Wednesday, December 25, 2019

ምርጫ 2012 እና እኛ!


  ==============
ከዚህ በፊት የምርጫ ካርድ እና እኛ ሆድና ጀርባዎች እንደነበርን ማስታወሱ  አይከፋም፡፡ በተለይ እኔ የምርጫ ካርድ ማውጣትን እንደ ኃጢአት ነበር የምቆጥረው፡፡ በርግጥም ኃጢአት ሆኖ ነበር፡፡ ምክንያቱም ካርዳችን ዋጋዋ ምንም ስላልነበር፡፡ 1997 ዓ.ም ዕድሜዬ ለመምረጥ አልደርስልኝ ቢል መታወቂያየ ላይ ዕድሜየ እንዲሞላ ፍቄ ሰርዤ ነበር ካርድ ያወጣሁ፡፡ ያ ይመስለኛል በተከታታይ ለነበሩ ምርጫዎች ካርድ የሚባል ነገር እንዳላይ ብዬ የመምረጥ መብቴን ከራሴ ላይ እንድገፍ ያደረገኝ፡፡ ዘንድሮ 2012 ዓ.ም በትክክል ምርጫው መካሄድ አለመካሄዱን ባላውቅም መምረጥ ብቻ አይደለም መመረጥም ይኖርብናል ብየ አስባለሁ፡፡
መምረጥ መመረጥ ለሀገር ቅን ከማሰብ የሚመጣ ፍቱን ሃሳብ ነው፡፡ የአንተ ካርድ ቤተ ክርስቲያንን እንድትቃጠል ለማድረግም ላለማድረግም ዋጋ አላት፡፡ የአንተ ካርድ ሀገርህ በሰላም እንድትኖርም እንዳትኖርም የማድረግ ልዩ ኃይል አላት፡፡ የአንተ ካርድ የሕይወትም የሞትም ካርድ ናት፡፡ ያችን ካርድ በእጅህ መያዝ ግድ ይላል፡፡ የክልልም ሆነ የፌዴራል ምክር ቤቶች ውስጥ ካህናት ጠምጥመው ቁጭ ብለው ሳይ ደሜ ይፈላ ነበር፡፡ ለካ ደሜ ይፈላ የነበረው እነርሱ ቢያንስ የአንድን አሕዛብ ወንበር መውረሳቸውን ስላላወቅሁ ነበር፡፡ ለሀገር ሰላም ማምጣት ከተፈለገ ወንበሮች ሁሉ  በጠመጠሙ ካህናት መሞላት አለበት፡፡  እነላሊበላ ንግሥናውን ከቤተ ክህነቱ ጋር ደርበው ሊያስተዳድሩ መነሣት አለባቸው፡፡ ከዚህ በኋላ የሞት የሽረት ትግል ውስጥ መግባት ግዴታችን የሚሆን ይመስለኛል፡፡ አሁን በርካታ ዕድሎች እጃችን ላይ አሉ እነዚያን እድሎች በሙሉ እንጠቀምባቸው፡፡ ግብጽ፣ ሶሪያ፣ ሕንድ ወዘተ በተጓዙበት እንቅልፍ የበዛበት ጉዞ መሄድ አይገባንም፡፡ እኛ መምራቱንም መመራቱንም ከልክ በላይ እናውቅበታለን፡፡ ስለዚህ ከቀበሌ እስከ ፌዴራል ድረስ ሕዝቡን ሊወክሉ የሚችሉ ሰዎችን በጥንቃቄ እንድንመርጥ ማሳሰብ ግዴታ ነው፡፡ የምርጫ ካርዳችንንም በጊዜው ማውጣት ግዴታችን ይሆናል፡፡ 
 
አባቶቻችን ሞተው ያቆዩንን ታሪካችንን እኛም በደማችን ጽፈን ለሚመጣው ትውልድ ሳይበረዝ ሳይከለስ ማውረስ ይኖርብናል፡፡ ድምጹ ተጽእኖ የሚፈጥር የምክር ቤት አባል ሊኖረን ይገባል፡፡ የገቡትን አንግፋቸው ሊገቡ ያሰቡትን እንደግፋቸው፡፡ እኔ ፖለቲከኛ አይደለሁም፡፡ እንዴት ማሳመን እንደሚቻልም አላውቅም፡፡ ነገር ግን ሀገርን ለማፍረስ ፖለቲካን ሽፋን አድርጎ ከሚመጣ ሰው ለሀገሬ መልካም ነገር አስባለሁ ብየ እገምታለሁ፡፡ ታዲያ ምንም ባልሠራ እንኳ የዚያን ሰው ወንበር መያዜ ትልቅ ነገር እንደሆነ አስባለሁ፡፡ ስለዚህ የተሻለውን የምንመርጥበትና ተሽለን በመገኘትም የምንመረጥበትን ነገር ከወዲሁ ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ ሌሎች ቀድመውናል ነገር ግን ዕድሉ አለን ተስፋ የሚያስቆርጥ ደረጃ ላይ አይደለንም፡፡ ሠርተን እናሳይ!
ሃይማኖትና ፖለቲካ ለየግል ናቸው በሚል የጅልነት ብሂል ሀገራችንን ለጠላት አሳልፈን ልንሰጣት አይገባም፡፡ ዳዊትም ሰሎሞንም ንጉሦች ነበሩ፡፡ በሀገራችን ቅዱስ ላሊበላም ንጉ ነበር፡፡ ነገር ግን ከቤተ ክህነት ጋር ያጋጫቸው ነገር አልነበረም፡፡ በመልካም ጥበብ መሩ አስተዳደሩ እንጅ፡፡ ንግሥናን ከክህነት ጋር አስተባብሮ መምራትን አስተምረውን አልፈዋልና በግብር በሃይማኖት ልንመስላቸው ይገባል፡፡

Thursday, December 5, 2019

‹‹ዝምታ ይበጃልም አይበጅምም!››

ዝም ብሎ እንደመመልከት ያለ ቁም ነገር የሚገኝበት ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ ሀገርን ያህል ነገር የዕቃ ዕቃ ጨዋታ በሚጫዎቱ መሪዎች እጅ ስትወድቅ ስታይ ዝም ከማለት ውጭ በእጅህ የሚገኝ ሌላ መፍትሔ የለም፡፡ በአህዮች የእርስ በርስ እርግጫ ብዙዎችን የሚያጠግበው ምስኪኑ ሳር እየተነቃቀለ ሲወድቅ ስትመለከት እጅህን በአፍህ ላይ ጭነህ “እግዚኦ” ከማለት ውጭ ሌላ ምንም መፍትሔ አይመጣልህም፡፡ ዶክትሬቱን ይዞ የሀገራችን አህዮች ከሚያስቡት ለመድረስ ዕድሜ ልኩ የማይበቃው ሰው እንደ ዐዋቂ በየሚዲያው ሲቦርቅ ስትመለከት ዝም ብለህ ከማየት ውጭ ሌላ አማራጭ የለህም፡፡ ልታደርገው የምትችለው በእጅህ ያለው ቀላሉ ነገር “ሪሞት” ህን ተጭነህ አንደበቱን መዝጋት ብቻ ነው፡፡

 
ታሪኩን ሳያውቅ የታሪክ አስተማሪ ሊሆን የሚዳዳውን የታሪክ ጠላት ስትመለከት ዝምታን ትመርጣለህ፡፡ የተናገርከውን በውል ሳይረዳ ለማጨብጨብ ብቻ የተፈጠረ በሚመስል እጁ ጣሪያውን በጭብጨባ የሚያናጋውን የአጨብጫቢዎች ማኅበር ስትመለከት ዝም ትላለህ፡፡  ነገን አርቆ በማይመለከት ሰው በተፈጠረ ሴራ እርስ በእርሳችን ስንተራረድ ስታይ ዝምታን ትመርጣለህ፡፡ ወሬ ማመላለስን ትልቁ ሥራው አድርጎ አምራች የሆነ ጉልበቱን ለወሬ ሞትኩ እያለ ሲደክምበት ስትመለከት ዝም ትላለህ፡፡ ሰው መሆኑን ዘንግቶ “ከየት ነው” በሚል ቦታ አምላኪነት ጦር የተነደፈ ወጣት ስትመለከት ዝም ትላለህ፡፡ በባዶ እግሩ ዘምቶ የታጠቀ ጠላትን በጦር እና በጎራዴ አፈር አስግጦ “ሀገርህ ይች ናት” ብሎ በነጻነት እንዲኖርባት ያስረከበውን ባለውለታውን ዘንግቶ አፉን ለስድብ የሚከፍት የተማረ ማይም አፉን ለስድብ ሲከፍት ስታይ ዝም ትላለህ፡፡ እኔን ብቻ ስሙኝ እያለ ወሬውን  ሊግትህ የሚጥር መስማት የተሳነው ትውልድ ሲነሣ ዝም ከማለት ውጭ አማራጭ የለህም፡፡


ዝምታ መልስ ነው፡፡ በርግጥም ለሚገባው ሰው መልስ ነው፡፡ ነገር ግን ዝም በማለት ሀገሪቱን የወሬ ማምረቻ ፋብሪካ ሲያደርጓት መመልከት ደግሞ የራስ ምታት ነው፡፡ የሚበጀው ነገር ከሚጮሁት ጋር አብሮ መጮህ ሳይሆን ረጋ ብሎ እያደመጡ ምላሽ መስጠት ነው፡፡ የሆነውን እና እየሆነ ያለውን ነገር እየተመለከትህ ነገ ምን ሊሆን እንደሚችል ለመገመት የግድ ነቢይ መሆን አይጠበቅብህም፡፡ የሀገራችን ፖለቲካ ህዝብን በቀላሉ እንዴት ማሳመን እና ድጋፉን ማግኘት እችላለሁ የሚል ሴራ የተሴረበት ነው፡፡ ለአንተ አስቦ ሳይሆን ለራሱ አስቦ ዕድሜውን ለማራዘም የሚጠቀምበት ቁልፍ መሳሪያ ነው ፖለቲካ፡፡ ኢህአዴግ ይባል የነበረው የግንባሮች ስብስብ ሀገራዊ ፓርቲ ሆኖ ብልጽግና ተባለ አሉን፡፡ ስሙን መቀየሩ ጥሩ ነው ምክንያቱም ሰው ሁሉ በድሮ ጠባዩ የሚጠላ ግንባር ስለነበር፡፡ ውሕደቱም መልካም ነው አንድነትን ያመጣ ይመስላል (የታይታ እና የማስመሰል)፡፡ ይህ ሁሉ በሰው ልብ ለመጎዝጎዝ የተሠራ ሴራ ይመስለኛል፡፡ “ለማ እና ዐቢይ ተጣሉ” ብለው ደግሞ ጮቤ የሚረግጡ ሰዎችን አያለሁ፡፡ የእነርሱ ጠብ የጉልቻ ጠብ ነው (የወንድማማች ማለት ነው)፡፡ ለማ መላ ኦሮምያን ይዟል፡፡ በዚያ ሁሉም ይወደዋል ሁሉም ያከብረዋል፡፡ ዓቢይን ደግሞ ሀገሪቱ ላይ እየተሠራ ባለው ነገር ህዝቡ ፊቱን መልሶበታል፡፡ ህዝቡ የመለሰበትን ፊት ለመመለስ የሁለቱ የተጣሉ መስለው ድራማ መተወን አንዱ አማራጫቸው ይመስለኛል፡፡ ዓቢይ ኢትዮጵያ እያለ ሲያቀነቅን ኢትዮጵያ ትቅደም የሚለውን የዜግነት ፖለቲካ አራማጅ ሁሉ ወደ ራሱ የመሰብሰብ አቅሙን ያጠናክራል፡፡ ለማ ኦሮምያ እያለ ሲያቀነቅን ኦሮሞ ትቅደም የሚለውን የጃዋር ሥሪት በሙሉ ወደ ራሱ ይስባል፡፡ ለማ የጃዋርን መመሪያ እየተቀበለ ወጣቱን ያደራጃል፡፡ በዚህ መካከል ኢትዮጵያ ትቅደም እያሉ በዓላማ ቆመው የቀሩ በተለይ እንደ አማራ ክልል ያሉ መሪዎች  ህዝባቸውን ከማስበላት በቀር አማራጭ አይኖራቸውም፡፡ በዚህ ጉዳይ የፖለቲካ ተንታኝ ለመሆን ያምረኛል አልተማርኩም እንጂ፡፡ በዚህ መስመር እኔ የሚታየኝ ለሌሎች ክልሎች የጨለመ መንገድ ነው (በተለይ ለአማራ)፡፡ ይህ በዚህ ይብቃኝ አክቲቪስት አይደለሁ ወይ የፖለቲካ ተንታኝ አያያዜ ላያምር ይችላል፡፡ ከጻፍኩ ደግሞ ያጎበደደ ጽሑፍ መጻፍ ደስ አይለኝም፡፡ እና ወደ ርእሴ ልመለስ፡፡


የእኔ መጥፋት ምንም የሚፈጥረው ተጽዕኖ እንደሌለ ባውቅም እኔ ዝምታ ይበጃል ብየ ከፌስቡክ መንደር ራቅ ብየ ነበር፡፡ ግን ሳየው መፍትሔ አይደለም፡፡ ዶክተርና ፕሮፌሰር ተብለው በዚያ ልክ ብቻ ከሆነ የማሰብ አድማሳቸው እኔ እልቃቸዋለሁ ብየ ራሴን ከፍ እንዳደርግ እድል ፈጥረውልኛል፡፡ ከእነርሱ ፕሮፌሰርነትና ዶክተርነት ይልቅ የእኔ ከ12 ዓመታት በፊት በሒሳብ ትምህርት የያዝኳት ዲፕሎማ እና ከ9 ዓመታት በፊት የያዝኳት የሒሳብ ትምህርት ዲግሪ እጅግ ትልቃቸዋለች ብዬ ለራሴ ሞራል ሰጠሁ፡፡ በጠፋሁባቸው ወቅቶች ብዙ ልጽፋቸው እያሰብኩ የተውኳቸው ነገሮች ነበሩ እነዚያን ዝም ብዬ በማሳለፌ ደስ ይለኛል፡፡ ምክንያቱም እነዚያን ነገሮች ብጽፋቸውም ባልጽፋቸውም አመለካከቱን የምለውጠው ሰው ስለማይኖረኝ ነው፡፡  ምክንያቱም ሰውን ለመለወጥ ከመነሣት አስቀድሞ ራስን መለወጥ ይበጃልና፡፡ በዚህ ጊዜ ንስሐ ገብቶ የጥሪ ቀንን እንደመጠበቅ ያለ ዕድለኛነት የለም፡፡ ግን እሱን እንኳ ለማድረግ ቀጠሮ በሚባል ውል አልባ ገመድ ተጠፍሬ አልፈጸምኩትም፡፡
ዝምታ የሚበጅ እና የማይበጅ አለው፡፡ የሚበጀው ዝምታ ሌሎችን ለማዳመጥ ሌሎችን ለመስማት የሚረዳ ነው፡፡ የማይበጀው ዝምታ ግን አላዋቂዎች እና ፍሬ አልባ ንግግር የሚናገሩ ሰዎችን ዝም ብሎ መስማት ነው፡፡ ስለዚህ ዝም በማለትም ዝም ባለማለትም ለሀገራችን ሰላም የራሳችንን ድርሻ እንወጣ እላለሁ፡፡
መልካሙ በየነ
25/03/2012 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፤ ኢትዮጵያ


Tuesday, November 5, 2019

“ኑ! ጌራ መድኃኒት ጅረት መድኃኔ ዓለም አንድነት ገዳምን እንታደገው”

=========================
የገዳሙ አስተዳዳሪ “ይህ ቦታ ለዚህ ትውልድ መዳኛ ቦታ ነው፡፡ ነገር ግን ለትውልዱ ተሠውሯል፡፡ ዓይንና ጆሮ ለየቅል ናቸውና ቦታውን አይታችሁ በግልጥ በረከትን ስትቀበሉ ያላችሁ” ይላሉ፡፡

#የቦታው_መገኛ፡-

በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት በጎንቻ ሲሶ እነሴ ወረዳ በመራጉፍ ቀበሌ ነው፡፡

#ወደ_ቦታው_ለመድረስ፡-

ከደብረ ማርቆስ 147 ኪ.ሜ ከአዲስ አበባ 322 ኪ.ሜ እንደተጓዙ ገምቦሬ ከምትባል ትንሽ ከተማ ይደርሳሉ፡፡ ከዚያም ወደ ምሥራቅ  አቅጣጫ በእግር ከ1 ሰዓት እስከ 1፡30 ተጉዘው ገዳሙን የሚያገኙት ሲሆን በመኪና ለሚጓዙ ደግሞ በእነጎዴ በኩል (ዋናውን የሞጣ  የአስፋልት መንገድ ይዘው ለሚመጡ) ከገንቦሬ ተገንጥሎ በሚገባው ጠጠር መንገድ ከ15-20 ደቂቃ ተጉዘው እነጎዴ ይደርሳሉ፡፡ ከዚያም በእግር ከ10-15 ደቂቃ ተጉዘው ገዳሙን ያገኙታል፡፡ በመርጡለ ማርያም አቅጣጫ ለሚመጡ ደግሞ በጨሞ በኩል የ1 ሰዓት የእግር ጉዞ ተጉዘው የሚያገኙት ሲሆን መደበኛ መኪና ስለሌለው በኮንትራት መኪና እስከ እነጎዴ ድረስም በመኪና መሄድ የሚቻልበት ዕድል አለ፡፡ ከሞጣ ለሚመጡ ደግሞ ጉንደ ወይን ከተማ እንደደረሱ እነጎዴ ድረስ 12 ኪ.ሜ በመኪና ሄደው ከ10-15 ደቂቃ የእግር ጉዞ አድርገው ገዳሙን ያገኙታል፡፡ የኮንትራት መኪና ወይም የግል መኪና ይዘው ለሚሄዱ ግን ከእነጎዴም የተወሰነ ርቀት ያህል ወደ ገዳሙ መጓዝ የሚያስችል መንገድ አለው፡፡

#የገዳሙ_አመሠራረት፡-

1213 . በአጼ ይኩኑ አምላክ ተመሠረተ፡፡ ይህ ዕድሜ በኢትዮጵያ ከሚገኙ ጥንታውያን ገዳማት መካከል አንዱ ያደርገዋል፡፡
#ምክንያተ_ምሥረታው፡- ዓፄ ይኩኖ አምላክ ሠራዊታቸውን እና ካህናትን አስከትለው የኦሪት መሥዋእት ይሰዋባት የነበረችውን ጥንታዊቷን መርጡለ ማርያምን ገዳም ጎብኝተው እና ተሳልመው ወደ  ሸዋ ሲመለሱ መሽቶባቸው አሁን ገዳሙ በሚገኝበት ቦታ ላይ ከነሠራዊታቸው አደሩ፡፡ ንጉሡ ዓፄ ይኩኖ አምላክ ሌሊት በህልማቸው በዚህ ቦታ ላይ በአምሳለልመ ያዕቆብ (ያዕቆብ በፍኖተ ሎዛ እንዳየው መሰላል) መላእክት ወደ ላይ ሲወጡ ወደ ታችም ሲወርዱ ተመለከቱ፡፡ ካህናቱ ታቦተ ሕጉን፤ ንጉሡ ሠራዊቱን ይዘው ዋሻው ውስጥ በድንኳን አድረዋል፡፡ ንጉሡ ጠዋት ተነሥተው ሊሄዱ  ሲሉ በጉዟቸው ሁሉ ይዘውት የሚንቀሳቀሱት ታቦተ መድኃኔዓለም ለካህናቱ አልነሣላቸው አለ፡በዚህ ጊዜ ንጉሡ ሕልማቸውን ለካህናቱ ነገሩዋቸው እነርሱም በዚህ ቦታ ገዳም እንዲገደም ፈቃደ እግዚአብሔር ነው ብለው ለንጉሡ ነግረው አሳመኗቸው፡፡ ንጉሡም በአካባቢው ያለውን ህዝብ በመሰብሰብ ከዛሬ ጀምሮ በዚህ ቦታ ላይ በፈቃደ እግዚአብሔር ገዳም መሥርተንላችኋል በማለት በትግዳር እና በብና በሁለቱ ወንዞች መካከል ባለው ጅራት መሰል ቦታ የመድኃኔዓለም ገዳም ተመሠረተ፡፡ ስሙም ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ጅረት መድኃኒአለም ተብሎ ይጠራል ንጉሡ ይኩኖ አምላክ በጊዜው ታቦቱን ከንጉሡ ጋር አጅበው ከነበሩት ካህናት መካከል የመጀመሪያውን አባት አባ ሲኖዲስ የተባሉትን ካህን የገዳሙ አበ ምኔት አድርገው በመሾም ወደ ሸዋ ሄዱ፡፡
#የአባ_ሲኖዲስ_ተጋድሎ፡- አባ ሲኖዲስ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የተለያየዩ ገቢረ ተአምራት በማድረግ ገዳሙን በማስፋፋት እና በአካባቢው አድባራትንና ገዳማትን በመመስረት አገልግሎት ሲሰጡ ቆይተዋል፡፡ ከእነሱም መካከል ዛሬ አቃቤት ኪዳነምሕረት ተብላ የምትጠራውን ሞፈር ቤት /እቃቤት/ በማድረግ፤ ቋሚ ጨርቅ እና እነጎዴ መካከል ከበረሀው ውስጥ የቅዱስ ቂርቆስን ገዳም ገድመዋል፡፡ይህንን እና ሌሎችን የትሩፋት ሥራወችን በመሥራት ገድላቸውን ፈጽመዋል፡፡

#ገዳሙ_ላይ_ይሠሩ_የነበሩ_ታላላቅ_ሥራዎች፡-

ለብዙ ዘመናት ገዳሙ እንደ ጥንታውያ ገዳማት እንደነ ዲማ ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ እንደነ መርጡለ ማርያም እና እንደሌሎች አድባራትና ገዳማት ዘወትር ይቀደስበት ነበር፡፡ የአብነት መምህራን በአይነት ማለትም የቅኔ፡ የድጓ፡ የአቋቋም፡ የቅዳሴ እና የትርጓሜ መጻሕፍት መምህራን ነበሩበት፡፡ ሁለት አቃቢዎችም ነበሩት፡፡

#የቦታው_ቃል_ኪዳን፡- አባታችን አባ ሲኖዲስ ስለገዳሙ ቃል ኪዳን ሲቀበሉ ከገዳሙ መጥቶ የተማጸነ የረገጠ ሁሉ እምርልሀለሁ የሚል እና ገዳሙን እስከለተ ምጽዓት ፈተና ቢበዛበት እንኳን ጸንቶ እንደሚኖር ቃልኪዳን ተቀብለውበታል፡፡ በዚህ ቦታ ታሪካዊ እና ተአምረኛ ጸበል የሚገኝ ሲሆን ብዙ ሕሙማን ከቅርብም ከሩቅም እየመጡ በጠበሉ እየተጠመቁ ከደዌአቸው ይፈወሳሉ፡፡ በዚህ ቅዱስ ቦታ 3 እስከ 4 ቀን ሱባኤ የያዘ እና የተጠመቀ ፈውስ ያገኛል በተከታታይም 22 ቅዱሳን አባቶች ለገዳሙ ቃልኪዳን ተቀብለውበታል፡፡

#የጥንታዊነቱ_ማስረጃዎች፡-

ጥንታዊ ቅርሳ ቅርሶች በውስጡ ይገኛሉ፡፡ በተጨማሪም ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እና ባለቤታቸው እቴጌ መነን በአንድ ወቅት የገዳሙ መነኮሳት በጸሎት እንዲያስቧቸው ከመባዕ ጋር ለገዳሙ መነኮሳት ደብዳቤ ልከው እንደነበረ እና ደብዳቤው ዛሬም ድረስ በዕቃ ቤት ይገኛል፡፡ ከታች የምትመለከቱት ፎቶ ነው፡፡ ደብዳቤው የተጻፈው ጥቅምት 30/1950 ዓ.ም ነው፡፡ ከዛሬ 62 ዓመት የተጻፈ በፊት መሆኑ ነው እንግዲህ፡፡ ኃይለ ሥላሴ ይህ ቦታ ጥንታዊ መሆኑን ስለሚያውቁም በገዳሙ የሚደረገው ጸሎትም ቅድመ እግዚአብሔር እንደሚደርስ የሚያምኑበት እንደሆነም መረዳት ይቻላል፡፡

#የገዳሙ_መተዳደሪያ፡-

ቀደም ብሎ መርጡለ ማርያም ወረዳ ይብራዛ ሥላሴ፡ እናርጅ እናውጋ ወረዳ አንጎታ ሥላሴ ፤ የዲጥ፡ ጎንቻ ሲሶ እነሴ ወረዳ ውኂዝ ኢየሱስ እና ሌሎችን ጨምሮ 21 ጉልት መተዳደሪያ ነበረው፡፡ በአሁኑ ወቅት ደግሞ በገዳሙ ውስጥ ባለው ይዞታ የሰብል ልማት፤ የእንስሳት እርባታ እና የአትክልትና ፍራፍሬ ሥራ በመሥራት ይተዳደራሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት በገዳሙ ውስጥ 58 መናንያን የሚኖሩ ሲሆን ወንድ 38 ሴት 20 ከእነዚህም መናንያን 43 አቅመ ደካማ ሲሆኑ መሥራት የሚችሉት ግን 15 ብቻ ናቸው፡፡ ይህም በመሆኑ ለጊዜው የገዳሙን መሬት ለአካባቢው አርሶ አደር በማከራየት በሚገኝ መጠነኛ ገቢ ይተዳደራሉ፡፡ ገዳሙ በደረሱበት የተለያየዩ ፈተናዎች እና ችግሮች ምክንያት የቀድሞ ይዞታው ባለመኖሩ በሸመት እና ልመና መተዳደር ጀምሮ ነበር አሁን ብዙ ገቢ ባይኖርም እንኳን በራሱ ለመተዳደር ጥረት እያደረገ ይገኛል

#በገዳሙ_ላይ_የደረሱ_ፈተናዎችና_አሁን_ያሉ_ችግሮች፡-

በየዘመኑ በደረሱ የተለያየዩ ችግሮች ገዳሙ በመጥፋት እና በመልማት ላይ ሲፈራረቅ ቆይቷል፡፡ በደረሰበት ፈተና መንፈሳዊ አገልግሎት ሲሰጥ ከቆየ በኋላ ገዳሙ በመፈታቱ የገዳሙ ቅርሳቅርሶች በመርጡለ ማርያም፤ በእነጎዴና ቋሚ ጨርቅ በሚገኘው በቅዱስ ቂርቆስ ዋሻ ተበትኖ ብዙ ዘመናትን ካሳለፈ በኋላ አባ ገብረማርያም በሚባሉት አበምኔት የቦታው ቅድስና ወደነበረበት እንዲመለስ በመንፈስ ቅዱስ ተገልጾላቸው ገዳሙን አቅንተው ቅርሳቅርሶችን ከያሉበት ሰብስበው ወደ ገዳሙ መልሰዋል፡፡ በአጼ ምኒልክ ዘመንሁለተኛ ጊዜ በመፍረሱ ቅርሳቅርሶች በወቅቱ ባለአባቶች /ባለርስቶች/ እጅ ቆይቷል፡፡ ታቦተ ህጉ እነጎዴ ማርያም ተደርቦ 50 ዓመታት በላይ አሳልፏል፡፡ የአቸፈር ተወላጅ የሆኑት አባ ወልደ ሐዋርያት በዲማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ዋሻ ሱባኤ ገብተው መልሰው ገዳሙን እንደሚያቀኑት በመንፈስ ቅዱስ ተነግሯቸው እንደገና 1945 . ወደ ገዳሙ መጥተው እንደገና አቋቋሙት፡፡ እኒህ አባት 1947 . ታቦተ ህጉንና ቅርሳቅርሶችን ከያሉበት ሰብስበው ወደነበሩበት መልሰዋል፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስካሁን 6 አበምኔቶች አስተዳድረውታል በየተለያዩ ቦታዎች ያሉ የገዳሙ ይዞታዎች በየጊዜው በሚደረገው የመንግስት ለውጥ ተወስደዋል፡፡

#ገዳሙ_አሁን_እያጋጠመው_ያለው_ችግር፡-

1ኛ. ቤተክርስቲያኑ በዘመን ብዛት በአሁኑ ጊዜ በመፍረስ ላይ ይገኛል፡፡ (ከታች በቶው እንደምትመለከቱት በአሳዛኝ ሁኔታ ቅኔ ማኅሌቱ ፈርሷል፤ ጣሪያውም መቅደሱ ላይ የሚያፈስ መሆኑ)
2ኛ. በገዳሙ የአገልጋይ እጥረት መኖሩ 1 አባት ውጭ /ን፤ ካህን፤ መምህር ወዘተ አለመኖር እና በአሁኑ ወቅት ሁሉንም መንፈሳዊ አገልግሎት ከሌላ አካባቢ በመፈለግ አገልግሎት ማግኘቱ፡፡ በዓመት 3 ጊዜ ብቻ የሚቀደስ ሲሆን ቀዳሽ ካህናትም ከመርጡ ለማርያም እና ከዲማ የሚመጡ ናቸው፡፡
3ኛ. ከመናንያኑ ውስጥ መሥራት የሚችሉት 15 ብቻ በመሆናቸው ገዳሙን ለማስተዳደር ሌላ ፈተና መሆኑ፡፡
4ኛ. ገዳሙ የተለያየ ጸጋ ያለው ቢሆንም በዘመናዊ የገቢ ማስገኛ ውስጥ አለመግባቱ፡፡
5ኛ. በአካባቢው ያለው ህብረተሰብ እና ወረዳው ለገዳሙ ትኩረት አለመስጠቱ፡፡
6ኛ. በጥንታዊነቱ ልክ እንደሌሎች ገዳማት ባለመታወቁ ጎብኝ አለመኖር፡፡
7ኛ. የእቃቤት ባለመኖሩ ጥንታዊ እና ታሪካዊ ቅርሶች ላይ ጉዳት እየደረሰ መሆኑ
በአሁኑ ወቅት ገዳሙ የሚፈልገው ድጋፍ፡-
1ኛ. ገዳሙን በአገር ውስጥና በውጪው ዓለም የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን እንዲያውቁት ማድረግ፡፡ (ለዚህም ይህን መልእክት ለሌሎች ማጋራት አንዱ ኃላፊነት መወጫ መንገድ ነው፡፡)
2ኛ. በተሠራለት አዲሱ ዲዛይን መሠረት ቤተክርስቲያኑ እና ለንዋየ ቅድሳት እቃ ቤት እዲሠራለት ማድረግ፡፡
3ኛ. በበጎ አድራጊ ምዕመናን የአብነት መምህር ተቀጥሮለት ተተኪ ዲያቆናት እና ካህናት እንዲወጡበት ማድረግ፡፡
4ኛ. ለገዳሙ መተዳደሪያ የሚሆን ቋሚ የገቢ ማስገኛ ፕሮጀክት የሚሠሩ አካላትን መጋበዝ፡፡
5ኛ. በአገር ውሥጥና በውጭ የሚገኙ ምእመናን ለአዲሱ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ማሠሪያ ገንዘብ እንዲለግሱ ማድረግ፡፡
6ኛ. የገዳሙ ታሪክ እና ቅርስ በህጋዊ መንገድ EOTC ቲቪ እና በማኅበረ ቅዱሳን ቲቪ ዘጋቢ ፊልም ተሠርቶለት በሚድያ እንዲተዋወቅ ማድረግ፡፡ (ይህ ለማድረግ አሁን ገዳን እያስተዳደሩት ያሉት አባት ለዚሁ ሥራ አዲስ አበባ መሄዳቸው ጅማሬው ጥሩ መሆኑን ያሳያል፡፡)
7ኛ. በኅትመት ውጤቶች በጋዜጣና በመጽሔት እንዲተዋወቅ በማድረግ በአገርና በውጭው ዓለም የሚኖሩ ምዕመናን የቦታውን ተዓምርና በረከት ተረድተው ለገዳሙ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ አድርገው እነሱም የበረከቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪ ማስተለለፍ፡፡
8ኛ. በገዳሙ ውስጥ ያለው ታሪካዊ ዋሻ ሱባኤ ለሚገቡ ምዕመናን እንዲተዋወቅ ማድረግ፡፡

#የገዳሙ_እንቅስቃሴ_አሁን_ያለበት_ሁኔታ፡-

1ኛ. በማኅበረ ቅዱሳን አዲስ ለሚሠራው ቤተ ክርስቲያን ዲዛይን በነጻ ተዘጋጅቶለታል፡፡ ይህን ለማስፈጸም ይረዳ ዘንድም ዓቢይ እና ንዑስ ኮሚቴ በማዋቀር ሕንጻ ግንባታውን ለመሥራት እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡ እስካሁን ድረስ በተደረገው እንቅስቃሴ 120,000 ሽህ ብር ገቢ ተሰብስቧል፡፡
2ኛ. የገዳሙን የግንባታ ፈቃድ ማስጨረስ ተችሏል፡፡
የአሁኑ የቤተክርስቲያን ሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ ስም ዝርዝር
1. ቆሞስ አባ ዮሐንስ መርሻ ... ሰብሳቢ
2. አባ ገብረሥላሴ ታረቀኝ .........ጸሐፊ
3. አባ ጣሰው ታምሬ ............../ያዥ

#ገዳሙን_መርዳት_ለምትፈልጉ_ወገኖች_ሁሉ፡-

ጌራ መድኃኒት ጅረት መድኃኔ ዓለም አንድነት ገዳም ህንጻ ቤተ ክርስቲያን (G/M JERET M/ALEM ANDNET GEDAM HINTSA)
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሂሳ ቁጥር፡1000260115937

#ስለገዳሙ_ተጨማሪ_መረጃዎችን_ለማግኘት

የገዳሙን አስተዳዳሪ ቆሞስ አባ ዮሐንስ መርሻን በስልክ ማግኘት ይቻላል፡፡ የጸሎት ሰዓታቸውን በማይነካ መልኩ ሰዓቱን እያመቻቻችሁ ደውላችሁ መጠየቅ ትችላላችሁ፡፡ የሞባይል ስልካቸው 0912361153 ነው፡፡
*** እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ አንድ ቀን ቦታውን በአካል ተገኝቼ ተመልክቼ ያለውን ሙሉ ነገር በዓይን እንዳየ ሰው ሆኜ የምጽፍላችሁ መሆኑን አሳውቃለሁ***
(ምንጭ፡- Tewaney Betsidiq Ethiopia የፌስቡክ ገጽ፡፡)