Tuesday, November 29, 2016

“እናቱ ስትባይ ለእኔም እናቴ ነሽ”

© መልካሙ በየነ

ኅዳር 21/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================
በመጀመሪያ  በሰላም በፍቅር በአንድነት ጠብቆ ለዚህ ለተቀደሰው ዕለት ያደረሰንን የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ የሆነውን አምላካችንን አመሰግነዋለሁ፡፡ ይህች ዕለት የተከበረች እና የተቀደሰች ከፍ ከፍም ያለች ናት፡፡ ካህኑ ዘካርያስ በቤተመቅደስ እንደ ፋና ስታበራ እመቤታችንን ተመልክቶባታል፡፡ ምንኛ የታደለ ካህን ነው? ቤተመቅደሳችንን አረከሰችብን ብለው ከቤተመቅደስ ለማባረር ነገር የሚሸርቡ ካህናት በነበሩበት በዚያ ወቅት የእግዚአብሔር አገልጋይ ቅዱሱ ካህን አምላክን ያጠመቀውን ትልቅ ነቢይ የወለደ ዘካርያስ እመቤታችንን ያከብራት እና ይገዛላት ይታዘዛትም ነበር፡፡ ይህ ካህን ከሴቶች ሁሉ የተለየ ድንቅ ነገር በእርሷ እንደሚደረግ መንፈስ ቅዱስ ገልጾለታል፡፡ ምሥጢረ ሥጋዌ በእርሷ እንደሚከናወን ተረድቷል፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለእውራን ብርሃናቸው፣ ለኃንካሳዎች ምርኩዛቸው፣ ለማይሰሙትም የመስሚያ ጆሯቸው፣ ለማይናገሩትም ልሳናቸው መግባቢያቸው፣ ለተራቡት ምግባቸው፣ ለታመሙት መድኃኒታቸው፣ ለተቸገሩት ደራሻቸው፣ ለተጨነቁት አረጋጊያቸው፣ ለተሠበሩት ጠጋኛቸው ናት፡፡ በእውነት ማንም የማይመስላት ማንም የማይተካከላት ማንም የማይደርስባት በማንም የማትመረመር ድንቅ እና ልዩ ፍጥረት ናት፡፡ በእግረ ኅሊናችን የዓለምን ዳርቻ ሁሉ ብናዳርስ፣ በክንፈ ኅሊናችን ሰማየ ሰማያት ብንመጥቅ፣ ወደ ጥልቁ እመቀ እመቃት ብንወርድ አንደርስባትም፡፡

ድንግል ማርያም እናት ናት፡፡ እናትነቷ ግን በዘር በሩካቤ ለተወለደ ህጻን አይደለም፤ በግብረ መንፈስ ቅዱስ ያለ ዘር ያለ ሩካቤ በማይመረመር ምሥጢር ለወለደችው አምላክ ነው እንጅ፡፡ እርሷ ልጅ ተብላለች፡፡ ወለተ ዳዊት ወለተ ኢያቄም (የዳዊት የኢያቄም ልጅ) ብለናታል፡፡ እርሷስ በዘር በሩካቤ ከሃና እና ከኢያቄም የተገኘች ናት፡፡ እርሷስ ልጅ ስትባል ብትቆይም እናት ለመባል በቅታለች፡፡ ድንግል ወእም (ድንግል እና እናት) ብለናታል፡፡ በተለያዩ ዘመናት የተነሡ ቅዱሳን፣ ሊቃውንት ድንግል ማርያምን በልዩ ልዩ ምሳሌዎች እየመሰሉ አስረድተውናል፤ በተለያዩ ቃላት አመስግነዋታል፡፡ ከምስጋናቸውም በላይ ስትሆንባቸው፤ የተደረገላትን ድንቅ ምሥጢርም ሲመረምሩ “ናርምም፤ ዝም እንበል” ይላሉ፡፡ አባ ሕርያቆስ እመቤታችንን የሚመስልበት ምሣሌ ቢያጣ “በመኑ ወበአምሳለ መኑ ናስተማስለኪ፣  በምን እና በምን ምሳሌ እንመስልሻለን” አለ፡፡ ይህ ቅዱስ አባት ምሳሌ አጣላት፡፡ ከፍ ብሎ በሰማይ ዝቅ ብሎ በምድር እንዳይመስላት የሰማይ እና የምድርን ፈጣሪ ዘጠኝ ወር በማኅጸኗ ተሸክማዋለች፡፡ ፈጣሬ ኩሉ (የሁሉ ፈጣሪ እና አስገኝ) ጌታን በጭኗ ታቅፈዋለችና፡፡ በእውነት በምን እንመስላታል?

ድንግል ማርያም እናት ተባለች፡፡ እናትነቷ ለዘለዓለም ልጅ ሲባል ለሚኖረው አምላክ ነው፡፡ ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷም ነፍስን ነስቶ በተዋሕዶ ተወልዷል፡፡ እርሱ በዘመን ብዛት አባት አይባልም፡፡ እኛ ልጅ ስንባል ብንኖር አባት ወይም እናት የምንባልበት ዘመን ይመጣል፡፡ እኛ ከእናት እና ከአባቶቻችን ብንወለድ እና ልጆች ብንባልም ባል ወይም ሚስት አግብተን ትዳር መስርተን ልጆችን ወልደን ልጅ ከመባል አባት ወይም እናት ወደመባል እንሸጋገራለን፡፡ አምላካችን ፈጣሪያችን ግን ለዘላለም ወልድ ሲባል ይኖራል፡፡ አስቀድሞ በማይመረመር ምሥጢር ከአብ ያለ እናት አሁን ደግሞ ከድንግል ማርያም ያለ አባት እንበለ ዘርእ ተወለደ፡፡ በፊትም ከአብ ሲወለድ ወልድ (ልጅ) ነው ዛሬም ከእመቤታችን ሲወለድ ወልድ (ልጅ) ነው፡፡ ዘመን ሲበዛ ወልድ (ልጅ) ወልድነቱ (ልጅነቱ) ተለውጦ አብ (አባት) አይሆንም፡፡ እመቤታችን ከሃና እና ከኢያቄም ተወልዳ ልጅ ስትባል ብትቆይም በኋላ ግን እናት ተብላለች፡፡ አምላክ ግን በፊትም አሁንም ያው ወልድ ነው፡፡ በፊትም አሁንም ወልድ (ልጅ) ለሚባል አምላክ ወልድ (ልጅ) ከመባል እናት ወደ መባል ለተሸጋገረችበት ምሥጢር ኅሊናችን እጹብ ድንቅ ይላል፡፡

ድንግል ማርያምስ እናት መባሏ ለአምላክ ብቻ አይደለም፡፡ ለእርሱ እናቱ ስትባል ለእኛም እናታችን ትባላለች፡፡ ይህንንም የሰጠን አምላካችን ነው፡፡ በዮሐ 19÷27 ላይ በወንጌላዊው ዮሐንስ በኩል ለሁላችን እናት ልትሆን አምላክ ሰጥቶናል፡፡ እናቱን እነኋት እናታችሁ ብሎ አስረክቦናል፡፡ ስሟን ጠርተን ዝክሯን ዘክረን እናታችን ብለን ውዳሴዋን ቅዳሴዋን አድርሰን የሞት ዜና ከማይነገርበት መንግሥተ ሰማያት እንገባ ዘንድ እንማጸናታለን፡፡ 

Wednesday, November 23, 2016

“ጾመ ነቢያት”

© መልካሙ በየነ

ኅዳር 14/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================
ይህ ጾም የገና ጾም በመባልም ይጠራል፡፡ ነቢያት እግዚአብሔር ለአዳም የሰጠውን ተስፋ እየጠበቁ አምላክ ይወርዳል ይወለዳል ብለው የጾሙት ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም በሦስቱ ዘመናት ማለትም በዘመነ ማቴዎስ፣ በዘመነ ማርቆስ እና በዘመነ ሉቃስ ኅዳር 16 ይጀምርና ታህሳስ 29 ይፈሰካል፤ በዘመነ ዮሐንስ ግን ኅዳር 15 ቀን ጀምሮ ታህሳስ 28 ቀን ይፈሰካል፡፡ እንደዚህ ሲሆን በአራቱም ዓመታት የጾሙ ቀናት 43 ይሆናል ማት ነው፡፡ ነገር ግን ከአራት ዓመት አንድ ጊዜ ኅዳር 15 የሚገባው ጾም ስለሚረሳ ሁልጊዜ ኅዳር 15 ቀን ጾሙ ይጀምራል፡፡ በዚህም የተነሣ በሦስቱ ዘመናት 44 ቀናት ይሆናል በዘመነ ዮሐንስ ግን 43 ቀናት ይጾማል፡፡ በአራት ዓመት አንድ ጊዜ የጾሙ ቀናት በ 1 ቀን ይቀንሳል፤ በሦስቱ ዘመናት 44 ቀናትን የምንጾመው ለጾም ማድላት ተገቢ ስለሆነ ነው፡፡
ስለዚህ ነቢያቱን አርአያ አብነት አድርገን እግዚአብሔር በተስፋ በበረከት ያኖረን ዘንድ፣ በጎውን የልቦናችንንም መሻት ሁሉ ይፈጽምልን ዘንድ፣ እንደ ቅዱሳን አባቶቻችን በቃሉ እንኖር ዘንድ እንጾመዋለን፡፡ ይህ ጾም በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15 ቁጥር 568 ላይ “ከእነርሱም የሚያንስ እንደ ረቡዕና እንደ ዓርብ የሚሆን አለ፡፡ ይኸውም ከልደት አስቀድሞ የሚጾም ጾም ነው፡፡ መጀመሪያው የኅዳር እኩሌታ ፋሲካው የገና በዓል ነው” በማለት መዝግቦት እናገኘዋለን፡፡ ሆኖም ግን አንዳንድ ወገኖች የጾሙን መግቢያ እና መውጫ ሲከራከሩበት እናያለን፡፡ ነገር ግን ይህ ቀኖና ቤተክርስቲያን እንጅ ዶግማ ባለመሆኑ የሚያከራክረን ጉዳይ ሊሆን አይገባውም፡፡ ፍቅረ እግዚአብሔርን በማሰብ ወደ ፍቅር ተመልሰን ለጾም በማድላትና ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን በማሰብ በፍቅር እንድናደርገው አባቶች ይመክሩናል፡፡ ስለዚህ በተሠራልን ሥርዓት እንመራ ዘንድ እመክራለሁ፡፡
በዚህ ጾም የሚነሣው መሠረታዊ ጉዳይ ነቢያቱ ዐርባ ቀናትን ብቻ ነው የጾሙት ይህ በትርፍነት የተጨመረው ዐራት ወይም ሦስት ቀን ከየት መጣ የሚል ነው፡፡ ነቢያቱ አርባ ቀናትን ጾሙ ስንል ኅዳር 19 ቀን ጀምረው ታህሳስ 29 ላይ ጾሙን ፈጸሙ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን አኛ ኅዳር 15 ቀን ጾሙ ይጀምራል እንላለን ይህ አይጣላምን ቢሉ አይጣላም፡፡ ለዚህ ማስረጃችን፡-
1ኛ. ከላይ እንዳየነው ፍትሐ ነገሥቱ የዚህን ጾም መግቢያ ሲገልጽ የኅዳር እኩሌታ ስላለ ነው፡፡ የህዳር እኩሌታ ደግሞ ህዳር 15 እንጅ ህዳር 19 አይደለም፡፡ 2ኛ. ስንክሳሩ ኅዳር 15 “ወበዛቲ ዕለት ጥንተ ጾመ ስብከተ ጌና ዘውእቱ ልደቱ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ሎቱ ስብሐት ዘሠርዕዎ ክርስቲያን ያዕቆባውያን ዘግብጽ ሣህሉ ወምሕረቱ የሃሉ ምስሌነ ለዓለመ ዓለም አሜን፤ በዚችም ቀን የስብከተ ጌና ጾም መጀመሪያ ነው፡፡ ይህም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለተወለደበት በግብጽ የሚኖሩ ያዕቆባውያን የሠሩት ነው፡፡ ይቅርታው ቸርነቱ ከእኛ ጋር ይኑር ለዘለዓለሙ አሜን” በማለቱ የህዳር እኩሌታ የሚለውን ኅዳር 15 ነው እንላለን፡፡
3ኛ. ሐዋርያው ፊልጶስ ኅዳር 16 በሰማእትነት ካሳረፉት በኋላ ሥጋውን ሊያቃጥሉ ሲነሡ መልአከ እግዚአብሔር ሥጋውን ሰወረባቸው፡፡ ከዚህ በኋላ ደቀመዛሙርቱ ከዕለቱ ጀምረው 3 ቀናትን እንደጾሙ  በኅዳር 18 ሥጋውን ሰጣቸውና ቀበሩት፡፡ ስለዚህም ሦስቱ ጾም ጾመ ፊልጶስ ተብሎ ተጨመረ፡፡

4ኛ. በዓለ ልደት ረቡዕና ዓርብ ቢውል ይበላበታልና ለዚያ ማካካሻ ወይም ምትክ የምትሆን ጾም የገሐድ ጾም አንድ ቀን ከጾመ ፊልጶስ በፊት ተጨመረችና ኅዳር 15 ቀን እንዲጾም አዘዙን፡፡ ጌታ የጾመው ጾም ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት ሆኖ ሳለ 55 ቀናትን እንደምንጾመው ያለ ነው፡፡ የመጀመሪያውን ሳምንት ጾመ ሕርቃል የመጨረሻውን ሳምንት ደግሞ የሕማማት ሳምንት በማለት እንደምንጾመው ሁሉ ይህንንም እንዲሁ አደረግን፡፡ ይህም የአባቶቻችን ትእዛዝ የአባቶቻችን ሥርዓት ነውና እኛም ተቀበልነው፡፡ አስቀድመን እንደተናገርነው በጾም ምክንያት ክርክር ቢነሣ መጾም ከመብላት እጅግ ይሻላል እንዳሉን እንጾመው ዘንድ ይገባናል፡፡

Friday, November 11, 2016

“ሁለቱ የሰይጣን ቀስቶች”

© መልካሙ በየነ

ኅዳር 2/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================
ዲያብሎስ ጥንተ ጠላታችን ነው፡፡ በአዳምና በሔዋን ላይ መርዙን ረጭቶ ከተድላ ቦታቸው ከገነት አስወጥቷቸዋል፡፡ ይህ ጠላት ዛሬ ድረስ በተለያዩ አጋጣሚዎች ቀስቱን ይወረውርብናል፡፡ ከቀስቱ ማምለጥና አለማምለጥ ግን በራሳችን ብርታትና ድክመት የተወሰነ ነው፡፡ ሰይጣን በዋናነት ሁለት ቀስቶችን ይወረውርብናል፡፡ የሚገርመው ነገር አንዱን ቀስት ስታመልጡ የውጊያ ስልቱን ቀይሮ በሌላ ቀስት መጠቀም እና ማጥቃት መቻሉ ነው፡፡ ብዙዎቻችን ሰይጣንን እንደ ቁራ ጥቁር፣ ጥርሱ የገጠጠ፣ ዓይኑ የፈጠጠ፣ ጥፍሩ የዘረዘረ ወዘተ ስለሚመስለን ጸአዳ ሆኖ በውበት አምሮና ደምቆ ሲመጣ እንታለላለን፡፡  ለመሆኑ ሰይጣን የሚጠቀማቸው ቀስቶች ምንድን ናቸው?

እኛን ለማጥቃት እና ለመማረክ ሰይጣን በዋናነት ሁለት ቀስቶችን ይጠቀማል፡፡ እነዚህንም እንደሚከተለው እንዘረዝራለን፡፡
1.   ጽድቅ እንዳትሠራ ማድረግ፤ ሰይጣን የጽድቅ ሥራ ሁሉ ጠላት ነው፡፡ ምክንያቱም ጽድቅ አይስማማውምና ነው፡፡ ሰይጣን የሚችለውን አቅም ሁሉ ተጠቅሞ ከጽድቅ ሥራ ያርቅሃል፡፡ አንተ በነፍስህ ተገድደህ ጽድቅ ልትሠራ ስትሞክር እርሱ ሥጋህን ተጠቅሞ ወደ ኃጢአት ይመራሃል፡፡ ስለዚህም ሰይጣን እንዳትጾም፣ እንዳትጸልይ፣ እንዳትሰግድ፣ እንዳትመጸውት፣ እንዳትራራ፣ ህግጋተ እግዚአብሔርን እንዳትጠብቅ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን እንዳታነብ፣ ቅዱሳት መካናትን እንዳትሳለም፣ ንስሐ እንዳትገባ፣ ሥጋ ወደሙን እንዳትቀበል፣ እንዳታስቀድስ፣ እንዳትዘምር፣ ድሆችን እንዳትረዳ፣ የተራቡትን እንዳትመግብ፣ የታሠሩትን እንዳትጠይቅ፣ የታመሙትን እንዳትጎበኝ፣ ወንጌልን እንዳትማር እና እንዳታስተምር፣ ቅዱሳንን አማላጆቼ እንዳትል፤ በእግዚአብሔር ህልውና እንድትጠራጠር፣ ጉቦ እንድትቀበል፣ በአራጣ እንድታበድር፣ በሃሰት እንድትመሰክር ወዘተ ያደርግሃል፡፡ የቅድስና ሥራ የሚባል ነገር እንዳትሠራ ሰይጣን ቀስቱን ይወረውርብሃል፡፡ አንተም ቀስቱን መመከት ካልቻልክ ዕድሜ ልክህን የጽድቅ ሥራ ሳትሠራ ትኖራለህ፡፡ ነገር ግን ቀስቱን የመመከት አቅም ኖሮህ ሰይጣንን ማሳፈር ከቻልክ ወደ ጽድቅ መንገድ እንደገባህ ታውቃለህ፡፡ ሆኖም ግን ከሰይጣን ቀስት አሁንም ቢሆን አታመልጥም፡፡ ጽድቅ እንዳትሠራ ከሚያደርግህ ጠላት ጋር ተዋግተህ ማሸነፍ ከቻልክ ሰይጣን ቀስቱን ይቀይራል፡፡ ምክንያቱም ጽድቅን ለመሥራት ቆርጠሃልና፡፡ ጽድቅን ለመሥረት ከቆረጥክ ያን ጊዜ ሰይጣን በሌላ ቀስት ይዘጋጅና ይመጣሃል፡፡ እርሱም ሁለተኛው ቀስት ሲሆን በውስጡ ሁለት የውጊያ ስልቶችን የያዘ ነው፡፡
2.  ዋጋ እንዳታገኝበት ማድረግ፤ ጽድቅን እንዳትሠራ ታግሎህ አንተ ግን አልሸነፍም ብለህ የሰይጣንን ምክር አልሰማም ካልክ ሰይጣን በዚህኛው ቀስት ሊያጠቃህ ይሞክራል፡፡ አሁን ሰይጣን ጽድቅ እንዳትሠራ ማድረግ ላይ ተስፋ ቆርጧል፡፡ ስለዚህ በምትሰራው የጽድቅ ሥራ ዋጋ እንዳታገኝ ማድረግ ይጀምራል፡፡ ይህንንም ቀስት የሚወረውርባቸው ሁለት ስልቶች አሉት፡፡ እነዚህም፡-
v  ባለህ ማስቀጠል፤  ሰይጣን በምትሠራው ሥራ ዋጋ እንዳታገኝበት እና ተስፋ የምታደርጋትን ቦታ እንዳትወርስ ማድረግ ይፈልጋል፡፡ ስለዚህ ያለው ምርጫ የጀመርካትን ነገር ሳታሳድግ ሳታጎለምስ በዚያው እንድትቀጥል ማድረግ ነው፡፡ ጾም፣ጸሎት፣ስግደት፣ ምጽዋት ወዘተ ማድረግን በትንሹ እና በጥቂቱ ጀምረሃል፡፡ ነገር ግን በዚሁ በጥቂቱ በጀመርከው የጽድቅ ሥራ ብቻ እንድትቀጥል ያድርግሃል፡፡ ለምሳሌ ጾም ስትጀምር እስከ 6 ሰዓት ድረስ ብቻ ከሆነ የምትጾም ሕጉ እስከ 9 እና ከዚያም በላይ እንደሆነ እያወቅህ ከዚህ ሰዓት በላይ ማለፍ እንዳትችል ያደርግሃል፡፡ እዚህ ላይ የጀመርካቸውን የጽድቅ ሥራዎች ሕጉ ከሚለው በታች እንድትሠራ በማድረግ ነው የሚፈትንህ፡፡ ንስሐ ለመግባት ቆርጠሃል በቃ በዚህ እንደማይፈትንህ አርግጠኛ ሆነሃል፡፡ ነገር ግን ንስሐ ስትገባ ወይ ከባድ ኃጢአት የምትለውን እንዳትናዘዝ ያደርግሃል አለበለዚያም ንስሐህን በቁርባን እንዳትደመድም ያደርግሃል፡፡ ጸሎት ላይም እንዲሁ ስትጀምር ውዳሴ ማርያምን በመጸለይ ከጀመርህ በቃ ከዚህ ሌላ ጸሎት እንደሌለ አድርጎ በዚሁ ጸሎት ብቻ ያስቀጥልሃል፡፡ ያውም በተመስጦ በተሰበሰበ ኅሊና ያይደለ ቃሉን በማነብነብ ብቻ እንድትጸልይ ያደርግሃል፡፡ በአጠቃላይ እዚህ ላይ ቅድስናን በሚያስገኙ ሥራዎች ላይ በትንሹ ከህጉ በታች በሆነ መልኩ ከተሰማራህ በኋላ በዚያው ከህጉ በታች እንድትቀጥል በማድረግ ዋጋ ማሳጣት ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ብዙ ዘመናትን ካቆየህ በኋላ አንተው ተሰላችተህ ከዚህ ሥራህ እንትሸሽ ያደርግሃል፡፡ ዋናውም ዓላማ ከጽድቅ ሥራ ማራቅ ነውና፡፡
v  ከንቱ ውዳሴን መጨመር፡- ሰይጣን ጽድቅን እንዳትሠራ ከታገለህ በኋላ በዚያ ከተሸነፈ በጀመርካት ትንሽየ ነገር በዚያው እንድትቀጥል ያደርግሃል፡፡ ከዚያም ቀስ በቀስ እንድትተዋት ያደርግሃል፡፡ ነገር ግን አልተወውም ብለህ የጽድቅ ሥራህን እያበዛህ ስትሄድ ከንቱ ውዳሴ የተባለውን አረም ይዘራብሃል፡፡ ከዚያም ሳትሠራ ሁሉ ሠራሁ ማለትን ያስጀምርሃል፡፡ ከእኔ በላይ ጿሚ፤ ከእኔ በላይ ሰጋጅ፤ ከእኔ በላይ ቆራቢ፤ ከእኔ በላይ መጽዋች፤ ከእኔ በላይ ሰባኪ፤ ከእኔ በላይ ዘማሪ፣ ከእኔ በላይ ንስሐ ገቢ፣ ከእኔ በላይ አገልጋይ ወዘተ ማለት ያስጀምረናል፡፡ ከዚያ በኋላ የቅዱሳኑን ገድል ሳይቀር መናቅ ትጀምራለህ፡፡ ከዚሁ ጋር ትእቢት ይይዝሃል፡፡ በቃ ሁሉን ነገር ከእኔ በላይ ለኃሳር ነው ማለት ትጀምራለህ፡፡ ከዚህ በኋላ የመናገር ሱስ ይይዝሃል፡፡ የሰራኸውንም ያልሰራኸውንም እየቀጣጠልህ እየጨማመርህ ማውራትን ትለምዳለህ፡፡ ለታይታ እና ለማስመሰል መባከን ትጀምራለህ፡፡ መለከት በፊቴ ካልተነፋልኝ ከበሮ ካልተደለቀልኝ ማለትን ትጀምራለህ፡፡ መድረኩን ይዘህ ማይኩን ጨብተህ ቅዱሳን እንዲህ ተጋደሉ ማለቱን ትዘነጋውና እኔ እንዲህ አድርጌ እንዲህ ፈጥሬ ወዘተ ማለት ትጀምራለህ ፡፡ አገልግሎትህ በሙሉ ራስህን በማስተዋወቅ ላይ የተጠመደ ይሆናል፡፡

ሰይጣን ጽድቅን እንዳትሠራ ማድረግ አልችል ካለ ያለው ምርጫ ወይ ባለህበት ማስቆም ነው አልያም ከንቱ ውዳሴን ማምጣት ነው፡፡ ስለዚህ ሰይጣንን ድል ነስቸዋለሁ ብለን ልንናገር የምንችልበት ደረጃ ላይ አልደረስንም ማለት ነው፡፡ ሰይጣንን ድል መንሳታችንን ማረጋገጥ ያለብን በጌታ ፍርድ ቆመን “ኑ የአባቴ ቡሩካን…” የሚለውን አጥንት አለምላሚ ቃል ከሰማን ብቻ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በየትኛው አቅማችን በየትኛው ቅድስናችን አፋችንን ሞልተን ሰይጣንን ድል እንደነሳነው እንናገራለን፡፡ ስለዚህ ከሰይጣን ፈተና ማምለጥ አይቻልምና የትግል ስልታችንን እንደአመጣጡ መቀያየር ተገቢ ነው፡፡ 

Wednesday, November 9, 2016

“አውሎግሶን”

© መልካሙ በየነ

ኅዳር 1/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================

“አውሎግሶን” ማለት “አቤቱ ክፈትልኝ፤ አቤቱ ግለጥልኝ” ማለት ነው፡፡ (ድርሳነ ሚካኤል ዘኅዳር)
ይህ ልመና እንደ መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት ያለ ልመና ነው፡፡ ዳዊት “አቤቱ ንጹህ ልብን ፍጠርልኝ፡፡ የቀናውንም መንፈስ በውስጤ አድስመዝ 50 እንዳለው ያለ ማለት ነው፡፡
የልባችን ክፋት ሲያይልብን፣ ማሥተዋል ሲጎድለን፣ መረዳት ሲሳነን፣ ተስፋችን ሲሟጠጥ፣ ኅሊናችን ሲታወክ ወዘተ አውሎግሶን ማለት ይገባናል፡፡ የደነቆረ ልቡናችን፣ ማየት የቸገረው ዓይናችን፣ ማሰብ የተሳነው ልቡናችን፣ ለፈጣሪ የተገዛ እንዲሆንልን ቅዱሳንን አማላጆቼ እንዲልልን አሁንም አውሎግሶን እንበል፡፡ በዘመናችን ተገቢ ልመና ከፈጣሪ መታረቂያ ጸሎት አውሎግሶን ነው፡፡ የተዘጋው ሲከፈት የተሰወረው ሲገለጥ ሰይጣን የኃፍረት ካባ ሲጎናጸፍ ነፍሳችን ሥጋችንን ገዝታ በነፍስ ጎዳና ትመራታለች፡፡ የሥጋ ገበያ ይቀዘቅዛል የነፍስ በረከት ምድሪቱን ይሸፍናታል፡፡ የመላእክቱ ጠባቂነት ይበዛልናል ስለዚህ ትናንት አበው አውሎግሶን እንዳሉ ዛሬ እኛም እንዲሁ ብለን ለነገው ትውልድ የሚድንበትን መንገድ እንዲከፈት የተሠወረው እንዲገለጥ አውሎግሶን በሉ ብለን እናስተምር፡፡

ዳዊት “አቤቱ ንጹህ ልብን ፍጠርልኝ፡፡ የቀናውንም መንፈስ በውስጤ አድስመዝ 50 ብሏል፡፡ ይህን የዳዊት ልመና እንደእኔ ዓይነቱ ሞኝ ዳዊት ድሮ የነበረውን ወይም ቀድሞ የተፈጠረለትን ልብ ፈጣሪ በጥበቡ እንዲቀይርለት (እንዲለውጥለት) የለመነ ይመስለዋል፡፡ ግን አይደለም፡፡ ልቡናው በኃጢአት ረክሷል፣ ልቡናው ሰው በመግደል አድፏል፣ ልቡናው የቀናውን መንፈስ ለማሰብ ተስኖታል፣ ልቡናው ጽድቅን እንዳያስብ ተዘግቷል፤ ልቡናው የሰውን ሚስት በማስነወር ቆሽሿል፣ ልቡናው ያልተፈቀደለትን የካህናትን ምግብ በመመገብ ኃጢአት ሠርቷል፡፡ ስለዚህ ነው ይህንን በኃጢአት የሚባዝነውን ልቡናየን ንጹሕ አድርግልኝ ማለቱ፡፡ ያለኝን ቀድሞ የፈጠርክልኝን ልብ በንስሐ ሳሙና ንጹህ አድርግልኝ ማለቱ ነው፡፡ ንስሐ እንድገባ በንስሐ እንድመላለስ በቅድስና እንድጓዝ አድርገኝ ሲል ነው፡፡ የእኛም ልመና ይኼ ነው መሆን ያለበት፡፡ እኛን ከፍጥረታት ሁሉ አልቆ አብልጦ ፈጥሮናል ነገር ግን በማይገባ የኃጢአት ሥራ እየባዘንን እንሳሳትን እንመስላለን፡፡ በርግጥ ሰው እንስሳዊ ባሕርይ አለው፡፡ እንስሳዊ ባሕርይውን ግን መቆጣጠር እንዲችል ሆኖ የተፈጠረ ድንቅ ፍጥረት ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ አንዳንድ ሰዎች በሬ ሲያዩ በሬ ባደረገኝ፣ ወፍ ሲያዩ ወፍ ባደረገኝ፣ አንበሳ ሲያዩ አንበሳ ባደረገኝ፣ ነብር ሲያዩ ነብር ባደረገኝ ወዘተ ይላሉ፡፡ የሚገርመው ነገር ዳዊት ንጹሕ ልብን ፍጠርልኝ ማለቱን አለማስተዋላችን ነው፡፡ ዳዊት ያለኝን የቆሸሸ ልቤን ንጹሕ አድርግልኝ አለ እንጅ የእንስሳትን ልብ ስጠኝ አላለም፡፡ እኛም የሚያስፈልገን ይኼ ልመና ነው፡፡ ያለንን ነገር ቀድስልን ባርክልን ንጹሕ አድርግልን ማለት ያስፈልገናል፡፡ የሌለንን ነገር ምኑን እንዲባርክልን እንለምነዋን? አውሎግሶን በሉ እባካችሁ፡፡ ሁሉም ከተዘጋብን ሁሉም ከተሠወረብን ከዚህ የልመና ቃል ውጭ ምንም አማራጭ የለንም፡፡ ልመናችንን እንድናስተካክል የተሠወረው እንዲገለጥልን የተዘጋው እንዲከፈትልን አውሎግሶን እንበል፡፡ ልቡናችን በኃጢአት ቁልፍ ተዘግቷል፤ የጽድቅ ጎዳና በዲያብሎስ ተንኮል ታጥሮብናል ተዘግቶብናል፤ የንስሐ ሳሙና ተደብቆብናል ስለዚህ የተዘጋው እንዲከፈት የተሠወረው እንዲገለጥ አውሎግሶን እንበል፡፡


ጸሎት ለመጀመር በጣም የከበደ እንዲሆን አድርጎ ሰይጣን በልባችን ገብቶ መጥፎ አረም ይዘራብናል፡፡ ለዚያም ነው ትንሿ ጸሎት ዳገት ሆና ለመጀመር የምትከብደን፡፡ አውሎግሶን ብለን ጸሎት ስንጀምር ግን ዳገቱ ሁሉ የተስተካከለ ሜዳ ይሆንና ውዳሴዋን ስንጨርስ አንቀጸ ብርሃኗን፤ አንቀጸ ብርሃኗን ስንጨርስ ይዌድስዋ መላእክትን፤ ያን ስንጨርስ አቡነ ዘበሰማያትን እርሱንም ስንጨርስ ቅዳሴዋን፣ መልክአዋን ሌሎችንም ለመጸለይ ልባችን ተከፍቶ በተመስጦ እንድንጸልይ ብርታት እናገኛለን፡፡ ማንም ማረጋገጥ የሚችለው እውነት ነው፡፡  ትንሽ ጸሎት ብንጀምር ትልቁን ጸሎት እንድንጀምር ሰይጣን የመቃወም ኃይሉ ይቀንሳል፡፡ አማትበን አቡነ ዘበሰማያትን ስንጀምር ሰይጣን መሸሽ ይጀምራል፡፡ በዚያ ላይ ስግደት ስንጨምርበት በኖ ይጠፋል፡፡ አውሎግሶን!!!

Friday, November 4, 2016

“ለምንት አንገለጉ አሕዛብ፤ አሕዛብ ለምን ያጉረመርማሉ” መዝ 2÷1

© መልካሙ በየነ
ጥቅምት 25/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================

ቃሉን የምናገኘው በመዝ 2÷1 ላይ ነው፡፡ አሕዛብ የሚባሉት በታቦት ፈንታ ጣዖት በግዝረት ፈንታ ቁልፈትን የሥራቸው መሠረት ያደረጉ ለሕገ እግዚአብሔር የማይገዙ ሰዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች ለእግዚአብሔር አይገዙም፤ አለመገዛትም ብቻ ሳይሆን ለእግዚአብሔር በሚገዙ ህዝቦች ላይ የሚነሣሡ ናቸው፡፡ ለዚህም ነው በተለያዩ ጉዳዮች በእግዚአብሔርና በማደሪያው ላይ የሚያጉረመርሙት፡፡ ማጉረምረም የቅድስና ሥራ አይደለም፤ ቅድስናውን በመናቅ የሚደረግ ነው እንጅ፡፡ ታዲያ አሐዛብ ለምን እና በምን ያጉረመርማሉ? የሚለውን ጥያቄ በጥቂቱ እንመልከት፡፡
v  በመንፈሳዊ ሥራዎች ላይ
አሕዛብ ምንም ዓይነት መንፈሳዊ ሥራን አይሠሩም አያሠሩምም፡፡ አይጾሙም አይጸልዩም አይሰግዱም አይመጸውቱም ንስሐ አይገቡም ወዘተ፡፡ ነገር ግን  አያጾሙም አያጸልዩም አያሰግዱም አያስመጸውቱም ንስሐ አያስገቡም ወዘተ፡፡ እነዚህ ሰዎች “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይበቀል” ያለችውን የእኛን አገር እንስሳ በግብር ይመስሏታል፡፡  እነርሱ አይጾሙም ነገር ግን ሌሎች ለሚጾሙት ጾም እነርሱ ጾሙ ይቀነስልን ብለው ያጉረመርማሉ፡፡ እነርሱ አይጸልዩም ነገር ግን ሌላው ለሚጸልየው ጸሎት በዛብን ብለው ያጉረመርማሉ፡፡ እነርሱ አይሰግዱም ነገር ግን ሌላው ለሚሰግደው ስግደት እነርሱ ስግደት አያስፈልግም እያሉ ያጉረመርማሉ፡፡ እነርሱ አይመጸውቱም ነገር ግን ሌላው ለሚመጸውተው ምጽዋት ጥቅም የለውም በማለት አብዝተው ያጉረመርማሉ፡፡ እነርሱ ንስሐ አይገቡም ነገር ግን ንስሐ የሚገቡትን ይኮንናሉ፡፡ ለምን በቀጥታ ለአምለካክህ አትነግረውም ከካህኑ ዘንድ ምን ያመላልስሃል ብለው ያጉረመርማሉ፡፡ በአጠቃላይ ለድኅነት ሥራዎች ሁሉ ፀር ናቸው፡፡ ለዚያም ነው አሕዛብ የሚያጉረመርሙት፡፡
v   ሥርዓት ይሻሻልልን
እነርሱ በቤቱ ሳይኖሩ በቤቱ እንዳሉ መስለው በማይመሩበት በማይተዳደሩበት ሥርዓት ላይ ያጉረመርማሉ፡፡ በማያገባቸው ነገር ሲጨቃጭቁ የሚያገባቸውን ነገር ይረሳሉ፡፡ ሥርዓቱን ማሻሻል እንደማይችሉ እያወቁ ውዥንብር ለመፍጠርና አማኙን ክርስቲያን ለመከፋፈል ደፋ ቀና የሚሉ ናቸው፡፡ ሥርዓቱ ይሻሻልልን እያሉ በሥርዓቱ ላይ ያጉረመርማሉ፡፡ ሲያሻቸውም የየራሳቸውን ሥርዓት ሰርተው በዚያ ሲመሩ ይታያሉ፡፡ ለምን እንዲህ አደረጋችሁ ሲባሉም ሥርዓቱ እንደዚህ ስለሆነ ነዋ በማለት በማያውቁት ሥርዓት ላይ በድፍረት ሲመሰክሩ ይሰማሉ፡፡ የሚገርመው ነገር አይጾሙም አይጸልዩም አይሰግዱም ንስሐ አይገቡም ነገር ግን የእነዚህን ሁሉ ሥርዓት ይነቅፋሉ ይሻሻልልን ብለውም ያጉረመርማሉ፡፡ በእውነት ለማይኖሩበት ለማይመሩበት ሥርዓት ምኑ ነው የሚሻሻልላቸው፡፡ በርግጥ ዓላማቸው እነርሱን የመሰሉ በርካት አህዛብን ማፍራት ነውው፡ ለዚህም ነው ሥርዓት ይሻሻልልን ብለው የሚያጉረመርሙት፡፡
v  ቤተክርስቲያን ትታደስ
የዚህ ጽንሰ ሃሳብ አራማጆች የቤተክርስቲያንን እውቅ መለያ ሀብቶች በማጥፋት ቅርስ አልባ በማድረግ የመናፍቃን መናኸሪያ እና ባዶ አዳራሽ ማድረግ ነው፡፡ የብራና መጽሐፍ እስከ 20 ሺ ብር ድረስ ተሸጠ ሲባል ሰምታችሁ ይሆናል፡፡ ይህ ለምን ሆነ? ስትሉ የቤተክርስቲያኒቷ ጥንታዊ መረጃዎች የተጻፉት በብራና ስለሆነ ህዝቡ መጻሕፍትን ከአብያተ ክርስቲያናት እየዘረፉ እንዲሸጡላቸው ለማድረግ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ መጻሕፍትን ሰብስበው ያቃጥሏቸዋል፡፡ ዋናው ዓላማቸው ይህ ስለሆነ ማት ነው፡፡ መዝሙራት ስብከቶች ዓለማዊነትን እንዲላበሱ ሆነው መዘጋጀት አለባቸው ብለው ዘፈን መሳይ መዝሙራትን የስድብ ውርጅብኝ የወረደበት የስብከት ካሴቶችን ይለቅቃሉ፡፡ ያሬድን ሳያውቁ ያሬዳዊ ዜማ በማለት ለመሸጥ በሞንታርቮ በየከተማው እየዞሩ የሚጮሁ ብዙዎች እየሆኑ ነው፡፡ አሕዛብ ቤተክርስቲያንን የራሳቸው መፈንጫ ለማድረግ እነርሱን የሚመች ህግ እንዲወጣ እና በአዲስ መልኩ እንዲሰራበት ይወተውታሉ፡፡


Tuesday, November 1, 2016

“ገነስትስ መቼ አማረብን?”

© መልካሙ በየነ

ጥቅምት 22/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================
በመጀመሪያ ( facebook.com/beyenemlkm እና/ወይም facebook.com/melkamtiwulid ) ላይክ ያድርጉ ከዚያ ጽሑፉን ያንብቡ ቀጥለውም ጽሑፉን SHARE, COMMENT, LIKE ያድርጉ፡-
==============================================
የምበላው የምጠጣው የለኝም ለዚህም ነው አምላኬን የማላመሰግነው፡፡ አንዳንዱን በጥጋብ ብዛት  እያዘለለ እኔን በረሃብ አለንጋ ይገርፈኛል ለዚህም ነው “ተመስገን” የማልለው፡፡ እኔ የምኖርበት ጎጆ የለኝም፡፡ የቀን ፀሐይ የሌሊት ቁር ይፈራረቅብኛል ውሎ እና አዳሬ መንገድ ዳር ነው፡፡ ያዘነ ይሰጠኛል ያላዘነም ይሰድበኛል በዚህ መልኩ ነው የምኖረው፡፡ መንገድ ዳር አላፊ እና አግዳሚውን ስለምን የምውል ችግረኛ ነኝ ለዚህም ነው አምላኬን “ተመስገን” የማልለው፡፡ እኔ የምለብሰው የሌለኝ የፀሐዩ ሙቀት ያቃጠለኝ የሌሊቱ ቁር ያኮማተረኝ የታረዝኩ ችግረኛ ነኝ፡፡ ሌላው ሦስት አራት ልብስ እየቀያየረ ባለበት ጊዜ፤ ጠዋት የለበሰውን ማታ ቀይሮ በሚወጣበት ጊዜ እኔ ግን እርቃኔን እንደ ድንጋይ ብርድና ሙቀት ይፈራረቅብኛል ለዚህም ነው አምላኬን የማላመሰግነው፡፡ እኔ በየሰው ቤት እየዞርኩ ጭቃ የማቦካ እንጨት የምፈልጥ ድንጋይ የምሰብር ቁፋሮ የምቆፍር የቀን ሰራተኛ ነኝ፡፡ እጀ እስኪያብጥ ድረስ አሠራለሁ ጉልበቴ እስኪዝል ድረስ እሸከማለሁ ነገር ግን ኑሮየን ሊቀይር የሚችል ገንዘብ አላገኝም፡፡ ጠዋት በሠራሁበት ምሳ ከሠዓት በኋላ በሠራሁበት እራት እመገብበታለሁ፤ ኑሮየ ከእጅ ወደ አፍ ነው፡፡ አንድ ቀን ሥራ ባቆም ማንም አያበላኝም፡፡ የማድርበት ቤት ደግሞ የለኝም በረንዳ ላይ ነው ወድቄ የማድረው፡፡ ለዚህም ነው አምላኬን “ተመስገን” የማልለው፡፡

እኔ ጤና አጥቸ እንቅልፍ ተነሥቼ የምኖር በሽተኛ ነኝ፡፡ በየህክምና ቦታው ተመላለስኩ መፍትሔ የለውም፤ በየፀበል ቦታዎች ሁሉ ተንከራተትኩ ምንም መፍትሔ አላገኘሁም፡፡ በባሕላዊ መንገድ ይፈውሳሉ ፍቱን መድኃኒት አላቸው ከሚባሉ ባለመድኃኒተኞችም ዘንድ ተመላልሻለሁ፡፡ ነገር ግን ገንዘቤን ከመበተን ውጭ ምንም ትርፍ ነገር አላገኘሁበትም፡፡ ከአልጋ ጋር እንደ ትኋን ተጣብቄ መኖር ከጀመርኩ ረዥም ዘመን ሆኗል፡፡ አንድ ቀን ብሎ የፈጣሪየ እርዳታ አልመጣልኝም አንድ ቀን እንኳ ከበሽታየ እንዳገግም ፈጣሪየ አላደረገም ለዚህም ነው የማላመሰግነው፡፡

እኔ በባእድ አገር ኑሮ አልሳካልኝ ብሎ የምኖር ስደተኛ ነኝ፡፡ ቋንቋቸውን አልችለውም ባሕላቸውን አልተላመድኩትም ምግባቸውን አልወደድኩትም፡፡ ነገር ግን የእንጀራ ጉዳይ ነውና በግድ እኖራለሁ፡፡ ገንዘቡ አልጠራቀምልህ ብሎኛል፤ ቤተሰቦቼን አሳልፍላቸዋለሁ ብየ ወጥቼ ራሴን እንኳ ማስተዳደር አልችል አልኩኝ፡፡ ቀን ከሌሊት ያዝዙኛል እንቅልፍ የሚባል ነገር በዓይኔ ከዞረ ከሳምንት በላይ ሆኗል፡፡ አገሬ የምመለስበት ገንዘብ አላጠራቀምኩም ኑሮየ ከእጅ ወደ አፍ ብቻ ነው፡፡ ሁሉ ነገር ለእኔ ባእዳ ነው፡፡ አገሬ መልሰኝ ብየ ፈጣየን ተማጸንኩት እርሱ ግን ይባስ ብሎ ለክፉ አሠሪዎች አሳልፎ ሰጠኝ ለዚህም ነው አላመሰግንህም የምለው፡፡ በስደት አገር የተወኝ ለችግር የጣለኝ እርሱ ነው ታዲያ እንዴት አመሰግነዋለሁ?

ብዙ ችግር፣ ብዙ መከራ፣ ብዙ ፈተና አለብን፡፡ ፈጣሪ የፈጠረው ፍጥረት ሁሉ አንድ ዓይነት አይደለም፡፡ አንዱን ድሃ ሌላውን ሃብታም፣ አንዱን ቀይ ሌላውን ጥቁር፣ አንዱን የተማረ ሌላውን ያልተማረ፣ አንዱን ረዥም ሌላውን አጭር፣ አንዱን ጌታ ሌላውን ባሪያ፣ አንዱን መልካም ሌላውን መጥፎ ወዘተ አድርጎ ፈጥሮታል፡፡ ፈጣሪ ሲፈጥረን በተለያየ መልኩ አድርጎ ነው፡፡ አላውቅ ብየ እንጅ ለዚህ ነበር ምስጋና የሚገባው፡፡ እኔ ድሃ ካልሆንኩ ሌላው ሃብታም ሊባል አይችልም በመካከላችን ያለውን ልዩነት እያየሁ ራሴን በተስፋ እንዳኖር ይረዳኛል፡፡ በበጎ ባስበው ኖሮ አምላክን ማመስገን የሚገባኝ እኔን ተመጽዋች ሌላውን መጽዋች ስላደረገው ነበር፡፡ እምነት ካለኝ ብታመም ያድነኛል ምናልባት ዋጋ የሚያሰጠኝ ህመም ከሆነ ግን ተመስገን ብለው ሲዖልን እንዳላይ ያደርገኛል፡፡ ኢዮብን ዘመዴ አደርገዋለሁ ማለት ነው፡፡ ገንዘብ ስለሌለኝ ፈጣሪየን አላመሰግነውም የምለው ለምንድን ነው? ገንዘብን መውደድ የይሁዳን ልብ አውሮ ፈጣሪውን በ30 ብር እንዲሸጥ ያደረገው እኮ ነው፡፡ ገንዘብ ቢኖረኝ ምናልባት ፈጣሪየን አሳዝንበት ይሆናል እንጅ እንደ አብርሃም ፈጣሪየን አላስደስትበትም፡፡ የምበላው የምጠጣው አጣሁ ብየ ፈጣሪየን አላመሰግንም ካልኩኝ ስበላ እና ስጠጣ ስጠግብ እንደምረሳው አውቃለሁ፡፡ እስራኤላውያን ከግብጽ ባርነት ሲወጡ መና ከደመና እየወረደላቸው ተመግበው ውኃ ከጭንጫ አለት ላይ እየፈለቀ ጠጥተው ሲጠግቡ ፈጣሪያቸውን ረስተው ጣዖት አሠርተው ለጣዖት ተንበርክከዋል፡፡ ጥጋብ እንዲህ ፈጣሪን ያስረሳል፡፡

ለነገሩማ አልገባህ ብሎኝ እንጅ ተድላ ደስታ በበዛባት ገነት እየኖሩ የሚበሉት ሳያጡ የሚጠጡት ሳይጎድልባቸው የሚለብሱት ሳያስፈልጋቸው አዳምና ሄዋን ትእዛዝ አፍረሰው አይደል እንዴ፡፡ ሰው ነኝ ለካ! አወ ሰው እኮ ነኝ፡፡ ታዲያ ሰው ፍላጎቱ ይረካል እንዴ? ሰው እኮ በቃኝን የማያውቅ ፍጥረት ነው፡፡ አንድ ሲኖረው ሁለትን ይመኛል፤ ሁለት ሲኖረው ሦስትን ይመኛል፤ ሦስት ሲኖረው ደግሞ አራትን ይመኛል ብቻ ተቆጥሮ የማያልቅ ፍላጎት ነው ያለው፡፡ ታዲያ ገንዘብ ቢኖረው ባይኖረው፣ ቢለብስ ባይለብስ፣ ድሃ ቢሆን ሃብታም፣ ቀይ ቢሆን ጥቁር፣ የቀን ሠራተኛ ሆነ የመንግሥት ሠራተኛ፣ ምንም ሆነ ምን ሰው ፈጣሪውን ላለማመስገን ምክንያት ያስቀምጣል፡፡ እንኳን የቅጣት ቦታችን መሬት ላይ ቀርቶ የተድላ ቦታችን ገነት ላይም ኖረን አላማረብንም፡፡ ምንም ምክንያት አያስፈልገንም የገነት ኑሮ ያላማረብን ሰዎች እስር ቤት ወርደን ያምርብናል ብለን አናስብ፡፡ ባለህ ነገር ፈጣሪህን አመስግን፣ ባለህ ነገር አቅድ፣ ባለህ ነገር ብቻ ኑር፣ ባለህ ነገር ደስ ይበልህ፣ ባለህ ነገር ተስፋህን አለምልም፡፡ የሌለህን ነገር ስትመኝ ያለህን ነገር ሳትጠቀምበት ትሰናበታለህ፡፡ እስኪ በቃኝ ማለትን እንልመድ፡፡ ገንዘቡ በቃኝ፣ መብላት መጠጣቱ በቃኝ፣ መልበስ ማጌጡ በቃኝ፣ ኃጢአትን መስራቱ በቃኝ፣ መቀማቱ በቃኝ፣ ሰውን ማሳዘኑ በቃኝ፣ ሰውን መግደሉ በቃኝ እንበል እስኪ፡፡ ሰው በወርቅ አልጋ ላይ የወርቅ ምንጣፍ አንጥፎ ቢተኛ አይረካም፡፡ ሰው የወርቅ ጫማ ተጫምቶ በወርቅ ልብስ አሸብርቆ ቢወጣ አይረካም፡፡ ሰው ጮማ ቢያወራርድ ጠጅ ቢያንቆረቁር አይረካም፡፡ ሰው መኖሪያ ቤቱን በዕንቍ ቢሽቆጠቁጠው በወርቅ መጋረጃ ቢከልለው ምንም አይረካም፡፡ ታዲያ ገነት ያላማረበትን መሬት ላይ እንዴት ይመርበት፡፡ የመሬት ላይ ኑሮ አላምርልህ ቢል አትደነቅ አትገረም ገነት መኖርም አላማረብህምና!!!