለህ መልስለት፡፡ ስለ እምነትህ የሚገባውን ሁሉ ልታደርግ ከእግዚአብሔር ዘንድ መብት ተሰጥቶሃል፡፡ ይህን መብትህን እንዳትጠቀም የሚኮረኩምህ ከሃዲ ቢነሣ እጅህን አትስጠው የፍርሐት ስሜትም አይሰማህ፡፡ የነቢዩ ሙሴ መንድም አሮን የፈራውን ፍርሐት ከልብህ አርቀው፡፡ ሙሴከእግዚአብሔር ጋር 6 ቀን ቃል በቃል እየተነጋገረ 34 ቀን እየነገረ ሲያስጽፈው ለ40 ቀን በሲና ተራራ በቆየ ጊዜ ሕዝበ እስራኤል አሮንን ከግብጽ ያወጣን ሙሴ ም እንደሆነ አናውቅምና ተነሥተህ በፊታችን የሚሄዱ አማልክት ሥራልን አሉት፡፡ እኔ እግዚአብሔር ነኝ ከእኔ ሌላ አማልክት አይሁኑልህ፡፡/ዘጸ20÷3/ የሚለውን አምላካዊ ትዕዛዝ ለመሻር ወሰኑ፡፡ እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ለማምለክ የግድ ሙሴ አብሯቸው መኖር ነበረበት እንዴ? አሮን ሕዝቡን ፈራ ገንዘብ ወዳጆች ናቸውና በሚስቶቻችሁ በወንዶችና በሴቶች ልጆቻችሁም ጆሮ ያሉትን የወርቅ ቀለበቶች ሰብራችሁአምጡልኝ አላቸው፡፡ ነገር ግን ሰይጣን አነሣሥቷቸዋልና ለወርቃቸውም አላዘኑም፡፡ ሕዝቡም እንደታዘዙት ወርቃቸውን ወደ አሮን አቀረቡት፤ እርሱም በመቅረጫ ቀረጸው ቀልጦ የተሠራ ጥጃም አደረገው፡፡ ቁጡዓን የሆኑትን ሕዝበ እስራኤል የፈራው አሮን የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ተላለፈ፡፡ እንዲህም አላቸው እስራኤል ሆይ እነዚህ ከግብጽ ምድር ያወጧችሁ አማልክት ናቸው አላቸው፡፡ ለዚያም ምስል መሥዋዕት እየሰዉ እየበሉና እየጠጡ እየዘፈኑም ሰገዱ፡፡በዚህም የተነሣ እግዚአብሔር በእስራኤላውያን ላይ ተቆጣ፡፡ /ዘጸ32÷1-ፍጻ/ ይህ አይነት ፍርሐት ከእግዚአብሔር ያርቃል፡፡ ለጣዖት ሲሰግዱ መሥዋዕት ሲሰው በፍርሐት የሚመለከት ሰው ከእግዚአብሔር ለመራቅ የወሰነ ሰው ነው፡፡ ይህን አይነቱን ፍርሐት ማስወገድ ተገቢ ነው፡፡ ጭንቅ ሲመጣብህ ፈተና ሲደርስብህ መጽናት ከቻልክ ብቻ ነው የዘላለም ርስት ወራሽ የምትሆነው፡፡ ሐዋርያት ልብሳቸውን ጥለው እስከ መሮጥ ድረስ ያደረሳቸው ፍርሐት ነው፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ ኢየሱስ ክርስቶስን 3 ጊዜ ለመካድ ያበቃው ፍርሐት ነው፡፡ ምንም እንኳን በኋላ ኃይልን ለብሰው አንገታቸውን ለስለት ጀርባቸውን ለግርፋት እስከመስጠት ድረስ የደረሰ ፍጹም ጽናት የተሰጣቸው ቢሆንም መጀመሪያ ላይ ግን ፍርሐት ነበረባቸው፡፡/ማር14÷50-52/፣ /ማር14÷66-71/ በአርግጥ እንደዚህ አይነቱ ፍርሐት ጊዜያዊ ፍርሐት በመሆኑ በንስሓ የመመለስ ዕድል ይሰጣል፡፡ የአሮንም ሆነ የሐዋርያት ፍርሐት ለጊዜው ነው፡፡ እንደ ነቢዩ ኢሳይያስ ያለ ፍርሐት ማለት ነው፡፡ንጉሡ ዖዝያን የማይገባውን ሥራ በቤተ መቅደስ ገብቶ አጥናለሁ ሲል ንጉሥ በመሆኑ ፈራው በዚህም የተነሣ ለምጽ ወጣበት ትንቢት ተነሣው፡፡ በኋላ ግን ተመልሶለታል ጊዜያዊ ፍርሐት ነበርና፡፡/ኢሳ6÷1-8/ ነገር ግን ያ በትንሹ የጀመረ ፍርሐት እያደገ ንስሓን በር ጭምር የሚዘጋ እንዳይሆን መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ለጊዜው ነው በሚል አስተሳሰብ ኃጢአት መሥራት አይገባም፡፡ የመመለሻ ዕድሜ ይኑረን አይኑረን የምናውቀው ነገር ስለሌለ ዘሬ ፍርሐትን ልናስወግድ ያስፈልጋል፡፡ እስከ መጨረሻው መጽናት ያስፈልጋል፡፡ እስከ መጨረሻው የሚጸና እርሱ ይድናል ይላልና፡፡/ማቴ2413/ እዚህ ላይ የቅድስት ሶስናን ታሪክ እንመልከት፡፡ ሶስና መልከ ቀና ስለነበረች በሐፀ ዝሙት የተነደፉ ረበናት ወይም ሥርዓት አስተማሪ ነን ባዮች በአትክልት ቦታ ውስጥ ሰውነቷን ስትታጠብ ሄደው እሺ በእጄ በይን እንቢ ካልሽ ግን ከጎረምሳ ጋር ስትዳራ አገኘናት ብለን በድንጋይ እናስወግርሻለን አሏት፡፡ ነገር ግን ይህን ኃጢአት አድርጌው እግዚአብሔር ከሚፈርድብኝ ሳላደርገው ሞት ቢፈረድብኝ ይሻለኛል ብላ በድንጋይ ነመወገርን ሳትፈራ ጮኸች፡፡ እነርሱም አብረው ጮኹ ከወንድ ጋር ስትዳራ አገኘናት ብለው አዕሩገ እስራኤል ተሰብስበው ተወግራ እንድትሞት ፈረዱባት፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ዳንኤልን ልኮ አዳናት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ነገር ሠሪዎችን እንደ አክርማ ሰነጠቃቸው፡፡/መጽሐፈ ሶስናን ተመልከት/

Thursday, October 8, 2015

መልካም ምኞት አገላለጻችን ከየት ወዴት?

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ባለፈው ቃል በገባሁላችሁ መሠረት ቃሌን ለመጠበቅ ኢትዮጵያዊውን የመልካም ምኞት አገላለጽ እና አሁን እየተበረዘ ስላለበት ሁኔታ እንመለከታለን፡፡ ኢትዮጵያዊነታችን ከሌላው ዓለም ሁሉ ልዩ የሚያደርገን በርካታ ነገር እንዳለው የታመነ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነት በደስታ በሐዘን የአንዱን ሌላው የሚጋራበት የባህል ማዕከል ነው፡፡ ሌላው ዓለም ምናልባት ሃዘንህን የተጋራ ደስታህንም እንዲሁ የተጋራ ሊመስል ቢችልም የመልካም ምኞት አገላለጹ ግን ሙሉ በመሉ ደስታህን እንዳልተጋራልህ ያሳያል፡፡ አንተ ስትደሰትም ሆነ ስታዝን ሌላው ሰው የሚጋራልህ ከሆነ እርሱ ኢትዮጵያዊነት መሆኑ አያጠራጥርም፡፡
ኢትዮጵያዊነት ደስታህ ደስታየ ነው ሲል “እንኳን ደስ አለህ!” ይልሃል አንተም “አብሮ ደስ ይበለን” ብለህ ትመልሳለህ፡፡ ይህ መልካም ምኞት መግለጫችን ደስታህ ደስታየ መሆኑን የሚጠቁም ነው፡፡ “አብሮ ደስ ይበለን” የሚለው ምላሽም እርሱን የሚያጎላ ነው ሁላችንንም ደስ ይበለን የሚል ስለሆነ፡፡ ሌላው “እንኳን አደረሰህ” የሚለው ሲሆን “እንኳን አብሮ አደረሰን” የሚለውን ምላሽ ያስከትላል፡፡ ያንተ መድረስ ለእኔ የእኔም መድረስ ላንተ ምኞታችን ነው ለዚህም ነው “እንኳን አደረሰህ” ስትባል “እንኳን አብሮ አደረሰን” የምትለው፡፡ እኔ ብቻ ሳልሆን ሁላችንንም እንኳን አደረሰን ብለን የምንመልሰው የሌሎቹንም ለዚያ ቀን መድረስ ስለምንመኝ ስለምናስብ ነው፡፡ መልካም ምኞት አገላለጻችን አንድን ወገን ብቻ የሚገልጽ አይደለም፡፡ ሌሎች ዓለማት ግን መልካም ምኞታቸው አንድ ወገን ተኮር ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነታችን ልዩ የሚያደርገን መልካም ምኞታችን ሁለት ወገን ተኮር መሆኑ ነው፡፡
አንድ ወገን ተኮር መልካም ምኞታቸው ኢትዮጵያዊነታችንን እየተፈታተነው ይገኛል፡፡ ውጮቹ “CONGRATULATION” ይላሉ መላሹም “THANK YOU” ይላል፡፡ “እንኳን ደስ አለህ” ሲባል “አመሰግናለሁ” ብሎ ይመልሳል ማለት ነው፡፡ የእኔ ደስታ አንተን አይመለከትም “እንኳን ደስ አለህ” ላልከኝ ግን “አመሰግናለሁ” ማለት ነው እንግዲህ፡፡ ኢትዮጵያዊነት ግን ደስታህ ደስታየ ነው እና አይመለከትህም አልልህም “አብሮ ደስ ይበለን” ብሎ ይመልሳል፡፡ ሌላው የምንመለከተው “የእንኳን አደረሳችሁ” መልእክታቸውን ነው፡፡ ውጮቹ “HAPPY NEW YEAR”፣ “HAPPY X_MASS”፣ “HAPPY EASTER” ወዘተ በማለት መልካም ምኞታቸውን ይገልጻሉ፡፡ እነዚህ መልካም ምኞቶች እኛ አገር ውስጥ ዋጋ የላቸውም፡፡ “መልካም አዲስ ዓመት”፣ “መልካም ገና”፣ “መልካም ፋሲካ” የሚል ቀጥተኛ ትርጉም ይይዛሉ፡፡ ታዲያ መላሹ “አመሰግናለሁ” ብሎ ይመልስ? ወይስ “እንኳን አብሮ” አደረሰን ይበል? ኢትዮጵያዊነት መቸም “አመሰግናለሁ” ብቻ ብሎ መልካም ምኞቱን ለሌሎችም ሳያጋራ ውጦ አይቀርም፡፡ ኢትዮጵያዊነት በመጀመሪያ “መልካም አዲስ ዓመት” አይልም “መልካም ገና” እና “መልካም ፋሲካ” ብሎም መልካም ምኞት አይገልጽም፡፡ የእኛ ያልሆነውን ነገር በፈረንጆቹ ተጽእኖ ከኢትዮጵያዊነታችን ጋር ቀላቀልነው እንጅ እኛ የምንለው “እንኳን ለአዲሱ ዓመት በሰላም አደረሰህ” ነው፡፡ መላሹም “አመሰግናለሁ” ሳይሆን “እንኳን አብሮ አደረሰን” የሚል ይሆናል፡፡ በሌላ አነጋገር እኔ ብቻ ሳልሆን አንተንም እንኳን አደረሰህ እያለው ነው፡፡ ፈረንጆቹ ግን “አመሰግናለሁ” ይሉሃል ምክንያቱም ያንተ ለዛ ቀን መድረስ አለመድረስ ምናቸውም አይደላማ!፡፡ ሌሎችንም በእነደዚህ ያለ ሁኔታ ነው እንኳን አደረሳችሁ የምንባባለው፡፡ ለገና በዓል “እንኳን ለጌታችን ለመድኃታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በሰላም አደረሰህ” እንዲሁም ለትንሣኤ በዓል “እንኳን ለጌታችን ለመድኃታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በሰላም አደረሰህ”  እንባባላለን መላሹም ከላይ እንደተመለከትነው “እንኳን አብሮ አደረሰን” ይላል፡፡

አሁን አሁን ግን በርካታ ኢትዮጵያዊነት ለዛችንን እያጣን ያለንበት ሁኔታ ነው፡፡ “እንኳን ለልደትህ በሰላም አደረሰህ” በማለት ፋንታ “HAPPY BIRTH DAY” ማለት የሚቀናው ኢትዮጵያዊ እየተበራከተ ነው፡፡ “መልካም ልደት”፣ “መልካም አዲስ ዓመት”፣ “መልካም ገና”፣ “መልካም ፋሲካ” ወዘተ እያልን የፈረንጆቹን አንድ ወገን ተኮር የሆነ መልካም ምኞት መግለጫ መጠቀም መጀመራችን ታሪካችንን የሚፈታተን እና ማንነታችንን የሚያበላሽ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነታችን ከሌላው የዓለም ክፍል ሁሉ ልዩ ያደርገናል፡፡ የአመጋገብ፣ የአለባበስ፣ የአነጋገር፣ የአረማመድ ልዩ ባህል አለን፡፡ ስንመገብ ዘመድ ጎረቤቱ ተሰብስቦ በአንድ መሶብ ከብቦ አንዱ አንዱን እያጎረሰ ይመገባል፡፡ ይህ ልዩ ፍቅርን የሚያሳይ ነው የሚጎርሰው ሰው ቆርሶ መጉረስ አልችል ብሎ አይደለም የምናጎርሰው ፍቅራችንን ለመግለጽ እንጅ፡፡ መተሳሰብ መረዳዳታችንን ለማሳየት የምንጠቀምባቸው ባህሎቻችን ናቸው፡፡ስለዚህ በሌሎቹ ተጽእኖ ስር ከመውደቅ ራሳችንን እንጠብቅ የሚል መልእክት አስተላልፋለሁ፡፡

Friday, October 2, 2015

ልኩን ያለፈ አሜን ከጭብጨባና እልልታ ጋር

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
እንደምን ሰነበታችሁ አምላከ ቅዱሳን እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ በሰላም በጤና አደረሳችሁ። በእርግጥ የመልካም ምኞት መግለጫዬ ብዙ ቀናትን ያሳለፈ መሆኑን እረዳለሁ። ነገር ግን የመናገር እና የመጻፍ መብቴን ፌስቡክ ስላልገደበኝ ብዬም በዓሉ ከመድረሱ በፊት ሳምንት እና ሁለት ሳምንት ቀድሜ እንኳን አደረሳችሁ አልልም። በዓላት የሚውሉባቸው ቀናት እንደ ፌስቡክ አቆጣጠር ቢሆን ኖሮ አንድ ዓመት የሚባለው 365 1/4 አይሆንም ነበር። ለምሳሌ የዘመን መለወጫ መስከረም 1 መሆኑን የቀን መቁጠሪያችን ያስረዳል። በፌስቡክ ግን ጳጉሜን 1 ጀምሮ ዘመን ይለወጣል። እንኳን ለአዲሱ ዓመት አደረሳችሁ የሚሉ መልካም ምኞት መግለጫዎች እኔ እቀድም እኔ እቀድም እየተባባሉ በሚመስል ሁኔታ በየግለሰቦች ይለጠፋሉ። ሳንደርስ እንኳን አደረሳችሁ መባባልን ማን አመጣ ብትሉኝ መልሴ ፌስቡክ የሚል ነው። አንድ ደቂቃ ስንት ተአምር እንደምትሰራብን ያልተረዳን ሰዎች ነን እንዲህ ከሳምንት በፊት እንኳን አደረሳችሁ የምንባባለው። ለማንኛውም መልካም ምኞትን በተመለከተ በሌላ ርእስ እንገናኝ ይሆናል አምላክ ፈቃዱ ይሁንና። ለጊዜው ወደ ዛሬው ርእስ እንመለስ።
አሜን /amen/ የሚለው ቃል ዓለምን ሁሉ ያስተሳሰረ ብቸኛ ቃል ነው። ቻይናዎችና ጃፓኖች ምን እንደሚሉ ባላውቅም ሁሉም የዓለም ቋንቋዎች ሁሉ አሜን የሚለውን ቃል እንደሚጠቀሙ ይነገራል። አሜን ማለት ይሁን፣ይደረግ የሚል ትርጉም አለው። ወደ ሀገራችን ከዚያም ወደ ቤተክርስቲያናችን እንግባና አሜንን እንመልከተው። አሜን የሚለው ቃል በቤተክርስቲያናችንም ከላይ ያየነውን ትርጉም ይይዛል። አባቶቻችን ሲመርቁን አሜን እንላለን ምርቃታችሁ ይሁንልን ይደረግልን ለማለት ነው። አሁን አሁን ግን ልክ እና መጠኑን ያለፈ አሜን እንዲሁም እልልታና ጭብጨባ የዋጠን ይመስለኛል። የተሐድሶ መናፍቃን ካስለመዱን መጥፎ ጸባያችን መካከል አንዱ ይሄው ነው። ሁሉም የሚያምረው ልክ እና መጠን ሲኖረው ነው። ማር ሲበዛ ይመራል አይደል ያለው የሀገሬ ሰው። ልክ እና መጠንን ከምታስተምር ቤተክርስቲያን ውስጥ ልክ ያለፈ ነገርን ማድረግ ድፍረት ሳይሆን አይቀርም። በእርግጥ ይህን ልክ እንድናልፍ "የዘመኑ መምህራንም" እጅ አለበት። የሚናገሩትን ነገር የሚጀምሩት አስጨብጭበው ነው። ከዚያም ርእስ የሌለው "ትምህርታቸውን" ይጀምራሉ በእርግጥ ያልተዘጋጀ መምህር ከዚህ የተሻለ ነገር ማድረግ አይችልም። በተደጋጋሚ "ክብር ለእሱ ይሁን" እያሉ ህዝቡን ያስጨበጭባሉ እልል ያስብላሉ። ሕዝቡም የሚባለውን ነገር ሳይሰማ እንኳ ያጨበጭባል እልል ይላል። "እስኪ እጃችሁን አሳዩኝ" ይላል "መምህሩ" ህዝቡ አሁንም ያጨበጭባል አይሰማም ይላቸዋል አሁንም ከቅድሙ አብልጠው ያጨበጭባሉ። የኪነ ጥበብ ሰዎች ዘፈን ሊዘፍኑ ወደ መድረክ ሲመጡ የሚደረግላቸውን አቀባበል በቤተክርስቲያናችን አውደ ምሕረቶች እያየነው ነው። 
በተለይ ትላልቅ በዓላት ላይ ደግሞ እንዲህ ማድረግ የሚወዱ የመድረክ መሪዎችም አሉ። አንዴ ስላስለመደው ገና የዕለቱ መምህር እገሌ ናቸው ሲል ህዝቡ ያጨበጭባል። መምህሩ ሲመጡ እያጨበጨቡ ይቀበሏቸዋል። ፋታ የሌለው ጭብጨባና እልልታ በጣም ስልችት የሚል። መምህሩም "ክብር ለእሱ ይሁን" ይላል ህዝቡም ያጨበጭባል። እሽ ክብሩ ለማን ይሁን ብለን ነው ያጨበጨብነው? እሱ የተባለው ማነው? ሰይጣን ነው ወይስ እግዚአብሔር ነው? ዝም ብለን መጮህ አይደለም እሱ የጅራፍ ባሕርይ ነው። ዝም ብሎ እልል ማለት አይደለም እሱ የእንቁራሪት ባሕርይ ነው። "ክብር ለእሱ ይሁን" የተባለለት እግዚአብሔር ከሆነስ የቱን ክብሩን ነው በእንደዚያ ያለ እልልታና ጭብጨባ የምንገልጸው? አንዳንዶች ደግሞ "አይሰማም እጃችሁ የት አለ?" እያሉ ደግመው ደጋግመው ያስጨበጭባሉ። ክብሩ ለእግዚአብሔር ነው ከተባለ ያስጨበጨቡንንና እልል ያስባሉንን ጩኸት እንዴት እግዚአብሔር አልሰማም? አልተሰማንም የሚሉ እነርሱ ናቸው ያስጨበጨቡን ደግሞ ለእግዚአብሔር ብለው ነው ታዲያ ሁለቱ ሃሳብ አይጣረስም ትላላችሁ? 
በእርግጥ አሁን አሁን ልማድ አድርገነዋል። "የሰማነውን ቃለ እግዚአብሔር በልቡናችን ያሳድርልን" ተብለን ስንመረቅ አሜን በማለት ፋንታ ትርጉም በማይሰጥ መልኩ በጭብጨባ እንመልሳለን። "ቃለ ሕይወትን ያሰማልን" ስንባል ደግሞ በእልልታ እናቀልጠዋለን። ትርጉሙ ምን ይሆን? ይህን የምለው ግን ለእውነተኞች መምህራን አይደለም እነርሱ እንዲህ ስለማያስደርጉ። እንደአጠቃላይ ጭብጨባ በሚያስፈልግበት ጭብጨባ፣እልልታ በሚያስፈልግበት እልልታ፣አሜን ማለት በሚያስፈልግበት አሜን ማለት ይገባል እንጅ ከመጠን ባለፈ ያውም ያለቦታው ማጨብጨብ እና እልል ማለት ትርጉም አልባ ነው። ቃለ እግዚአብሔርም ለመማር የመጣን ሰው ለጆሮ በሚሰቀጥጥ እልልታና ጭብጨባ ልናደነቁር አይገባም።