Monday, August 8, 2016

"ውዳሴ ዘሠሉስ ውዳሴ በሠሉስ... አክለለ ምክሕነ"

©መልካሙ በየነ
ነሐሴ 3/2008 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ ኢትዮጵያ
ውዳሴሃ ለእግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ ዘይትነበብ በዕለተ ሠሉስ፡፡
ለምስጋና ሁለተኛ ለፍጥረት ሦስተኛ ቀን ነው፡፡ በዚህም ቀን እመቤታችን ትመጣለች የብርሃን ምንጻፍ ይነጸፋል የብርሃን ድባብ ይዘረጋል፡፡ ከዚያ ላይ ሁና ሰላም ለከ ኦ ፍቁርየ ኤፍሬም ትለዋለች እርሱም ታጥቆ እጅ ነሥቶ ይቆማል፡፡ ወድሰኒ ትለዋለች በዕለተ ሰኑይ ክርክር አልቋልና ባርክኒ ይላታል፡፡ በረከተ ወልድየ ወአቡሁ ወመንፈስ ቅዱስ ይኅድር በላእሌከ ትለዋለች፡፡ ተባርኮ ምስጋናዋን ይጀምራል፡፡
ውዳሴ ዘሠሉስ ውዳሴ በሠሉስ ውዳሴሃ ለእግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ ዘይትነበብ በዕለተ ሠሉስ ይላል ቃለ ጸሐፊ ነው እርሱ ግን አክሊለ ምክሕነ ብሎ  ይጀምራል፡፡
አክሊለ ምክሕነ…. አክሊል የወዲህኛው ምክሕ የወዲያኛው
ወቀዳሚተ መድኃኒትነ…. ቀዳሚት የወዲህኛው መድኃኒት የወዲያኛው
ወመሠረተ ንጽሕነ…. መሠረት የወዲህኛው ንጽሕ የወዲያኛው
ኮነ በማርያም ድንግል… በማርያም ድንግል ሆነልን አለ፡፡ ማርያም ናት ሲል ነው፡፡ አንድም በዚህ ቀን ከነገሥታት ዳዊትን፣ ከመሣፍንት ኢያሱን፣ ከደናግል ኤልያስን አስከትላ መጥታለች፡፡ ዳዊት ምንም ንጉሠ ነገሥት ብትባል የመመኪያችንን ዘውድ ማምጣት አልተቻለህም፡፡ ኢያሱም መድኃኒት ብትባል የደኅንነታችን መጀመሪያ መሆን አልተቻለህም፡፡ ኤልያስም ንጹሕ ድንግል ብትባል የንጽሕናችን መሠረት መሆን አልተቻለህም፡፡ የመመኪያችን ዘውድ የደኅንነታችን መጀመሪያ የንጽሕናችንም መሠረት ድንግል ማርያም ናት ሲል ነው፡፡ አንድም አክሊሎሙ ለሰማዕት እንዲለው አክሊለ ሰማዕት የሚባል ጌታ፤ ጥንተ ሕይወቶሙ እንዲለው ጥንተ ሕይወት የሚባል ጌታ አኃዜ ዓለም በእራኁ ኩሉ እኁዝ ውስተ እዴሁ መሠረተ ዓለም ይጸውር ድደ ወይነብር ጠፈረ እንዲል፡፡ መሠረተ ዓለም የሚባል ጌታ በድንግል ማርያም   ተገኘልን፡፡
ትላንት ስሟን አላነሣም ዛሬ ስሟን አነሣ በእንግዳ ልማድ እንግዳን ዕለቱን ስሙን አይጠሩትም ከዋለ ካደረ በኋላ ስሙን ይጠሩታል በዚያ ልማድ ማርያም ማለት ፍጽምት ማለት ነው፡፡ ለጊዜው መልክ ከደም ግባት አስተባብራ ተገኝታለችና፡፡ ፍጻሜው ግን ንጽሐ ሥጋ ከንጽሐ ነፍስ ድንጋሌ ሥጋ ከድንጋሌ ነፍስ አስተባብራ ተገኝታለችና፡፡ አንድም ጸጋ ወሐብት ማለት ነው ለጊዜው ለእናት ለአባቷ ጸጋ ሆና ተሰጥታለች ፍጻሜው ግን ለሰው ሁሉ ጸጋ ሁና ተሰጥታለችና፡፡ አንድም መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት ማለት ነው ምእመናንን መርታ ገነት መንግሥተ ሰማያት አግብታለችና፡፡ አንድም ልዕልት ማለት ነው፡፡ ሮም አርያም ማለት ልዑል ማለት እንደሆነ፡፡ እርሷንም መትህተ ፈጣሪ መልዕልተ ፍጡራን ይላታልና፡፡ አንድም ማኅበረ መሐይምናን ወሕዝብ ተለአኪተ እግዚአብሔር ወሰብእ ተፈሥሒ ቤተ እስራኤል ወተሐሰዪ ቤተ ይሁዳ ማለት ነው፡፡ አንድም ማርያም ማለት እግዝእተ ብዙኃን ማለት ነው ያንንማ ዘዕብራይስጢ እንጅ አይለውም ብሎ ማሪሃም ማለት ቅሉ እግዝእተ ብዙኃን ማለት ነው፡፡ አብርሃም ማለት አበ ብዙኃን ማለት እንደሆነ፡፡
እንተ ወለደት ለነ ዘእግዚአብሔር ቃለ… መመኪያነቷን በቅጽል አመጣው አካላዊ ቃልን በወለደችልን በድንግል ማርያም ተገኘልን፡፡
ዘኮነ ሰብአ በእንተ መድኃኒትነ… እኛን ስለማዳን ሰው የሆነ
እምድኅረ ኮነ ሰብአ ጥዩቀ አምላክ ፍጹም ውእቱ… ሰውም ከሆነ በኋላ ፍጹም አምላክ ነው፡፡ ሐራ ጥቃ ቃል ሥጋ ሆነ ያለውን ይዘው ወደ ታች ተለወጠ ይላሉና ሰውም ከሆነ በኋላ ፍጹም አምላክ ነው አለባቸው፡፡
ወበእንተዝ ወለደቶ እንዘ ድንግል ይእቲ… ስለዚህ ነገር ማኅተመ ድንግልናዋ ሳይለወጥ ወለደችው
መንክር ኃይለ ወሊዶታ ዘኢይትነገር… ድንቅ የሚሆነው የመውለዷ ሥራ የማይመረመር ነው፡፡ የማይመረመር የመውለዷ ሥራ ድንቅ ነው፡፡
ሰአሊ ለነ ቅድስት… በማይመረመር ግብር ከወለድሽው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኝልን፡፡ ሐተታ እንደ ሰኞ ።

No comments:

Post a Comment