Tuesday, April 28, 2015

በጣም አልበዛም ግን?

ኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት በርካታ ችግሮች ይገጥሟታል፡፡ አንዱ ችግር ሌላውን ተከትሎ ስለሚመጣ አንዱን አዝነን ሳንጨርሰው ሌላው አሳዛኝ ችግር ይተካል፡፡ የአንዱ ችግር ተከትሎ መምጣትም ያለፈውን ያስረሳናል፡፡ አሁን እየሆነ ያለው ጉዳይ ይህ ነው፡፡ በአገሪቱ አለመረጋጋት ሳቢያ በየመን ይኖሩ የነበሩ ወገኖቻችን እጅግ አስጨናቂ መከራ ላይ መውደቃቸውን እያሰብን ሳለን ከወደ ደቡብ አፍሪካ የሰማነው ጉዳይ እነርሱን እንድንዘነጋቸው አደረገን፡፡ ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ወገኖቻችን በእሳት ተቃጠሉ በአደባባይ በስለት ተቆረጡ እጅግ አለቀስን፡፡ ለነጻነታቸው ጉልህ አስተዋጽኦ የነበራት አገራችን ኢትዮጵያ ናት፡፡ ያንን ነጻነታቸውን ከተጎናጸፉ በኋላ ግን ይህንን ክፉ ሥራ ፈጸሙብን፡፡ ስለ እነርሱ ስናለቅስ ስናነባ 30 ወንድሞቻችን በሊብያ በረሃ ደማቸው ከውኃ ጋር  ጎረፈ፡፡ አሰቃቂ ዘግናኝ የተባለውን መከራ ተቀበልን፡፡ አብዝተን በምሬት አለቀስን እንባችንን አፈሰስን በአደባባይም በሰላማዊ ሰልፍ ሀዘናችንን ገለጽን ሆኖም ግን ሀዘናችን ሃዘናቸው ያልሆኑ ፖሊሶች በአገራችንን በዱላ ቀጠቀጡን፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን አምላክን ከመለመን ውጭ ምንም ማለት ስለማንችል “አንመካም በጉልበታችን፣ እግዚአብሔር ነው የእኛ ኃይላችን” እያልን ዘመርን፡፡ ያም ሆኖ በዚያ አለፈ፡፡ ሲኖዶሱ በ 7 ቀናት ጸሎተ ፍትሐት ረሳቸው፣ መንግሥትም በ 3 ቀናት ብሄራዊ ሀዘን ዘነጋቸው እኛ ቤተሰቦቻቸው ግን እስከመቼም ድረስ አንዘነጋቸውም አንረሳቸውም፡፡
በጣም የሚሳዝነውና የሚገርመው ጉዳይ ግን እስከዛሬ ድረስ በመገናኛ ብዙኃኑ የሚነገረው ዜና መሰል ትርኪ ምርኪ ንግግር ነው፡፡ “እስልምናን አይወክልም” ከሚለው በሻገር እኛ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያን ከእስላም ለብዙ ዘመናት በፍቅር አብረን የኖርን ነን፤ እንዲያውም መስጊድ ሲሰራ ክርስቲያኑ፤ ቤተ ክርስቲያን ሲሰራም እስላሙ ማህበረሰብ ይደጋገፋሉ ተባለ፡፡ ትክክል ነው ለብዙ ዘመናት አብሮነታችን ዘልቋል፡፡ አንድ በጣም የበዛው ጉዳይ ግን “በጋብቻም ተሳስረናል” ተብሎ የሚገለጸው የመገናኛ ብዙኃኑ ግዴለሻዊ ዘገባ ነው፡፡ ፍቅራችን ምን ወደር ባይኖረው፣ እጅግ ብንረዳዳ፣ በለቅሶ በደስታ ብንጠያየቅ፣ አብረን በጉርብትና ብንኖር በጋብቻ ግን ልንተሳሰር እንዴት እንችላለን? ፖለቲካው ምን ያህል ጫና እየፈጠረብን እንደሆነ ልብ ልንለው ይገባል፡፡ የሃይማኖት መሪዎች በአንድ ወንበር ተቀምጠው፣ እጅ ለእጅ ተያይዘው ፎቶ ቢነሱ፣ ቪዲዮ ቢቀረጹ ከፊት የነበራቸውን ፍቅር የሚያሳይ ነው እንጅ ሌላ መልእክት ያለው አይመስለኝም፡፡ አሁን አሁን  ግን ድሮ ከነበራቸው አንድነት የተለየ ሌላ አንድነት የፈጠሩ ይመስል ለታይታ በአደባባይ እጅ ለእጅ መያያዝን የፍቅር መገለጫ አድርገውታል፡፡ ቤተክርስቲያን እንዲገቡም ሳይፈቀድላቸው አልቀረም፡፡ በጣም በዛ “ፍቅራችን” ከልኩ አለፈ ሥርዓት እየተጣሰ እንዲህ ያለ ነገር መሠራቱ አስፈላጊ መስሎ አይታየኝም፡፡ እስላሙ ያረደውን ክርስቲያኑ፤ ክርስቲያኑ ያረደውን ሙስሊሙ አለመመገብን እንደልዩነት የሚመለከተው መንግሥት አንዱ ያረደውን ሌላው እንዲመገብ ማድረጉ አይቀሬ ነው፡፡ በጋብቻ ተሳስረናል ላለ አካል ይህን ማድረግ እጅግ ቀላል ነዋ!!!

ስደት ለምን?

ኢትዮጵያውያን ለምን ይሰደዳሉ? የሚለውን ከባድ ጥያቄ መጠየቅ ግድ ከሚልበት ሰዓት ላይ እንደደረስን የተረዳሁት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ነው፡፡ ለኢትዮጵያውያኑ አገር ለቅቆ በባእድ አገር መበተን ዋናው ምክንያት ምንድን ነው? በውኑ ይችን ቅድስት አገር ጠልተው ይሆን የተሰደዱት? እስኪ የገባኝን የተረዳሁትን ትንሽ ነገር ልበላችሁ፡፡ ብዙዎች በችግር ወድቀው መድረሻ ባጡበት በዚህ ጊዜ ወደ ሊብያ፣ ወደ ደቡብ አፍሪካ፣ ወደ የመን ወደ ሌሎችም አገራት  ለመጓዝ (ለመሰደድ) የሞከሩ እንዳሉ በመገናኛ ብዙኃን ሲነገር ሰምተናል፡፡ እርሱማ አበውስ “ከረሃብ ጦር ይሻላል” ብለው የለም እንዴ? ትክክል ነው መከራ ያስጨንቃል፣ ረሃብ ክፉ ነው ለስደት ይዳርጋል፣ ነገ ተስፋ የምናደርገውን እንጅ ስንጓዝ የሚደርስብንን መከራ ከምንም አንቆጥረውም ምክንያቱም እዚህ ብንቀመጥም በአእምሮ ከመቁሰል፣ በረሃብ አለንጋ ከመገረፍ የዘለለ ምንም ነገር ላናተርፍ እንችላለን፡፡ ኢትዮጵያውያን የማይገኙበት ቦታ አንታርክቲካ ብቻ ነው፡፡ በሌላው የዓለም ክፍል ነፋስ እንደበተነው እህል እንደዚያው ተበትነዋል፡፡ ወገኖቻችን ለእኛ ሲሉ፣ ለቤተሰቦቻቸው ሲሉ፣ ለአገራቸው ሲሉ ተበትነዋል፡፡
ስደት የቅድስና መንገድ እንደሆነ እረዳለሁ፡፡ እነ ቅዱስ አትናቴዎስን፣ እነ ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅን ለአብነት ያህል መጥቀስ እንችላለን፡፡ ዓላውያን ነገሥታት በተነሡባቸው ወቅት ከተከበረው መንበራቸው ወርደው ለስደት ተዳርገዋል፡፡ ለምን ተሰደዱ? የሚለውን ጥያቄ ስንመለከት እንጀራ ፍለጋ  ወይም የቤተሰቦቻቸውን ኑሮ ለመቀየር ነው ብለን አንመልስም፡፡ ምክንያቱም ህዝቡ እጅግ አብዝቶ የሚወዳቸው  የተቀደሱ የዓለም ብርሃን የነበሩ ጳጳሳት ናቸውና፡፡ ወንጌል “የሚያሳድዷችሁን መርቁ” ስለሚል ያንን የወንጌል ቃል ይፈጽሙ ዘንድ ተሰደዱ፡፡ ዓለም አልተገባቻቸውምና በምድረ በዳ ተንከራተቱ፣ ተራቡ፣ ተጠሙ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ስደትም እንዲሁ ለቅድስና ነው ብል የተሳሳትኩ አይመስለኝም፡፡ እንጀራ ፍለጋም ይሁን ለፖለቲካ ነጻነት አገርን ለቅቆ መሰደድ የወንጌልን ቃል መፈጸም ነው፡፡ እኔ እስከሚገባኝ ድረስ ሰላሙን ለማግኘት ነጻነቱን ለማስከበር ብቸኛው መንገድ ስደት ሆኖ ያገኘው ሰው ቢሰደድ ኃጢአት የለበትም፡፡ ከተማረ ሰው ይልቅ ለአበባ ምርት ቅድሚያ በምትሰጥ አገር ውስጥ መኖር ከመረረው ያ ሰው ብቸኛው ምርጫው ስደት ነው፡፡ በአገሩ ላይ ከሁለተኛ ዜጋ በሚያንስ ክብር እየኖረ ያለ ሰው ቢሰደድ ፍርዱ በተሰደደው ሕዝብ ሳይሆን ባሰደደው ወገን ላይ ነው፡፡ ለስኳር መሰለፍ፣ ለውኃ መሰለፍ፣ ለዱቄት መሰለፍ፣ ለመብራት መሰለፍ፣ ለታክሲ መሰለፍ፣ ለዘይት መሰለፍ ወዘተ ክንዱን ያዛለው ህዝብ ቢሰደድ ማነው ሊጠየቅ የሚገባው ህዝቡ ወይስ አስተዳዳሪው? ትምህርቱን በሚገባ ተምሮ ዲፕሎማውን፣ ዲግሪውን፣ ማስተርሱን፣ ዶክትሬቱን ወዘተ ያጠናቀቀ ሰው የሥራ እድል ለማግኘት ሲሞክር ቀድመው በሥራው ላይ በተቀመጡ 8ኛ ክፍልን እንኳ ባግባቡ ባላጠናቀቁ ሰዎች ሲሰደብ ሲንቋሸሽ ሲሸማቀቅ መሰደድ ሲያንሰው ነው፡፡ በኢንቨስትመንት ሥም ለውጭ ኢንቨስተር ከ100,000 ሄክታር መሬት በላይ በነጻ በሚሰጥባት አገር ውስጥ እኛ ዜጎቿ 1 .ሜ  ከ 1000 ብር ባላነሰ ዋጋ በምንገዛበት ሁኔታ መኖር ሲያቅተን ብንሰደድ ማነው ተወቃሹ? የፖለቲካ መሪዎቹ እስከውጭ ድረስ እየሄዱ በሚማሩበት፣ በሚታከሙበት እና በሚዝናኑበት ገንዘብ ላይ ማዘዝ የማይችለው ሕዝብ በረሃብ አለንጋ ሲገረፍ፣ ነጻነቱ ሲገፈፍ፣ ቴክኒክ ለመማር እንኳ ክፍያ ሲጠየቅ፣ ሙያውን በአግባቡ ባልተማረ ሃኪም በማይገባ መድኃኒት በበሽታው ላይ ሌላ በሽታ ሲጨምር መታገስ ያልቻለ ህዝብ ቢሰደድ ነውሩ ምኑ ጋር ነው? የወገኖቻችን ሞት አብዝቶ አሳዝኖናል እና በአደባባይ ማልቀስ አለብን ብሎ የወጣ ሰላማዊ ህዝብ ላይ ዱላ የሚሰነዝር፣ አስለቃሽ ጋዝ የሚረጭ  ፖሊስ በተሰማራባት አገር ውስጥ መኖር ሲሰለቸው ሰው ቢሰደድ ማው የሚጠየቀው? በሃይማኖቱ ያበረቱኛል ያላቸው አባቶች የፖለቲካ መሪዎች ሲሆኑበት ህዝቡ ቢሰደድ ምን በደል አለበት?
ኢትዮጵያውያን በእውነት ቅዱስ ነን፡፡ ስለራሳችን ቅድስና መመስከር የተገባ ባይሆንም እኔ ግን እመሰክራለሁ፡፡ እኔ ቅዱስ አይደለሁም ህዝቡ ግን ሲበዛ ቅዱስ ነው፡፡ ለምን? በአገሩ ሰርቶ በአገሩ መኖርን የሚጠላ ለዚያውም ኢትዮጵያዊ ሰው ይገኛል ብየ አላምንም፡፡ ነገር ግን በአገሩ የሚያሰራው ሲያጣ እንዳይሰራ ያደረገውን አካል ከመቃወም፣ ረብሻ ከመፍጠር ይልቅ ስደትን ይመርጣል፡፡ ክፉን በክፉ የሚቃወም ኢትዮጵያዊ እንደሌለ ማሳያው ይኸው ነው፡፡ ከግብጽ የጀመረው አብዮት ወደ ሊብያ ብሎም ወደ የመንና ሶሪያ ሲዘልቅ ተረኛ አገር ትሆናለች ተብላ ብዙዎች ይጠብቋት የነበረ ኢትዮጵያን ነው፡፡ ነገር ግን የህዝቡ ጨዋነት፣ ቅዱስነት እዚህ ላይ ትልቅ ማሳያ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ተቃውሞ ያልተነሣው ህዝቡ ፈሪ ስለሆነ፣ የተደራጀ ፖሊስ ስላለ፣ ህዝቡ 1 ለ 5 ስለተደራጀ፣ ችግር ስላልገጠመው፣ በሰላም ስለሚኖር፣ መንግሥት እንደሚለው 11 በመቶ ስለተመነደግን፣ መሰረተ ልማት ስለተሟላልን፣ ሥራ አጥ ስለቀነሰ ወዘተ አይደለም ህዝቡ ጨዋና ቅዱስ ስለሆነ ብቻ ነው፡፡ በአገሩ መኖር የቸገረው ሰው ይሰደዳል፡፡ ቢሮ ክራሲ ያዛለው ሰው ይሰደዳል፡፡ ህጋዊ ሆኖ ለመሄድ ዓመት ደጅ መጥናት የሰለቸው ሰው በኮንቴነር ታፍኖ በበረሃ በጥምና በረሃብ እየተገረፈ ይሰደዳል፡፡ በቃ ምርጫ የለውማ! እዚህም ሞት እዚያም ሞት ብሎ ወስኗላ!  ለሌላው የሚያስብ ህዝብ ማለት ኢትዮጵያዊ ብቻ ነው፡፡ አገሬን አልለቅም በአገሬ መብቴን አስከብራለሁ፣ ነጻነቴን እጎናጸፋለሁ የሚል ሰው የግብጹን ተቃውሞ ኢትዮጵያ ውስጥም መፍጠር አይሳነውም ነበር፡፡ ነገር ግን ርኅራኄ በማይሰማው ፖሊስ የሚገደለውን  የወገኑን ሞት፣ እልቂት  ያስባል፣ የሚወድመውን ሃብትና ንብረት፣ ቅርስ እና ታሪክ ከግምት ውስጥ ያስገባል ስለዚህ ብቸኛው አማራጭ ራሱን ይዞ መሰደድ ብቻ ነው፡፡ ለሌላው መጨነቅ፣ ክፉን በክፉ አለመመለስ (አለመቃወም) ማለት ይህ ነው፡፡ ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች የተባለውም ለዚህ ነው እኮ፡፡ ህዝበ ኢትዮጵያ እግዚአብሔርን እንጅ መሪውን ፈርቶ አያውቅም፡፡ በዚህ ልንተማመን ይገባል፡፡ ስንቱ ገንዘብ የሞላው፣ ሁሉ የተረፈው ባለሃብት አገሩን ለቅቆ ወጥቷል? ስንቱ የተማረው የተመራመረው ከከርሰ ምድር እስከ ጠፈር አበጥሮ የሚያውቀው ምሁር ነው የተሰደደው? ታዲያ ኢትዮጵያ የተሰደዱት ለእንጀራ ፍለጋ ብቻ ነው ማለትን እንዴት እንደፍራለን፡፡ መንግሥት ራሱን መፈተሽ የሚገባው ጉዳይ ኢትዮጵያኑ ለምን ተሰደዱ የሚለውን ጉዳይ ነው፡፡ ህዝቡ ሁሉ ተሰድዶ አልቆ ዛፍና ውኃውን ገደል ተራራውን ሸለቆ ኮረብታውን የሚወስዳቸው ያጡ እንስሳትን ብቻ የሚመራ ብቸኛው መንግሥት ተብሎ እንዳይነገር እፈራለሁ፡፡ ህዝቡ ያልፈለገው ዲሞክራሲያዊ መንግሥት ስለዲሞክራሲ ሲል ሲለቅ እንጅ የሙጥኝ ብሎ ሲቀመጥ ያየሁት የእኛውን ልማታዊ መንግሥት ብቻ ነው፡፡ በእርግጥ ከውጭ በሚያገኘው ምንዛሬ ቤቱን የሚገነባ የፖለቲካ መሪ ስላለን በዚህ ላንገረም እንችል ይሆናል፡፡
በአጠቃላይ ለወገኖቻችን ስደት ዋናው ተጠያቂው በመምራት ላይ ያለው መንግሥት ብቻ ነው፡፡ አየነው እኮ የሆነውን ሁሉ ዛሬ እንደድሮው ሊደልለን የሚችልበት   ምንም ወኔ የለውም፡፡ ይችን የመሰለች ቅድስት አገር ትቶ በባእድ አገር መንገላታት ያ ክፉ ስደት ግን ለምን?  አኔን የሚናፍቀኝ ያ እውቀቱ ለዓለም መብራት የሆነው የተማረው ወገናችን ሁሉ ተመልሶ በእውቀቱ አገሩን ገንብቶ ድሮ የነበራትን ኃያልነት የሚመልስበት ቀን ብቻ ነው፡፡ ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይጠብቃት፡፡
ታናሽ ወንድማችሁ የምሆን መልካሙ ነኝ፡፡

Monday, April 27, 2015

የ ISIS ዳግም ግድያ በኢትዮጵያ

ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች የተባለላት የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም  የአስራት የበኩራት አገር ናት፡፡ ታዲያ ይች አገር በተለያዩ ዘመናት ክርስትናን የሚቃወሙ አረመኔዎች እጅግ በርካታ ፈተናዎችን ሲያደርሱባት እንደነበር የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡ አረመኔው ግራኝ መሀመድ ጨካኟ ዮዲት ጉዲት እንዲሁም በቅርቡ ፋሽስት ኢጣሊያ ከዚያም በኋላ በኢትዮጵያ የተመሠረተው የደርግ መንግሥት በቤተክርስቲያናችን ላይ ጦራቸውን ሲያዘምቱ ምእመናንን ለሞት ሲዳርጉ ክርስትናዊ የሆኑ ትውፊቶችን ሲያጠፉ የኢትዮጵያን ታሪክ ሲበርዙ መቆየታቸው የማይካድ ሃቅ ነው፡፡ እነዚህ አረመኔዎች በተነሡባቸው ጊዜያት ሁሉ በርካታ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ምእመናን  እና ካሕናት ጳጳሳት ሳይቀሩ ለሞት ተዳርገዋል፡፡ እነዚያ ለሞት የተዳረጉት ወገኖቻችን በተቀደሰው የሰማዕትነት (የምስክርነት) ሥራቸው ስናወሳቸው ነበር ወደፊትም እናወሳቸዋለን እንማርባቸዋለን፡፡ ማንም ቢሆን ስለእምነቱ የመጣበትን ጠላት በትእግሥት ሊያሸንፍ ይገባዋል፡፡ የጥላቻ ማጥፊያ ብቸኛው መሳሪያ ፍቅር ነውና፡፡ ለዚያም ነው እኛ ኢትዮጵያውያን በፍቅር መኖራችን ለዓለም ሁሉ ተምሳሌት ሆነን እንድንዘልቅ የረዳን፡፡
በቅርብ ቀናት ክርስትናን ለማጥፋት (ለዚያውም ጠላቴ ናት ያላትን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን) የሚንቀሳቀሰው ጨካኙ ሃይማኖታዊ ቡድን ራሱን  ISIS ብሎ የሚጠራው እስላማዊ መንግሥት በ 30 ኢትዮጵያውያን ላይ የፈጸመውን ዘግናኝ ተግባር አይተናል ተመልክተናል አዝነናል አልቅሰናልም፡፡ ከሃዘኑ ባሻገር ምን ተደረገ ለሚለው ግን ጥያቄው ጥያቄ ውስጥ እንደሆነ የሚቀጥል ለመሆኑ እየተመለከትን ነው፡፡ እጅግ እስኪሰለቸን የምንሰማው የመገናኛ ብዙኃኑ የጋዜጠኞች ንግግር የሚያስረዳን ግን የሞቱት ኢትዮጵያውያን ህገ ወጥ ስደተኞች ናቸው በሚል ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ለይ ብቻ የተመሠረተ ነው፡፡ እሽ ሕገወጥ  ስደተኞች ናቸው እንበል ISIS የሚገድለው  ሕገወጥ ስደተኛ ማነው ብሎ ነው እንዴ ከሆነ ጥሩ፡፡ እንደዚህ ከሆነ ከዚህ የምገነዘበው ነገር አለ እርሱም ISISን ያደራጀው የኢትዮጵያ መንግሥት  እንደሆነ፡፡ ለምን አደራጀው ስንል ሕገወጥ ስደተኞችን ከሕጋዊ ስደተኞች እንዲለይለት፡፡ በቃ፡፡ ስለዚህ ጋዜጠኞችም ሆኑ የመንግሥት አካላት የሐይማኖት መሪዎችም ሆኑ ተራው ምእመን ሕገወጥ እና ህጋዊ ስደት የሚለውን ከአእምሯችን ፍቀን ልናወጣው ይገባል፡፡የኢትዮጵያኑ ሞት ከስደት ጋር የተያያዘ ነገር ስላልሆነ፡፡ ስንቱ ሰው ነው ዛሬ በስደት የሚኖረው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ እኮ ከአንታርክቲካ በስተቀር ሰው በሚኖርባቸው አረገራት ሁሉ ተበትኖ የሚኖር ነው፡፡ ታዲያ ያ ሁሉ ሰው ተገደለ እንዴ፡፡ አልተገደለም፡፡ ለእነዚህ ሞት ዋናው ምክንያት ክርስትናቸው መስቀላቸው ብቻ ነው፡፡ አለቀ፡፡ በዚህ ልንወናበድ አይገባም፡፡ ሰማዕትነታቸውን አጉልተን ልናወጣው ይገባል እንጅ ስደታቸውን ልናጎላው የፖለቲካ ፍጆታ ልናደርገው አይገባም፡፡
ሌላው ከሃይማኖት አባቶች የሰማነው መግለጫ መሰል ንግግር ዳግም ግድያን ለመፈጸማቸው ማስረጃ ነው፡፡ ISIS ን እናወግዛለን የሚል መፈክር ይዞ መዞር ብቻውን ISISን ያጠፋል ማለት ከሆነ አምላክ ይፋረደናል፡፡ ከሃይማኖት መሪ ነን ባዮች ይልቅ የተሻሉ መምህራንን የተመለከትነው በሊብያ በረሃ ከዚያ ከውኃማው አካባቢ ነው፡፡ ስለእውነት መራራ ሞትን የታገሱት እነዚህ ቅዱሳን ሰማእታት ስለክርስትናቸው ታረዱ በጥይት ተደበደቡ ጳጳሱን ተቀድመውት መንግሥተ ሰማያትን ወረሱ፡፡ እኛ እዚህ ስለክርስትናችን ባልተፈተንበት ቦታ ሳለን የምንቀልድበትን ክርስትና እነርሱ እስከሞት ድረስ ታምነው በደማቸው ኢትዮጵያን ቀደሷት፡፡ ሲኖዶሱ ምን አለ ምን መግለጫ ሰጠ፡፡ ሊባል ይገባው የነበረው ነገር ተባለ ወይ ስንለ አልተባለም ነው መልሱ፡፡ ክርስትና ሰይፍ ለሚያነሱባችሁ ሰይፍ አንሱ አይልም እንዲያውም ቀኝ ፊትህን ለሚመታህ ግራ ፊትህን ደገሞ ስጠው ይላል፡፡ በአጠቃላይ ክርስትና ስለእምነታችሁ ስለመንግሥተ ሰማያት ተሰደዱ ሙቱ ይላል እንጅ አሳድዱ ግደሉ አይልም፡፡ ለዚህም ነው ከነማተባቸው አንገታቸውን ለስለት የሰጡት፡፡ ይህን የተቀደሰውን ሰማዕትነት ከምንም ባለመቁጠር መንግሥት ከሚዘበዝበን ፖለቲካ የበለጠ ፖለቲካዊ ዝብዘባ ከሃይማኖት መሪዎች አንፈልግም፡፡ የትኛው የሃይማኖት መሪ ነው በሊብያ የተሠዉት ኢትዮጵያውያን ስለሃይማኖታቸው ፍቅር ነው እና ሰማዕታት ናቸው ብሎ ባለማፈር የተናገረው፡፡ ይህን ብል እንዲህ እደረጋለሁ በሚል ፍርሃት ተሸብበን ወገናችን እስከመቼ አገሩን ትቶ ሲኮበልል ይኖራል፡፡ እኛ ለማንም መሬታችንን እየሰጠን በሃገራችን መኖር እንደ እሳት እየፈጀን  እስከመቼ እንቀጥላለን፡፡ አባቶች መስቀሉን ከፍ አድርገው የሚመሩትን ሕዝብ ሃዘን ካልተረዱ በጣም አሰቃቂ ግድያ ማለት እርሱ ነው፡፡ አቡነ ጴጥሮስን ዛሬ ላይ ምነው ባገኘናቸው ነበር፡፡ ኢትዮጵያ ለፋሽስት ኢጣሊያ እንድትገዛ ከፋሽስቱ የመጣላቸውን የመኪና፣ የቤት፣ የገንዘብ እና የተለያዩ የማግባቢያ ሽልማቶች ከምንም ባለመቁጠር ኢትዮጵያ ለፋሽስቱ እንዳትገዛ በተቀደሰ መስቀላቸው በተከበረው ስልጣናቸው መላ ኢትዮጵያን አወገዙ፡፡ ይህንን ውግዘት የሰማው ፋሽስትም በጥይት ደብድቦ ገደላቸው፡፡ አያችሁ የአገር ፍቅር ማለት፡፡ በአፍ ከመናገር ባለፈ በተግባር የተረጋገጠ የአቡነ ጴጥሮስ የአገር ፍቅር፡፡ ታዲያ ዛሬ ምነው ይሄ የአገር ፍቅር ጠፋ፡፡ ምእመናን በሚከፍሉት ገንዘብ የምንተዳደር አባቶች ትንሽ ቆም ብለን  የምናስብበት ወቀት ላይ ነን፡፡
እጅግ የሰለቸኝ ሌላው ነገር ISIS የማንንም እምነት አይወክልም የሚለው የቂልነት ንግግር ነው፡፡ እስላማዊ ነኝ እያለ፣ ቁራንን ካልተቀበላችሁ ብሎ እያስገደደ፣ የሸሪአ ሕግን ተቀበሉ ብሎ እያስፈራራ የማንንም እምነት አይወክልም የሚለው አባባል ጅልነትን የሚያሳይ ነው፡፡ “ሃይማኖት አንዲት ናት የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ አንግበው የሚንቀሳቀሱ አንዳንድ ክርስቲያኖች አሉ” ስንባል በዝምታ አለፍነው፡፡ አወ አሉ ብለን በራሳችን ላይ ፈረድን፡፡ የመጽሐፉን ቃል ዘንግተን መንግሥት የሚቀባጥረውን ፖለቲካ አብረን ተናገርነው፡፡ በክርስትናችን ላይ አፈርን፡፡ ቃሉ መጽሐፍ ውስጥ መኖሩንም ተጠራጠርን፡፡ ያ የመጽሐፍ  ውዱስ ቃል እንደ አንድ ተራ መፈክር ተቆጥሮ “መፈክር አንግበው” ስንባል ይህንን ለማስረዳት የሞከረ ማነው አረ ማንም፡፡ ያ የያዝነው የመጽሐፍ ቃል ሰው አልገደለም እኮ ነገር ግን ክርስቲያኖች እንዲህ አደረጉ ተባልንበት፡፡ ዛሬ 30 ንጹሃንን የገደለው እስላም የማንንም እምነት አይወክልም ማለት ምን ማለት ነው? ሙስሊሙ ማህበረሰብስ ይበል መንግስትም ይበል ሲኖዶሱ እንዴት እንዲህ ይላል፡፡ ግጭት ይቀሰቅሳል ተብሎ ታስቦ ከሆነ እኛ ክርስቲያኖች በማረድ ደም በማፍሰስ ላይ አልተመሰረትንምና አናደርገውም፡፡ እኛ ብንሆን ኖሮ እኮ አስተምረን እንመልሳቸዋለን ብለዋል ተብለን ነበር እኮ፡፡ እስላም ነን ባዮች ናቸው ያረዱን ታዲያ እነዚህ እስልምናን የማይወክሉ ከሆነ ሙስሊሙ ማህበረሰብ አስተምሮ ሊመልሳቸው ይገባል፡፡ ቅድስት አገር ኢትዮጵያ  የዐረቡ ክፍል ባሳደዳቸው ጊዜ እስልምና እምነትን የሚከተሉ ሰዎችን ከነእምነታቸው ተቀብላ ያስተናገደች እንጀራዋን ቆርሳ ያበላች ብቸኛ አገር እንደሆነች ማንም የሚመሰክረው ሃቅ ነው፡፡ ክርስቲያኑ ከእስላሙ ጋር በፍቅር እና በመተባበር በመረዳዳት እና በመተዛዘን እንኖራለን፡፡ በዚህ መዋደዳችንም ብዙ ዘመናትን አስቆጥረናል ወደፊትም እንደዚሁ እንዘልቃለን፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ እስላሞች ይህንን አረመኔያዊ ተግባር ላይፈጽሙት ይችላሉ ISIS የተባሉት እስላሞች ግን አድርገውታል፡፡ አባቶቻችን ደፍረው ያልተናገሩት ጉዳይ ይኼ ነው፡፡ እስላም የሆኑት ISIS ክርስቲያን የሆኑ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንን ገድለዋል፡፡ እኛ ግን እነርሱን ለመግደል አናስብም ምክንያቱም ክርስቲያኖች ስለሆንን ማለት ነበረባቸው አላሉንምና እናዝናለን፡፡የ ISIS ዳግም ግድያ በኢትዮጵያ ተፈጽሟል የሚያሰኘን ቅሉ ይኸው ነው፡፡ ከዐረፉት ወንድሞቻችን ረድኤት በረከቱን አምላካችን ይክፈለን፡፡ አሜን፡፡

Wednesday, April 22, 2015

ሰማዕታተ ሊቢያ


ሰማዕታተ ሊቢያ
 “ሰማዕት” የሚለው ቃል ከግዕዝ ቋንቋ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ምስክርነት ማለት ነው፡፡ እምነት አንለውጥም፣ ማተብ አንበጥስም፣ ከእግዘዚአብሔር ሌላ አምላክ የለም ብለው ስለሚያመልኩት አምላክ ታምነው አንገታቸውን ለስለት ደረታቸውን ለጦር የሰጡ ሰዎች ሁሉ ሰማዕታት ይባላሉ፡፡ እነዚህ ሰማዕታት ከራሳቸው ክብር ይልቅ የእግዚአብሔርን ክብር አብልጠው በቃል የሰሙትን በተግባር የቀየሩ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስን ቃል በንባብ ብቻ ሳይሆን በተግባር የተረጎሙ ናቸው፡፡ ከሥጋ ሞት ይልቅ የነፍስን ሞት አብልጠው የሚፈሩ ለመሆናቸው ማረጋገጫው ይህ ቅዱስ ሰማዕትነት ነው፡፡ ዓለምን እየተፈታተናት ያለው በግፍ የሰውን ልጅ እንደ እንስሳት የማረድ (ለእንስሳት ከሚሰጥ ክብር በታች)፣ በጥይት የመደብደብ አስነዋሪ እና አስቀያሚ ተግባር ላይ የተሠማሩ የሰውን ልጅ ከመጤፍ የሚቆጥሩ “ሰው መሰል ሰው በላ” ፍጡራን ናቸው (አሸባሪ የሚለው ቃል የሚገልጻቸው ስላልመሰለኝ ነው)፡፡ እነዚህ “ሰው መሰል ሰው በላ” ፍጡራን በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ስሞችን ለራሳቸው እየሰጡ ዘግናኝ ተግባራትን ሲፈጽሙ ተስተውለዋል፡፡ ከዚህ በፊት በተወሰኑ አገራት ብቻ ተወስነው ሲፈጽሙት የነበረውን አሰቃቂ ድርጊት አሁን ላይ ዓለም አቀፋዊ ይዘት እንዲኖረው በማድረግ በተለያዩ የዓለም አገራት ላይ ይህን ከሰብአዊ ፍጡር የማይጠበቀውን ክፉ ሥራ እንደ ተቀደሰ ሥራ አድርገው መፈጸማቸውን ቀጥለዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ እያየነው እና እየሰማነው ያለው ነገር እጅግ የከፋ እየሆነ መምጣቱን ነው፡፡ የአገር መከላከያ ሰራዊቱን ልብስ የመሰለ ለብሰው ሰላም አስከባሪ መስለው በመንገድ የሚጓዘውን ሁሉ ክርስቲያን መሆን አለመሆኑን እያጣሩ ክርስቲያን ከሆነ ወደ አዘጋጁት “ኮንቴነር” አፍነው በማስገባት ወደ እንግልት ቦታቸው ይወስዷቸዋል፡፡ በዚያም የእንግልት ቦታ እምነታቸውን እንዲለውጡ፣ ማተባቸውን እንዲበጥሱ በብዙ ስቃይ ያንገላቷቸዋል፡፡ ይህን ስቃይ ሳይሰቀቁ እምነታቸውን እንደማክዱ፣ ማተባቸውን እንደማይበጥሱ ካሳወቁ ወደሚቀጥለው እጅግ ዘግናኝ ወደሆነው ጉዞ ይቀጥላሉ፡፡ ይኸውም የሰውን ልጅ ርኅራኄ በሌለበት ግፍ በስለት መቆራረጥ አልያም በጥይት በተደጋጋሚ መደብደብ ነው፡፡ ይህ ሁሉ መከራ የሚደርስባቸው ስለእግዚአብሔር መንግስት፣ ስለመስቀል ክብር ስለክርስትና ነው፡፡ ክርስትና በተግባር ሲፈተሽ እንዲህ አይነት ስቃይ ውስጥ መግባትንም የሚጠይቅ መሆኑን ያረጋገጡልን ሁሉ ሰማዕታት ይባላሉ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም በሀሙስ ውዳሴ ማርያም እንዲህ ሲል ተናገረ፡-- “ሰማዕታት የዚችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ ደማቸውንም ስለእግዚአብሔር አፈሰሱ መራራ ሞትንም ታገሡ” የሰማዕትነት ሥራ ይህ ነው፡፡ 1. የዚችን ዓለም ከንቱነት መረዳትና መናቅ 2. ደምን ስለእግዚአብሔር ሲሉ ማፍሰስ (መታመን) 3. መራራ ሞትን መታገስ ሰማዕታት እነዚህ ታላላቅ ሀብታት አሏቸው፡፡ እኛ ዓለምን ለመናቅ የምንችልበት ደረጃ እና ቅድስና ላይ አልደረስንም ሰማዕታት ግን ደርሰውበታል ከዚያም በላይ አልፈውታል፡፡ እኛ ስለ እግዚአብሔር ብለን ስለእግዚአብሔር ምስክርነት አንገታችንን ለስለት ደረታችንን ለጦር አልሰጠንም፣ በእሳት አልተቃጠልንም፣ በፈላ ውኃ አልተቀቀልንም ሰማዕታት ግን የህንን ሁሉ በተግባር አረጋግጠውልናል፡፡ እኛ ሞትን እንጠላልን፡፡ ቤተሰቤን ማቄን ንብረቴን ለማን ሰጥቼ እያልን የሥጋን ሞት እንፈራለን፡፡ መከራ ለሚያጸኑብንም ከነፍስ ይልቅ የሥጋን ሞት ስለምንፈራ በመከራው እንሰቀቃለን፡፡ ሰማዕታት ግን “ሥጋን የሚገድሉትን አትፍሩ ይልቅስ ነፍስን የሚገድሉትን ፍሩ” የሚለውን የወንጌል ቃል በተግባር መራራ የሆነውን ሞት ታግሰው አሳይተውናል፡፡ ሰማዕትነት በብዙ መንገድ ሊፈጸም ይችላል፡፡ የሰማዕትነት መሠረት ግን አንድ ብቻ ነው እርሱም “አምላኬን አልክድም እምነቴን አልለውጥም ማለት ነው” ይህንን ስንል ድርጊት ፈጻሚዎች በስለት፣ በእሳት፣ በጦር፣ በውኃ፣ በተለያዩ ዘግናኝ ተግባራት ግድያ ሊፈጽሙብን ይችላሉ፡፡ እነዚህ የሚፈጸሙብን አስነዋሪ ተግባራት የተናገርነውን ቃል በተግባር የመግለጣችን፣ ለቃሉ መታመናችንን የምናሳይበት ማረጋገጫ ነው፡፡ ሰማዕትነት ድሮ በእነ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ በእነ ቅዱስ እስጢፋኖስ፣ በእነ ቅዱስ ቂርቆስ… ብቻ የቀረ አይደለም ዛሬ በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመንም ሰማዕትነት እየተፈጸመ ያለ ቅደስና ነው፡፡ ክርስቲያን በመሆናቸው ብቻ በተለያዩ አገራት እየተገደሉ ያሉ ወገኖቻችን ሰማዕታት ናቸው፡፡ ይህን የሰማዕትነት ክብር የተጎናጸፉ በርካታ የዓለም አገራት ዜጎች አሉ፡፡ በቅርቡ ሚያዝያ 11 /2007 ዓ.ም ደግሞ ይህ የሰማዕትነት ክብር ለቅድስቲቱ አገር ለኢትዮጵያ ደረሳት፡፡ በአፍሪካዊቱ አገር በሊቢያ ይኖሩ የነበሩ 30 ኢትዮጵያውያን ራሱን “እስላማዊ መንግሥት” በእንግሊዝኛ አጠራሩ “ISLAMIC STATE (IS)” ብሎ የሚጠራው የ “ሰው መሰል ሰው በላ” ስብስብ ሰብአዊነት በጎደለው ጭካኔ በስለት አርዶ በጥይት ደብድቦ በግፍ ገደላቸው፡፡ እነዚህ ኢትዮጵያውያን በሃይማኖታቸው ላይ ለሚመጣ ነገር ድርድር የሌላቸው ናቸው፡፡ መራራ የሆነ ሞትን ለመታገስ የበቁት ክርስቲያን በመሆናቸው ብቻ የመጣ ስለሆነ ነው፡፡ እነዚህ ሰማዕታት እምነታቸውን ቢለውጡ፣ ማተባቸውን ቢበጥሱ ኖሮ ለዚህ የሰማዕትነት ክብር ባልበቁ ነበር፡፡ ነገር ግን እኛ በንባብ የምንሰማውን የወንጌል ቃል እነርሱ እንዲህ ነው ብለው በተግባር ገለጡልን ለእኛም አሳዩን እኛም አየነው፡፡ ሰማዕትነትን እኛም ዛሬ አየነው፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ገድል ሲነበብ “እንዴት ያን ያህል መከራ የሰው ልጅ ሊሸከም ይችላል” እያልን ልባችንን ለኑፋቄ ስንከፍት የነበርን ሰዎች እዩት እንግዲህ እንዲህ አይነቱን አሰቃቂ ተግባር ግፍ እና መከራ የእኛው ልጆች፣ የእኛው ወንድሞች በሚገባን ኢትዮጵያዊ ቋንቋ እና ለዛ ሲያስረዱን፡፡ እነዚህን ሰማዕታት የወለዱ እናቶች የተባረኩ የተመሰገኑ ናቸው፡፡ባለማዎቅ እነዚህን ሰማዕታት “ነፍስ ይማር” የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ ነፍስ ይማር የምንል እኮ ክርስተናቸውን በተግባር ስለእግዚአብሔር ምስክር ሆነው ስለሞቱ ሰማዕታት አይደለም፡፡ እርሱ የራሱ የሆነ ቦታ አለው እነዚህ ጋር ግር ቦታ የለውም፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በዐረፈ ጊዜ “ነፍስ ይማር” ያሉ ሰዎች ከነበሩ ተሳስተዋል፡፡ ከሰማዕታቱ ረድኤትና በረከት አምላካችን እግዚአብሔር ያካፍለን አሜን፡፡

Wednesday, April 1, 2015

የተዋሱትን ማበላሸት

ሰላም ጤና ይስጥልኝ እንደምን ከረማችሁ ውድ ጓደኞቼ፡፡ ሰላመ እግዚአብሔር በያላችሁበት ይጠብቃችሁ፡፡ ከጠፋንበት ፈልጎ በቸርነቱ ጥላ ሥር ለሚያሳርፈን፤ ዓለም ከመፈጠሩ በፊት በነበረ ዓለምንም አሳልፎ በሚኖር አምላክ ረድኤት ተከልለን ለምንኖር ለእኛ ነገን በቸርነቱ ይጠብቀን ዘንድ ለእርሱ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ የሰውን ልጅ ከፍጥረት ሁሉ አክብሮ እና አልቆ መፍጠሩን ሁልጊዜም ቢሆን ልንዘነጋው የሚገባ አይደለም፡፡ እኛ ከመላእክትም በላይ እጅግ የምንዋብበት ትልቅ ጸጋን አልብሶናል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም እመቤታችንን ባመሰገነበት ድርሳኑ እንዲህ አለ “አንች ከመላእክት ትበልጫለሽ…” እንግዲህ ልብ እናድርግ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሰው ትባላለህ፡፡ እግዚአብሔር እጅህን ሲሰጥህ አንድ ብቻ ማድረግ ሲቻለው ሁለት አደረገልህ፡፡ ለምን ሁለት እጅ ሁት እግር፣ ሁለት ዓይን… ኖረኝ ብለህ አትጨነቅ አትመራመር ይሆናል፡፡ እርሱ ግን አንተ ላንተ ከምታስበው በላይ ስላን ስለሚያስብልህ ሁለት ሁለት አድርጎ ፈጠረልህ፡፡ ምክንያቱም አንዱ ቢዝል ሁለተኛው እንዲያበረታው ነው፡፡ አንዱ በሆነ ጉዳት ሥራውን ቢያቆም ሌላኛው ተክቶ እንዲሰራልህ ነው፡፡ አንተ ግን ይህን ሁሉ ላታስተውለው ትችላለህ፡፡ እግዚአብሔር የሰጠህን ነገር ታበላሸዋለህ፡፡ እግዚአብሔር ይህን ሁሉ ሀብት በነጻ ሲሰጥህ ሠርተህ እንድትከብርበት አመስግነህ እንድትጸድቅበት ነው፡፡ ወደ ኃጢአት ስትጓዝ እግር ባይኖረኝ ኖሮ ይህ ኃጢአት ማድረግ እችል ነበርን? ብለህ ራስህን ጠይቅ፡፡ አይተህ ስትመኝ በልብህም ስታመነዝር ዓይን ባይኖረኝ ኖሮ ይህን ኃጢአት እሰራ ነበርን? ብለህ ራስህን ጠይቅ፡፡ ሰውን የሚስቀይም ንግግር ስትናገር ወይም አሉባልታ እና ሃሜት ስታበዛ ምላስ ወይም አፍ ባይኖረኝ ኖሮ ይህን ኃጢአት እሰራ ነበርን? ብለህ ራስህን ጠይቅ፡፡ ፊት አይተህ ስታደላ ይህን የስልጣን ወንበር አምላክ ባይሰጠኝ ኖሮ ይህን ኃጢአት እሰራ ነበርን? ብለህ ራስህን ጠይቅ፡፡ ለእነዚህ ሁሉ መልስ መስጠት ከቻልክ አንተ ከኃጢአት ትርቃለህ ማለት ነው፡፡ በዓለምሰው ናት፡፡ ነገር ግን መላእክት ሳይቀሩ ይሰግዱላትና እጅግ ያከብሯት ይፈሯትም ነበር፡፡ ለምን ብንል አምላክን ለመውለድ በቅታ ተገኝታለችና ነው፡፡ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ በመፈጠሯ እኛን ትመስላለች፡፡ ስለዚህ ሰው በመሆኗ እንመካባታለን፡፡ ሌላው ግን አምላክ አክብሮ የፈጠረን ለመሆናችን ማሳያው “ሰውን በአርአያችን እንደ ምሳሌያችን እንፍጠር” ማለቱ ነው፡፡ የእግዚአብሔር የማይመረመር አርአያ እና አምሳል እኛ ነን፡፡ ምሳሌውን እና አርአያውን አስመስሎ የፈጠረው ፍጡር ሰው ለመሆኑ ብዙ ምስክሮችን ልንሰጥ እንችላለን ነገር ግን ለመግቢያነት ያህል ይህንን ካነሳን ይበቃናል፡፡ እንግዲህ የሰው ልጅ የከበረ ፍጥረት እንደሆነ ከተረዳን እግዚአብሔር እኛን ያከበረበት በርካታ ስጦታ ሰጥቶናል፡፡ ነገር ግን ስጦታውን ልቀማችሁ መልሱልኝ ስላላለን ራሳችን የፈጠርነው ያህል እንቀልድበታለን( እናበላሸዋለን)፡፡ እግዚአብሔር ለእኛ የሰጠንን ነገር እንደተዋስነው አድርገን እናስብ፡፡ እግር፣ እጅ፣ ዓይን፣ ጆሮ፣ ምላስ፣ አፍንጫ፣ ጸጉር፣ ልብ፣ ኩላሊት ወዘተ… ይቅርታ ዘርዝረን ልንጨርሰው ስለማንችል ነው፡፡ በምድር ላይ ያሉትን ሁሉ ንዱ ግዙ ስለተባልን የምድር ንጉሧ እኛ ነን፡፡ ይህም ማለት በምድር ያሉ ሀብታት ሁሉ እግዚአብሔር ለእኛ የሰጠን ሀብታችን ናቸው ማለት ነው፡፡ መሬት፣ ጸሐይ፣ ጨረቃ፣ ክዋክብት፣ አየር፣ ውኃ፣ ነፋስ፣ ዕጽዋት ወዘተ… ስለማያልቁ እነዚህን ብቻ ጠቀስኩ እንጅ ምኑ ተዘርዝሮ የፈጣሪ ውለታ፡፡ የሰው ልጅ ትልቅ ሲሆን እጅግ ትንሽ፣ ክቡር ሲሆን እጅግ ወራዳ፣ ሃብታም ሲሆን እጅግ ምስኪን ለመሆኑ ምክንያት እግዚአብሔር ነፍጎት ሳይሆን ከእግዚአብሔር የተበረከተለትን ስጦታ (የተዋሰውን ነገር) በአግባቡ ባለመጠቀሙ ነው፡፡ እግዚአብሔር ወደ ቤቱ እንድትሄድበት እግር ሰጠህ አንተም ተቀበልህ ነገር ግን ይህን ትልቅ ስጦታ ዘንግተህ ወደ ጠንቅ ዋይ፣ መተተኛ፣ ስርቆት… ብትሄድበት አንተ የተዋስከውን በአግባቡ መጠቀም ያቃተህ ሰነፍ ስትኖር ከሌሎች ፍጡራን ጋርም በሰላም መኖር አለብህ ምክንያቱም አምላክ የሰጠህ እንድትጠቀምባቸው እንጅ ኃጢአት እንድትሠራባቸው አይደለምና፡፡ አብዝተህ ስትጨፍር፣ ስትዘል ፣ ስትዘፍን፣ ስትሰክር … የተሸከመችህን ምድር ልብ ልትላት ይገባሃል፡፡ አብዝተህ ስትዘልባት ምድር እንደ እንቁላል “ጥርቁስ” ብትል እና ተከፍታ ብትውጥህስ፡፡ ስለዚህ ሁሉ ነገር በልክ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ወንድሜ ሆይ!! አምላክ የሰጠህን ስጦታ (መክሊት) በአግባቡ ልትጠቀምበት ይገባል፡፡ ባለህ ነገር ጥሩ ሥራ ልትሠራ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ያለን ሃብት ሁሉ በአግባቡ ካልተጠቀምንበት በቅጽበት ሊጠፋ የሚችል ነው፡፡ ስንት ወገኖቻችን በመኪና አደጋ፤ በመብራት፣ በእሳት እና በመሳሰሉት አደጋዎች ድሮ የነበራቸውን ውበት አጥተው ዓይናቸው ፈርጦ እግራቸው ተቆርጦ ቀርተዋል፡፡ ይህንን ልብ ልንለው ይገባናል፡፡ እግር፣ እጅ፣ ዓይን፣ ጆሮ፣ ምላስ፣ አፍንጫ፣ ጸጉር፣ ልብ፣ ኩላሊት ወዘተ… የተሰጡን ትልቅ ስጦታዎች ናቸውና በእነዚህ ስጦታዎች በአግባቡ ልንጠቀም ይገባናል፡፡ የተዋስነውን ይህን ሃብት ልናበላሸው አይገባም፡፡ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡