Friday, August 5, 2016

“ቃና የለሹ ቃና”

© መልካሙ በየነ
ሐምሌ 29/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

ዓላማ አድርጎ የተነሣው ሁላችንም ኢትዮጵያውያን ውስጣችን እንድናደርገው ነው፡፡ ውስጣችን ስናደርገው ደግሞ ባሕል፣ ወግ፣ እሴት፣ እምነት እና ፍቅር ከእያንዳንዳችን ይርቃሉ፡፡ ላይ ላዩን ስንመለከተው በመዝናናት የሚጀምር ይሁን እንጅ ውስጡ እና ፍጻሜው ግን  ሃይማኖታዊ ሳይሆን አይቀርም የቃና የለሹ ቃና!
አንድ የኢትዮጵያ ብሮድ ካስቲንግ ባለሥልጣን በእነዚህ የግል ቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ላይ ተጠይቆ በገሪቱ ቴሌቪዥን ማሰራጫ በኢ.ቢ.ሲ ሲመልስ “የእኛ ባለሥልጣን ለማንኛውም የግል ቴሌቪዥን ጣቢያ እውቅና አልሰጠንም፡፡ ሆኖም ግን እስካሁን ድረስ ከተከፈቱት የቴሌቪዥን ጣቢያ ፕሮግራሞች የአገራችንን ባህል፣ ወግ እና እሴት የሚጻረሩ አይደሉም” ብሏል፡፡ በእውነት የእኛ ባሕል ቀኑን ሙሉ ከቴሌቪዥን ስክሪን ላይ አፍጥጦ መዋል ነው እንዴ? የእኛ ባሕል እና እሴት እኮ መረዳዳት፣ መከባበር፣ መፈቃቀር፣ እንግዳን መቀበል፣ ፈጣሪን ማመስገን፣ሥራን አብዝቶ መሥራት፣ ጀግንነት ወዘተ ነው፡፡ ባሕልና እሴት ፖለቲካ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ፖለቲካ ደጋፊም አለው ተቃዋሚም አለው ህላችን ግን ለሁላችን ነው ለተቀዋሚውም ለደጋፊውም፡፡ በእውነት እነዚህ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች የሀገራችንን መንግሥት ደካማ ጎኖች የሚገልጹ ቢሆኑ ኖሮ ይህን ያህል ዕድሜ ይኖራቸው ነበር? የኢሳትን እድል ይገጥማቸው ነበር፡፡ እንደ ዳይኖሰር ከምድረ ገጽ ይጠፋ ነበር፡፡
የእኛ ባህል፣ ወግ እና እሴት በቃና የለሹ ቃና እንደሚቀርበው ዛራ እና ቻንድራ የተንዛረረ እና የተቸናደረ፣ እንደ ኩዚና ጉኒ የተንኳዘዘ እና የተንጓነነ፣ እንደ ጥቁር ፍቅር ውስጡ የጠቆረ፣ እንደ ውበት እስረኞች በውበት የታሠረ፣ እንደ መንታ ገጽ ልቡ በመንታ መንገድ የሚጓዝ አይደለም፡፡ እነዚህ ፊልም ተብየዎቹ የሚቀርቡባቸውን ሰዓታት ተመልከቱት፡፡ ተያይዘው ለ24 ሰዓታት ለ7 ቀናት የሚዘልቁ ናቸው፡፡ ይህ ደግሞ በተለይ ወጣቶቹን ከሥራ አግቶ ተቀምጠው እንዲውሉ እና የቴሌቪዥናቸውን የስክሪን መጠን  ወይኔ 21 ቢሆን ኖሮ! ወይኔ 41 ኢንች ቢሆን ኖሮ! ወይኔ ፍላት ቢሆን ኖሮ!ወይኔ እንዲህ ሆኖልኝ ኖሮ! ወዘተ ብቻ እንዲሉ አስገድዷቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ ሃይማታዊም፣ ባህላዊም እሴት የለውም፡፡ ዓላማው ከሃይማኖት፣ ከሐገር ፍቅር፣ ከፖለቲካ፣ ከማንኛውም ማኅበራዊ ግንኙነት ግዴለሾች ማድረግ ብቻ ነው፡፡
ዓላማው ሃይማታዊ ግዴለሾች ለማድረግ ነው የምለው ዝም ብየ አይደለም፡፡ የሚተላለፉበት ሠዓት ግን ከብዙ ሃይማኖታዊ ክዋኔዎች የሚያርቅ ነው፡፡ በዛራና ቻንድራ ስንንዛረርና ስንንቸናደር የሰርክ መርሀ ግብር ያልፈናል፡፡ ችግር የለውም አንዴ ደርሼ እመጣለሁ እያልን ስንጠብቅ እነ ኩዚና ጉኒ መጥተው ያንጓንኑናል ያንኳዝዙናል፡፡ በቃ ቀረ ነገ እሄዳለሁ እንል እና ራሳችንን እንጽናናለን ከዚያም ነገ እንደዛው ይኼው ተመሳሳይ ሂደት ይቀጥላል፡፡ ስለዚህ ዓላማው ሃይማታዊ ነው የምላችሁ ለዚህ ነው፡፡
እንደዚህ ዓይነት ተጽእኖዎች ምናልባትም የፕሮቴስታንቱ ሊሆኑ እንደሚችሉ እገምታለሁ፡፡ መብራትና ውኃን ተመልከቷቸው መቸ መቸ እንደሚመጡና መቸ መቸ እንደሚሄዱ አስተውሉ፡፡ ውኃ እሁድና ቅዳሜ ስትፈስ ትውልና ሰኞ ጀምራ ትደርቃለች፡፡ ሰንበትን ውኃ ከቤቴ አላስገባም የሚለው የአገራችን አማኝ ሳይወድ በግዱ እንዲያስገባ ይገደዳል ማለት ነው፡፡ መብራትንም እንዲሁ ተመልከቱት፡፡ ገጠር ላይ እና ከተማ ላይ የሚጠፋበት ቀን ይለያያል፡፡ ገጠር ላይ በዓላትን እየጠበቁ ማብራት ሥራን እየጠበቁ ማጥፋት ልማድ ሆኗል፡፡ ከበረሃው ከደጋው ወደ ወፈጮ ቤቶች እህላቸውን ጭነው ይተምማሉ፡፡ በዚያም ወፍጮ ቤት ይከትሙና መብራት መጣ መብራት ሄደ ሲሉ ይከርማሉ፡፡ በጣም ታላላቅ በሚባሉ በዓላት ዕለት መብራት ይመጣል፡፡ መብራትን በመጠበቅ ከቤቱ ሳምንት ያህል ርቆ የሰነበተ ህዝብም በዓሉን ከምንም ሳይቆጥር አስፈጭቶ ይኼዳል፡፡  ከተማ ላይ ስትሄዱ ግን መብራት የሚጠፋው በታላቅ በዓላት ቀን ነው፡፡ በእነዚህ ታላለቅ በዓላት አብያተ ክርስቲያናት የማኅሌት ሥርዓቱን ለህዝቡ ለማሰማት በድምጽ ማጉያ ተጠቅመው ስለሚቆሙ ይህንን ህዝቡ እንዳይሰማ መብራት ይቋረጣል፡፡ በእርግጥ ይህ እንደሚደረግ የታወቀ ስለሆነ አብዛኞቹ በከተማ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የራሳቸው የሆነ ጀነሬተር ገዝተው በመገልገል ላይ ናቸው፡፡
ቃና የለሹ ቃናም ከእነዚህ የፕሮቴስታንት ዓላማ ካነገቡ ሰዎች እጅ የገባ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ስለዚህ በተለይ ወጣቱ ሱስ እንዳይሆንባችሁ ቃና የሚለውን የቴሌቪዥን ፕሮግራም በመጠን እና በልክ እንጠቀምበት፡፡ ብንችል ከቻናል ሊስቱ ላይ እናጥፋው ባንችል የምንመለከትበትን ሰዓት ሃይማኖታዊ እሴቶቻችንን በማይጋፋ መልኩ እናመቻች፡፡ ቃና ውስጤ ነው የሚለው መፈክራቸው ቀላል እንዳይመስለን፡፡ ውስጣችን እየሆነ መጥቷል ውስጣችን ደግሞ ደማችን ነው ደማችን ደግሞ ድንግል ማርያም ያለችበት ደም ነው፡፡ ታዲያ ውስጣችን ነው ሲሉን እኮ ደማችን ውስጥ ያለችውን ድንግል ማርምያን አስወግደው በእነርሱ ቃናነት ሊለውጡት ነው፡፡

በእርግጥ 2008 ለቃና መፈጠር ብቻ አልነበረም ዘመን የሆነው፡፡ ሌሎችም እንደ አሸን የፈሉ ጣቢያዎች ተፈልፍለዋል፡፡ ባህላችንን፣ ወጋችንን፣ እሴታችንን፣ ሃይማኖታችንን የሚጋፋ ቃና የለሹ ቃና ስለሆነ ብቻ ነው እንጅ፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን የቴሌቪዥን ሥርጭት ጀምሯል ታላቅ ፓትርያርክ የነበሩትን የጸሎት እና የትህትና አባት የነበሩትን 3ኛው ፓትርያርክ አቡነ ተክለሃይማትን ከዘመናቸው ዘመን ባይገጥመንም እንኳ ትምህርታቸው እየተላለፈ ነውና እንስማው እስኪ፡፡ በቃና የለሹ ቃና ውስጣችንን ከምናጣ ውስጣችን ይሆን ዘንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤትክርስቲያንን የቴሌቪዥን ሥርጭት እንከታተል እላለሁ፡፡ ይህን የምላችሁ ግን እንደ ምክር ነው እንጅ ለማስተዋወቅ ወይም ጥላቻን ለመፍጠር አይደለም፡፡ እንደምትሩኝ ግን ተስፋ አደርጋለሁ!!!

No comments:

Post a Comment