Wednesday, August 10, 2016

“ወሥሉጥ ስምኪ በኀበ እግዚአብሔር”


© መልካሙ በየነ
ነሐሴ 04/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
የአባ ሕርያቆስ ረድኤት በረከት ይደርብንና እመቤታችንን ባመሰገነበት ቅዳሴው እንዲህ አለ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም እንዲህ ብለው ተረጎሙልን፡፡ የቃሉ በረከት በሁላችን ላይ ይደርብን አሜን፡፡
ወሥሉጥ ስምኪ በኀበ እግዚአብሔር፡፡ ስምሽም በእግዚአብሔር ዘንድ በማማለድ ሥሉጥ ነው፡፡ ይህም በአንድ ሰው ታውቋል፡፡ ታሪክ እጅግ ገንዘቡ የበዛ የተረፈው አንድ ባለጸጋ ነበረ ላዝማሪ ለዘዋሪ እየሰጠ አለቀበት፡፡ አንድም የዚህ ዓለም ገንዘብ ሲሰበሰብ እንጅ ሲጠፋ አይታወቅምና፡፡ ኅልፈቱ ቅድመ አስተርእዮቱ እንዲል፡፡ ከዚህ በኋላ ከብሬ በኖርሁበት አገር ተዋርጄ ሰጥቼ በኖርሁበት አገር ለምኜ  አልኖርም ብሎ አገር ጥሎ ቁርበት ጠቅሎ ሲሄድ ሰይጣን የጨዋ ልጅ መስሎ ከጎዳና ቆይቶ ወዴት ትሄዳለህ አለው ከብሬ በኖርሁበት አገር ተዋርጄ ሰጥቼ በኖርሁበት አገር ለምኜ  አልኖርም ብየ አገር ጥየ ቁርበት ጠቅልየ መሄዴ ነው አለው፡፡ ያዘነ መስሎ ደንጊያውን በምትሐት ወርቅ አስመስሎ ይህን ብሰጥህ አትመለስምን አለው፡፡ ይህንንማ ካገኘሁ ስንኳን ለእኔ ለልጅ ልጄ አይበቃም አለው ከዚህ በኋላ ሰጠው አንተም ፈቃዴን ፈጽምልኝ አለው፡፡ ምን ላድርግልህ አለው፡፡ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስን ካድልኝ መላእክት ጻድቃን ሰማዕታትን አያማልዱም በል አለው፡፡ ካደ አያማልዱም አለ፡፡ ከተለያዩ በኋላ ነገር ረስቼ ቆየኝ አለው፡፡ ምእመናን አፍረው አክብረው ስሟን የሚጠሯት ማርያም የምትባል አለች ወላዲተ አምላክ መሆኗን ካድልኝ አለው፡፡ የለማኝ ምኩዜን ምን ይዞ ይሄዷል ጉዞ እንዲሉ እርሷንስ አይሆንም አለው፡፡ እንኪያስ አምጣ ብሎ ወርቅ አስመስሎ የሰጠውን ደንጊያ ተቀብሎ ልብ ራሱን ብሎ ገደለው፡፡ መላእክተ ጽልመት ነፍሱን ከሥጋው ለይተው እጅ አድርገዋታል፡፡ መላእክተ ብርሃንም የጌታን ቁርጽ ፍርድ ሳያዩ አይለዩምና ከእመቤታችን ዘንድ ሂደው ምነው ዝም አልሽ ይህች ነፍስ ከሥጋው የተለየች ባንቺ ምክንያ አይደለምን አታማልጅም አሏት፡፡ እርሷም መሐር ሊተ ወልድየ ዛተ ነፍሰ አለችው፡፡ ከልብኑ ይትመሐር  አባቴን እኔን የባሕርይ ሕይወቴ መንፈስ ቅዱስን የወዳጆቼ የመላእክትን የጻድቃን የሰማዕታት አማላጅነታቸውን የካደ ይማራልን አላት፡፡ ዘጸውዐ ስምኪ ወዘገብረ ተዝካረኪ እምሕር ለኪ ያልኸው ቃልህ ይታበላልን አለችው፡፡ ያውስ ቢሆን የሕጸጸ ምግባር ነው እንጅ የሕጸጸ ሃይማት ነውንነገር ግን ከሥጋሽ ሥጋ ከነፍስሽ ነፍስ ነሥቼ ሰው መሆኔ ፈቃድሽን ላልፈጽምልሽ ነውን ምሬልሻለሁ አላት፡፡ እንኪያስ ከማርህልኝ ነፍሱን ከሥጋው አዋሕደህ አስነሣልኝ  አለችው፡፡ ነፍሱን ከሥጋው ጋር አዋሕዶ አስነሣላት  ለምን ካድህ አለችው፡፡ ባጣ አላት ያጣ ይለምናል እንጅ ይክዳልን  አሁንም ከልጄ አማልጄህ እንዲህ ካለ ቦታ ምግብህን አዞልሃልና ሂድ አለችው፡፡ በዚያች ቦታ አንድ ባለጸጋ ነበር፡፡ አንዲት መልከ መልካም ልጅ ነበረችው፡፡ ባለጸጋ መጥቶ ልጅህን ስጠኝ ያለው እንደሆነ ልጄን በመልክ አትተካከላትም ይለዋል፡፡ መልከ መልካም መጥቶ ስጠኝ ያለው እንደሆነ ልጄን በገንዘብ አትተካከላትም ይለዋል፡፡ እንዲህ አድርጎ ከፍቅሩ ጽናት የተነሣ ያኖራት ነበረ፡፡ በዚያች ቀን እመቤታችን ከቤተ ክርስቲያን እንዲሄድ አድርገዋለች፡፡ የባለጸጋ ጸሎት አጭር ነውና የሰጠኸኝን አትንሣኝ ይህችን አንዲት ቅንጣት ልጄን ባርክልኝ ብሎ ተቀመጠ፡፡ ወዲያው ተደሞ መጣበት፡፡ ያም ሰው ጠፈር ጠፈሩን እያየ ሲዞር ከሱ አጠገብ ደረሶ ቆመ፡፡ ልጅህንም ከብትህንም ለዚህ ሰው ስጠው አለችው፡፡ ቀና ቢል አየው፡፡ ከዚህ በኋላ ወስዶ ልጁንም ከብቱንም ሰጥቶት ወዲያው ዐረፈ፡፡ እርሱም ቆርቦ የእመቤታችንን ስሟን ሲጸራ ዝክሯን ሲዘክር የሚኖር ሁኗል፡፡ ከሞተም በኋላ በዚህ ጊዜ ያልፋልየማይባል መንግሥተ ሰማያትን አውርሰዋለችና እንዲህ አለ፡፡
፩ዱ ነዳይ ዘክሕደ ሃይማኖቶ ኪያኪ ክሕደ ሶበ አበየ በቅድመ ሰይጣን ዘአስሐቶ
አሚነ ዚአኪ ድንግል ለአድኅኖ ነፍሱ በቍዐቶ
እንዘ ይሴባሕ ተአምርኪ ወለጽጌኪ ምሕረቶ
ተንሥአ እምንዋሙ ወአተወ ቤቶ እንዳለ ደራሲ፡፡
(ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጉም ገጽ 30 እና 31)
ይቆየን……

No comments:

Post a Comment