Monday, May 29, 2017

ፍኖተ እግዚአብሔር--- ክፍል ፲፩



© መልካሙ በየነ

ግንቦት 22/2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ተጽሕፈ እም አሐዱ ሊቅ ኢትዮጵያዊ ኅሩይ ወመፈክራዊ
ጌታው አለቃ ኅሩይ

፲፬ኛ አንቀጽ
ኃይልና ክሂል ሥልጣንም በአካል የማይከፈሉ አንድ እንደሆኑ ይናገራል፡፡
ጥያቄ:- የሥላሴ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን፣ በአካል ከሦስት ይከፈላል ማለት ይገባልን? መልስ:- አይገባም፤ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን፣ በአካል የሚከፈል ሦስት ከሆነ፣ አእምሮ ንባብ ሕይወት የሌለው፤ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን የለውምና፤ አእምሮም ንባብም ሕይወትም ከሦስት ይከፈላል ያሰኛልና፤ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን የሚባል፤ አእምሮ ንባብ ሕይወት እንደሆነ፣ “ንግበር ሰብአ በአርአያነ ወበአምሳሊነ” ዘፍ ፩÷፳፮  በተባለው በሰው እንዲታወቅ፤ ከየመጻሕፍቱ እያመጣን በብዙ አንቀጽ እናስረዳለን:: ንባብ:- “እግዚአብሔር ገብሮ ለእጓለ እመሕያው ርቱዕ፤ ወገብረ ሕላዌሁ ከሀሌ” ትርጉም:- “እግዚአብሔር ሰውን የቀና አድርጎ፤ ባሕርዩንም አዋቂ አድርጎ ፈጠረው” ጥበበ ሰሎሞን ፪÷፳፫ ብሏል:: ይህንንም ንባብ ዮሐንስ ኤጲስ ቆጶስ ዘኢየሩሳሌም ሲተረጉም ፳፬ኛ ንባብ:- “ይብል ዘንተ ከመ ቦቱ ሥልጣን በርእሱ ባሕቲቱ፤ ወይክል ያቅም ትሩፋተ” ትርጉም:- “ከሃሊ ማለትን በራሱ ብቻ ሥልጣን እንዳለው፣ ትሩፋቱን መፈጸም እንዲቻለው ሲያስረዳ ይህን ተናገረ ብሏል::” (ክፍል ፩ ብቻ) ሃ.አበው ምዕ ፶፪÷፲፭ ማቴዎስም በወንጌል ጌታችን ለሐዋርያት ምሳሌ መስሎ ሲያስተምራቸው ሰምተው ቤተ አይሁድ እንዳደነቁ ሲጽፍ:- ንባብ:- “እምአይቴ ሎቱ ዝንቱ ኩሉ ጥበብ ወኃይል” ትርጉም:- “ለእርሱ ከወዴት ተሰጠው፤ ይህ ሁሉ ጥበብ ኃይልስ አሉ” አለ:: ማቴ ፲፫÷፶፬ ኃይል ያለውን ንባብ አእምሮም እንደሆነ ያስተውሏል:: ቅዱስ ጳውሎስም ንባብ፦ “ወብነ ዝንቱ መዝገብ ውስተ ንዋየ ልሕኩት፤ ከመ ይኩን ዕበየ ኃይል ዘእምኀበ እግዚአብሔር፤ ወአኮ ዘእምኀቤነ” ትርጉም፦ “ይህም መዝገብ /ነፍስ/ በሸክላ ዕቃ አለን:: የኃይል ታላቅነት ከእኛ ያይደለ ከእግዚአብሔር ይሆን ዘንድ” አለ:: (፪ኛቆሮ ፬÷፯-፰) የዚህም ምሥጢሩ ከእግዚአብሔር የተገኘ ብዙ እውቀት ይሰጠን ዘንድ፣ በሥጋችን ነፍስ አለች ማለት ነው:: ኃይል ያለው ለነፍስ የተሰጠ እውቀት መሆኑን ያስተውሏል:: አሞንዮስና አውሳብዮስም፤ የአዳምን ተፈጥሮ ሲናገሩ፣ በመቅድመ ወንጌል ንባብ፦ “ወተፈጸመ ፍጥረቱ ለአዳም በዝንቱ ዘቦ ውስቴቱ ፫ ኃይል፤ ኃይለ ዘርዕ፤ ኃይለ እንስሳ፤ ወኃይለ ንባብ፤ ወኃይል እንስሳዊት ህውክት ይእቲ ዘበስምረት ወይእቲ ባ እምነ አእምሮ ወበዘባቲ ኃይል ዘይእቲ እንስሳዊት ወውስቴታ ይትረከብ ነጽሮ ወሰሚዕ” ትርጉም፦ “የአዳም ተፈጥሮ ኃይለ ዘርእ፣ ኃይለ እንስሳ፣ ኃይለ ንባብ ባለው በዚህ በሦስቱ ኃይል ፍጹም ሆነ:: ኃይለ እንስሳ የተባለችው እንስሳዊት እውቀት በፈቃድ የምትነሣሣ ናት:: ለዚህችውም ከእውቀት ወገን አላት፤ ባላትም እውቀት ይችውም እንስሳዊት ናት:: በእሷም ማየት መስማትም ይገኛል” ብለው ሁሉን ቆጥረው ተናግረዋል:: (መቅድመ ወንጌል) “ኃይለ ንባብ” ያሉትንም:- ንባብ፦ “ዛ ይእቲ ማኀተመ ሕይወት መንፈሳዊት፣ እንተ ባቲ አክበሮ እምኩሉ ፍጥረት ዘታሕተ ሰማይ፤ ወትትዐወቅ በኃይለ ንባብ:: ዛ ይእቲ አርአያ ገጹ ለእግዚአብሔር ወአምሳሊሁ፤ ኩናኒተ ሥጋ ወኃይሉ፤ በእንተ ዘኮነት አሐተ ውስተ ኩሉ፤ ወባቲ ይትረከብ ጥበብ ዘየሐስብ ወየኀሪ ልብ፤ ወአእምሮ አዝማን፤ ወመካናት፤ ወኩሉ ምግባራት እንተ ትከውን በዘይእቲ ላዕሌሁ:: በሥልጣን ባሕታዊት ሥዕልት ዘእንበለ ገቢር:: ወገብረ ላቲ ሥልጣነ ውስቴታ ትግብር ዘከመ ኀርየት፤ እንዘ አልቦ ዘይኰንና ወዘይሄይላ፣ ከመ ትኩን ሠናያቲሃ ወእከያቲሃ በስምረተ ኅሊናሃ፤ በአምሳለ መላዕክት” ትርጉም፦ “ይህችም መንፈሳዊት የምትሆን ከሰማይ በታች ካለው ፍጥረት ሁሉ ለይቶ እርሱን ያከበረባት የሕይወት ፍጻሜ ናት:: ምሥጢርንም በመናገር ትታወቃለች፤ የእግዚአብሔር መታወቂያው፤ የምትመስለውም ናት:: ሥጋን የምትገዛው ዕውቀቱም ናት:: በሥራው ሁሉ አንድ ስለሆነች ልብ የሚሻው የሚመረጠውም ጥበብ ዘመኖችንና ቦታቸውን ማወቅ በእርሷ ይገኛል:: የሚሠራውም ሥራ ሁሉ ሥጋን በተዋሐደች በእርሷ ነው:: በዕውቀት ልዩ ናት፤ ግብር እምግብር ያልተፈጠረች ናት:: በጐነቷም ክፉነቷም በመላዕክት አምሳል በራሷ ፈቃድ ይሆን ዘንድ፤ የሚገዛት የሚያዛትም ሳይኖር እንደወደደች ልትሠራ:: የምትሠራበትንም ስልጣን /ዕውቀት/ ለእርሷ ሰጧት ብለዋል” (ዝኒ ከማሁ መቅድመ ወንጌል) ብሏል:: ፊልክዩስም ንባብ፦ “ወእንተሰ እምፍጥረታ ባቲ ሥምረት፣ ክሂል፣ ወፍትወት፣ ለገቢረ ጽድቅ ወአእምሮ ዘበአማን” ትርጉም፦ “ከተፈጠረች ጀምሮ የተሰጣት ፈቃድ ዕውቀትም መሻትም ጽድቅን ለመሥራትና እውነተኛውን እውቀት ለማወቅ ነው” ብሏል:: አሁን ከዚህ በላይ እንደተናገርነው፣ ኃይልም ክሂልም ሥልጣንም የተባለ፣ አእምሮና ንባብ ሕይወትም እንደሆነ፤ “ንግበር ሰብአ በአርአያነ ወበአምሳሊነ” በተባለ በሰው የታወቀ የተረዳ ሲሆን፣ ኃይል ስልጣን ክሂል እንደ አካል ከሦስት ይከፈላል ማለት፤ በሦስቱ አካላት በየራሳቸው ሦስት ልብ፣ ሦስት ቃል፣ሦስት እስትንፋስ አሉ ማለት እንደሆነ ታወቀ ተረዳ፤ እንዲህም ከሆነ፣ የዚህ ሃይማኖት መንገድ የዮሐንስ ተዐቃቢ መንገድ መሆኑ የማይጠረጠር ነው::
ክፍል ፩
አንዳንድ ሰዎች እንደሚናገሩት ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን፣ በአካል ከሦስት የሚከፈልና የሚለይ ከሆነ፤ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል ወልድ በእመቤታችን በድንግል ማሕፀን ሥጋን ፈጥሮ በተዋሐደ ጊዜ የተዋሐደውን ሥጋ በማን አካል ባለ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን ፈጥሮ ተዋሐደ ይባላል፤ በራሱ ስልጣን ብቻ ፈጥሮ ተዋሐደ እንዳይባል፤ አብም መንፈስ ቅዱስም፤ ፈጥረው እንዳልተዋሐዱት መጻሕፍት በብዙ አንቀጽ ይመሰክራሉ:: /ማስረጃ/ ሰሎሞን ንባብ፦ “ትቤ ጥበብ ፈጠረኒ እግዚአብሔር መቅድመ ተግባሩ” ትርጉም፦ “ጥበብ ከፍጥረቱ ሁሉ አስቀድሞ እግዚአብሔር ፈጠረኝ አለች” ብሏልና:: ምሳ ፰÷፳፪ ይህንም ሲተረጉም ባስልዮስ ዘቂሣሪያ ፲፪ኛ ንባብ፦ “ይብል ዘንተ በእንተ ልደቱ በሥጋ ከመ ውእቱ ፍጡር ወግቡር” ትርጉም፦ “በሥጋ ስለተወለደው ልደት ሰው መሆኑን መናገር እንደሆነ ሲያስረዳ “ፈጠረኒ” አለ” ብሏል:: (ሃይ አበው ክፍል ፩) ሃ. አበው ምዕ ፴፪÷፲፫  ዳግመኛም ንባብ፦ “እስመ ብሂለ ወለደኒ ይተረጉም በእንተ መለኮት፤ ወብሂለ ፈጠረኒ ይትረጉም በእንተ ትስብእቱ” “እመሰ ለሊሁ ወልደ እግዚአብሔር ይቤ እስመ እግዚአብሔር ፈጠረኒ ለምንትኑ ይትመለክ እንከ እስመ ብሄለ ወለደኒ ይተረጎም በወልደ እግዚአብሔር ወብሂለ ፈጠረኒ በእንተ ትስብእቱ” ትርጉም፦ “እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር ፈጠረኝ ካለ እንኪያ ለምን አምላክ ይባላል? ቢሉ ወለደኝ ማለት የእግዚአብሔር ልጅ ስለመሆኑ ፈጠረኝ ማለትም ሰው ስለመሆኑ ይተረጎማልና”  ትርጉም፦ “ወለደኒ ያለው ስለ መለኮቱ ይተረጉማል” ብሏላ:: (ሃይማኖተ አበው ክፍል ፪)  (ዝኒ ከማሁ ፴፪÷፲፰ ) ቴዎዶስዮስ ተአማኒ በጽድቅም ፴፩ኛ ንባብ፦ “ወበእንተዝ ይቤ፤ ዝኩ ሥጋ ቅዱስ ጸርሐ እንዘ ይብል፤ ሊተ ለጥበብ ፈጠረኒ እግዚአብሔር እምቅድመ ተግባሩ፤ እስመ ዝኩ ሥጋ ቅዱስ ጥበብ ውእቱ ዘተነግረ በብዙኅ መክፈልት” ትርጉም፦ “ያ ክቡር ሥጋ፣ ጥበብ እንደሆነ፣ በብዙ አንቀጽ ተነግርዋልና፣ ስለዚህ ያ ቅዱስ ሥጋ፤ እግዚአብሔር ከፍጥረቱ አስቀድሞ፤ ጥበብ እኔን ፈጠረኝ ሲል አሰምቶ እንደ ተናገረ ሰሎሞን ተናገረ” ብሏል:: (ሃይማኖተ አበው መልዕክት ፪ኛ) ሃ. አበው ምዕ ፹፫ ÷ ፬-፮ ኢሳያስም ንባብ፦ “ፈጠረኒ በውስተ ከርሥ ከመ እኩን ገብሮ” ትርጉም፦ “አገልጋዩ እሆን ዘንድ በማሕፀን ፈጠረኝ አለ” ብሏል:: ኢሳ ፵፱÷፭ ቅዱስ ጳውሎስም ንባብ፦ “ምእመን ለዘፈነዎ” ትርጉም፦ “ለላከው /ለሾመው/ የታመነ ነው” ያለውን ዕብ ፫÷፪:: ኤጲፋንዮስም ፳፮ኛ ንባብ፦ ”ምእመን በኀበ ዘገብሮ” ትርጉም፦ “በፈጠረው ዘንድ የታመነ ነው” ብሎታል:: (መልዕክት ፫) ሃ. አ በው ምዕ ፶፬÷፶፱ ቴዎዶስዮስም በ፫ኛው መልዕክት ፴፩ኛ ንባብ፦ “በኀበ ዘፈጠሮ” ትርጉም፦ “በፈጠረው ዘንድ” ብሎታል:: በማቴዎስ ወንጌልም ንባብ፦ “እስመ ዘይትወለድ እምኔሃ እመንፈስ ቅዱስ ውእቱ” ትርጉም፦ “ከእርሷ የሚወለደው በመንፈስ ቅዱስ ነው” ያለውን ማቴ ፩÷፳:: ዮሐንስ አፈወርቅ ሲተረጉም:- ንባብ፦ “እስመ መንፈስ ቅዱስ ውእቱ ዘፈጠረ ውስተ ከርሠ ድንግል ሥጋሁ ለቃል፤ ውእቱ እምግብረ ስምረቱ ለመንፈስ ቅዱስ” /ትርጉም/ “በድንግል ማሕፀን ሥጋን የፈጠረ መንፈስ ቅዱስ ከፈቃዱ ሥራ የተገኘ ነው” ብሏል:: ዳግመኛ:- ንባብ፦ “ፈጠረ ሎቱ እግዚአብሔር መቅደሰ ሕያወ በመንፈስ ቅዱስ” ትርጉም፦ “እግዚአብሔር በመንፈስ ቅዱስ ሕያው መቅደስ ሥጋን ፈጠረለት” በታተመው ሃይማኖተ አበው ያለው ዘር ትንሽ ይለያል በምሥጢር ግን አንድ ነው ብሏል:: (ክፍል ፩)  ሃ. አበው ምዕ ፷፮÷፮  ይህን የመሰለ በየአንቀጹ የተናገረው ብዙ ነው፤ ይህን በመመልከት በአብ አካል ብቻ ወይም በመንፈስ ቅዱስ አካል ብቻ ባለ ሥልጣን ተፈጠረ እንዳይባል፣ ወልድ በገዛ ሥልጣኑ ሥጋውን ፈጥሮ እንደተዋሐደ መጻሕፍት ይመሰክራሉ:: /ማስረጃ/ ዘቂሣርያ ባስልዮስ ፲፪ኛ ንባብ፦ “ወኢንብል እስመ አብ ፈጠረ ሎቱ፤ ከመ ኢንረስዮ ነኪረ እምነ መለኮቱ፤ አላ ለሊሁ ፈጠረ ለርእሱ፣ እስመ ቦቱ ምልክና ምስለ አብ በኩሉ ግብር” ትርጉም፦ “አብ ብቻ ሥጋን ፈጠረለት አንልም፤ ከመለኮቱ ልዩ እንዳናደርገው እርሱ እራሱ ሥጋን ፈጠረ እንላለን እንጅ፣ በሥራ ሁሉ ከአብ ጋራ ሥልጣን አለውና” ብሏል:: (ድርሳን ፩ ማር ኤፍሬም) ሃ. አበው ዘባስልዮስ ምዕ ፴፬÷፲፩ ንባብ፦ “ወእምኔሃ ነሥአ ሥጋ ዘውእቱ ፈጠረ፤ ወለሊሁ ፈጠረ ዘነሥአ” ትርጉም፦ “እርሱ የፈጠረውን ሥጋ ከእርሷ ነሣ፤ የነሣውንም ሥጋ እርሱ ፈጠረ” ከታተመው ሃይማኖተ አበው ዘር በቃል አገባቡ ይለያያል ብሏል:: (ድርሳን ፩) ሃ. አበው ዘ ኤፍሬም ምዕ ፵፯÷፬ አውክንድዮስም ንባብ፦ “ወኢተሳተፎ መኑሂ በፈጢረ ሥጋሁ አላ ለሊሁ ፈጠረ ለባሕቲቱ” ትርጉም፦ “ሥጋውን በመፍጠር ማንም አጋዥ አልሆነውም፤ እርሱ ብቻ ሊዋሐደው፣ እርሱ ፈጠረው እንጂ” ብሏል:: (መልዕክት ፩) ሃ.አበው ምዕ ፵፬÷፫ አትናቴዮስም ዘእስክንድርያ:- ንባብ፦ “ወሥጋሁሰ ለእግዚእነ ግቡር ውእቱ እስመ ለሊሁ ገብሮ ለርእሱ” ትርጉም፦ “የጌታችን ሥጋስ ፍጡር ነው፤ እርሱ ለራሱ ፈጥሮታልና” ብሏል:: (ሃ.አበው) ክፍል ፲፬: ይህን የመሰለ የተናገሩ ሊቃውንት ብዙ ናቸውና፣ በየአንቀጹ እየገቡ መመልከት ነው:: ኃይል፤ ክሂል፤ ሥልጣን፤ በአካል ከሦስት የሚለይ ከሆነ፤ ይህ ሁሉ ንባብ በምን ምሥጢር ተስማምቶ ይገኝ ይሆን? እኛስ አባቶቻችን እንደነገሩን፣ ይህን ሁሉ ንባብ በምሥጢር በማስማማት፤ ወልድ በአካሉ ባለች በገዛ ሥልጣኑ ሥጋውን ፈጥሮ ተዋሐደ ብለን እናምናለን:: አምነን በወልድ አካል ያለች ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን፣ በአብና በመንፈስ ቅዱስ አካል ያለች አንዲት ናትና:: መጻሕፍት አንድነታቸውንና ሕልውናቸውን ለመንገር አብ ፈጠረው፤ መንፈስ ቅዱስ ፈጠረው እርሱ፤ እራሱ ፈጠረ ያሉትን የመጻሕፍትን ቃል አስማምተን፤ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን፣ ከሦስት የማይከፈል አንድ እንደሆነ እናምናለን::
ይቀጥላል፡፡
ይቆየን፡፡

Sunday, May 28, 2017

ፍኖተ እግዚአብሔር--- ክፍል ፲



© መልካሙ በየነ

ግንቦት 21/2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ተጽሕፈ እም አሐዱ ሊቅ ኢትዮጵያዊ ኅሩይ ወመፈክራዊ
ጌታው አለቃ ኅሩይ

ክፍል ፩
ሦስቱን በአንድ ልብ እንዲያውቁ፣ በአንድ ቃል እንዲናገሩ፣ በአንድ እስትንፋሰ የሕይወት ሥራ እንዲሠሩ የሚያደርጋቸው፣ ሦስቱን የሚያገናዝብ መለኮት አንድ ቢሆን ነበረ፤ መለኮት በአካል የሚለይ ሦስት ከሆነ ግን፣ ለሦስቱ በየራሳቸው ልብ፣ ቃል፣ እስትንፋስ አላቸው ማለት ግድ ነው:: እንዲህም ከሆነ መጻሕፍት የተናገሩት ቃል ሁሉ ሐሰት ሆነ ማለት ነው:: እኛስ በአካል ሦስት በመለኮት አንድ ብለው አብን ልብ፣ ወልድን ቃል፣ መንፈስ ቅዱስን እስትንፋስ በማለት መጻሕፍት የመሰከሩት እውነት እንደሆነ አውቀን ተረድተን እናምናለን፤ ይህንም የሚያስረዳ አቡሊድስ:- “ወልድሂ ቃሎሙ ለአብ ወመንፈስ ቅዱስ፤ ወመንፈስ ቅዱስሂ መንፈሶሙ ውእቱ ለአብ ወወልድ፤ ወበዝንቱ አእመርነ ከመ ፩ዱ ውእቱ መለኮተ ስላሴ፣ ወሎቱ ንሰግድ:: ወአበዊነሂ እለ ተጋብኡ በኒቅያ ይቤሉ እመቦ ዘይፈልጥ መለኮቶ ለእግዚአብሔር አብ እም ወልድ ወእም መንፈስ ቅዱስ ውጉዘ ለይኩን ብለዋል” ትርጉም፡- “ወልድም ለአብ ለመንፈስ ቅዱስ ቃላቸው ነው፤ መንፈስ ቅዱስም ለአብ ለወልድ  እስትንፋሳቸው ነው፤ የሦስቱ አካላት መለኮት አንድ እንደሆነ በዚህ አውቀን ለርሱ እንሰግዳለን ። በኒቂያ የተሰበሰቡ አባቶቻችንም አንዱን የእግዚአብሔር አብን መለኮት ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ የሚለይ እንደኛ በአብ ትእዛዝ እንደተፈጠሩ የሚናገር ፤ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ከዚህ ከአንዱ ከአብ ባሕርይ አልተገኙም የሚል ቢኖር ውጉዝ ይሁን” ብለዋል።  (አንቀጽ ፴፭ኛ ፩ እይ) ሃ. አበው ምዕ ፴፱ ÷ ፰ ዮሐንስ ዘእስክንድርያም:- ንባብ:- “አአምን በ፩ዱ አምላክ፤ ወአአምር ተዋሕዶተ ሥላሴ፤ ወሥላሴ በተዋሕዶ፤ ወተዋሕዶትኒ በእንተ ፩ መለኮት ዘ፫ አካላት በአሐቲ ክብር፤ ወሥላሴኒ ዓዲ በእንተ ተዋሕዶተ አምላክኒ ዘ፫ አካላት ዘውእቶሙ:- አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ:: እስመ ምሥጢረ ሥላሴ ይትሌለይ በአካላት ወኢይትሌለይ በመለኮት፣ ወለእመኒ ንስምዮሙ ለ፫ አካላት በ፫ አስማት ኢንሬስዮሙ ሠለስተ አማልክተ፤ ወኢይከውን ዝንቱ፤ አላ ፩ አምላክ፤ ዘውእቱ አብ ምስለ ወልዱ ወመንፈስ ቅዱስ እምቀዲሙ እንበለ ፍልጠት::” ትርጉም:- “በአንድ አምላክ አምናለሁ፤ አንድነት በሦስትነት፣ ሦስትነትም በአንድነት እንዳለም አውቃለሁ፤ አንድነትም በአንዲት ክብር ያሉ የ፫ቱ አካላት መለኮት አንድ ስለሆነ ነው:: ዳግመኛም በአምላካችን ተዋሕዶ ላይ የሚነገር ሦስትነትም አካላት ሦስት ስለሆኑ ነው:: እኒሁም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ናቸው:: የሥላሴ ምሥጢር በአካል ይለያያል፤ በመለኮት ግን አይለይምና፣ ሦስቱን አካላትም በሦስት ስሞች ብንጠራቸው፣ ሦስት አማልክት አናደርጋቸውም:: ሦስት አማልክት ማለት አይገባምና፣ አንድ አምላክ ናቸው እንጅ:: ይኸውም ከጥንት ጀምሮ ያለመለየት ከልጁና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ የነበረ አብ ነው ብሏል::” /ሃይ. አበው ድርሳን ፩/ ሃ. አበው ምዕ ፺ ÷ ፭ ዳግመኛም ንባብ:- “እንዘ ሊሉያን እሙንቱ ይከውኑ ፩ እስመ መለኮተ ሥላሴ ፩ ወበሰለስቲሆሙ ሀሎ ፩ መለኮት::” ትርጉም:- “ልዩ ሲሆኑ በአንድነት ይኖራሉ:: የሦስቱ መለኮት አንድ ነውና፣ በሦስቱም አካላት አንድ መለኮት አለና ብሏል::” /ሃይ.አበው ድርሳን ፩/ (ዝኒ ከማሁ ቁ. ፲፫)፡፡ ፴፭ኛ ዮሐንስ ዘእስክንድርያም ንባብ:- “ንሕነሰ ነአምን ከመ ወልድ ይትዋሐድ በመለኮት ምስለ አብ ወመንፈስ ቅዱስ:: ወእመቦ ዘኢየአምን ከመ ፩ መለኮት ንሕነ ናውግዞ” ትርጉም:- “እኛስ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በመለኮት እንዲዋሐድ እናምናለን:: መለኮት አንድ እንደሆነ የማያምን ቢኖር ግን እኛ እናወግዘዋለን” (ዝኒ ከማሁ ምዕ ፺ ÷ ፲፭ )ብሏል:: ኪራኮስም ፴፮ኛ ንባብ:- “ወእሙንቱ ይነብቡ በዘያብህም ልሳናቲሆሙ እንተ ኢኮነት ግሥጽተ:: አኮ ከመዝ ሃይማኖትነ ለነሰ ለርቱዓን፤ አላ ፩ አምላከ ንሰብክ፣ ወ፩ ሕላዌ ወ፩ መለኮተ፣ ወ፩ ኃይለ፤ ወኢንብል ከመ በዝየ ሱታፌ ለ ፫ አካላት፣ በከመ ይቤ ዮሐንስ ዘይሰመይ ተዐቃቢ ዘይትሜካህ በእበዱ ምስለ እለ ይብሉ ሠለስቱ አማልእክት ወሠለስቱ ሕላዌ ዘሠለስቱ አካላት:: አኮ ዝንቱ ንባበ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን::” ትርጉም:- “ያልተሠራች ያልተቀጣች አንደበታቸውን ምላሽ የሚያሳጣ ነገርን ይናገራሉ:: የቀና እምነትን የምናምን የእኛ ግን፣ እምነታችን አንድ አምላክ ብለን ነው እንጅ፣ ሦስት አማልክት ብለን አይደለም:: በአንድ ኃይል ያለ አንድ ባሕርይ አንድ መለኮት እንደሆነ እናስተምራለን:: በዚህ አንቀጽ መለኮትን አንድ ነው እንዳልነ፣ ልዩ ልዩ የሚሆኑ አካላትን አንድ የምንል አይደለንም:: በስንፍናው የሚመካ ተዐቃቢ የሚባል ዮሐንስ ሦስት አማልክት ከሚሉ ሰዎች ጋራ የሦስቱን አካለት በባሕርይ ሦስት እንዳለ፣ መለኮትን አንድ በማለታችን አካላትን አንድ አንልም:: ይህ የቅድስት ቤተክርሰቲያን አነጋገር አይደለምና” ብሏል:: (ሃይ. አበው መልዕክት ፩) ሃ.አ በው ምዕ ፺ ፩ ÷ ፲-፲፩፡፡ ዳግመኛም:- ንባብ፦ “ንትዐቀብ ከመ ኢንምሀር በልሳናቲነ በዝንቱ መካን ከመ ንብል ሠለስቱ አማልክት ወ፫ ሕላውያት እስመ ዘይብል ዘንተ ናሁ ተሀበለ ያስተጋብዕ ሎቱ ብዙኃነ አማልክተ::” ትርጉም:- “ሦስት አካላት በማለታችን ሦስት አማልክት ሦስት ሕላውያት የማለትን ትምህርት ለአንደበታችን ልማድ ከማድረግ እንጠበቅ:: ይህን የሚል ሰው እነሆ ብዙ አማልክትን ይሰበስብ ዘንድ ይደፍራልና” ብሏል:: (ዝኒ ከማሁ ቁ. ፲፮)፡፡  ዮሐንስ ዘአንጾኪያ ፵፯ኛ ንባብ:- “ንህነሰ ናሰትት የታተመው “ናዓትት” ይላል ቃሎሙ ለአላውያን እለ ይትአመኑ ብዙኃነ አማልክተ ወሕላውያተ ፍሉጣነ ለ፩ እግዚአብሔር ዘኢይትከፈል በሕላዌ መለኮት:: ወናወግዝ ዓዲ እለ ይብሉ ሠለስቱ መለኮት እንተ ዘአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ::” ትርጉም፦ “እኛስ በመለኮት ባሕርይ ለማይለይ ለአንድ እግዚአብሔር ልዩ ልዩ ሕላውያትን የሚሰጡ ብዙ አማልክትን የሚያመልኩ የአላውያንን ትምህርታቸውን እንነቅፋለን:: ዳግመኛም የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ የሚሆን መለኮትን ፫ የሚሉትን እናወግዛለን” ብሏል:: (ሃይ. አበው ክፍል ፩) ሃይማኖተ አበው ምዕ ፶፫ ÷ ፬ ዳግመኛም:- ንባብ:- “ወሶበሂ ንቤ ሠለስቱ አካላት በበአካላቲሆሙ ንቤ ፩ ባሕርየ ፍጹመ፣ ወ፩ ሕላዌ ወ፩ መንግሥት ወ፩ እበይ ወ፩ ክብር ይትበሀሉ በእንተ እሉ ሠለስቱ አካላት አብ ብርሃን ወልድ ብርሃን መንፈስ ቅዱስ ብርሃን እንዘ ፩ ብርሃን ዘኢይትከፈል ወዘኢይትዌለጥ በሕላዌ መለኮት:: ወዓዲ ንብል አብ ሕይወት ወልድ ሕይወት መንፈስ ቅዱስ ሕይወት እንዘ ፩ ሕይወት:: ወካእበ ይተበሀል አብ ፩፤ ወልድ ፩ መንፈስ ቅዱስ ፩ ወለለ ፩ እምአካላት ፩ ሕላዌ ወ፩ አምላክ እሙንቱ:: ወኢይትበሀሉ ፫ አማልክተ አኮ ዘንተአመን በ፫ እደው ወ፫ አማልክት ወኢበ ፫ መለኮት:: አላ ንትአመን በ፫ አካላት ወ፫ ገጻት እንተ ፩ ባሕርየ መለኮት” ትርጉም:- “፫ አካላት በየአካለቸው አሉ ብንል፣ ፍጹም ባሕርይን ፩ ፣ ሕልውናንም አንድ ብለን፣ ፩ መንግሥት አንድ እበይ /ጌትነት/ አንድ ክብር ነው እንላለን:: አካላት ፫ ስለሆኑ በመለኮት ሕላዌ /አኗኗር/ የማይከፈልና የማይለይ አንድ ብርሃን ሲሆን፣ አብ ብርሃን፣ ወልድ ብርሃን፣ መንፈስ ቅዱስ ብርሃን ይባላሉ:: ዳግመኛም በመለኮት አኗኗር አንድ ሕይወት ሲሆኑ አብ ሕይወት፣ ወልድ ሕይወት፣ መንፈስ ቅዱስ ሕይወት ነው እንላለን:: ዳግመኛም አብ አንድ ይባላል፣ ወልድ አንድ ይባላል፣ መንፈስ ቅዱስ አንድ ይባላል:: ከአካላትም እያንዳንዱ አንድ ሕላዌ አንድ አምላክ ናቸው:: ሦስት አማልክት ግን አይባልም:: መገናዘብ እንደሌላቸው ሰዎች አድርገን በሦስት ሰዎች በሦስት አማልክት፣ በሦስት መለኮት፣ የምናምን አይደለንም:: ባሕርየ መለኮት አንድ በሚያድርጋቸው በሦስት አካለት፣ በሦስት ገጻት እናምናለን እንጂ”  ሃ. አበው ዘዮሐንስ ምዕ ፻፲፬ ÷ ፬-፮  ብሏል:: ዳግመኛም:- ፶፫ኛ ዲዮናስዮስ ዘአንጾኪያ:- ንባብ:- “ወንትአምን በዝንቱ ሕላዌ፣ ወንሰግድ አሐተ ስግደተ፤” ብሎ ተነሥቶ /አንቀጽ ፩ እይ/ “ንህነሰ ንሰብክ ከመዝ ወንሰግድ ለ፩ አምላክ ባሕቲቱ፣ ወንትአመን ከመ ፩ መለኮት ዘሠለስቱ አካላት፣ ወኢንበውእ ውስተ ከፊለ መለኮት ወመንግሥት:: አላ ንብል ፩ ሕላዌ፣ ወ፩ መንግሥት፣ ወአሐቲ ሥምረት፣ ወ፫ አካላት ወ፫ ገጻት እንበለ ተዘርዎ::” ትርጉም “እኛስ እንዲህ እናስተምራለን፤ ለአንድ አምላክ ብቻም እንሰግዳለን:: የ፫ አካላት መለኮትም አንድ እንደሆነ እናምናለን:: መለኮትንም መንግሥትንም ወደ መክፈል አንገባም:: አንድ ሕልውና፣ አንድ መለኮት፣ አንድ መንግሥት፣ አንድ ፈቃድ፣ ያለመለያየትም፣ ሦስት አካላት፣ ሦስት ገጻት እንላለን እንጂ ብሏል:: (እመልዕክተ ሲኖዲቆን) ዳግመኛም:- ንባብ:- “ውእቱሰ ፩ አምላክ ወአኮ ፫፡ ፩ እግዚእ ወአኮ ብዙኃን:: ወክብረ ምልክናሂ ልዑል ለመለኮት፤ ወበመለኮት ምልክና፤ ወቅድስት ሥላሴ ይእቲ ትትመለክ፤ ወትትአመር በ፫ አካላት:: ወተዋሕዶተ መለኮቶሙ ርሑቅ እምኩሉ ክፍለት፤ ወእመኩሉ ፍልጠት::” ትርጉም:- “እርሱስ አንድ አምላክ ነው እንጂ ፫ አማልክት አይደለም፤ አንድ ጌታ ነው እንጅ ሦስት ጌቶች አይደለም:: ከፍ ያለ የአምላክነት ክብርም ለመለኮት ነው፤ መግዛትም በመለኮት ነው:: ልዩ ሦስትነትም በሦስት አካላት እንዳለች ታውቋል፤ በአንድነትም ትመለካለች:: የመለኮታቸውም አንድነት ከመከፈል ከመለየትም የራቀ ነው”ብሏል:: (፳፫ኛ እመልዕክተ ሲኖዲቆን) ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙም:- “ወኢይትሀበሉ ኅጉላን ያብኡ ውስተ ቅድስት ሥላሴ ፍልጠተ መለኮት” ብሏል:: (አንቀጽ ፩ እይ ሃይ. አበው ፪) ሱኑትዮስ ዘእስክንድርያ:- ንባብ:- “ዘኢየአምን ወዘኢይትአመን ከመ ፩ መለኮቶሙ፤ ወ፩ ህላዌሆሙ፤ እንተ ሠለስቲሆሙ፣ ወ፩ ቃሎሙ፣ ወ፩ ምግባሮሙ ውጉዘ ለይኩን::” ትርጉም:- “ሦስት ሲሆኑ መለኮታቸው አንድ፣ ሕልውናቸውም አንድ፣ ቃላቸውም አንድ፣ ምግባራቸው አንድ እንደሆነ የማያምንና የማያሳምን የተለየ ይሁን” ብሏል:: (ሃይ. አበው ክፍል ፩) ሃይማኖተ አበው ምዕ ፻፲ ÷ ፵፩ ፵፱ኛ አትናቴዎስ ዘአንጾኪያም:-  “ወሶበሂ ንቤ ፩ እግዚእ ወ፩ ህላዌ ወ ፩ መለኮት” አንድ ጌታ አንድ አኗኗር አንድ መለኮት ባልን ጊዜ  ብሏል:: (አንቀጽ ፪ እይ) ሃይማኖተ አበው ምዕ ፻፮ ÷ ፰ ባለቤቱም ጌታ በኦሪት:- ንባብ:- “ኢታምልክ ባዕደ አምላከ ዘእንበሌየ” ብሏል:: ትርጉም:- “ከእኔ በቀር ሌላ ባዕድ አምላክ አታምልክ” አለ:: ዘጸ.፳÷፫፤ አንድ አድርጎ በአንድ አንቀጽ “ዘእንበሌየ” አለ እንጂ ከሦስት ለይቶ “ዘእንበሌነ” አላለም:: ዳዊትም:- ንባብ:- “ወኢትስግድ ለአምላክ ነኪር፤ እስመ አነ ውእቱ እግዚአብሔር አምላክ፤ ዘአውጻእኩከ እምድረ ግብፅ” ትርጉም:- “ለባዕድ አምላክ አትስገድ፣ እኔ እግዚአብሔር አምላክህ ነኝና ከግብጽ ምድር ያወጣውህ አለ እግዚአብሔር” ብሏል:: መዝ. ፹፩÷፱ አንድ አድርጎ በአንድ አንቀጽ “አነ አምላክከ” አለ እንጅ፤ ከሦስት ከፍሎ አብዝቶ “ንሕነ አማልክቲከ” አላለም፤ ሙሴም በኦሪት:- ንባብ:- “ስማዕ እስራኤል ፩ እግዚአብሔር አምላክከ”:: ትርጉም:- “እስራኤል እግዚአብሔር አምላክህ አንድ እንደሆነ ስማ ዕወቅ” ብሏል:: ዘዳ ፮÷፬ ጌታም በወንጌል ንባብ:- “አነ ወአብ ፩ ንሕነ” ትርጉም፦”እኔና አብ አንድ ነን” ብሏል:: ዮሐ ፲:፴  ዳግመኛም ንባብ:- “ለግብርየ እመኑ አንትሙ፤ ከመ ታእምሩ ወትጠይቁ፤ ከመ አነ በአብ፣ ወአብ ብየ” ትርጉም:- “በሥራየ እመኑ ታውቁ ትረዱም ዘንድ፣ አብ በእኔ እንዳለ፤ እኔ በአብ” ብሏል ዮሐ ፲÷፴፰:: ይህ ሁሉ ቃል መለኮትንና አምልኮትን ከሦስት የማይከፍል ሦስቱን አካላት የሚያዋሕድና የሚያገናዝብ እንደሆነ የሚያስረዳ ነው:: ይህንም የመሰለ በየአንቀጹ የተነገረው ብዙ ነው፤ ነገር ግን ሁሉን ልንጽፈው አይቻለንምና ከባሕሩ ገብቶ በየአንቀጹ መመልከት ነው::
ይቀጥላል፡፡
ይቆየን፡፡

Thursday, May 25, 2017

ፍኖተ እግዚአብሔር--- ክፍል ፱



© መልካሙ በየነ

ግንቦት 18/2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ተጽሕፈ እም አሐዱ ሊቅ ኢትዮጵያዊ ኅሩይ ወመፈክራዊ
ጌታው አለቃ ኅሩይ
===========================

፲፪ኛ አንቀጽ
የመለኮት ንባቡ አንድ ትርጓሜው ብዙ እንደሆነ ይናገራል::
መለኮት ንባቡ አንድ ሲሆን፣ ትርጓሜው ብዙ ነው ፩ኛ ብርሃን ይሆናል:: ማስረጃ:- አግናጥዮስ:- ንባብ:- “እኁዛን እሙእንቱ በፅምረተ ፩ መለኮት ዘውእቱ ብርሃን ዘይሰርቅ እምኔሁ ሥላሴ” እንዳለ:: ሃይማኖተ አበው ምዕ ፲፩ ÷ ፰-፱ ጥያቄ:- በዚህ አንቀጽ ብርሃን የተባለ መለኮት ከሦስት የሚከፈል ከሆነ፣ አንዱን ልብስ ሦስት ሰዎች ከሦስት እንዲለብሱ፣ ሦስቱ አካላት አንዱን ብርሃን ከሦስት ተካፈሉት ሊባል ይገባልን? መልስ:- እኛስ በአብ አካል ያለች ብርሃን በወልድ አካልና በመንፈስ ቅዱስ ያለች አንዲት ብርሃን ናትና፣ “በአንድ መለኮት አንድ አድራጊነት፤ የተገናዘቡ ናቸው፤ ይህም መለኮት የአካል ሦስትነት የሚገኝለት አንድ ብርሃን ነው” ብሎ አግናጥዮስ ስለነገረነ፤ ከሦስት የማይከፈል አንድ ብርሃን በሦስቱ አካላት እንዳለ እናምናለን:: ማስረጃ:- ዮሐንስ ዘአንጾኪያ ፶፩ኛ ንባብ:- “አብ ብርሃን ወልድ ብርሃን መንፈስ ቅዱስ ብርሃን ዳዕሙ ውእቱ ፩ ብርሃን ዘኢይትከፈል ወኢይትዌለጥ በህላዌ መለኮት” ትርጉም:- “አብ ብርሃን ነው ወልድ ብርሃን ነው መንፈስ ቅዱስ ብርሃን ነው፤ ነገር ግን በመለኮት ሕላዌ የማይለወጥ የማይከፈል አንድ ብርሃን ነው” ብሏል:: (ሃይ. አበው ክፍል ፩) ሃይማኖተ አበው ምዕ ፻፲፬÷፭፡፡ ፪ኛ ሕይወት ይሆናል ማስረጃ:- አግናጥዮስ ዘአንጾኪያ:- ንባብ:- “ኢተአምርኑ ከመ ለእመ ትቤ መለኮት ሞተ፣ ትከውን ቀታሊሆሙ ለሥሉስ ቅዱስ እስመ ባሕርየ ሥላሴ ፩ ውእቱ ዘውእቱ ፩ መለኮት” ትርጉም:- “መለኮት ሞተ ብትል አንተ የሥሉስ ቅዱስ ገዳያቸው እንድትሆን አታውቅምን? የሥላሴ ባሕርይ አንድ ነውና፤ ይኸውም አንድ /ሕይወት/ መለኮት ነው” ብሏል:: (ሃይ. አበው ክፍል ፩) ሃይ. አበው ምዕ ፲፩ ÷ ፲፫-፲፬ በዚህ አንቀጽ መለኮት የተባለ ባሕርይ ሦስቱን አንድ የሚያደርግ አንድ ሕይወት እንደሆነ ያስተውሏል:: ሕይወት የተባለ መለኮት በአካል ከሦስት የሚከፈል ከሆነማ አንዱ ቢሞት ሦስቱ ሞቱ እንደምን ባላሰኛቸውም ነበር? አንድ ቢሆን አይደለምን? በሕይወት ከሚመሳሰሉ ብዙ ሰዎች አንዱ ቢሞት ሁሉም ሞቱ ያሰኛልን:: ፫ኛ አገዛዝ ይሆናል:: ማስረጃ:- ነቢዩ ዳዊት ንባብ:- “ውስተ ኩሉ በሐውርት መለኮቱ” ትርጉም:- “አገዛዙ በሀገሮች ሁሉ ነው” እንዳለ:: መዝሙር ፻፪÷፳፪ ፬ኛ ጌትነት ይሆናል:: ማስረጃ:- ጳውሎስ ንባብ:- “ወከመዝ ይትአመር ኃይሉ ወመለኮቱ ዘለዓለም” ትርጉም:- “የዘለዓለም የሚሆን ኃይሉ ጌትነቱም እንዲህ ይታወቃል” እንዳለ:: (ሮሜ ፩÷፳) ቅዱስ ጴጥርስም ንባብ:- “ዘበኃይለ መለኮቱ ወኀበ ለነ ኩሎ ምግባረ ዘይወስድ ኀበ ሕይወት ወጽድቅ” ትርጉም:- “በጌትነቱ ኃይል ወደ ሕይወትና ወደ ጽድቅ የሚወስድ ምግባርን የሰጠን” ብሏል:: (፪ኛ ጴጥ ፩÷፫) ኄሬኔዎስም ፫ኛ:- ንባብ:- ቅዱስ ጳውሎስ “እስመ ዘሐመ ተሰቅለ በድካም፤ ሕያው ውእቱ በኃለ እግዚአብሔር” ትርጉም:- “ደክሞ የተሰቀለውና የሞተው በእግዚአብሔር ኃይል ሕያው ነው” ያለውን (፪ኛ ቆሮ ፲፫ ÷፬-፭) ሲተረጉም:- ንባብ፦ “ወሐይወ በኃይለ እግዚአብሔር ዘውእቱ መለኮት” ትርጉም:- “በእግዚአብሔር ኃይል ተነሣ፣ ይኸውም መለኮቱ ነው” ብሏል:: (ሃይ. አበው ክፍል ፩) ሃይ. አበው ምዕ ፯ ÷ ፴ በዚህ መለኮት የተባለ ጌትነት ወይም ሥልጣን እንደሆነ ማስተዋል ነው:: ፭ኛ ክብር ይሆናል:: ማስረጃ:- ሐዋርያው ጴጥሮስ ንባብ:- “ከመ በእንተ ዝንቱ ትኩኑ ሱቱፋነ ለመለኮተ ዚአሁ” ትርጉም:- “ስለዚህ ነገር የክብሩ ተካፋዮች ትሆኑ ዘንድ ለምግባር ለትሩፋት ሁሉ” ፪ኛ ጴጥሮስ ፩÷፬ ባለው መረዳት ነው:: ፮ኛ ባሕርይ ይሆናል:: ማስረጃ:-(፶፪ኛ) ዲዮናስዮስ ሊቀ ዻዻሳት ዘአንጾኪያ:- ንባብ:- “ይሴለሱ በአካላት ወይትወሐዱ በመለኮት” እንዳለ አንቀጽ ፪ እይ:: ፯ኛ አምላክነት ይሆናል:: ማስረጃ (፶፭ኛ)/ዮሐንስ ዘአንጾኪያ ንባብ:- “ይገብር መንክራተ በመለኮቱ፤ ወይትዌከፍ ሕማማተ በትስብእቱ” ትርጉም:- “በአምላክነቱ ተአምራትን ያደርጋል፣ በሰውነቱ መቀበል” አንዳለ (ክፍል አንድ) እመልክተ ሲኖ. በ፲፩ኛው አንቀጽ፤ ነገሩን ኋላ በ፲፪ኛ አንቀጽም እናመጣዋለን ያልነው ይህ ነው::ሲኖዲቆን ይህ ሁሉ አንድ  የሚሆኑበትና የሚገናዘቡበት ነው እንጂ፤ የሚለያዩበት አይደለም:: ይህን ያህል ስህተት የሚያመጣ የመለኮትን የምሥጢሩን ስልት አስተውሎ አለመመልከት ነው:: መለኮት በአካላት የሚለይ ቢሆንስ፣ ሦስቱ ባልተጠሩበትም ነበረ:: ወላዲ፣ ተወላዲ፣ ሰራጺ ማለት በግብር፤ አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ ማለት  አካል፤ ልብ፣ ቃል፣ እስትንፋስ ማለት በከዊን፤ የሚለያዩባቸው ስሞች ስለሆኑ፤ እየራሳቸው ተጠሩባቸው እንጂ ሦስቱ ሁሉ አልተጠሩባቸውም፤ አምላክ፣ መለኮት፣ ከዊን ማለት ነው:: እግዚአብሔር ማለት ግን በባሕርይ አንድ የሚሆንበት በሕልውና የሚገናዘቡበት በመሆኑ ሦስቱ ተጠሩበት:: ሐተታ:- ሦስቱ መለኮት ለማለት፤ ሳዊሮስ ዘገብሎን በተረፈ ቄርሎስ “እስመ ፫ቱ ኁልቈ መለኮቱ” ያለውን የሚጠቅስ ቢኖር፣ መልሱ ምሥጢሩን ባይመለከት ነው እንጂ ቢመረምረውስ ይህን ምስክር አድርጐ ባልተነሣም ነበር፤ አሁን በአርእስቱ እንደተናገርነው፤ሦስቱ ስለተጠሩበት “፫ ኍልቊ መለኮቱ” አለ:: የሚዋሕዱበት አንድ እንደሆነ ሲያስረዳ መለኮቱ ብሎ በአንድ አንቀጽ ተናገረው:: እንደእነሱ አነጋገር ቢሆን ኖሮ ግን “መለኮታቲሆሙ” ባለ ነበረ እንጂ፣ መለኮቱ ባላለም ነበር:: ምሥጢሩም አትናቴዎስ ዘእስክንድር:- ንባብ:- “አምላክ ውእቱ አብ፣ አምላክ ውእቱ ወልድ፣ አምላክ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፤ ወኢይትበሀሉ ሠለስተ አማልክተ፤ አላ ፩ አምላክ” ትርጉም:- “አብ አምላክ ነው፣ ወልድ አምላክ ነው፣ መንፈስ ቅዱስ አምላክ ነው፤ ነገር ግን አንድ አምላክ ይባላሉ እንጂ፣ ሦስት አምላክ አይባሉም” (ሃይ. አበው ክፍል ፬) ሃይማኖተ አበው ዘአትናቴዎስ ምዕ ፳፭ ÷ ፬  ብሏል:: ልብ፣ ቃል፣ እስትንፋስ ማለት በከዊን የሚለያዩበት በህልውና የሚገናዘቡበት እንደሆነ ከዚህ አስቀድመን በ፪ኛው አንቀጽ ተናግረናል:: ይህውም ሕያዋን የሚያሰኛቸው ሕይወት ነው፤ ሕይወትም እንደሆነ “ንግበር ሰብአ በአርአያነ” ባለው በሰው ይታወቃል:: ሰው አእምሮው ንባቡ እስትንፋሱ የተለየው እንደሆነ ሞተ ይባላል፤ ካልተለየው ግን ሕያው ነው ይባላል እንጂ ሞተ አይባልም:: የእግዚአብሔር የባሕርዩን ከዊን ከሚመሰክሩ መጻሕፍት አንድ ደገኛ መጽሐፍ ሰው ነውና:: ማስረጃ:- ቅዱስ ቁርሎስ ዘእስትጉቡዕ ንባብ:- “ወኮንኩ መጽሐፎ ለክርስቶስ” ትርጉም:- “የክርስቶስ መጽሐፍን ሆንኩ” ንባብ:- “ወየአምር መጽሐፈ እግዚአብሔር” ትርጉም፦ “የእግዚአብሔር መጽሐፍ ሰው ያውቃል” እንዳለ፤ በ፲፩ኛው አንቀጽ ነገሩን ኋላ በ፲፪ኛ አንቀጽም እናመጣዋለን ያልነው ይህ ነው::
፲፫ኛ አንቀጽ
ሥላሴ ዓለምን በአንዲት ቃል እንደፈጠሩ
“ለሥላሴ በየራሳቸው ልብ፣ ቃል፣ እስትንፋስ አላቸው ካልተባለ፣ ሥላሴ በአካል ፍጹማን ናቸው አያሰኝም” ለተባለው ጥያቄ መልሱን ከነምስክሩ በ፲ኛው አንቀጽ አስረድተናል፤ ከዚያ የቀረውንም በዚህ አንቀጽ እንናገራለን:: ለሦስቱ አካላት በየራሳቸው ቃል አላቸው ማለት እንዳይገባ ቃላቸውም አንድ ወልድ ብቻ እንደሆነ የሚያስረዳ ነገር በሥነ-ፍጥረት እናሳያለን:: እግዚአብሔር በዕለተ እሑድ “ለይኩን ብርሃን” ካለ ጀምሮ፤ በዕለተ ዓርብ፣ “ንግበር ሰብአ በአርአያነ” እስኪል ድረስ በነቢብ የፈጠረው ፍጥረት ብዙ ነው:: በማንኛቸው ቃል ተፈጠረ ይባላል በአብ በተለየ ቃሉ እንዳይባል ፍጥረት የተፈጠረ በወልድ ቃልነት እንደሆነ መጻሕፍት በብዙ አንቀጽ ይመሰክራሉ:: ከብዙም በትቂቱ የሚያስረዳ ዮሐንስ ወንጌላዊ:- ንባብ:- “ቀዳሚሁ ቃል ውእቱ” ትርጉም:- “አስቀድሞ ቃል ነበረ” ብሎ ተነሥቶ ንባብ:- “ወቦቱ ኩሉ ኮነ ወዘእንበሌሁሰ አልቦ ዘኮነ ወኢምንትኒ እምዘኮነ” ትርጉም:- “ሁሉም በእርሱ ሆነ ያለ እርሱ ግን የሆነ የለም ምንም ከሆነው ሁሉ” ብሏል:: ዮሐ ፩÷፪-፫ ቅዱስ ጳውሎስም:- ንባብ:- “ወአሐዱ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘኩሉ በእንቲአሁ ወንሕነኒ ቦቱ” ትርጉም፦ “አንድ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉ በእርሱ የሆነ፣ እኛም በእርሱ” ብሏል:: ፩ቆሮ ፰÷፮ ዳግመኛም ንባብ:- “ወበድኀሪሰ መዋዕል በወልዱ ዘረሰዮ ወራሴ ለኩሉ፤ ወቦቱ ፈጠሮ ለኩሉ” ትርጉም:- “እርሱ በኋለኛው ዘመን በልጁ ነገረን፤ ሁሉን ወራሽ ባደረገው፣ ዓለሙንም ሁሉ በፈጠረበት” ብሏል:: ዕብ ፩÷ ፪ ከአረጋዊ መንፈሳዊ ማስረጃ ንባብ:- “ወዓዲ ይሰመይ ወልድ በእንተ ዘተፈጥረ ቦቱ ኩሉ፤ ወካዕበ ወልድ ይሰመይ ቃለ፣ እስመ አእምሮቱ ለእግዚአብሔር ውእቱ” ትርጉም:- “ዳግመኛ ሁሉ በእርሱ ስለተፈጠረ ወልድ ይባላል፤ ወልድም ቃል ይባላል፣ የእግዚአብሔር መታወቂያው ነውና” ብሏል:: /ድርሳን ፳፪/ አትናቴዎስም ዘእስክንድርያ ፲፩ኛ ወደ አክኒጦስ በጻፈው መጽሐፍ አክኒጦስ የቆጵሮስ ኤጲስ ቆጶስ ነበር ። ሃ.አ በው ምዕ ፳፱ ÷፩ ገጽ ፺ ንባብ:- “ኢንፈልጦ ለወልድ እምቃል፣ ከመ ካልእ ውእቱ፤ ወባሕቱ ንብል እስመ ቃል ውእቱ ወልድ ዘቦቱ ኩሉ ኮነ” ትርጉም:-  ወልድን ከቃልነቱ ልዩ አድርገን አናወጣም፤ ወልድ ዓለም ሁሉ የተፈጠረበት ቃል ነውና፣ ወልድ ቃል ነው እንላለን እንጂ” ብሏል:: (ድርሳን ፲፭) ይህን የመሰለ በየአንቀጹ የተናገረው ብዙ ነው:: ደግሞ ይህን ተመልክተን በወልድ ቃልነት ብቻ ተፈጠረ እንዳንል፤ አብን ከፈጣሪነት ማውጣት ይሆናል፤ በዚኸውም ቃል አልፈጠረም እንዳንል ገንዘቡ ባልሆነ በሌላ ቃል ተናገሮ ፈጠረ ማለት ለልቦና አይረዳም:: ይህ ካልሆነ ብለን አብን ከፈጣሪነት እንዳናወጣውም በየአንቀጹ መጻሕፍት ይመሰክሩብናል:: ማስረጃ:- ሙሴ እስራኤልን /ንባብ/ “አኮኑ ዝንቱ አብ ፈጠረከ፤ ፈጠረከሂ ወገብረከ” ትርጉም:- “ይህ አብ የፈጠረህ አይደለምን? ፈጥሮ ወገን ያደረገህ አይደለምን?” ብሎታልና ዘዳ ፲፪÷፮ በዚህ አንቀጽ “ንግበር ሰብአ በአርአያነ ወበአምሳሊነ” ያለው የአብ ቃል እንደሆነ ያስረዳል:: ነቢይም ንባብ:- “ወበቃለ እግዚአብሔር ፀንዓ ሰማያት፣ ወእምእስትንፋሰ አፉሁ ኲሉ ኃይሎሙ” ትርጉም:- “በእግዚአብሔር ቃል ሰማዮች ተሠሩ፤ ሃ. አበው ምዕ ፴፩ ÷ ፵፩ ሠራዊቶቻቸውም ሁሉ በአፉ እስትንፋስ” ብሏል:: መዝ ፴፫ ÷፮ ዮሐንስ ወንጌላዊ በቅዳሴው ንባብ:- “ወኩሎ ተግባረከ ፈጠርከ በቃልከ” ትርጉም “ፍጥረትህን ሁሉ በቃልህ ፈጠርህ” ብሏል:: አትናቴዎስም ዘእስከንድርያ ንባብ:- “ፈጠረ አብ ኩሎ ፍጥረተ በቃሉ፣ ዘውእቱ እምነ መለኮቱ ወበመንፈሱ ቅዱስ” ትርጉም:- “አብ ፍጥረቱን ሁሉ ከባሕርይው በተገኘ በቃሉና በቅዱስ መንፈሱ ፈጠረ” ብሏል:: (ሃይ. አበው ፲፫ ክፍል) ሃ.አ በው ምዕ ፴፩ ÷ ፵፩ ሠለስቱ ምዕትም ፫ኛ በፀሎተ ሃይማኖት ንባብ:- አብን “ገባሬ ሰማያት ወምድር ዘያሰተርኢ ወዘኢያስተርኢ” ትርጉም:- “ሰማያትና ምድርን የሚታየውንም የማይታየውንም የፈጠረ” ወልድንም ንባብ:- “ዘቦቱ ኲሉ ኮነ ወዘእንበሌሁሰ፣ አልቦ ዘኮነ ወኢምንትኒ ዘበሰማይኒ ወዘበምድርኒ” ትርጉም:- “ሁሉ በእርሱ የተፈጠረ በሰማይም በምድርም ያለ እርሱ የተፈጠረ ምንም የለም” ብለዋል::  ይህን የመሰለ በየአንቀጹ የተነገረው ብዙ ነው:: ነገር ግን መጻሕፍት ፍጥረት ሁሉ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ ገንዘብ በሚሆን በአንድ ቃል ተፈጠረ ሲሉ፣ ሦስቱን አካላት በአንድ መለኮት የማያገናዝቡ ሰዎች በየራሳቸው ሦስት ቃሎች አሉ ባሉ ጊዜ፣ በማናቸውም ቃል ተፈጠረ ይሉት ይሆን ወይስ በሠርግ፣ በዱለት፣ በገበያ የተሰበሰበ ሰው፣ ሁሉም በየቃሉ እየተናገረ፣ በአንድነት ሲጮህ እንዲሰማ፣ ሦስቱ አካላት በየቃላቸው አንድ ጊዜ ሲናገሩ ተሰሙ ይሉ ይሆን፣ መጻሕፍት በመሰከሩ ነው እንጂ፤ በጉሥዓተ ልብ አይደለምና፣ ይህ ከብዙ ስህተት የሚያደርስ ስለሆነ፣ ይህን ነገር ጠንቅቀን እናስተውል::
ይቀጥላል፡፡
ይቆየን፡፡

ለቤተክርስቲያናችን ዘበኞች ራሳችን እንሁን!



© መልካሙ በየነ

ግንቦት 17/2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ቤተ ክርስቲያናችን ይህን ያህል ዘመን ስትኖር በፈተናዎች አልፋ ነው፡፡ አርዮስ ወልድ ፍጡር ብሎ በመነሣቱ አልተናወጠችም እለ እስክንድሮስን ወልዳለችና፡፡ ቀጥሎም መቅዶንዮስ መንፈስ ቅዱስ ሕጹጽ ብሎ ተነሣ በዚህም አልተናወጠችም  ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙን፣ ኔክታሪዎስን እና  የእስክንድርያው ጢሞቴዎስን ወልዳለችና፡፡ ንስጥሮስ ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ አይደለችም ወላዲተ ሰብእ ናት በማለቱ ቤተክርስቲያናችን አልተናወጠችም ቄርሎስን ወልዳ አሳድጋለችና፡፡ ልዮን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለት ባሕርይ አንድ አካል ነው በማለቱ ቤተክርስቲያናችን አልተናወጠችም ጥርሱን ለውልቃት ጽሕሙን ለመነጨት ቆርጦ ለሃይማኖቱ ተጋዳይ የሆነ ዲዎስቆሮስን ወልዳለችና፡፡ እንግዲህ በእነዚህ ሁሉ ዘመናት ፈተናዎች ከቤተክርስቲያናችን አልራቁም ነበር፡፡ ዛሬ እዚህ ቦታ እንዲህ ተደረገ እዚህ ቦታ እንዲህ ተፈጠረ ስንል አዲስ የቤተክርስቲያናችን ፈተና ነው ብለን አይደለም፡፡ ትንቢቱ መፈጸሙ ግድ ነው ትንቢቱ ሐሰት አይደለምና ታዲያ ለበጎቻቸው ግድ የማይላቸው እረኞች እንደሚነሡ የተነገረ ትንቢት ነው፡፡ በእውነተኛ አባቶች ተመስለው ሊነጥቁን የሚመጡ እረኛ መሳዮች እንዳሉ መጽሐፉ ነግሮናል፡፡ ሐሳዊ መሲህ እንደሚነሣ እኔ ክርስቶስ ነኝ በማለት የተመረጡትን እንኳ እስከ ማሳት የሚደርስ ልዩ ልዩ ምትሐታዊ ተአምራትን እንደሚያደርግ የተነገረ ነገር ነው፡፡ ታዲያ ትንቢቱ መፈጸሙ እንደማይቀር የተረዳ የታወቀ ነው፡፡ እኛን ግን ያንገበገበን ይህ ትንቢት በእኛ ዘመን በመፈጸሙ ብቻ ነው፡፡ ከዚህ በፊት አይተነው የማናውቀውን እንግዳ ነገር እየተመለከትንም ስለሆነ ነው፡፡ የልማቱ እና የጥፋቱ፣ የጽድቁ እና የኩነኔው፣ የእውነቱ እና የሐሰቱ መሸጋገሪያ ዘመን ላይ መሆናችን ብቻ ነው የሚያብሰለስለን፡፡
በጣም የምናከብራቸው በጣምም የምንወዳቸው ጳጳሳት እና ሊቃነ ጳጳሳት እነ አቡነ ቀሌሜንጦስ፣ እነ አቡነ ቀውስጦስ፣ እነ አቡነ እስጢፋኖስ፣ እነ አቡነ ቄርሎስ እነ አቡነ ገብርኤል ወዘተ የዚህ ትንቢት ሰለባዎች የሆኑ ይመስለኛል፡፡ የተመረጡትን እስኪያስቱ ድረስ ድንቆች ተአምራትን ያደርጋሉ እንዳለ ወንጌል፡፡ የተመረጡት የተባሉት እነዚህ ናቸው ዛሬ ግን እረኝነታቸውን ወደ ጎን ትተው  ከበጎቻቸው ጋራ ፍጥጫ ላይ ናቸው፡፡ ለተሐድሶዎቹ የእግር እሳት ሆነውባቸው የነበሩት አቡነ ቀውስጦስ በዚህ ሁኔታ መገኘታቸው የሚያሳዝነኝ ሲሆን አምላክ ወደ ልቡናቸው እንዲመልሳቸውም ለእኔ ከማልቀስ ውጭ ሌላ አማራጭ ያለ አይመስለኝም፡፡ እርሳቸው ማለት እኮ በመናፍቃኑ ዘንድ በቅጽል ስማቸው “ቀውስ” “ጦስ” ተብለው ነበር የሚጠሩት፡፡ አዎ ለመናፍቃኑ “ቀውስ” ነበሩባቸው ምን ቀውስ ብቻ “ጦስ” ም እንጅ፡፡ ታዲያ ዛሬ ያ የእረኝነት ተልእኳቸው የት ገባ? የኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ላይ ችግሮች እንዳሉ ብዙዎች ጽፈዋል ብዙዎችም ተችተዋል፡፡ እኔ ግን ከጅምሩ ስህተት ነው የምለው ሲኖዶሱን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለማድረግ የሚያስችላቸውን ህግ ባወጡበት ጊዜ ነው፡፡ ኤጲስ ቆጶሳት ሲመለመሉ በየክልሉ ኮታ መሰጠቱ በራሱ ችግር ፈጣሪ ነበር፡፡ ለሸዋ፣ ለጎንደር፣ ለጎጃም፣ ለጋምቤላ፣ ለኦሮምያ ወዘተ የሚለው ኮታ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ካልሆነ በቀር ለሲኖዶሳችን ተገቢነቱ ጥያቄ ውስጥ ነው፡፡ ይህ በሰውነት አስተሳሰብ እንጅ በእግዚአብሔርነት አስተሳሰብ ላይ ያልተመሠረተ ለመሆኑ ጥርጥር የለውም፡፡ ጵጵስና የብሔር ተዋጽኦ ላይ የተመሠረተ ሳይሆን በእግዚአብሔር ምርጫ ላይ የተመሠረተ መሆን ነበረበት፡፡ የቀደሙ አባቶቻችን በሠሩልን ሕግ እና ሥርዓት መሠረት ለዚህ ለከበረው መዓርግ ብቁ የሆኑትን ኤጲስ ቆጶሳት ለእግዚአብሔር ማቅረብ ተገቢ ነው፡፡ እነዚህ የሚቀርቡት ኤጲስ ቆጶሳት ግን ከአንድ ክልልም ሊሆኑ ከአንድ ሰፈርም ሊሆኑ ይችላሉ እርሱ ችግር ስላልሆነ፡፡ ይህን የምላችሁ በእውነተኛዪቱ እምነት ህግና ሥርዓት ጵጵስና ተጨማሪ አደራ እንደሆነ እና ለዚህ አደራ ብቁ አይደለሁም ብለው በሚሸሹበት ዘመን ሆኘ ነው፡፡ ጵጵስናን ለተጨማሪ “ቢዝነስ” መጠቀም የሚፈልጉ ሰዎች በበዙበት እና ለምን እኔ አልተመረጥኩም በሚባልበት በዛሬው ዘመን ሆነን ካሰብነው ግን “ጎጠኝነት” የሚያስብል ነው፡፡ ሐዋርያትን እስኪ ተመልከቷቸው የትኛውን አህጉር ነው የሚወክሉት? ዮሐንስ እና ያዕቆብ ወንድማማቾች ናቸው የዘብዴዎስ ልጆች፡፡  እንድርያስና ጴጥሮስ ወንድማማቾች ናቸው፡፡ አያችሁት ከአንድ ቤትም ሁለት ሁለት መረጠ እኮ፡፡ እንደእኛ ህግ ግን መሥፈርቱን አሟላም አላሟላም የሆነ ክልልን ወክሎ እንዲመረጥ እናደርጋለን፡፡ ለዚህም የጋምቤላውን አባ ተክለ ሃይማኖትን ማንሣቱ በቂ ምስክር ነው፡፡ አምላክ ፍርዱን ይስጣችሁና! በእውነት በጋምቤላ ክልል አንድ መነኩሴ ብቻ ነው ያለ እንዴ ብቻውን እንዲወዳደር የተደረገው? ለማንኛወም ይህን ጉዳይ በዚሁ ልተወውና ወደ ርእሰ ጉዳየ ላምራ፡፡
ዘመኑ ዘመነ መናፍቃን ዘመነ ከሐድያን ነው፡፡ ክህደቱ እና ምንፍቅናው ደግሞ ከቤተክርስቲያናችን ውጭ ሳይሆን እዛው ውስጧ መቅደሷ ውስጥ ገብቷል፡፡ ታዲያ ከበሩ እስከ መቅደሱ ድረስ ቅጽረ ቤተክርስቲያናችንን የመጠበቅ ሥራ ዘብ የመቆም ተግባር መፈጸም ያለብን እኛ ብቻ ነን፡፡ ይህን ማድረግ ያለብን ደግሞ ገነት መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ብቻ ሳይሆን ታሪክም እንዳይወቅሰን ነው፡፡ እነ እለእስክንድሮስን እነ ቄርሎስን እነ ዲዎስቆሮስን በታሪካችን ውስጥ የምናነሣቸው ለቤተክርስቲያናችን አምድ ጽንዕ ምሰሶ ሆነው በዘብነታቸው ታሪካዊ ገድልን ስለፈጸሙ ስለተጋደሉ ነው፡፡ ስለዚህ መልካሙን ገድል ስለቤተክርስቲያናችን ስንል ልንፈጽም ይገባናል፡፡ አመጣጣቸው እኛን በእጅጉ ሊፈትን በሚችል መልኩ ነው፡፡ ቀሚሳቸውን ለብሰው አስኬማቸውን ጭነው ቅናተ ኀቄ ታጥቀው መስቀላቸውን ጨብጠው ነው፡፡ ምንም ይሁን ምን ግን ተኩላ በበግ ቆዳ ተሸፍኖ ስለመጣ ብቻ በግ ሊባል አይችልም፡፡ መስቀሉ፣ ቆቡ፣ ቅናቱ፣መቋሚያው፣ ቀሚሱ ወዘተ ሁሉ ነገር ገበያ ላይ በስፋት ይሸጣል፡፡ ስለዚህ ማንም ገዝቶ ሊጠቀምበት እንደሚችል ጠንቅቀን ልናውቅ ይገባናል፡፡ ለእናታችን ቅድስት ቤተክርስቲያን ዘብ እንቁምላት ብለን ከተነሣን ከዚህ እንጀምር፡፡ በቀሚሳችን አይቀልዱብን፣በአስኬማችን አይነግዱብን፣ በመስቀላችን አያስመስሉብን ሁሉም ንብረቶቻችን ክብር ይኑራቸው፡፡
ይህንን የተሐድሶአውያኑን ቀስት በዘብነታችን መመከት የምንችለው በምን መልኩ ነው የሚለውን ጉዳይ አጥርተን እንመልከተው፡፡ ዘብነታችን ምን መልክ መያዝ አለበት ካልን፡-
v  ዘብነት 1. ሁሉም የአብነት ትምህርትን በሚችለው አጋጣሚ ሁሉ መማር አለበት፡፡ የሚችል ሰው ጉባዔ ቤት ገብቶ ሁሉንም የቤተክርስቲያናችን እውቀት ማወቅ አለበት፡፡ ያልቻለ ሰው ደግሞ ዘመናችን ቴክኖሎጅው የተራቀቀበት ዘመን ስለሆነ ሁሉንም የአብነት ትምህርቶችን በድምጽም ሆነ በምስል እየቀረጸ ከቤቱ ቁጭ ብሎ ጊዜ ሰጥቶ ማጥናት እና መማር ይችላል፡፡ ያጠናውን ነገር በአግባቡ መያዙን ለማረጋገጥ ከአብነት መምህራን ጋር ተገናኝቶ ስህተቱን በማረም ሙሉ መሆን ይቻላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ማኅበረ ቅዱሳን በሚያቀርባቸው የአብነት ትምህርቶች ውስጥ በመሳተፍ ጊዜን በአግባቡ በመጠቀም መማር ይቻላል፡፡ አሁን ድራማ ፊልም ጨዋታ ምናምን የሚባል አሸንክታብ ጥለህ መገኘት አለብህ፡፡
v  ዘብነት 2. በነጻ ማገልገል፡፡ ይህኛው ዘብነት ዘብነት 1 በኋላ የሚመጣ ጸጋ ነው፡፡ የአብነት ትምህርቶችን ከተማርክ በኋላ ክህነት ማምጣት ከቻልህ ክህነት ታመጣለህ ማምጣት የማትችል ከሆነ ግን ትምህርትህን ብቻ ይዘህ ቤተክርስቲያን ውስጥ ትገባለህ፡፡ ታዲያ አገልግሎትህ ፍቅረ ንዋይ የሌለበት ለነፍስህ ብቻ ብለህ ይሁን፡፡ በቃ በነጻ አገልግል፡፡ በነጻ ማገልገል ስትጀምር ለ ”ቢዝነስ” ብሎ ቆቡን ያጠለቀው መሸሽ ይጀምራል፡፡ የምንኩስናው ቦታ ከተማ እንዳልሆነ መረዳት ይጀምራል፡፡ የምንኩስናው ቦታ በጾም በጸሎት የሚታገሉበት በረኃ ነው፡፡ እዚያ የአራዊቱን ድምጽ ፈርቶ የአጋንንቱን ፈተና ሸሽቶ ከተማ ለከተማ ቀሚሱን እያዝረከረከ የሚዞረውን አስመሳይ መነኮስ ሁሉ ቀልብ ያስገዛልሃል፡፡ በቃ አገልግሎት በነጻ ይሁን፡፡ ጳጳስም በለው የመምሪያ ኃላፊም በለው ሥራ አስኪያጅም በለው ቀዳሽም በለው ምንም በለው ምን በነጻ ያለገንዘብ አገልግል ተብሎ የነጻ አገልግሎት መስጠት ከተጀመረ ያን ጊዜ ቆቡን እየጣለ አዲስ “ቢዝነስ” ይጀምራል፡፡ ቤተክርስቲያናችንን ለቅቆ ይሄድልናል፡፡ ለአገልግሎት ሳይሆን ለፊርማ ብሎ ሰዓታት እና ማኅሌት የሚቆመው፣ ኪዳን የሚያደርሰው ቅዳሴ የሚቀድሰው ሁሉ በነጻ አገልግል ሲባል በሉ ደህና ሁኑ ብሎ ከቤታችን መውጣት ይጀምራል፡፡  
v  ዘብነት 3. የያገባኛልነት ስሜትን መላበስ፡፡ ሁሉም ሰው ለቤተክርስቲያኑ ክብር ያገባዋል ይመለከተዋልም፡፡ ስለዚህ ቃጭል እያቃጨለ ስለ ጊዮርጊስ ስለ ማርያም እያለ የስእላትን ክብር ዝቅ በማድረግ በየመንገዱ በስእላት የሚነግደውን ነጋዴ ሁሉ እያነቁ ለፖሊስ ማስረከብ አለብን፡፡ የቤተ ክርስቲያን ማሰሪያ ተዘከሩን እያለ ተሰርተው በተመረቁ አብያተ ክርስቲያናት ሳይቀር ለልመና መናኸሪያ ለመናኸሪያ የሚዞረውን ነጋዴ ሁሉ እያነቁ መያዝ ነው፡፡ ስእላችን ክብር ይኑረው፣ ስማችን ክብር ይኑረው፣ ለማኞች ናቸው አንባል፡፡ ይህ ይቆጨን፡፡ ባለቤት የሌላት እስከምትመስል ድረስ ሁሉም ተነሥቶ የሚነግድባት ቤተክርስቲያናችን ታሳስበን እንጅ፡፡ ሁላችንም ያገባናል ሁላችንም ይመለከተናል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ ቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ የሚባል ደንቀራ መወገድ አለበት ይመለከተናል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ተሸነፈ፤ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስህተት ሰራ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወራጅ ቀጠና ገባ ወዘተ እየተባለ ሲነገር እንዴት አይሰቀጥጠንም፡፡ ስእላትን አስፋልት ላይ አንጥፈው የሚሸጡ፣ ከደብረ ሊባኖስ ከግሸን ተባርኮ የመጣ መስቀል እያሉ በሞንታርዶ የሚጮኹብንን እያነቅን ለፖሊስ እንስጣቸው፡፡ የራሷ የቤተክርስቲያናችንን ሱቅ እንከፍትላታለን፡፡
v  ዘብነት 4.  የቶማስን እምነት መያዝ፡፡  ዘንድሮ መጠርጠር ጥሩ ነው፡፡ ቶማስ ኢየሱስ ክርስቶስን የተወጋ ጎንህን ካልዳሰስሁ አላምንም ብሎታል፡፡ በቃ! ይህ ለዘንድሮ ሰዎች ለእኛ ጥሩ ትምህርት ነው፡፡ ቀሚሱን ስለለበሰ አስኬዋውን ስለደፋ ብቻ መነኩሴ ነው ብለህ አትታለል፡፡ ውስጡን ማንነቱን ዳሰው ካልዳሰስኸው አትመን፡፡ እርሳቸው ጳጳስ ናቸው አይሳሳቱም አትበል ንስጥሮስ ፓትርያርክ እንደነበረ አትዘንጋ፡፡ እኛ ከሰበክንላችሁ ወንጌል ውጭ የሰማይ መልአክም ቢሰብክላችሁ አትቀበሉ ብሎናል ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ በቃ መልአክ መስሎ ከሰማይ ቢወርድም አንሰማም!!!
v  ዘብነት 5. ከቤተክርስቲያን አለመራቅ፡፡ ብዙዎቻችን እኔን ጨምሮ ከቤተክርስቲያን ርቀናል፡፡ መቅደሳችን ውስጥ ገብተው ሲቀድሱ ላለማየት ሸሽተኛል፡፡ ይህ ግን መፍትሔ አይደለም፡፡ ሕጓን ሥርዓቷን እንማር ሁላችንም ሰንበት ትምህርት ቤት እንግባ፡፡ ልጆቻችንን እየያዝን እንማማር፡፡ ታሪካችንን እምነታችንን እናጥና፡፡ ሥርዓቷን ሕጓን እንማር፡፡ ከዚህ የወጣ ካየን ግን እንታገል፡፡
ሌሎችን የዘብነት ባሕርያት ለእናንተ ተውኩት፡፡ ለመወያያ ያህል ስለሆነ እናንተም በየቤታችሁ ተወያዩበት፡፡ ከዚያም አስተያየታችሁን ግለጹ፡፡ እንግዲህ በዚህ መልኩ ቤተክርስቲያናችንን ልእልናዋን ማስጠበቅ አለብን፡፡ ህዝቡ ባለቤት መሆን  ዘብ መቆምም ካልቻለ ከዚህ የባሰ ነገር እንደሚገጥመን አትጠራጠሩ፡፡ ማንም የሚፈነጭባት ሆነች እኮ! ባለቤት የሌላት መሰለች እኮ! እንዴ ምንድን ነው ዝምታችን!!!