Friday, November 27, 2015

ምኑን ልከራየው????


© በመልካሙ በየነ
ሕዳር 16/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ቤት የለኝ አልሠራሁ መሬቱ የመንግሥት፣
መኖር ደግሞ አለብኝ ተጠልየ በቤት፣
ታዲያ የት ልኑረው ወዴት ብየ ልግባ፣
የራሴ ማስገቢያ ስለሌለኝ ታዛ ሆዴ እጅጉን ባባ፣
ዓይኔ ራሰ በእንባ፡፡
እንባዬን ጠርጌ ቀና ስል በድንገት፣
 “ይከራያል” የሚል  አየሁኝ ከርቀት፣
ችግር ያበሰለኝ ማደሪያ አጥቼ፣
እየተንሰፈሰፍኩ ቤቱን ተጠግቼ፡፡
የሚከራየውን አሳዩኝ አልኳቸው፣
አሳዩኝ ዶርሚቱን ከነመመሪያቸው፣
መመሪያ ቁጥር አንድ…
አምሽቶ መግባት መስከር መወላገድ፣
ቆሻሻ መጣል እንጀራ መጋገር ማድቤትን ማቆሸሽ ሴት ልጅን ማሳደድ፣
አምጥቶ  ማሳደር ጓደኛና ዘመድ፣
ሳያንኳኩ መግባት ሳልፈቅድ ወጥቶ መሄድ፣
ከዶርም ያባርራል ሳትወድ በግድ፡፡
መመሪያ ቁጥር ሁለት…
ሽንት ቤት ውስጥ ገብቶ ደቂቃን ማባከን፣
ሳልፈቅድ መጠቀም መብራት እና ውኃን፣
ያስወጣል ከግቢ ካልጠበቅህ ይህንን፡፡
… እናም መመሪያውን ተጋበዝኩትና ፣
ዶርሚቱን አየኋት ፈቀዱልኝና፡፡
ዶርሚቱ እንዲህ ናት…
የግድግዳ ቀለም ምንም ያልነካካት፣
ክፍተቱ የበዛ መስኮትና በር የተገጠመላት፣
አንድ አልጋን መዘርጋት የማይቻልባት፣
ኮርኒስ የሚባለው ያልተሰበከባት፣
ምንም ምን የሌላት፣
ፈጣሪ የሰጠን  ጭቃ እንኳ በአግባቡ ያልተለጠፈባት፣
መመሪያ እና ደንብ ክልከላ እና ዛቻ የተንሰራፋባት፣
ለአቅመ ኪራይ የማትበቃ ባዶ ሆና አገኘኋት፡፡
እ ኔ-- ም… ውስጤ ተክኖ ልቤ አዝኖ ተክዞ፣
ዋጋዋ ስንት ነው? ብየ ጠየቅኋቸው ዓይኔ በእንባ ፈዞ፡፡
“ሶስት መቶ ነው ለአንድ ከሆነ፣
ስድስት መቶ ነው ለሁለት ከሆነ፣
ዘጠኝ መቶ ነው ለሦስት ከሆነ፣”
እያሉ ሲጠሩት የብሩን ጋጋታ፣
በጣም ተገርሜ “ኪራይ ነው ወይስ ሽያጭ” አልኳቸው በእርጋታ፡፡
ምን ይላል! ይሄ ሰው፣
በሦስት መቶ ነው ቤቴን የምሸጠው?
ይልቅስ ከያዝከው፣
“ይከራያል” የሚለውን ጽሑፍ አሁን ልገንጥለው፣
አሉኝ ቀና ብለው::
እኔም ተገርሜ እጅግ ተደምሜ፣
በቤት አልባነቴ እኔን ተቀይሜ፣
እከራይ ነበር ዶርምስ ቢኖርዎ፣
አሁን ያሳዩኝ ግን ዶርም አይደለም ከቶ ቅር ካላልዎ፡፡
እናም! ያኔ ዶርም ሰርተው “ይከራያል” ሲሉ፣
መጥቼ እይዛለሁ መመሪያን ሲያቀሉ፡፡
አሁን ግን! ዶርም የሎት ምኑን ልከራየው???
ያው ቤት አልባነቴን ይዤው እኖራለሁ፡፡

(ማስታወሻነቱ፡ በዶርም አጥረት ሳይሆን በዶርም ውጥረት፤ በዶርም ማጣት ሳይሆን በዶርም ቅጣት ላለሁት ለእኔ እና ለመሰሎቼ ይሁን)

Wednesday, November 18, 2015

አገሬ ኢትዮጵያ!!




© በመልካሙ በየነ
ሕዳር 8/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
አገርም ቢሏችሁ ከአገር በላይ ቅድስናን ከንጽሕና፣ ውበትን ከቁንጅና፣ ጀግንነትን ከፍልስፍና… ጋር አቆራኝታ እጆቿን ወደ ፈጣሪ ዘርጋታ የኖረች፣ እየኖረች ያለች ወደፊትም የምትኖር ፈጣሪ ውብ አድርጎ የሠራት አገር ናት ኢትዮጵያ፡፡ ይች አገር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስማቸው ተመዝግቦ ከምናገኛቸው ቦታዎች መካከል አንዷ ናት፡፡ ገነትን ከሚያጠጧት አራት አፍላጋት መካከል አንዱ የኢትዮጵያው ግዮን ወይም አባይ እንደሆነ ዘፍጥረት ላይ እናነብባለን፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያ ለገነት ማጠጫ የሚሆን ትልቅ ወንዝ ለገነት የታጨ ቅዱስ ሕዝብ ያላት አገር ናት ማለት ነው፡፡ ኢትዮጵያ በተለያዩ መሪዎቿ የተለያዩ ስሞችን ተቀብላለች፡፡ አቢሲኒያ፣ ኢትዮጵያ እየተባለች ተጠርታለች፡፡ በአቢስ አቢሲኒያ በኢትዮጲስ ኢትዮጵያ ተብላ የተጠራችው አገራችን ኢትዮጵያ የሚለውን ስም ካገኘች በኋላ የመሯት መሪዎቿ “አዲሲቷ፣ አሮጊቷ” የሚል ቅጥያ ከመቀጠል ውጭ ስመ ተፋልሶ አላደረጉባትም፡፡ ኢትዮጵያ ስትነሣ ዓለምን የሚያስደንቀው የአኩስም ሐውልት፣ የላሊበላ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናት፣ የጎንደር ፋሲለደስ ቤተ መንግስት፣ በሐረር የጀጎል ግንብ፣ በጎጃም የጣና ሐይቅና በደሴቱ ያሉ ገዳማት፣ የሰው ልጅ መገኛ መሆኗን የሚመሰክረው የሉሲ ድንቅነሽ አጽም፣ የተለያዩ ቋንቋዎችና ባህሎች ተስማምተው የሚኖሩባት፣ ገነትን የሚያጠጣው የአባይ ወንዝ ወዘተ… ትዝ የሚላቸው ፈረንጆቹ ብቻ ናቸው፡፡ እኛ ግን “በቅርብ ያለ ጠበል …” እንዲሉ ከምንም አንቆጥራቸውም፡፡ እኛ የራሳችን ሃብትና ንብረት እንዴት ትዝ አላለንም? በእርግጥ በዚህ ዘመን በአሁኑ ሰዓት ስለብዙ ነገሮች እነዚህ ሁሉ ሃብቶቻችን ትዝ እንዳይሉን ከባድ ተጽእኖዎች አሉብን፡፡ ከእነዚህ ተጽእኖዎችም መካከል የመጀመሪያው የገዢው መንግሥት ተጽእኖ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ከመሸለም ከማድነቅ ይልቅ መቅጣት የሚቀናው ማኅበረሰብ ማፍራታችን ነው፡፡
ኢትዮጵያ በተለያዩ ዘመናት የተለያዩ አስተሳሰቦችንና አመለካከቶችን ያነገቡ አንዳንዶች ለራሳቸው ጥቅም ጥቂቶቹም ለአገራቸው ለወገናቸው ጥቅም ሲሉ የኖሩ መሪዎችን አይታለች ተቀብላም አስተናግዳለች፡፡ ማን ነው ለአገሩ የሞተው መሪ? ማን ነው በጠላት እጅ መሞትን የናቀው? ቴዎድሮስ አይደለም እንዴ? ነው፡፡
 “መቅደላ አፋፉ ላይ ጩኸት በረከተ
የሴቱን አናውቅም ወንድ አንድ ሰው ሞተ” የተበላው ለማን ነው? የወንዶች ወንድ፣ የጀግኖች  ጀግና፣ ህዝቡን አሳልፎ ያልሰጠ፣ በጠላት እጅ በነጭ እጅ ላለመሞት ወስኖ የአገሩን የወደፊት ራእይ ሰንቆ፣ አደራውን ለቀሪው ትውልድ አስረክቦ በያዘው ሽጉጥ ራሱን ያሳለፈ የመቅደላው ጀግና የኢትዮጵያው ጀግና ቴዎድሮስ ዘ ኢትዮጵያ ፡፡ በአገራችን ታሪክ ውስጥ የመጀመሪያና የመጨረሻ የሆነውን መድፍ ነጮቹን ቀጥሮ ጋፋት ላይ ያሠራ ብቸኛው መሪ፡፡ ታዲያ ምን ዋጋ አለው አንዱ ጀግና የሞተለትን ጉዳይ አንዱ ፈሪ ቀበቶውን አላልቶ ሱሪውን አውልቆ ይቀበለዋል፡፡ በቴዎድሮስ የጀመረው ጀግንነትና የአገር ፍቅር በዚያው መጠን ቀጥሎ ዮሐንስ አራተኛ ለአገሩ ለወገኑ ሲል ባደረገው ጦርነት በሱዳኖች አንገቱን ተቆረጠ፡፡ የአገር ገዢዎች ለአገር መልማትም ሆነ መጥፋት ምክንያቶች ናቸው፡፡ እንግዲህ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ለአገር ፍቅር ለወገን ብሎ ራስን አሳልፎ በመስጠት  በኩል ቆራጥ መሪዎች እነዚህ እንደነበሩ ማሳያዎቼ  ናቸው፡፡ እነዚህ መሪዎች ጀግናዎቼ ናቸው በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥም ስማቸውን መስማት የምሻው የእነዚህን ምርጦች ነው፡፡ ምክንያቱም የሞቱለት ዓላማ ትልቅ ስለሆነ እና ለወደፊት ማስቀመጥ የፈለጉት ራእይ ምን እንደሆነ ሳስብ የሚገርም ስለሆነ ነው፡፡ በጠላት እጅ አልሞትም መሞቴ ካለቀረ ግን በራሴ እጅ ሞትን እመርጣለሁ ብሎ በባእድ መገዛትን ተጸይፎ መሞትን ያህል ወኔ የያዘ መሪ አይገርም ማን ይግረም ታዲያ፡፡  ምናልባት ልብ ልንለው የሚያስፈልገው ነገር  ከእነዚህ በፊት እና በኋላ ሌሎች ምርጦች የሉም ለማለት አይደለም፡፡ እነዚህ ሁለቱ ለአገራቸው ለወገናቸው ራሳቸውን ለሞት አሳልፈው ስለሰጡ በልጠውብኝ እንጅ ለኢትዮጵያ ዘመናዊ ስልጣኔ በር ከፋች የነበሩት ምኒልክም ለአገራችን ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳበረከቱ አልዘነጋሁትም፡፡ የመጀመሪያው ተሽከርካሪ መኪና የኢትዮጵያን ምድር የረገጠው፣ ስልክ ተዘርግቶ መደዋወል የተጀመረው፣ የፖስታ አገልግሎት የተጀመረው ዘመናዊ ስልጣኔ ኢትዮጵያን የነካካት መቼ  ነው? በዘመነ ምኒልክ አይደለም እንዴ? አረ ነው ምን መዋሸት ያስፈልገዋል፡፡ ከአውስትራሊያ ጋር በመገናኘት አሁን ለአገራችን ህዝብ በተለይ ለገጠራማው ክፍል ዋስትና እየሆነ ያለውን ባህር ዛፍ ወደ አገራችን ያመጡት ማን ሆኑና፡፡ በዘመናዊ መሳሪያ ከራስ ጸጉሩ እስከ እግር ጥፍሩ  ድረስ ተከናንቦ ኢትዮጵያን ለመውረር የመጣውን የኢጣሊያ ጦር በጀግንነትና በወኔ አድዋ ላይ ድራሹን ያጠፉት የአበሻ መሪ ማን ሆኑና፡፡ ጠላትን በመጣበት እግሩ አሳፍረው የመለሱ ድንቅ ኢትዮያዊ መሪ ምኒልክ ሁለተኛ፡፡ የዛሬዪቱን አንገቷን የተቆረጠችውን ሳይሆን ያችን ባለወደቧን ኢትዮጵያ ቅርጽና ግዛቷን እንድትይዝና በዚያ ካርታ እንድትታወቅ ያደረጉ መሪ ናቸው፡፡ በታሪካችን ውስጥ የሚገርመው ነገር ያለፈውን መሪ በበጎ ማንሣት አልተለመደም እንጅ ስንት በጎ ነገር ነበረን መሰላችሁ፡፡ ሃይለ ሥላሴን በብዛት የምናነሣቸው በበጎው አይደለም፡፡ ምንም እንኳ ከላይ ያየኛቸውን መሪዎች ያህል ለአገራችን ስልጣኔ አስተዋጽኦ ባያበረክቱም በተለያዩ ተጽእኖዎች ተነሣስተው የቻሉትን ያህል ግን አድርገዋል፡፡ የአፍሪካ ኅብረትን ከመመሥረት ባለፈ በመዲናችን አዲስ አበባ ጽ/ቤት እንዲኖረው ያደረጉ እሳቸው ናቸው፡፡ ዘመናዊ ትምህርት የሰይጣን ትምህርት ነው በሚል አስተሳሰብ ታንቆ የነበረውን የአገራችን ሕዝብ አሳምነው ዘመናዊ ትምህርትን ወደ ኢትዮጵያ ያመጡ ዘመናዊ ትምህርት ቤቶችን ከፍተው ዘመናዊ ትምህርትን ያስጀመሩ እሳቸው ናቸው፡፡ ምንም ያህል ብንተቸውም በበጎ ጎኑ ባናነሣውም  የመጀመሪያውን የተጻፈ ሕገ መንግሥት ለአገራችን ያስተዋወቁ ብቸኛ መሪ ናቸው፡፡ አገራችን አሁን ከአደጉት አገራት ተርታ ያለችውን ጀርመን ለመጀመሪያና ለመጨረሻ ጊዜ ስንዴ የለገሰች በጃን ሆይ ዘመን ነው፡፡ ለአገራችን የመጀመሪያ የሆነውን የጽሕፈት መኪና ወደ አገራችን ያመጡ ጃንሆይ ናቸው፡፡ ይህ ማለት ግን አገራዊ ስህተት አልሰሩም ማለት አይደለም፡፡ ማንም መሪ የሚሠራውን የአገር ስህተት ሰርተዋል፡፡ በተለይ ኢጣሊያ ኢትዮጵያን ለሁለተኛ ጊዜ በወረረ ጊዜ አገር ለቅቀው መሄዳቸውና ያም አልበቃቸው ብሎ ጦርነቱ ካለቀ በኋላ አገር ውስጥ ተመልሰው አገርን በአርበኝነት ሲጠብቅ የነበረውን ጀግና በላይ ዘለቀን መስቀላቸው ዓበይት ስህተቶች ናቸው፡፡ ከጃን ሆይ ቀጥሎ የመጣው ወታደራዊ መንግሥትም አዲስ አስተሳሰብን “ሶሻሊዝም” የሚባለውን ለአገራችን አስተዋውቋል፡፡ እድገት የሚመጣው በኅብረት ነው የሚል አመለካከት ነበረው፡፡ መፈክሩም “ኢትዮጵያ ትቅደም” የሚል ነበር በዚህ መፈክር ውስጥ የሚመጣብን ኢትዮጵያ በዓለም ስልጣኔ ላይ ቁንጮ ስትሆን ማየትን ነው፡፡ ዛሬ በቆረጠው ምትክ እንኳ የማይተክለው ደን ኢንተርፕራይዝ ብለን ያቋቋምነው ተቋም ሲቆርጠው የሚውለው ደን በማን ዘመን የተተከለ ነው እንላለን? በማይናወጥ መሠረት ላይ የታነጹት የቀበሌ ቢሮዎች እንዲሁም የቀበሌ ቤቶች በተጨማሪም ትምህርት ቤቶች መቼ የታነጹ ናቸው? አሁን ከገነባናቸው ይልቅ በደርግ ዘመን የተሠሩት ናቸው ጥንካሬ ያላቸው፡፡ እንደ እድል ሆኖብን አንድ መንግሥት ሄዶ ሌላው ሲመጣ ያለፈው መንግሥት የሠራቸውን ነገሮች ሁሉ ማፍረስ እንወዳለን፡፡ መታሰቢያውን እንደመስሰዋለን፣ ይጠቀምባቸው የነበሩ ቢሮዎችን፣ መሥሪያ ቤቶችን እናፈርሳቸዋለን፣ ታሪክን ዜሮ ብለን እንደገና እንጀምራለን፡፡ አሁን ላይ በተለያዩ ኃላፊነት ቦታዎች የተቀመጡ ሰዎች በማን ትምህርት ፖሊሲ እንደተማሩ ራሳቸው እኮ ያውቁታል፡፡ ነገር ግን ያለፈ ታሪክን በበጎ ስለማንመለከት ለዚህ ነው ደርግን በበጎው የማናነሣው፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ አሁን እየመራን ወዳለው መንግሥት ደርሰናል፡፡ የአሁኑ መንግሥት ከክፋቱ ይልቅ በጎነቱ ጎልቶ እንዲታይ የአገራችን መገናኛ ብዙኃን ትልቅ ድርሻ ይይዛሉ፡፡ ክረምት ላይ የተቀረጸውን አረንጓዴ ሰብል በበጋው እያሳዩ በመስኖ የተመረተ ምርት ነው ይሉናል፡፡ ስልጣኔውም እየመጠቀ ስለሆነ ይህንን ነገር ለአገራችን ህዝብ ብቻ ሳይሆን ለዓለም እንዲደርስ ስለተደረገ ውጮቹ ኢትዮጵያ አድጋለች ተመንድጋለች እያሉ ባላዩት ባልሰሙት ነገር ላይ ይመሰክራሉ፡፡ በጣም የሚገርመኝ የዚህ መንግሥት አገራዊ ስህተት ሁሉን አቀፍ የሆኑትን ብሄራዊ በዓላት እና የሃይማኖት በዓላትን ከማክበር ይልቅ ጥቃቅን የሚባሉ ነገሮችን ለወር ለሁለት ወር ከዛም ለረዘመ ጊዜ ሲያከብር ማየታችን ነው፡፡ በእውነት ኅሊና ላለው ሰው የአድዋን ጦርነት ያሸነፍንበትን የካቲት 23 ከማክበርና ብአዴን የተመሰረተበትን ህዳር 11፣ ኢህአዴግ ደርግን ያሸነፈበትን ግንቦት 20 ከምናከብር ትልቅ ስሜት ሊሰጠን የሚችለው የትኛው ነው? በየካቲት 23 ስም የተሰየመ ትምህርት ቤት፣ ሆስፒታል፣ መንገድ፣ አደባባይ የት አለ? ግንቦት 20 የሚለውን ስያሜ ግን ለብዙ ነገሮች ሰጥተነዋል፡፡ ግንቦት 20 የሚባል ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በምሥራቅ ጎጃም ዞን አዋበል ወረዳ እንዳለ አውቃለሁ፡፡ የካቲት 23 የሚባል ትምህርት ቤት ግን አላውቅም፡፡ የውጭን ጠላት አሸንፎ ዓለም አቀፋዊ እውቅናና ዝና ያጎናጸፈን የትኛው ነው? ሌላው የገዣችን ትልቅ ስህተት ካለፉት በጎ ነገሮችን መማር አለመቻሉ ነው፡፡ በእርግጥ ያን ጊዜ ድሮ የነበሩት መሪዎቻችን እንዲህ በቀላሉ ዓለምን መድረስ የሚችሉበት ሥልጣኔ የነበራቸው ስላልሆኑ እንጅ በጎ ስራ ስላልሰሩ አይደለም እውቅና ያላገኙት፡፡ አንድ ዛፍ ተክሎ ሺህ ጊዜ በሚዲያ መቅረብና ማቅረብ፣ አንድ ሽንኩርት አብቅሎ ሺህ ጊዜ ሚዲያ ላይ መውጣት እና ማውጣት የተጀመረው አሁን ቅርብ ጊዜ ነው፡፡ በእውነት ግን! ባህር ዛፍ ተከለ ተብሎ በሚዲያ ከመታየት ይልቅ ባሕር ዛፍን ወደ ኢትዮጵያ ያመጣው ሰው ማን እንደሆነ ፎቶውን እንኳ ብናሳይ አይበልጥም ነበር? የዘመናዊ ትምህርትን ጥራትና ሽፋን፣ የትምህርት ቤቶቻችንን ቁጥር እያነጻጸርን ሺህ ጊዜ እስኪሰለቸን ከሚነግሩን ይልቅ ዘመናዊ ትምህርት ኢትዮጵያ ውስጥ ማን እንዳስጀመረው? ሲጀመር የነበረው የህዝቡ አቀባብል ምን ይመስል እንደነበር ምነው በነገሩን፡፡ ባለፉት ዘመናት ለአገራቸው ለወገናቸው ሲሉ ውድ ሕይወታቸውን አሳልፈው የሰጡ ጀግኖቻችን አድራሻቸው የት አለ? መታሰቢያ ሀውልታቸው የት ቆመ? በቅርቡ ከ1983 ዓ.ም ወዲህ ማለቴ ነው በየክልሉ የሰማዕታት ሃውልት እየተባለ ሲቆምላቸው (አይቁምላቸው ማለቴ አይደለም) ለቴዎድሮስ እና ለገብርዬ፣ለዮሐንስና ለምኒሊክና፣ ለበላይ ዘለቀ የትኛው ክልል ላይ ነው መታሰቢያ ሐውልት የቆመላቸው ምናልባት አሁን ካልፈረሰ በወረዳ ደረጃ ተሰርቶላቸው ሊሆን ይችላል፡፡ የትኛው ትምህርት ቤት፣ የትኛው ሆስፒታል፣ የትኛው አደባባይ ነው በስማቸው የተጠራ? የሚገርመው ነገር አሁን በቅርቡ ላለፉት ባለራዕይ መሪ ስንት ትምህርት ቤት፣ ስንት መንገድ፣ ስንት አደባባይ፣ ስንት ስታዲየም፣ ስን ሆስፒታል፣ ስንት ፓርክ ነው በስማቸው የተሰየመ? ብቻ ታሪክ ይቀሰን! የእነ ቴዎድሮስ የእነ ዮሐንስ የእነ በላይ ዘለቀ ደም ይክሰሰን፡፡ ድሮ እነርሱ ደርግን የጣሉት በትጥቅ ትግል ነበር ምክንያቱም አስተሳሰቡና ርእዮቱ ለኢትዮጵያ ተገቢ ነው ብለው ስላላመኑ፡፡ ዛሬ ግን የትጥቅ ትግል የሚጀምርን ሰው አሸባሪና ኪራይ ሰብሳቢ ከማለት ውጭ ለአገሩ ለወገኑ ለሕዝቡ አስቦ ነው ብለን መቼ ተረዳን፡፡ አስተሳሰባችን አመለካከታችን ከጫካ አስተሳሰብና አመለካከት መቼ ተለየ? ለዛም እኮ ነው ከእኛ በላይ ፖሊሲ፣ ከኛ በላይ መሪ፣ ከኛ በላይ ካድሬ፣ ከኛ በላይ ሕገ መንግሥት የትም የለም ብለን የምንከራከረው፡፡ የተማረ ሰው መለያው “ይህ ስህተት ነው” ሲሉት ስህተቱን መመልከት መቻሉ ነበር የዚህኛው የኛ ገዢ ግን መማሩ ያልጠቀመው ይመስላል፡፡ አልተማረም እንዳንል ውጭ አገር ድረስ ሄደው ዲግሪ፣ ማስተርስ፣ ዶክትሬት ጭነው ተመልሰዋል ተማሩ እንዳንላቸው ደግሞ ዋይታችንን ችግራችንን ብሶታችንን አልተረዱልንም፣ አመለካከትና አስተሳሰባቸውን አልቀየሩልንም፡፡ በእርግጥ ኢትዮጵያን በነበረችበት ስልጣኔ ላይ ሳይሆን አፍርሰው እንደገና ወደ ስልጣኔ ጎዳና ስላመጧት በርካታ ጊዜያትን ሊወስድ እንደሚችል እናስባለን፡፡ ነገር ግን ሁል ጊዜ ጅማሬ የለም መጨረሻ ሊኖረው ያስፈልጋል፡፡ ከ83 ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ ጅማሬ ላይ ነን ሊባል አይገባውም ነበር፡፡ የጅማሬ ራዕያችን መቼ ነው አውን ሆኖ የምንመለከተው?
ሌላው የአገራችንን ታሪክ ከማድነቅ ይልቅ እንድንዘነጋውና እንድረሳው ትዝ እንዳይለን ያደረገን ጉዳይ ከመሸለም ይልቅ ለቅጣት የሚፈጥን ማኅበረሰብ ማፍራታችን ነው፡፡ በየቤታችን አስተዳደጋችን እንዲሁ ነው፡፡ ታሪክን እያስተማሩ ለአገር ፍቅር እንዲኖረን ከማድረግ ይልቅ “አንተ ወሬኛ” እየተባልን ታሪክን ለመማር እና ለመስማት ተሸማቀቅን አድገናል፡፡ ተረት ንገሩን ስንላቸውም የቀበሮና የበግ ተረት ነው የሚተርቱልን፡፡ እኛም እሱኑ ለመድነውና ቀበሮና በጎች ሆነን ቀረና፡፡ በጀመርነው የጥንቱ ስልጣኔ እና ትልቅነት ላይ አንዳች ነገር መጨመር ያልተቻለን ከማበረታታት ይልቅ ማሸማቀቅና ማስፈራራትን ባህላችን አድርገን በመኖራችን ነው፡፡ ለብዙ ዘመን በበጎ ስራህ ስትነሣ፣ ስትመሰገን፣ ስትወደስ፣ እንደ እርሱ አድርጋችሁ ሥሩ እየተባለ አርአያነትህ ሲጎላ፣ ህዝቡም አንተን ሲከተልህ ትኖራለህ መቼም ከሰው ልጅ ስህተት አይጠፋምና አንድ ቀን ታጠፋለህ ለብዙ ዘመን ይዘኸው የነበረው ስምና ዝናህ ከመ ቅጽበት ይለወጥና ትታሰራለህ ወይም ትቀጣለህ፡፡ አውሮፕላን ብትሠራ፣ መርከብ ብትገጣጥም፣ አዲስ ጥበብ ብታመጣ ማንም አያደንቅህም ሊቀጣህና ሊወግርህ የተዘጋጀው ግን አያሌ ነው፡፡ ሃይለ ሥላሴ በላይ ዘለቀን ለምን ሰቀሉት? ርስታቸውን ቀማቸው ወይስ መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ አደረገባቸው? አረ ምንም፡፡ ጀግንነቱ በህዝቡ ዘንድ ስለገነነ እና በርካቶች ስለተከተሉት ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ምቀኝነታችን ያስቸግረናል፡፡ ምቀኛ መሪዎች ደግሞ ተፈራርቀውብናል፡፡ እነሱ የሚሰሩት ብቻ ትክክል ይመስላቸዋል፣ ያለፉት መሪዎች የሰሩት ሁሉ ደግሞ ስህተት ይመስላቸዋል ለዛ ነው ታሪካችን እንዲህ ዘቅጦ የቀረው፡፡ ስንት ሽህ ጊዜ በጎ ነገር ብትሠራ መልካም ነገር ቢኖርህ ለሎች ሁሉ አርአያ ብትሆንም ሽልማት አታገኝበትም እውቅናን አትጎናጸፍበትም፡፡ በአንጻሩ ግን ትንሽ ስህተት ብትሰራ ከሰምንት ሰዓት የሥራ ሰዓት ውስጥ 10 ደቂቃ ብትሸርፍ ሽራፊ ደመወዝ ይሰጥሃል፡፡ የጽሑፍና የቃል ማስጠንቀቂያ ማስፈራሪያና ዛቻ እንዲሁም አዲስ ስም ከኪራይ ሰብሳቢነት እስከ አሸባሪነት እና ትምክህተኛነት ድረስ ያሉት ስድቦች ይዘንቡብሃል፡፡ መሪዎችህም የሚደሰቱት በመሸለም ሳይሆን በመቅጣት ነው ምክንያቱም አስተዳደጋቸውና አስተሳሰባቸው ነዋ፡፡ ማበረታታት የሚባለው ነገር ተዘንግቷል፡፡ አዲስ ፈጠራ ፈጥረህ ስልክ በነጻ መደወል ብትጀምር ፈጠራህን የሚያበረታታ ፍርድ ቤት የለም 25 ዓመት ጽኑ እስራት የሚል እንጅ፡፡ ታዲያ በዚህ ሂደት ታሪክህን ማጥናት እንዴት ልትደሰት ትችላለህ?
አገራችንን አምላክ ይጠብቅልን፡፡


Thursday, November 12, 2015

እውነተኛ ሰላም

© በመልካሙ በየነ
ሕዳር 2/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

…ይህ ሰላም ዘላለማዊ ዕረፍትን የሚያጎናጽፍ ከእግዚአብሔር የሚሰጥ ልዩ ሃብት ነው፡፡ በቅዳሴው ጸሎት ካህኑ “ሰላም ለሁላችሁ” ብሎ የሚጸልይልን ይህን ሰላም ነው፡፡ ለዚህም ነው “ከመንፈስህ ጋራ” ብለን ያንን እውነተኛ ሰላም እናገኝ ዘንድ የምንማጸነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት በመዝ 28÷ 11 ላይ “እግዚአብሔር ሕዝቡን በሰላም ይባርካል” የሚለውን መዝሙር ይዘን እኛም በቅዳሴ ጸሎታችን ውስጥ “የሰላም ንጉሥ ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ሰላምን ስጠን ሰላምንም አጽናልን” እያልን እውነተኛ ሰላማችን እንድትጸናልን ሰላማዊ የሆነውን የሰላም ንጉሥ በየዕለቱ እንለምነዋለን፡፡ ይህ ሰላም ለአገር፣ ለወገን፣ ለፍጡራን ሁሉ የሚያስፈልግ መሆኑን በመረዳት በቅዳሴ ጸሎታችን ላይ በተደጋጋሚ እናነሣዋለን፡፡ ይህ በተደጋጋሚ የምንማጸነው ሰላም ከዲያብሎስ፣ ከፍርሃት፣ ከጭንቀት፣ ከመከራና ከሃዘን ጠብቆ ሙሉ ደስታን የሚያጎናጽፍ ልዩ መሣሪያ ነው፡፡ ብዙዎች ልባቸው በጭንቀትና በፍርሃት በሚሸበርበት ጊዜ የአንተ ውስጣዊ ሰላምህ አይናጋም፡፡ በጦርነት መካከል ተሰልፈህ የመሸነፍ ስሜት ጠፍቶ የማሸነፍ ወኔ ትጎናጸፋለህ፡፡ በዚህም የተነሣ ውስጣዊ መረበሽ፣ መጨነቅ ብን ብሎ ይጠፋልህና እውነተኛ ሰላም በፊትህ ትፈስሳለች፡፡ በከባድ አደጋዎች መካከል የብዙዎች  ልብ በፍርሃትና በጭንቀት ቀልጦ ዋይታ ሲበዛባቸው አንተ ግን ምንም እንደማያውቅ ሕጻን ንጹሕ ሰላምን ተሸፋፍነህ በደስታ ትቦርቃለህ፡፡ በከንቱ በመጨነቅ እና በማልቀስ አንዳች ነገር መፍጠር እንደማትችል እውነተኛ ሰላምን የሠጠህ አምላክ ያስተማረህ ወንጌል በሕይወትህ ትርጉም እያገኘ ፍሬ ሲያፈራ አንተም ፍሬውን ስትመገብ ይበልጥ ደስታህ ይጨምራል፡፡ ብዙዎች እንቅልፍ በማጣት ሲባዝኑ አንተ በንጹሕ እረፍት መካከል ትሰማራለህ፡፡ “እግዚአብሔር እረኛየ ነው የሚያሳጣኝም የለም በለመለመ መስክ ያሰማራኛል በእረፍት ውኃ ዘንድም ይመራኛል” /መዝ22÷1/ የሚለውን የቅዱስ ዳዊት ዝማሬ በእውነተኛ ሰላም መካከል ትዘምራለህ፡፡ የአገሬን ጥፋት አታሳየኝ እያለ ይለምን የነበረው በእግዚአብሔር ጥበብ ለድውያን የሚሆን ዐጽቀ በለስን ቆርጦ እንዲያመጣ የተላከውና ዐጽቀ በለሷን ይዞ መጥቶ ከዛፍ ሥር እንዳረፈ በዚያው ለ66 ዓመት ያህል በእንቅልፍ አሳልፎ የአገሩን ጥፋት ከማየት የሰወረውን አቤሜሌክ ወደ አንተ ያመጣዋል፡፡ እርሱም እውነተኛ ሰላምን በሚገባ በተግባር ያረጋግጥልሃል ይተረጉምልሃልም፡፡ ያ እውነተኛ ሰላም ታላቅ የሆነ መንፈሳዊ ኃይል አለው፡፡ “ስለዚህ ኤልሳቤጥ የማርያምን ሰላምታ በሰማች ጊዜ ጽንሱ በማኅጸን ዘለለ” /ሉቃ 1÷41/ እውነተኛ ሰላም እንዲህ በማኅጸን ያለውን ጽንስ ሳይቀር ደስ የሚያሰኝና የሚያዘልል ነው፡፡  ያ ሰላም በየዋህነትና በንጽሕና ከእግዚአብሔር ጋር በመሆን የሚገኝ ነው፡፡ ያን ሰላም ዮሐንስ እንዲህ ገልጾታል “ ሰላምን እተውላችኋለሁ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም”/ዮሐ14÷27/ እውነተኛ ሰላም ከእግዚአብሔር የሚገኝ  ዓለምም ከምትሰጠው ሰላም እጅጉን የተለየ ለመሆኑ ይህ ቃል ምስክር ነው፡፡ ዓለም የምትሰጠው ሰላም የሐሰት ነው፡፡ የጠፋው ልጅ ታሪክ ይህንን በሚገባ ያስረዳናል፡፡ በአባቱ ቤት የነበረው እውነተኛ ሰላም ሆኖ ሳለ ወደ ዓለም ገባ፤ ዓለምም ገንዘቡን በሚገባ ከጨረሰች በኋላ ሰላም ነፈገችው፡፡ በዚህም የተነሣ እንደገና ተመልሶ ወደ ቀድሞው ሰላም ወደ አባቱ ቤት ገባ፡፡/ሉቃ15÷11-24/ ይህ ልጅ እውነተኛ ሰላም የሚገኘው በአባቱ ቤት ብቻ መሆኑን ተረዳ፡፡ ከእግዚአብሔር ስትርቅ የምታጣው ይህንን ዓይነት ሰላም ነው፡፡ እግዚአብሔር ይህን ሰላም እንድታጣ ከተወህ ወጥተህ መግባት አትችልም፤ ለሴኮንዶች ያህል እንኳ እረፍት አታገኝም፡፡ ድምጽ በሰማህ ኳ ባለ ቁጥር ትሸበራለህ፡፡ ያ እውነተኛ ሰላም በገበያ መካከል ገብተህ ድምጽ ሳትሰማ የምትወጣበት ነበርና አሁን ግን እርሱን በማጣትህ ትጨነቃለህ፣ ፍርሃት ይበዛብሃል፣ ተቅበዝባዥ ትሆናለህ፡፡ ስለዚህ ወደ እውነተኛው ሰላም ወደ አባትህ ቤት ልትመለስ ያስፈልጋል፡፡ በኃጢአት የቆሸሸ ማንነትህን በንስሓ አጥበህ ወደ አባትህ ቤት ልትመለስ የምትችልበት ዕለት ዛሬ ብቻ ስለሆነ እውነተኛ ሰላምን ወደሚሰጠው አባትህ ቤት ተመለስ፡፡ እውነተኛ ሰላም ለእግዚአብሔር ክብር እንድትመሰክር ሊወግሩህ ድንጋይን በያዙ ሰዎች መካከል ወይም ሊፈጩህ በተዘጋጁ ወፍጮዎች መካከል ቆመህ እውነቱን እንድትገልጥ ትረዳሃለች፡፡ የፍርሃት ካባን ታወልቅልህና የቅዱስ ጊዮርጊስንና የቅዱስ እስጢፋኖስን ሰማእትነት እስክትቀበል ድረስ ታጸናሃለች፡፡ ለሚወግሩህም ሰዎች “ይህን ኃጢአት አትቁጠርባቸው” የሚል ፍጹም ፍቅር የተሞላበት ልመና እንድታቀርብ ውስጥህን በንጹሕ ፍቅር ታትምሃለች፡፡ /የሐዋ 7÷60/ ስለዚህ ያንን እውነተኛ ሰላም ገንዘብህ ልታደርገው ይገባል፡፡ ከኃጢአትህ ተመልሰህ በንጽሕናና በቅድስና በየዋህነትም ሆነህ ብትገኝ እውነተኛ ሰላም ወደ አንተ ትመጣለች፡፡ እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ ትእዛዙን ጠብቀህ ብትጓዝ እውነተኛ ሰላም ከአንተ ጋር ትጓዛለች፡፡ ስለዚህ ከእግዚአብሔር ጋር በመታረቅ እንደእርሱ መልካም ፈቃድ በመጓዝ ከቤቱ ሳትርቅ በእውነተኛ ሰላም ልትኖር ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን ይህን የማታደርግ ከሆነ እውነተኛ ሰላም እጅጉን ትርቅሃለች፡፡

Wednesday, November 11, 2015

“አይምሰላችሁ!!!”

© በመልካሙ በየነ
ሕዳር 2/2008 ዓ.ም
ደብረማረቆስ፣ ኢትዮጵያ
ወገኖቻችን መጠንቀቅ እንዲገባቸው ልንጠነቀቅና ልናስተውል የሚገባንን ነገር ለመንገር ብዕሬን አነሣሁ፡፡ የሚቀበል ይቀበላል የማይቀበል ደግሞ አይቀበልም አለመቀበሉንም ሆነ መቀበሉን ግን በነጻነት አስተያየት መስጫው ላይ መተው ይቻላል፡፡ ይህን ካልኩ በኋላ ወደ መልእክቴ እገባለሁ፡፡
ዘመኑ ቀርቧልና ንስሐ ግቡ እያለች ልጆቿን በምግባርና በትሩፋት የምትጠብቅ እናት ቅድስት ቤተክርስቲያን በአሁኑ ሰአት ባስተማረቻቸው ልጆቿ እና ምንም በማያውቋት ጥላቻ ከባድ ፈተና ላይ ናት፡፡ ነገር ግን እስካሁን ካሳለፈቻቸው በርካታ ፈተናዎች የበለጠ ስላልሆነ በጥበብና በማስተዋል እንደምታልፍ ጥርጥር የለኝም፡፡ ነፋስ በነፈሰ ቁጥር ባለማስተዋል የምንነፍስ፣ በበረሩበት የምንበር፣ በሄዱበት የምንሄድ፣ በገቡበት የምንገባ፣ በወጡበት የምንወጣ እግዚአብሔርን ከመደገፍ ይልቅ የሰው ምርኩዝ የምንመረኮዝ በርካታዎች ነን፡፡ ከንቱ ሰማዕትነት ለመክፈልም የምንጣደፍ የሆነ ያልሆነውን የምንዘባርቅ መረጃዎችን ከማገላበጥ መጻሕፍትን ከማንበብ ይልቅ የሰዎችን አባባልና ወሬ የምናመላልስ “አባ እገሌ እንዲህ ብለው” ፣ “እማ እገሊት እንዲህ ብለው”፣ “እዚህ ገዳም እንዲህ ተብዬ”፣ “አባ እገሌ ራዕይ አይተውልኝ” ወዘተ አያልን ባለማስተዋል የተበላን በርካታዎች እንደሆንን ልንዘነጋው አይገባም፡፡ “የአባ እገሌ” ሃሳብ ከመጽሐፉ ጋር አልገጥም ይላል “የእማ እገሊት”ም ራዕይ እንዲሁ መጽሐፍ ቅዱሱን ይጋጨዋል ነገር ግን የምንወዳቸው የምናከብራቸው “አባ አባ፣ እማ እማ” የምንላቸው ዝቅ ብለን ጉልበታቸውን የምንስማቸው ናቸውና የተናገሩት እነርሱን ለሚቃወም ሁሉ ዘብ እንቆምላቸዋለን፡፡ አንድ ሰው የሆነ ውለታ ሊውልልህ ይችላል ያ ውለታው ግን እምነትህን እንድትለውጥ የሚያደርስ ተጽእኖ ሊኖረው አይገባም፡፡ ውለታ የዋለልህ በመሆኑም ብቻ “በዚህ ምድር  እንደእርሱ ያለ ሰው ፈጽሞ አይገኝም”፣ “አረ በፍጹም እርሱ እንዲህ አይነት ነገር አያደርግም” ወዘተ እያልክ ልትሞግትለት ጥፋቱን እራሱ አምኖ እንኳ “በፍጹም ይህን ያደርጋል ብዬ አልገምትም ዝም ብሎ አምኖ ይሆናል እንጅ” እያልክ ልትከራከር ሁሉ ትችላለህ፡፡ ግን አይደለም…
አይምሰላችሁ! አትሞኙ! የጠመጠመ ሁሉ ካህን አይደለም፤ ድምጽ ያለው ሁሉ ዘማሪ አይደለም፤ ጥቅስ የጠቀሰ ሁሉ ሰባኪ አይደለም፣ ደብተር የያዘ ሁሉ ተማሪ አይደለም፣ ቾክ የያዘ ሁሉ መምህር አይደለም፣ ጋወን የለበሰ ሁሉ ሃኪም አይደለም፣ በተሸከርካሪ ወንበር የተቀመጠ ሁሉ ኃላፊ አይደለም፡፡ በቃ! ይህንን ደፍረን እንናገረዋለን! እየሆነ ያለው ነገር እሱ ስለሆነ፡፡ ተሐድሶ መናፍቃን አይደለም ይህንን ማድረግ ቀርቶ ሌላም ሌላም ለማድረግ እቅዱ ስላላቸው ማለት ነው፡፡ ነገር ግን በግልሰቦች ደረጃ ወርደን ቅዱስ ሲኖዶስ አውግዞ ሳይለያቸው ድሮ እንመጻደቅባቸው እንዳልነበር ሁሉ አሁን አብዛኛው ሰው ንቆ ሲተዋቸው “ፓስተር እገሌ” ለማለት መቅደማችን በራሳችን የመተማመኑ ጉዳይ ጥያቄ ውስጥ ያስገባዋል፡፡ በመኪና የሄደ ሁሉ ሹፌር ሊሆን አይችልም፤ በአውሮፕላን የበረረ ሁሉ ፓይለት ሊሆን አይችልም፣ ትምህርት ቤት የገባ ሁሉ ተማሪ ሊሆን አይችልም፣ ዩኒቨርሲቲ የተማረ ሁሉ ሊመረቅ አይችልም፡፡ ስለዚህ በቤተክርስቲያን ያደገ ሁሉም እንዲሁ የቤተ ክርስቲያን ልጅ ሊሆን አይችልም፡፡ እዚህ ላይ ማስተዋል ይገባናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለብዙ ጊዜ እንዲቆይ በዚያ እንዲያድግ ምክንያት የሆነው ምንድን ነው? እናትነቷን ፈልጎ ነው ወይስ ሌላ ጥቅም ፈልጎ? የሚለው መመለስ አለበት፡፡ በርካታ አርቲስቶችን መመልከት ትችላላችሁ፡፡ ኮፒ ራይትን ማስቆም ባለመቻሉ ዛሬ ያወጡት ዘፈን ነገ በዓለም ሁሉ ይደመጣል አንድ ካሴት እንደሸጡ ሁሉም ሰምቶ ይሰለቸዋል ይህ በመሆኑ ምንም ህይወታቸውን የሚለውጥ ገንዘብ ማግኘት አልተቻላቸውም፡፡ በዚህ የተነሣ አብዛኞቹ ወደ ሃይማኖቱ ገብተው እምነታቸውን እንደሽፋን ተጠቅመው “ዘፋኝነተን አቁሜ ዘማሪ ሆኛለሁ” እያሉ “አርቲስት ዘማሪ እገሌ” እየተባለ መዝሙር አይሉት ዘፈን ቅጡን ያጣ አድርገው እያሳተሙ ሲቸበችቡት ይውላሉ፡፡ ታዲያ እነዚህ ሰዎች ነገ ያ የኮፒ ራይት መብት ቢጠበቅላቸው ወደ ዘፈናቸው ላለመመለሳቸው ምን ዋስትና አለ? ምንም፡፡
እግዚአብሔር ያደረገልንን ውለታ ለግለሰቦች አሳልፈን የምንሰጥ ግለሰቦች አሳልፈን የምንሸጥ የአምላካችንን ስም ከማመስገን ይልቅ የግለሰቦችን ስም እየጠራን ያኑርልን የምንል ከንቱዎች፡፡ ምንም ያህል ነገር ከሰው ቢደረግልን ያን እንዲያደርግልን የረዳንን አምላክ ወዴት እንዘነገዋለን? አምላካችን ሲሰደብ ኢየሱስ አማላጅ ሲባል ቅዱሳኑ ሲሰደቡ አያማልዱም ሲባሉ ስናጨበጭብ የነበርን ሰዎች ዛሬ አንድ ግለሰብ እንዲህ ሆነ እንዲህ ተደረገ ሲባል አካኪ ዘራፍ እንላለን፡፡ ለመሆኑ መቅደም የነበረበት ለማን ነው? ለአምላካችን ወይስ ለግለሰቦች? እኔ በጣም ይገርመኛል ምን ዓይነት አዚም እንደተጫነን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ ጴጥሮስ የውስጣቸው ቅድስና ለልብሳቸው ብሎም ለጥላቸው ሲሆን በጥላቸው ድውይ ሲፈውሱ አላነበብንም እንዴ?ሺህ ጊዜ  አንብበነዋል፡፡ ታዲያ በሮም አደባባይ ቁልቁል ሲሰቀሉ ምን ተነፈስን? ምንም፡፡ ምክንያቱም የአምላክ ፈቃድ ነዋ!!! ታዲያ ዛሬስ??????????