Friday, March 31, 2017

የቅብዓት ምንፍቅና ምንጭ---ክፍል ፲፪


© መልካሙ በየነ
መጋቢት 22/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

ስለጌታ ልደቶች
ወልደ አብ ገጽ 216-217 “የጌታችን ልደቱ ስንት ነው ቢሉ ኹለት ነው። እንዴት ኹለት ነው እምቅድመዓለም በመለኮቱ ተወለደ ብለናል ኋላም በማኅጸን በሰውነቱ ከአብ ተወለደ እንላለን ዳግም ከእመቤታችን በስጋ በጎል ተወለደ እንላለን ይህማ ሦስት አይደለምን እንደምን ኹለት ነው ቢሉ እምቅድመዓለም በመለኮቱ የተወለደው ልደትና ዛሬ በማኅጸን በሥጋ በቅብአተ መንፈስ ቅዱስ የተወለደው ልደት አንድ ልደት ይባላል እንጅ ኹለት አይባልም። ኹለት ጊዜ ቆጥረነው አንድ ማለታችን እንዴት ነው ቢሉ እምቅድመዓለም በመለኮቱ የወለደው አብ ነው። ዛሬም በሰውነቱ በማኅጸን የወለደው አብ ነው እንጅ ሌላ አይደለም። ወላዲው ተወላዲው ዛሬም የተወለደበት መንፈስቅዱስ ያ የጥንት የባሕርይ ሕይወቱ ስለአልተለወጠ አንድ ልደት ይባላል እንጅ ኹለት ልደት አይባልም። ለዚህም ምሳሌ ያስረዳል ምሳሌ እንዴት ያስረዳል ቢሉ እነሆ ዛሬ ሰው አዲስ ሸማ ለብሶ ያነን በከረጢት ከቶ ዳግመኛ አውጥቶ ቢለብሰው አንዱን ሸማ ኹለት ጊዜ ለበሰው ተብሎ አንድ ሸማ ይባላል እንጅ ኹለት አይባልም። ዳግመኛ በአንድ ዘውድ ሁለት ሦስት ነገሥታት ቢነግሡበት ኹለት ሦስት ነገሥታት ነገሡበት ተብሎ አንድ ዘውድ ይባላል እንጅ ኹለት ዘውድ አይባልም” እንደሚል እና ሦስተ መሠረታዊ ስህተት እንዳሉበት ገልጠናል፡፡ ከሦስቱ መሠረታዊ ስህተቶች መካከል ሁለቱን ባለፉት ተከታታይ ክፍሎች ተመልክተናል፡፡ ዛሬ በዚህ ክፍል የምንመለከተው ሦስተኛውን መሠረታዊ ስህተት ይሆናል እርሱም ምሳሌ ያስረዳል ተብሎ የተመሰለውን ከንቱ ምሳሌ ነው፡፡
“እምቅድመዓለም በመለኮቱ ተወለደ ብለናል ኋላም በማኅጸን በሰውነቱ ከአብ ተወለደ እንላለን ዳግም ከእመቤታችን በስጋ በጎል ተወለደ እንላለን ይህማ ሦስት አይደለምን እንደምን ኹለት ነው ቢሉ እምቅድመዓለም በመለኮቱ የተወለደው ልደትና ዛሬ በማኅጸን በሥጋ በቅብአተ መንፈስ ቅዱስ የተወለደው ልደት አንድ ልደት ይባላል እንጅ ኹለት አይባልም። ኹለት ጊዜ ቆጥረነው አንድ ማለታችን እንዴት ነው ቢሉ እምቅድመዓለም በመለኮቱ የወለደው አብ ነው። ዛሬም በሰውነቱ በማኅጸን የወለደው አብ ነው እንጅ ሌላ አይደለም። ወላዲው ተወላዲው ዛሬም የተወለደበት መንፈስቅዱስ ያ የጥንት የባሕርይ ሕይወቱ ስለአልተለወጠ አንድ ልደት ይባላል እንጅ ኹለት ልደት አይባልም” ይላሉ፡፡ እውነት ይኼ ለማንም ለሚያይ ሁሉ እንደግንባር ግልጥ የሆነ  የተሸሸገ ነገር የሌለው አይደለምን? እዚህ ላይ በግልጥ የምንመለከተው ሦስት ልደትን ማመናቸውን ነው፡፡ መጻሕፍት “ሁለት ልደታትን እናምናለን” ብለው ስላጠሩባቸው ለመንፈራገጥ አልመች ቢላቸው ሦስት ጊዜ ቆጥሮ ሁለት ማለት ይገባል ብለው ተናገሩ፡፡ እነርሱ የሚጠቅሷቸው በግልጥ የተቀመጡት የጌታ ልደቶች እነዚህ ናቸው፡፡
1.  እምቅድመ ዓለም በመለኮቱ የተወለደው ልደት
2.  በማኅጸን በሥጋ በቅብአተ መንፈስ ቅዱስ የተወለደው ልደት
3.  ከእመቤታችን በስጋ በጎል ተወለደ በማለት ሦስት ልደታትን አስቀምጠውልናል፡፡
እነዚህ ልደታት መካከል 2ኛው ልደት በየትኛውም መጽሐፍ ተጽፎ እንደማይገኝ ባለፉት ተከታታይ ክፍሎች በማስረጃ በማስደገፍ ጽፈናል፡፡ እነርሱ እንደሚሉት 1ኛ እና 2ኛ ላይ የተገለጡት ልደቶች አንድ ተብለው ይቆጠራሉ እንጅ ሁለት አይባሉም ይላሉ፡፡ ለምን ለሚለው መልስ ሲመልሱ “ኹለት ጊዜ ቆጥረነው አንድ ማለታችን እንዴት ነው ቢሉ እምቅድመዓለም በመለኮቱ የወለደው አብ ነው። ዛሬም በሰውነቱ በማኅጸን የወለደው አብ ነው እንጅ ሌላ አይደለም። ወላዲው ተወላዲው ዛሬም የተወለደበት መንፈስቅዱስ ያ የጥንት የባሕርይ ሕይወቱ ስለአልተለወጠ አንድ ልደት ይባላል እንጅ ኹለት ልደት አይባልም” ይላሉ፡፡ በእውነት ምንም የማይመስል የማይገናኝ ከንቱ ነገር ነው፡፡ “እምቅድመዓለም በመለኮቱ የወለደው አብ ነው። ዛሬም በሰውነቱ በማኅጸን የወለደው አብ ነው እንጅ ሌላ አይደለም” ማለት ምን ማለት ነው? እዚች ላይ ያዝ አድርጓት እስኪ፡፡ የቀደመ ልደቱ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ ሳይቀድም ሳይከተል ያለእናት በመለኮት በረቂቅ ምሥጢር የተደረገ ነው፡፡ የዛሬው ልደቱ ደግሞ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ በመለኮት አይደለም ምክንያቱም አብ የወለደው በሥጋ ነው ብለውናላ፡፡ በመለኮት ነው ካሉ ወልድ በመለኮቱ ስንት ጊዜ ተወለደ ብለን እንጠይቃቸዋለን፡፡ በሥጋ ነው የወለደው ካሉን ደግሞ መለኮታዊ አካል ሥጋዊ አካልን መለኮታዊ ባሕርይም ሥጋዊ ባሕርይን ይወልድ ዘንድ ይቻላልን ብለን እንጠይቃቸዋለን፡፡ አዎን ሊወልድ ይቻለዋል ካሉን የቀደመው ልደቱ ከአብ በመለኮት ነው የዛሬው ልደቱ ደግሞ ከአብ በሥጋ ነውና ሁለት ብለን እንቆጥረዋለን እንጅ አንድ ልደት አንለውም ብለን በዚህ እንረታቸዋለን፡፡ ነገር ግን እነርሱ መረታትን ስለማይሹ “ወላዲው ተወላዲው ዛሬም የተወለደበት መንፈስ ቅዱስ ያ የጥንት የባሕርይ ሕይወቱ ስለአልተለወጠ አንድ ልደት ይባላል እንጅ ኹለት ልደት አይባልም” ብለው መከራከራቸው አይቀርም፡፡ ነገር ግን ወላዲው አብ ይሁን ተወላዲውም ወልድ ይሁን አይቀየር አይለወጥ እንጅ ልደቱ ግን ለየቅል ነው እንላቸዋለን፡፡ ምክንያቱም “የቀደመው ልደት በመለኮት የዛሬው ልደት በሥጋ” ነውና ልደቱ በጣም ይለያያል እንላቸዋለን፡፡ አብ በመለኮት ቅድመ ዓለም የወለደው ልደት እና ዛሬ በማኅጸነ ማርያም በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ የወለደው ልደት እጅግ የተለያየ እንደሆነ ልብ ማለት ተስኗቸዋል፡፡ ለዚህም እኮ ነው ይች “ዛሬ አብ በማኅጸነ ማርያም በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ ወለደው” የምትለዋ ተጨማሪ የፍልስፍና ልደት ትቅር መጽሐፍ አይደግፋትም የምንለው፡፡ የጻፉትን ነገር ስትመለከቱት ፈራሽ ነገር ነው፡፡ ቀጥለው ለዚህም ምሳሌ ያስረዳል ይሉናል፡፡ ልብ በሉ! ሦስት ልደት ቆጥረው ሁለት ልደት ነው ብለው ሙልጭ ብለው ለጠፉበት ክህደት የተሰጠ ምሳሌ መሆኑ ነው፡፡ እንዲህ ይላል ምሳሌው “ለዚህም ምሳሌ ያስረዳል ምሳሌ እንዴት ያስረዳል ቢሉ እነሆ ዛሬ ሰው አዲስ ሸማ ለብሶ ያነን በከረጢት ከቶ ዳግመኛ አውጥቶ ቢለብሰው አንዱን ሸማ ኹለት ጊዜ ለበሰው ተብሎ አንድ ሸማ ይባላል እንጅ ኹለት አይባልም። ዳግመኛ በአንድ ዘውድ ሁለት ሦስት ነገሥታት ቢነግሡበት ኹለት ሦስት ነገሥታት ነገሡበት ተብሎ አንድ ዘውድ ይባላል እንጅ ኹለት ዘውድ አይባልም”፡፡ እነዚህን ምሳሌዎች ዘርዘር አድርገን ፍትፍት ብትንትን አድርገን እንመልከታቸውማ!
1.  አዲሱ ሸማ ጉዳይ ከልደቱ ጋር እስኪ ይዛመድ፡፡
ምሳሌነቱ፡- ሸማው ወልድ ነው፡፡ ለባሹ አብ ነው፡፡ ስለዚህ ለበሰ ለሚለው ቃል አቻው ወለደ የሚለው ይሆናል ማለት ነው፡፡ ከረጢቱ የድንግል ማርያም ማኅጸን ምሳሌ መሆኑ ነው፡፡ ልብ በሉ አስተውሉ ወገኖቼ!!! የጌታ ልደት እንደዚህ በከረጢት ገብቶ እንደመውጣት ያለ ተራ ነገር አድርገው ማሰባቸው ኅሊና ቢስ መሆናቸውን ያስረዳል፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን ሸማው ወልድ መጀመሪያ በለባሹ (አብ) ተለበሰ (ተወለደ) ቀጥሎ በከረጢት በተመሰለው የድንግል ማርያም ማኅጸን አደረ (ተዋሐደ) ከዚያ ከዚህ ከረጢት ለባሹ (አብ) አውጥቶ ለበሰው (ወለደው) ማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ ለባሹም ልብሱም አልተቀየረም አልተለወጠም ትክክል ነው፡፡ ነገር ግን ስንት ጊዜ ለበሰው ብለን ብንጠይቅ ለባሹ እና ልብሱ ስላልተለወጡ ስላልተቀየሩ አንድ ጊዜ ለበሰው ሊባል ይችላል እንዴ? በእውነት ግን አንድ ልብስ የሚያረጀው ብዙ ጊዜ ስለተለበሰ አይደለምን ታዲያ በከረጢት አስገብተው እያወጡ ሲለብሱት ያው አንድ ጊዜ ብቻ እንደተለበሰ ይቆጠራል ከተባለማ በጣም ጥሩ የኑሮ በዘዴ መምህር ሆነዋል ማለት ነው፡፡ ይች ግን ጥሩ ፍልስፍና ሳትሆን አትቀርም፡፡ በእውነት ልብስ በከረጢት እያስገቡ ከዚያ እያወጡ ሲለብሱት ለባሹም ልብሱም ስላልተቀየረ አንድ ተለበሰ ነው የሚባል ብለው አረፉት፡፡ ሁለት ጊዜ ስለተለበሰ ሁለት ሸማ ሳይሆን አንድ ሸማ ይባላል የሚለው ትክክል ነው፡፡ ነገር ግን በሸማው የተመሰለው ወልድ አይለወጥ አይቀየር እንጅ ሁለት ጊዜ ተወልዷል ማለት ነው፡፡ ለዚህ ነው ይህ ምሳሌ “እምቅድመዓለም ከአብ የተወለደውንና በማኅጸነ ማርያም ከአብ የተወለደውን ሁለት ልደት ሁለት ብለን እንድንቆጥር እንጅ አንድ ብለን እንድንቆጥር አያደርግም እና የወልድ ልደቶች ሦስት ናቸው እንደሚሉ ጥሩ ምሳሌ ነው” የምንለው፡፡
2.  ዘውዱ ጉዳይ ከልደቱ ጋር ያለው ምሳሌነት ሲዛመድ፡፡
“ዳግመኛ በአንድ ዘውድ ሁለት ሦስት ነገሥታት ቢነግሡበት ኹለት ሦስት ነገሥታት ነገሡበት ተብሎ አንድ ዘውድ ይባላል እንጅ ኹለት ዘውድ አይባልም”
ምሳሌነቱ፡- ዘውዱ አብ ነው፡፡ ነጋሹ ወልድ ነው፡፡ ንግሥናው የልደት ምሳሌ ነው፡፡ እዚህ ላይ በአንዱ ዘውድ (በአብ) ብዙ ነገሥታት (ልጆች) ይነግሡበታል (ይወለዱበታል) ማለት ነው፡፡ ታዲያ ይኼ ምኑ ነው ሦስት ልደት ብለው የቆጠሩትን ሁለት እንድንል የሚያሳምነን? ምናልባት እዚህ ላይ “ዘውዱ” እንደ ልደት ተቆጥሮ ከሆነ ነጋሹ ወልድ አንጋሹ አብ ናቸው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ በአንዱ ዘውድ ሁለት ሦስት ነገሥታት እንደሚነግሡበት ሁሉ በአንዱ ልደትም ሁለት ሦስት ልጆችን ወለደ ያሰኝባቸዋልና ይህም የተዋረደ ከንቱ ምሳሌ እንደሆነ በዚህ እንረዳለን፡፡
ስለዚህ በመጽሐፍ ያልተጻፈ በሊቃውንት በመምህራን ያልተነገረ እንግዳ የሆነ ትምህርትን ዝም ብላችሁ መቀበል እንደማይገባችሁ ለሁሉም የቅብዓት እምነት ተከታዮች ሁሉ መልእክቴን አስተላልፋለሁ፡፡ መሰዳደቡን መጨቃጨቁን ትተን እውነትን ወደ መመርመር እንግባ፡፡ እኛ ከተሳሳትን መጽሐፍ ጠቅሳችሁ ሊቃውንቱን አብነት አድርጋችሁ እውነቱን አሳዩን እናንተ ከተሳሳታችሁ ግን እኛን ምሰሉን!!!
የጌታን ሁለት ልደታት ሊቃውንቱ እንዴት ይገልጹታል የሚለውን በቀጣይ ክፍል እንመለከታለን፡፡
ይቆየን፡፡
ይቀጥላል፡፡

Wednesday, March 29, 2017

የቅብዓት ምንፍቅና ምንጭ---ክፍል ፲፩


© መልካሙ በየነ
መጋቢት 21/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

የጌታ ልደቶች
በቅብአተ መንፈስ ቅዱስ ከበረ የሚሉ ወገኖች  “አብ ልጁ ወልድን ከድንግል ማርያም ማኅጸን በሥጋ ወለደው” ብለው እኛ ከምናምናቸው ልደቶች በተጨማሪ ይጠቅሳሉ። እዚህ ላይ ግን አንዳንድ ምሥጢር ያልገባቸው የቅብዓት እምነት ተከታዮች በጣም የሚገርም ነገር ይናገራሉ፡፡ “በተዋሕዶ ከበረ የምትሉ ሰዎች ገናን በ28 እና በ29 እያከበራችሁ ሦስት ልደት ታምናላችሁ” ይላሉ፡፡ እነዚህ በጣም የሚያስቁ ምሥጢር ያልጠነቀቁ ጨቅላ ቅባቶች ናቸው፡፡ ታህሳስ 28 እና 29 የልደት በዓል የሚከበርባቸው ቀናት ናቸው፡፡ እንደእነርሱ አስተሳሰብ ከሆነማ ጌታችን በየዓመቱ  ይወለዳል ማለት እኮ ነው፡፡ በዓል ማክበሪያ ቀንና እና የበዓሉ መከበሪያ ምክንያትንማ ጠንቅቀን ማዎቅ አለብን፡፡ ለምን ከዐራት ዓመት አንድ ጊዜ ታህሳስ 28 ቀን ልደትን ታከብራላችሁ የሚል ጥያቄ ከመጣ እሱን ሥርዓት ስለተሠራልን ዶግማ ስላልሆነ ነው ብለን  እንመልሳለን፡፡ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገት፣ ጰራቅሊጦስ፣ በየዓመቱ መቸ መቸ ነው የሚከበሩ ለምን ይቀያየራሉ ለምንስ በጥንተ ቀናቸው አይከበሩም ብለን ራሳችንን እንጠይቅ ልደትማ ከዐራት ዓመት አንድ ጊዜ ብቻ እኮ ነው ያውም በአንድ ቀን ልዩነት ብቻ፡፡  እነዚህ የጠቀስኩላችሁ በዓላት ግን በየዓመቱ ከጥንተ ቀናቸው እጅግ በራቀ ሁኔታ ነው የሚከበሩ ለምን ሥርዓት ቀኖና ስለሆነ ዶግማ መሠረተ እምነት ስላልሆነ ብቻ ነው፡፡ ሌላ ምሥጢር የለውም፡፡

ወልደአብ የተሰኘው የክህደት መጽሐፋቸው ገጽ 216-217 ስናነብ እንዲህ ይላል። “የጌታችን ልደቱ ስንት ነው ቢሉ ኹለት ነው። እንዴት ኹለት ነው እምቅድመዓለም በመለኮቱ ተወለደ ብለናል ኋላም በማኅጸን በሰውነቱ ከአብ ተወለደ እንላለን ዳግም ከእመቤታችን በስጋ በጎል ተወለደ እንላለን ይህማ ሦስት አይደለምን እንደምን ኹለት ነው ቢሉ እምቅድመዓለም በመለኮቱ የተወለደው ልደትና ዛሬ በማኅጸን በሥጋ በቅብአተ መንፈስ ቅዱስ የተወለደው ልደት አንድ ልደት ይባላል እንጅ ኹለት አይባልም። ኹለት ጊዜ ቆጥረነው አንድ ማለታችን እንዴት ነው ቢሉ እምቅድመዓለም በመለኮቱ የወለደው አብ ነው። ዛሬም በሰውነቱ በማኅጸን የወለደው አብ ነው እንጅ ሌላ አይደለም። ወላዲው ተወላዲው ዛሬም የተወለደበት መንፈስቅዱስ ያ የጥንት የባሕርይ ሕይወቱ ስለአልተለወጠ አንድ ልደት ይባላል እንጅ ኹለት ልደት አይባልም። ለዚህም ምሳሌ ያስረዳል ምሳሌ እንዴት ያስረዳል ቢሉ እነሆ ዛሬ ሰው አዲስ ሸማ ለብሶ ያነን በከረጢት ከቶ ዳግመኛ አውጥቶ ቢለብሰው አንዱን ሸማ ኹለት ጊዜ ለበሰው ተብሎ አንድ ሸማ ይባላል እንጅ ኹለት አይባልም። ዳግመኛ በአንድ ዘውድ ሁለት ሦስት ነገሥታት ቢነግሡበት ኹለት ሦስት ነገሥታት ነገሡበት ተብሎ አንድ ዘውድ ይባላል እንጅ ኹለት ዘውድ አይባልም” ይላል። እዚህ ጽሑፍ ላይ በዋናነት ሦስት መሠረታዊ ስህተቶችን እንመለከታለን፡፡
1.   በመጻሕፍት ተጽፎ የማናገኘው “አብ ወልድን በማኅጸነ ማርያም በቅብአተ መንፈስ ቅዱስ ወለደው” የሚል ስህተት አለበት፡፡
2.   መጻሕፍት “ለሰማያዊ ልደቱ እናት ለምድራዊ ልደቱም አባት አትሹለት” እያሉ እዚህ ላይ ግን “ለምድራዊ ልደቱ አባት ሽተውለታል” ስለዚህም ሁለተኛ ስህተት ብለን ቆጠርነው፡፡
3.   የተቀመጠው ምሳሌ “ሦስት ጊዜ የተቆጠረውን ልደት ሁለት” ብለን እንድንቀበለው የሚያደርግ ማስረጃ አለመሆኑ፡፡
በእነዚህ ቅደም ተከተሎች በማስረጃ እያስደገፍን የዚህን ስህተት እናጋልጣለን፡፡ “ወልድ ዋሕድ በተዋሕዶ ከበረ” የምንል ክርስቲያኖች የምናምናቸው ልደታት ሁለት ናቸው፡፡ እነዚህም፡-
1.  ቅድመዓለም ባሕርይ ዘእምባሕርይ አካል ዘእምአካል ሳይቀድም ሳይከተል በዚህን ጊዜ ተወለደ በማይባል ረቂቅ ጥበብ ወልድ ከአብ ያለ እናት የተወለደው ቀዳማዊው ልደት ነው፡፡
2.  የአዳምን በደል ለማጥፋት ከሴት የሚወለድበት ዘመን በደረሰ ጊዜ በኅቱም ድንግልና በግብረ መንፈስ ቅዱስ በተዋሕዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም ያለአባት የተወለደው ደኃራዊው ልደት ነው፡፡
ሊቃውንቱ “ቀዳማዊ ልደቱ በደኃራዊ ልደቱ ታወቀ” ይላሉ፡፡ ሁለቱም ልደታት ከሰው ኅሊና በላይ ከመመርመርም እጅግ የራቁ ናቸው፡፡ ማንም እነዚህን ልደታት መርምሮ አይደርስባቸውም በረቂቅ ምሥጢር የተከናወኑ ናቸውና፡፡ ስለዚህ ቤተክርስቲያናችን የምትቀበላቸው የምታምናቸው የምታስተምራቸው በመጻሕፍት የጻፈቻቸው የጌታ ልደቶች ቅድመ ዓለም ያለእናት ከአብ በመለኮት የተወለደው ልደት እና ድኅረ ዓለም ያለአባት ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ የተወለደው ልደት ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በቅብዓት መናፍቃን ዘንድ “ወልድ በማኅጸነ ማርያም በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ ከአብ ተወልዷል” የሚለው ሦስተኛው ልደት በየትኛውም የቤተክርስቲያናችን መጻሕፍት ዘንድ ተመዝግቦ አናገኘውም፡፡ ለዚህም በርካታ ማስረጃዎችን እንጠቅሳለን፡፡ በእውነት “ወልድ ከአብ ሁለት ጊዜ ተወለደ” የሚል መጽሐፍ ከወዴት ይገኛል? የትም አይገኝም፡፡ ታዲያ ይህ “ሦስተኛው ልደት” ከየት መጣ ስንል አንድ የሚጠቅሱት ጥቅስ አለ እርሱም መጽሐፈ ምሥጢር ምእራፍ 3 ቁጥር 46 ነው፡፡

ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በዚህ መጽሐፉ ላይ የጻፈው እንዲህ የሚል ነው፡፡ “ነገርነኬ በእንተ ህላዌ መለኮቱ ወትስብእቱ እምድኅረ ስጋዌሁ ኢንቤሎ ወልደ እግዚአብሔር በመለኮቱ ወወልደ እጓለእመሕያው በትስብእቱ፤ ድንግልኒ ወለደት ዘኢዚአሃ መለኮተ በዘዚአሃ ሥጋ ምስለ ዘዚአሃ ሥጋዌ ፤ አብኒ ወለደ ዘኢዚአሁ ሥጋ በዘዚአሁ መለኮት ምስለ ዘዚአሁ ኃይል ዘህሉና አምላክ ፤ ስለመለኮቱ እና ስለ ትስብእት ህልውና እነሆ ተናገርን፡፡ ሰው ከመሆኑ በኋላ በመለኮቱ የእግዚአብሔር ልጅ በሰውነቱም የሰው ልጅ አንለውም፡፡ ድንግልም ለእርሷ በተገባ ሥጋዌ የእርሷ በሆነ ሥጋ የእርሷ ያልሆነውን መለኮት ወለደችው ፤ አብም የባሕርይው ያልሆነውን ሥጋ የባሕርዩ ከሆነ የህሉና አምላክ ኃይል ጋር የእርሱ በሆነ መለኮት ወለደ” የሚል ነው፡፡ ከዚህ ትምህርት መካከል ቅብዓቶች አብ በማኅጸነ ማርያም ወልዶታል ለሚለው ክህደታቸው ቆርጠው የወሰዱት “አብም የባሕርይው ያልሆነውን ሥጋ የባሕርዩ ከሆነ የህሉና አምላክ ኃይል ጋር የእርሱ በሆነ መለኮት ወለደ” የሚለውን ነው፡፡ ልብ በሉ እንግዲህ መለኮታዊ አካል ሥጋዊ አካልን፤ ሥጋዊ አካልም መለኮታዊ አካልን፤ መለኮታዊ ባሕርይ  ሥጋዊ ባሕርይን፤ ሥጋዊ ባሕርይም መለኮታዊ ባሕርይን  ሊወልድ ይቻላልን? ሊቁ ይህን የተናገረው በእውነት እነርሱ እንደሚሉት ነውን? አይደለም፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የእውቀት ጽዋእን የጠጣ አባቶች ያላስተማሩትን እንግዳ ትምህርት ለመናገር ነውን? አይደለም፡፡ ሃይማኖተ አበው ዘጎርጎርዮስ ም 60 ቁ 20 ላይ “ዛሬ ግን ከድንግል ብቻ ተወለደ ድንግልናዋንም ባለመለወጥ አጸና ድንቅ የሚሆን መጽነስዋ የታመነ ይሆን ዘንድ ቅድመዓለም ከአብ እንደተወለደም ለማመን መሪ ይሆን ዘንድ” የሚለውን ትምህርተ ሊቃውንት ዘንግቶት ይሆን ለምድራዊ ልደቱ አባት የሻለት? አይደለም፡፡ ሊቁስ ወደ ምሥጢር ሄዶ “አብም የባሕርይው ያልሆነውን ሥጋ የባሕርዩ ከሆነ የህሉና አምላክ ኃይል ጋር የእርሱ በሆነ መለኮት ወለደ” ብሎ ተናገረ፡፡ ከተዋሕዶ በኋላ የቃል ገንዘብ ለሥጋ የሥጋ ገንዘብም ለቃል ገንዘቡ እንደሆነ እናምናለን፡፡ ታዲያ ይህንን ካወቅን ቃል ከሥጋ ጋራ በተዋሐደ ጊዜ ሥጋ “ወልደ አብ ቃለ አብ” መባልን ገንዘቡ አደረገ ብንል እውነት ነገር ነው፡፡ ስለዚህም ሥጋ ቀዳማዊ አምላክ ሆነ ቀዳማዊ አምላክ በመሆኑም ወልደ አብ ተባለ በሥጋ ወለደውም ተባለ፡፡ ለወልድ አባቱ የሆነ አብ ለክርስቶስም (ለሥግው ቃል) አባቱ ተባለ ማለት እኮ ነው፡፡ ስለዚህ ሥጋ ወልደአብነትን (የአብ ልጅ መባልን) ገንዘቡ አደረገ አለ ሊቁ፡፡ ይህን ምሥጢር አርቀቆ የተናገረበት ግሩም ትምህርት እንደሆነ በዚህ እንረዳለን፡፡ አብ በማኅጸነ ማርያም ወልድን ዳግም ወልዶት ቢሆን ኖሮ በግልጽ በጎላ በተረዳ ነገር በተናገረልን ነበር፡፡ ነገር ግን ሊቁ ይህንን አልተናገረውም፡፡ የመጽሐፈ ምሥጢር 3÷46ን ትርጓሜ በሰፊው ማብራሪያ ለማየት ከፈለጉ ይህንን ሊንክ ተጭነው ያንብቡ፡፡ ወንድማችን ዲያቆን ሰሎሞን በብሎጉ ላይ በጥሩ ማብራሪያ አስቀምጦታል እና ይህንን መድገም አያስፈልግም በሚል ነው፡፡

እነርሱ በተረዱት አረዳድ ከሆነማ “እመቤታንም በመለኮት ወልዳዋለች ያሰኝባቸዋል” እኛ ግን አባቶቻችን እንዳስተማሩን “ወልደ አብ በመለኮቱ ወልደ ማርያም በትስብእቱ” እንላለን፡፡ ይህም ማለት በመለኮቱ ከአብ ተወለደ በሰውነቱም ከድንግል ማርያም ተወለደ ማለት ነው፡፡ ድንቅነቱም እኮ ይህ ነው “መለኮትን በሰውነት መውለድ”፡፡ መለኮትን በመለኮት መውለድ፤ ሰውን በሰውነት መውለድማ ምን ይደንቃል? ይህ አያስደንቅም አያስገርምም ማለት አይደለም ነገር ግን በጣም የሚደንቀው በጣምም የሚገርመው “መለኮትን በሰውነት መውለድ” ነው ለማለት ፈልጌ ነው፡፡ መለኮትን በሥጋ መውለድ ማለት “ስፉህ፣ ረቂቅ፣ ምሉዕ የሆነን መለኮት ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በጸባብ ማኅጸን ተሸክሞ ጊዜው ሲደርስ ድንግልናዋን ሳይጥስ ሳይለውጥ ከአምላክነቱ ሳይለወጥ ሰው በሚወለድበት ሥርዓት መውለድ ነው” ይህ ድንቅ ጥበብ ረቂቅ ምሥጢር ነው፡፡ ሥጋ ከመለኮት ጋራ ሲዋሐድ በመጠባበቅ ነው፡፡ ተዋሕዶ ስንል ተዓቅቦ ያለበት ተዋሕዶ ማለታችን ነውና!!!
ይቆየን፡፡
ይቀጥላል፡፡

Tuesday, March 28, 2017

የቅብዓት ምንፍቅና ምንጭ---ክፍል ፲


© መልካሙ በየነ
መጋቢት 20/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ጠቅለል ባለ መልኩ የዛሬዎቹ የቅብዓት እምነት ተከታዮች ክፍል ፱ በተጠቀሱት አራቱም ባህሎች ውስጥ የሚዋኙ ናቸው፡፡ ተዋሕዶ ያለ ቅብዓት ክብርን አያሳልፍም በማለታቸው ለጥምቀት፣ ለተክሊል፣ ለንሥሐ መደምደሚያው ቁርባን እንደሆነ ሁሉ ለተዋሕዶም መደምደሚያው ቅብዓት ነው ያሰኝባቸዋል፡፡ ይህንንም መጽሐፋቸውን እየጠቀስን እንመልከተው፡፡ ወልደ አብ ገጽ 219 ላይ “ይህ የጸጋ ልጅነት የሌለው ባእድ ሥጋ እምቅድመ ዓለም የባሕርይ ልጅነት ካለው መለኮት ጋራ ቢዋሐድ የቃልን ገንዘብ ተቀብሎ ወልደአብ ቃለ አብ ቃለ መንፈስ ቅዱስ ሆነ ልጅነት አገኘ፡፡ ይህ ልጅነት ያለው ቃል ልጅነት ከሌለው ሥጋ ጋራ ቢዋሐድ በሥጋ ርስት ልጅነትን የሚሻ ሆነ፡፡ እንዘ ባዕል ውእቱ በኩሉ አንደየ ርእሶ እን ጳውሎስ ፪ኛ ቆሮ ም፰ ቁ፱ ስለዚህ ከእምቅድመ ዓለም ልደቱ ፩ድ ለማድረግ በሰውነቱ የባሕርይ ህይወቱን በመላ ተቀብሎ ከአብ ተወለደ እንጅ የቀደመ ልጅነቱስ አልተነሣውም፡፡ ወልድስ በሰውነቱ መንፈስ ቅዱስን ከአብ ተቀብሎ ባይወለድ ወልድ በሰውነቱ እንደ አብ ባልገዛም አብም ለወልድ በሰውነቱ አገዛዙን ክብሩን በመላ በሰፋ ባልሰጠውም ነበር ኢይሁብ ክብርየ ለባዕድ ለተሳትፎ ወስብሐትየ ለግልፎ እን ኢሳ ም፵፪ ቁ፰ መንፈስ ቅዱስን ከአብ ተቀብሎ ቢወለድ ግን እንደአብ ገዛ አዘዘ፡፡ አብም ለወልድ በሰውነቱ አገዛዙን ክብሩን ሰጠው አኮ ዘይሁብ እግዚአብሔር አብ መንፈሶ በመስፈርት አላ አብሰ ያፈቅር ወልዶ ወኲሎ ኲነኔሁ አወፈዮ ለወልዱ ውስተ እዴሁ እን ወን ዮ ም፫ ቁ፴፬፡፡ ወረሰዮ ወራሴ ለኲሉ እን ጳው ዕብ ም፩ ቁ፪” ይላል። ይህ የመጽሐፋቸው ክፍል እርስ በርሱ የሚጋጭ ሃሳብ ይዟል ነገር ግን የቅብአት እምነት ተከታዮች አይጋጭም ይላሉ። ስለዚህ የማይጋጭ ሃሳብ ከሆነ ሊስማማ የሚችለው እንደሚከተለው ይሆናል። መጀመሪያ ሁለት የተዋሕዶ ሂደቶች ይከወናሉ። የመጀመሪው “ይህ የጸጋ ልጅነት የሌለው ባእድ ሥጋ እምቅድመ ዓለም የባሕርይ ልጅነት ካለው መለኮት ጋራ ቢዋሐድ የቃልን ገንዘብ ተቀብሎ ወልደአብ ቃለ አብ ቃለ መንፈስ ቅዱስ ሆነ ልጅነት አገኘ” የሚለው መለኮት ከሥጋ ጋር ያደረገው ተዋሕዶ ነው። በዚህ ተዋሕዶ ላይ መለኮት ከሥጋ ጋር ተዋሐደ እንጅ ሥጋ ከመለኮት ጋር አልተዋሐደም። በዚህ ተዋሕዶ ሥጋ የቃልን ገንዘብ ገንዘቡ አድርጎ በቃል መጠሪያ ተጠራ ቃለ አብ ቃለ መንፈስ ቅዱስ ተባለ ማለት ነው። የሚገርማችሁ እስከዚህ ድረስ መለኮት የሥጋን ገንዘብ ገንዘቡ አላደረገም በሥጋ ስምም አልተጠራም። ስለዚህ ሙሉ ተዋሕዶ ይደረግ ዘንድ ሥጋ ከመለኮት ጋር መዋሐድ አለበት ይኸኛው ቀጣዩ ተዋሕዶ ነው። ሁለት ነጥላ ተዋሕዶዎች ናቸው እንግዲህ አንድ ሙሉ ተዋሕዶን የሚፈጥሩት። በእርግጥ ይህንን የምንላችሁ እነርሱ “ተዋሐደ” እያሉ ስለጻፉት እንጅ እንደ እኛ ትምህርት ግን ይኼ ተዋሕዶ አይባልም። ተዋሕዶ ከተባለም እንኳ የኅድረት ተዋሕዶ ሊሆን እንደሚችል ብቻ ነው የምናስበው። ቀጣዩ ተዋሕዶ ደግሞ የሥጋ ከመለኮት ጋር መዋሐድ ነው። “ይህ ልጅነት ያለው ቃል ልጅነት ከሌለው ሥጋ ጋራ ቢዋሐድ በሥጋ ርስት ልጅነትን የሚሻ ሆነ” ይላሉ ሥጋ ከመለኮት ጋር እንደተዋሐደ ለማጠየቅ። ቅድም ልጅነት አገኘ ቃለአብ ቃለ መንፈስ ቅዱስ ሆነ ያሉት ሥጋ አሁን ከመለኮት ጋራ ሲዋሐድ መለኮት በሥጋ ርስት ልጅነትን የሚሻ ሆነ፡፡ ምክንያቱም መለኮት ሥጋን ቢዋሐደው ሥጋ በመለኮት ርስት ልጅነትን አገኘ እንጅ ሥጋ ከመለኮት ጋር ስላልተዋሐደ መለኮት በሥጋ ርስት ልጅነት አላገነም ነበርና ይህንን ልጅነት ለማግኘት ሥጋ ከመለኮት ጋር ተዋሐደ ይላሉ። ስለዚህ ቃል በሥጋ ርስት ልጅነት ያገኝ ዘንድ ሥጋ ከመለኮት ጋር መዋሐድ ያስፈልገዋል ማለት ነው። ከዚህ ቀጥሎ እነዚህ ሁለት የተዋሕዶ ሂደቶች ከተጠናቀቁ በኋላ ይፈጠራል ይላሉ ይቅር ይበለንና። አርዮስ ወልድ በመለኮቱ ፍጡር ቢለው ክህደት ሆነበት ታዲያ እነዚህስ ወልድ ከሥጋ ጋራ ተዋሕዶ ተፈጠረ ሲሉ ክህደት የማይሆነው  እንዴት ነው? ከተዋሐደ በኋላ እንደተፈጠረ ወልደ አብ ገጽ 131 “ ሥጋ ሲፈጠር መለኮት ከሥጋ ጋራ ተዋሕዶ አብሮ ተፈጠረ ካላሉ እንደ ንስጥሮስ ፪ አካል ማድረግ ኃደረ በብእሲ ማለት ነውና ክህደት ነው” ይላሉ፡፡ ወልደ አብ ገጽ 127 ላይም እንዲሁ “… በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከተከፈለ ደመ ድንግልና ጋራ ተዋሕዶ ተፈጥሯልና” ይላሉ፡፡ ወልደ አብ ገጽ 126 ላይ ደግሞ ሲፈጠር እና ሲዋሐድ አንድ ጊዜ እንደሆነ ይናገራሉ  “… ተዋሕዶ ተፈጠረ ሳይዋሐድ አልተፈጠረም፡፡ ተዋሕዶ ሳይፈጠር አልቆየም፡፡ ሲዋሐድ ሲፈጠር አንድ ጊዜ ነው፡፡ ከተፈጥሮ ተዋሕዶ ቀደመ ባሉ ጊዜ ከቅብዓትም ተዋሕዶ ቀደመ ማለት ይሆናል” ብለው ጽፈዋል፡፡ እስካሁን ባየናቸው የመጽሐፍ ክፍሎቻቸው የቃል ከሥጋ ጋር ተዋሕዶ መፈጠርን የሚያስረዱ ናቸው ሎቱ ስብሐት፡፡  አሁን መለኮት ከሥጋ ጋር ሥጋም ከመለኮት ጋር ተዋሕዶ ተፈጥሯል ማን ፈጠረው? የሚለውን ጥያቄ ግን ማንም ሊመልሰው አይችልም ምክንያቱም አምላክ ከሥጋ ጋር ተዋሕዶ ተፈጥሯል ብለውናልና ከአምላክ ውጭ ማን ሊፈጥር ይችላል? ደግሞ በጣም የሚገርመው ጉዳይ “መለኮት ከሥጋ ጋር ተዋሕዶ ተፈጠረ ካላሉ ክህደት ነው” ማለታቸው ነው። እንግዲህ ይህ ተዋሕዶ ከተከናወነ በኋላ የተፈጠረው አካል እንደ አብ እንደ መንፈስ ቅዱስ ያዝዝ ይገዛ ዘንድ በቅብአት መክበር ያስፈልገዋል፡፡ ይህንንም ወልደ አብ ገጽ 166 ላይ “… መንፈስ ቅዱስን በመላ ተቀብሎ ከአብ ቢወለድ በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ የባሕርይ አምላክ የባሕርይ ልጅ ሆነ” ይላሉ፡፡ ከዚህእንደምንረዳው ለቅብዓት እምነት ተከታዮች ከተዋሕዶ በኋላ ቅብዓት መክበሪያ፣ መደምደሚያ እንደሆነ ነው፡፡ ሆኖም ግን እግዚአብሔር በመለኮት፣ በህልውና፣ በአገዛዝ፣ በመፍጠር፣ በማሳለፍ አንድ እንደሆነ ዘንግተውታል፡፡ ይህን የሥላሴ በመፍጠር አንድ መሆን ምሥጢር ባይዘነጉት ኖሮ መለኮት ከሥጋ ጋር ተዋሕዶ ተፈጠረ ማለት ክህደት እንደሆነ በተረዱት ነበር፡፡ በእርግጥ የሥላሴን በህልውና መገናዘብንም አልተረዱትም፡፡ ወልደ አብ ገጽ 232 ላይ “ተዋሕዶ ክብር የሚያሳልፍ ንዴትን የሚያጠፋ መስሏቸው የቃልን ክብር ለሥጋ ካሳለፍን ብለው ለመንፈስ ቅዱስ ቦታ ቢያጡለት በተዋሕዶ ከበረ ቅብአት አልረባውም ብለው ተነሥተዋል” ብለው መጻፋቸው የሥላሴን በህልውና መገናዘብ ባለማሰብ ነው፡፡ በህልውና እንደሚገናዘቡ ቢያውቁ ኖሮማ ወልድ ባለበት አብና መንፈስ ቅዱስም እንደሚገኙ ማወቅ ይገባቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ይህን ስላልተረዱ ለሦስቱም አካላት ማለትም ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ በዚህ የተዋሕዶ ምሥጢር ላይ አንተን ይህን ሥራ እኔ ይህን ልሥራ ተባብለው ሥራ እንደሚከፋፈሉ ሠዎች ለየብቻቸው የግብር ክፍፍል ሲያደርጉላቸው እንመለከታለን፡፡ ለዚህም ነው እኛን ሲወቅሱ የአምላክን ምሉዕ በኩለሄነት ዘንግተው በአንድ ቦታ ወስነው “ለመንፈስ ቅዱስ ቦታ ቢያጡለት” ማለታቸው፡፡ እነርሱ ለእያንዳንዳቸው ቦታ ሰጥተዋቸዋል ማለት ነው፡፡ ይህም ይታወቅ ዘንድ ወልድ በመለኮቱ ከሥጋ ጋር ተዋሐደ፡፡ ቀጥሎም አብ መለኮት የተዋሐደውን ሥጋ ፈጠረው፡፡ በመጨረሻም መንፈስ ቅዱስ ከመለኮት ጋር ተዋሕዶ በአብ የተፈጠረውን ሥጋ በቅብዓትነቱ አከበረው፡፡ ለዚህ ነው እኛ “በተዋሕዶ ከበረ” ስንል ለመንፈስ ቅዱስ ቦታ አጡለት ብለው የወቀሱን፡፡ ጭራሽ ለአብ ለወልድ እና ለመንፈስ ቅዱስ ለየግላቸው የሆነ ሥራ ፍለጋ ነው የገቡት!!!
በአጠቃላይ “በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ ከበረ” የሚለው ኑፋቄ ከተዋሕዶ በኋላ በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ መክበር አለበት የሚል አስተምህሮ የያዘ ነውና ቅብዓትን ለተዋሕዶ መደምደሚያ ሲያደርግ ይታያል፡፡ መጽሐፍ ግን ሊደግፋቸው አይችልም፡፡ ሃይማኖተ አበው አመ ዘሐዋርያት ምእራፍ 6 ክፍል 2 ቁጥር 28 ላይ “ዘገብረ ሎቱ ሥጋ እምድንግል ንጽሕት እግዝእትነ ማርያም ወውእቱ ገባሬ ኩሉ ሰብእ ወዘተንሥአ ባሕቲቱ እምነ ሙታን ውእቱ ዘያነሥእ ኩሎ ሙታነ፤ ከንጽሕት ድንግል እመቤታችን ሥጋን ፈጥሮ የተዋሐደ እርሱ ነው ሰውን ሁሉ የፈጠረ እርሱ ነው ከሙታን ተለይቶ የተነሣ ሙታንንም ሁሉ የሚያስነሣ እርሱ ብቻ ነው” ይላል፡፡ ስለዚህ ወልድ የተዋሐደውን ሥጋ ራሱ ፈጠረው እንጅ ከሥጋ ጋር ተዋሕዶ አልተፈጠረም፡፡

የቅብዓት ምንፍቅና ምንጭ---ክፍል ፱


© መልካሙ በየነ
መጋቢት 19/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ


ከተዋሕዶ በኋላ ቅብዓት ለምን አስፈለገ?
አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላት መጽሐፋቸው ገጽ 780 ላይ የቅብዓት ባህል 3 ክፍል አለው ይላሉ፡፡ መጀመሪያ በፋሲል ዘመን የተነሡት እነዘኢየሱስ መጽሐፍ “አንደየ ርእሶ” ይላልና “ቃል በተዋሕዶ ዜገ ከሥጋ ሲዋሐድ የባሕርይ ክብሩን አጣ ለቀቀ ሲቀባ ወደ ጥንተ ክብሩ ተመልሶ በሰውነቱም በአምላክነቱም አንድ ወገን በቅብዓት የባሕርይ ልጅ ሆነ ብለዋል” ይላሉ፡፡ በፋሲል ዘመን የነበሩት የመጀመሪያዎቹ የዚህ የክህደት አስተምህሮ ጠንሳሾች ቃል ከሥጋ ጋር ሲዋሐድ የባሕርይ ክብሩን ከዐይን ጥቅሻ በምታንስ ጊዜ ስለዜገ ማለትም ስለደሐየ፣ ስለ አጣ፣ ስለተቸገረ ወደ ቀደመ ባሕርይ ክብሩ ለመመለስ ቅብዓት ያስፈልገዋል ባዮች ናቸው፡፡ ይህ አስተምህሮ ደግሞ አስቀድመን እንዳየነው ሚጠትና ውላጤ የተባበሩበት ክህደት ነው፡፡ ዛሬም በተወሰኑ ሰዎች ይህ ምንፍቅና ሲነገር እንሰማዋለን፡፡ በመጽሐፋቸው ላይም ወልደ አብ ገጽ 219 አጣ፣ ደሐየ፣ ተቸገረ (ዜገ) ሲሉ “…ይህ የጸጋ ልጅነት የሌለው ባእድ ሥጋ እምቅድመ ዓለም የባሕርይ ልጅነት ካለው መለኮት ጋራ ቢዋሐድ የቃልን ገንዘብ ተቀብሎ ወልደአብ ቃለ አብ ቃለ መንፈስ ቅዱስ ሆነ ልጅነት አገኘ፡፡ ይህ ልጅነት ያለው ቃል ልጅነት ከሌለው ሥጋ ጋራ ቢዋሐድ በሥጋ ርስት ልጅነትን የሚሻ ሆነ” ብለዋል፡፡ ቀጥለውም ወደ ቀደመ ክብሩ መመለሱን ሲገልጹ ወልደ አብ ገጽ 166 ላይ  “… መንፈስ ቅዱስን በመላ ተቀብሎ ከአብ ቢወለድ በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ የባሕርይ አምላክ የባሕርይ ልጅ ሆነ” በማለት ጽፈዋል፡፡ በተጨማሪም ወልደ አብ ገጽ 219 ላይ “ወልድስ በሰውነቱ መንፈስ ቅዱስን ከአብ ተቀብሎ ባይወለድ ወልድ በሰውነቱ እንደ አብ ባልገዛም አብም ለወልድ በሰውነቱ አገዛዙን ክብሩን በመላ በሰፋ ባልሰጠውም ነበር” በማለት አብን ሰጭ ወልድን ደግሞ ተቀባይ መንፈስ ቅዱስን ስጦታ ሲያደርጉ ይታያሉ፡፡ ስለዚህ ነው እንግዲህ ቅብዓተ መንፈስ ቅዱስን ጠቀመው ረባው ማለታቸው፡፡ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ ባይወለድ ኖሮ ወልድ እንደ አብ እንደ መንፈስ ቅዱስ መግዛት ማዘዝ አይችልም ነበር ማለታቸው ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ ቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ ያስፈልገዋል ለማለት እንደሆነ እንረዳቸዋለን፡፡ ስለዚህ በመንፈስ ቅዱስ ቅብዓትነት የባሕርይ አምላክ የባሕርይ ገዥ ሆነ ማለት ያስነቅፋል፡፡ ይህንንም ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ብሏል “ዳግመኛ በዚህ ድርሳን እግዚአብሔር ሕያው አምላክ የሆነ ሥጋን በመንፈስ ቅዱስ ፈጠረ ዓለምንም በእርሱ አዳነ ብንል ዐላዋቆች ይነቅፉናል” ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈወርቅ ም 68 ክ 28 ቁ 43፡፡
ወልደ አብ ገጽ 230 ላይ ደግሞ ለመለኮት የማይቀፀል ቃል እንዲህ ብለው ቀፀሉ “በዚህም በባሕርይ ልጅነቱ እኛ ብቻ ተጠቅመንበት አልቀረንም እርሱም ተጠቀመበት እንጅ” ይላሉ፡፡ ወልድ ምን ተጎድቶ ምን ጎድሎበት ነው በመወለዱ ተጠቀመ የሚባለው፡፡ ይባስ ብለው ገጽ 233 ላይ “ቅብአቱስ እንደረባው ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ እንደአስተካከለው...” ብለው ወልድን ከባሕርይ ክብሩ ዝቅ ሲያደርጉት ይስተዋላሉ፡፡ በመወለዱ ተጠቀመ የሚባለው በእውነት ምን ጎድሎበት ይሆን? ሃይማኖተ አበው ዘኤፍሬም ም 47 ቁ 5 ግን እንዲህ ይላል “የድንግልን ሥጋ መረጠ ሰው መሆኑን ሊያስረዳ ፍጹም አካሉን በማኅጸኗ ፈጠረ ከእርሷ ሥጋን የተዋሐደ እጠቀምበታለሁ ብሎ አይደለም” ይላል፡፡
ሁለተኛው ባህላቸው በአንደኛው ዮሐንስ ዘመን የተነሡት እነ አካለ ክርስቶስ “ዜገ” የሚለውን የእነ ዘኢየሱስን ትምህርት ነቅፈው አጸይፈው መጽሐፍ “እስመ ተዋሕዶ አእተታ ለምንታዌ ይላልና ሥጋ በተዋሕዶ አንድ አካል ሆነ እንጅ የአምላክነት ክብር አላገኘም፡፡ ሲቀባ ግን ክብር ተላልፎለት ተፈጥሮ ተገብሮ ጠፍቶለት በቅብዓት የባሕርይ ልጅ የባሕርይ አምላክ ሆነ ብለዋል” ከመጀመሪያዎች የሚለያቸው መቀባትንና መለወጥን ለሥጋ ብቻ መስጠታቸው ነው፡፡ በዚህ ዘመንም የተነሡት ይዘውት የመጡት ክህደት ከመጀመሪያዎቹ ተመሳሳይነት ያለው ክህደት ነው፡፡ የዛሬዎቹ የቅብዓት አማኞችም ይህንን ባህል ደግፈው ይታያሉ፡፡ ወልደ አብ ገጽ 232 ላይ  “ተዋሕዶ ክብር የሚያሳልፍ ንዴትን የሚያጠፋ መስሏቸው የቃልን ክብር ለሥጋ ካሳለፍን ብለው ለመንፈስ ቅዱስ ቦታ ቢያጡለት በተዋሕዶ ከበረ ቅብአት አልረባውም ብለው ተነሥተዋል፡፡ ለሊህ ምን ይመልሷል ቢሉ ተዋሕዶማ ሁለትነትን አጠፋ አንድነትን አጸና እንጅ ንዴትን አላጠፋም ክብርን አላሳለፈም” ይላሉ፡፡ እነርሱ ተዋሕዶን የሚረዱበት አረዳድ እኛ የተዋሕዶ አማኞች ከምንረዳበት አረዳድ እጅጉን የተለየ እንደሆነ በዚህ እንገነዘባለን፡፡ ተዋሕዶ ለእነርሱ ሁለትነትን አጥፍቶ አንድነትን ብቻ ያጸና ነው እንጅ የሥጋ ንድየት በቃል ብዕልነት እንዳልተወገደ ያምናሉ፡፡ እኛ ደግሞ ሁለትነት ጠፍቶ አንድነት ሲጸና የሥጋ ንድየት በቃል ብእልነት ተወግዶ ቅድምና የሌለው ሥጋ ቀዳማዊ ሆነ አምላክም ሆነ እንላለን፡፡ ሰው አምላክ ሆነ አምላክ ሰው ሆነ ማለት ስለዚህ ነው፡፡ የሥጋ ገንዘብ (ከኃጢአት በቀር) ለመለኮት ፤ የመለኮትም ገንዘብ ለሥጋ ገንዘቡ ሆነ የምንለው በተዋሕዶተ መለኮት ነው እንጅ በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ አይደለም፡፡
ሦስተኛው ባህላቸው በዐጼ ቴዎድሮስ ዘመን የተነሡት እነአለቃ ጎሹ ናቸው፡፡ እነዚህ ደግሞ በቅብዓት ብቻ ማለትን ነቅፈው “መጽሐፍ በሁለቱም ሁሉ በተዋሕዶ ከበረ በቅብዓት ከበረ ይላልና ቅብዓት ያለተዋሕዶ ተዋሕዶም ያለቅብዓት ብቻ ብቻውን አያከብርም በተዋሕዶና በቅብዓት በአንድነት የአምላክነት ክብር ከብሮ የባሕርይ ልጅ ሆነ ብለዋል” ይላሉ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፡፡ በዚህ ዘመን ያሉት የቅብዓት እምነት አራማጆችም ይህንን ደግፈው ይታያሉ፡፡ ወልደ አብ በተሰኘ መጽሐፋቸው ገጽ 126 ላይ “… ተዋሕዶ ተፈጠረ ሳይዋሐድ አልተፈጠረም፡፡ ተዋሕዶ ሳይፈጠር አልቆየም፡፡ ሲዋሐድ ሲፈጠር አንድ ጊዜ ነው፡፡ ከተፈጥሮ ተዋሕዶ ቀደመ ባሉ ጊዜ ከቅብዓትም ተዋሕዶ ቀደመ ማለት ይሆናል” በማለት በተዋሕዶ እና በቅብዓት እንደከበረ ይናገራሉ፡፡
ሌላው አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ራሳቸው ከቅብዓት ሦስቱ ባሕሎች ካሏቸው ውጭ ሌላ ባህል አላቸው፡፡ እርሳቸው እነዚህን ሦስቱን የቅብዓት ባህሎች ከገለጹ በኋላ ማብራሪያ ብለው የገለጹት ሌላ ባህል ውስጥ የሚያስገባ ክህደት ነው፡፡ እርሳቸው “ተቀብዐ” የሚለው አንቀጽ ለቃል በመሆኑ “ቃል መንፈስ ቅዱስን በመቀባቱ መሢህ፣ ንጉሥ፣ ዳግማይ፣ በኩረ ምእመናን ሆነ” ይላሉ፡፡ ይህ የአለቃ ኪዳነ ወልድ አስተምህሮ ወልድን ፍጡር ነው ካለው ከአርዮስ የሚደምር ክህደት ነው፡፡ አርዮስ ወልድን በመለኮቱ ፍጡር እንዳለው ሁሉ አለቃ ኪዳነ ወልድም የጻፉት ወልድ በክብር በሥልጣን ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ እንደሚያንስ ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ባህል ከአርዮስ ባህል ያስገባል፡፡ ምክንያቱም “ቃል መንፈስ ቅዱስን በመቀባቱ ከበረ” የሚል ሌላ ባሕል ነው፡፡ “ቃል ክቡር አምላክ የሆነው በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ ነው” ማለታቸው መሆኑን ልብ ይሏል፡፡
ከላይ ባየናቸው የቅብዓት ባሕሎች ውስጥ የመለኮት ወደ ሰውነት መለወጥን (ውላጤን) ደግፈው የሚገኙ ክህደቶች ናቸው፡፡ ከዚህ ውላጤ በኋላ ደግሞ በቅብዓት ከከበረ በኋላ አምላክ ሆነ እንደ አብ እንደ መንፈስ ቅዱስ ገዛ ይላሉና ወደ አምላክነት ክብር መመለስን (ሚጠትን) ያሳያል፡፡ ስለዚህ በእነዚህ በሦስቱም ውላጤና ሚጠት ይታያል፡፡ እናውቃለን ምሥጢር እንጠነቅቃለን የሚሉ የዘመናችን የቅብዓት እምነት ተከታዮች በእነዚህ ከላይ በተጠቀሱት ሦስት ባሕሎች ውስጥ የተወሸቁ ናቸው፡፡ ሦስቱንም ዓይነት ባሕል ደግፈው የሚገኙ ናቸው፡፡ ስለዚህ ነው እንግዲህ “በቅብዓተ መንፈስ ቅዱስ ከበረ” ማለት ክህደት ነው ምንፍቅና ነው የምንለው፡፡
ይቆየን፡፡
ይቀጥላል፡፡