Wednesday, August 20, 2014

የመናፍቃን እውርነት!


እውርነትን በ2 ከፍለን ልንመለከተው እንችላለን፡፡ ይኸውም፡- የዓይንና የልብ እውርነት በማለት ነው፡፡ በጣም አስቸጋሪውና ብዙዎችን ለጉዳት የዳረጋቸው የልብ እውርነት ነው:: “ልብ ካላየ ዓይን አያይም” እንዲሉ በልባቸው መታወር ምክንያት ዓይናቸው የሚያየውን እጃቸው የሚዳስሰውን ሁሉ ማየት መጨበጥ የተሳናቸው ብዙዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ፡- ድንግል ማርያም አታማልድም ምክንያቱም መጽሐፍ ውስጥ ታማልዳለች የሚል ጥቅስ የለምና ብለው በድንቁርና ማስረጃ ይሞግታሉ:: ልብ ካላችሁ ስሙኝ ልጠይቃችሁ መልሱልኝ::
1. መጽሐፍ ቅዱስ የተደረገውን ሁሉ አጠቃልሎ ይዟልን? አላጠቃለለም ለዚህም ማስረጃ አለኝ ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ 2ኛ ዮሐ 1፥12 ላይ “እንድጽፍላችሁ የምፈልገው ብዙ ነገር ሳለኝ በወረቀትና በቀለም ልጽፈው አልወድም ዳሩ ግን ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ወደ እናንተ ልመጣ አፍ ለአፍም ልናገራችሁ ተስፋ አደርጋለሁ” ይላል፡፡ እንዲሁም በ 3ኛ ዮሐ1÷13 ላይም “ልጽፈው የምፈልገው ብዙ ነገር ነበር ዳሩ ግን በቀለምና በብርዕ ልጽፈው አልወድም” ይላል:: ይህ ሐዋርያ ድንግልን በመስቀሉ ሥር የተቀበለ ነው:: /ዮሐ19÷27/ ስለድንግል አማላጅነት በይበልጥ የሚያውቀው ቅዱስ ዮሐንስ ነው:: ምክንያቱም እነኋት እናትህ ተብላ በእናትነት የተሰጠችው ለእርሱ ነውና፡፡ እኛም እናታችን የምንላት በዮሐንስ በኩል ለሁላችንም የተሰጠችን ስለሆነ ነው፡፡ ዮሐ 21፥25 ላይ እንዲህ ይላል “ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ ኹሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል” ይላል ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉንም ድርጊት በሙሉ አላሰፈረልንም ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ትውፊትም ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ አንዱ ለአንዱ ማለትም አባት ለልጁ ለልጅ ልጁ በቃል ያወረሰው ትምህርት አለ፡፡ ለምሳሌ ያህል በዘፍጥረት ላይ እግዚአብሔር አዳምን በአርአያውና በአምሳሉ እንደፈጠረው ይናገራል፡፡ ከዚያም ከግራ ጎኑ ደግሞ ሔዋንን እንደፈጠረለት ይናገራል፡፡ ከዚያ በኋላ አዳም ሔዋንን አወቃትና ቃየን ተወለደ፡፡ በመቀጠልም አቤል ተወለደ፡፡ ከዚያም ቃየን አቤልን ገደለው አዳምም ሔዋንን አወቃትና ሴት ተወለደ፡፡ ከዚያ በኋላ ሴት ሄኖስ የተባለ ልጅን ወለደ፡፡ መናፍቃን እዚህ ላይ ይቆማሉ እንግዲህ ሴት ማን የምትባል ሴት አግብቶ ነው ልጅ የወለደ? እንደመጽሐፍ ቅዱስ ገለጻ ከሆነ በዚያን ወቅት ያለችው ብቸኛ ሴት እናቱ ሔዋን ብቻ ነበረች፡፡ እስከዚህ ዘመን ድረስ በሕይወት መኖር አለመኖሯ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ባይገለጥም ማለት ነው፡፡ እስደ መጽሐፉ ግን እስከዚህ ዘመን ድረስ የተገለጠችው ሴት እሷ ብቻ ናት፡፡ ታዲያ ልጇ ሴት ከሔዋን ልጅ ወለደ ልትሉን ነውን? በፍጹም አንቀበላችሁም፡፡ እኛ ብዙ ማስረጃዎችን በትውፊትም በመጽሐፍም እናቀርባለን፡፡ ይህንን በሚገባ የሚያብራራልን የቅዱስ ጴጥሮስ ደቀመዝሙር እንደሆነ የሚናገረው ቀሌምንጦስ በጻፈው መጽሐፈ ቀሌምንጦስ ነው፡፡ ይህንን መጽሐፍ መናፍቃኑ አይቀበሉትም፡፡ ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ምልጃዋንም በዮሐ2 ላይ የቃና ዘገሊላውን የመጀመሪያ ተአምር ልብ ይሏል:: መናፍቃን ይህንንም በእውርነት ያጣምሙታል እርሱን ስሙት” ብላለችናኢየሱስን ብቻ ነው የምንሰማ” ይላሉ:: ወይን ማለቁን ማን ነገራት? መናፍቃን ሆይ እንደፈረስ ላይ ላዩን ሳትጋልቡ ከፊትና ከኋላ የተጻፈውን ነገር ሁሉ ተረጋግታችሁ በማስተዋል አንብቡ:: ይህ ቃል የመስማማት ነው:: ወይን ስላለቀባቸው ወይን እንዲሰጣቸው ልጇን ጠየቀችከአንች ጋር ምን ጠብ ምን ክርክር አለኝ ጊዜየ ገና አልደረሰምና” አላት:: ይህ ስለብዙ ነገር ተነግሯል ሰፊ ሐተታ አለው፡፡ በቀላሉ ለማየት ያህል፡-
v  ጊዜየ ገና አልደረሰም ማለቱ፡-
1.  ይህን ተአምር የማደርግበት ጊዜ ገና ነው ምክንያቱም በማድጋው ያለው ወይን ሙሉ በሙሉ አላለቀም ነበርና፡፡ ሳያልቅ ተአምሩን ቢያደርግ ውሃውን ወይን አደረገ ሳይሆን ጥቂቱን ወይን አበረከተው ይባል ነበርና፣
2.  በወቅቱ ይሁዳ የለም ነበርና ውሃውን ወይን ሲያደርግ ተአምሩን ባይመለከት ኖሮ እርሱ ተአምሩን ከሌሎች ሐዋርያት ለይቶ ስለከፈለብኝ እኔም ለአይሁዳውያን አሳይዝኩት ብሎ ምክንያት ይኖረው ነበርና ምክንያ እንዳይኖረው ይሁዳ እስኪመጣ ድረስ ለመጠበቅ፤
3.  እግዚአብሔር ለሥራው ሁሉ ጊዜ እንዳለው ለማጠየቅ፣
4.  ዓለምን የማድንበት በመስቀል የምሰቀልበት ጊዜ ገና አልደረሰም ለማለት ነው፡፡
ከዚህ በሗላ ነው እንግዲህ ጊዜው ሲደርስ “እርሱን ስሙት የሚላችሁን አድርጉ” ያለቸው:: እናትና ልጅ ተስማሙ ምልጃዋ ሠራ ዶኪማስ ከማፈር ዳነ:: አንድ መናፍቅድንግል ማርያም ታማልዳለች የሚል ጥቅስ ከመጽሐፍ ቅዱስ አጣሁ” አለኝ እኔምዓይን ያላቸውን ጠይቅ ያሳዩሃል” አልኩት:: ለምን እንደዚህ መለስክለት አትሉኝም መቼም ምክንያቱም የማየትና ያለማየት የማስተዋልና ያለማስተዋል ጉዳይ እንጅ ጥቅስ ጠፍቶ አይደለም፡፡ ድንግል ማርያም በሉቃስ ወንጌል ሉቃ 1:48 ላይትውልድ ሁሉ ያመሰግኑኛል” አለች:: ትውልድ የሚባለው ከ 3ቱ አይወጣም ትውልደ ሴም፣ ትውልደ ካምና ትውልደ ያፌት ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ ብጽእት እያሉ በአማላጅነቷ አምነው ይማጸኗታል ያመሰግኗታል ማለት ነው:: ድንግል ማርያም በትውልደ ሴም፣ በትውልደ ካምና በትውልደ ያፌት ብጽእት ተብላ የምትመሰገን ናት ማለት ነው፡፡ ታዲያ የዛሬ መናፍቃን ትውልዳቸው ከየት ይሆን ምልጃዋን አንቀበልም ብጽእት አንላትም ያሉት? የሰው ልጅ የድንግልን እናትናትና አማላጅነት ቢክድ ኖሮ ዶኪማስ በቃናው ሠርግ ልጇን ብቻ በጠራ ነበር ግን አላደረገውም:: አያችሁ ዶኪማስ ሲያከብራት:: በሉቃስ ወንጌል እንደተጻፈው መልአኩ ገብርኤል በመፍራት አምላክን እንደምትወልድ አበሰራት:: አያችሁ የሰማይ መላእክት እንኳ ሲያከብሯት:: ኢየሱስ የተገኘው ከድንግል ማርያም ሥጋ ነው:: ኢየሱስ ክርስቶስን ያወቅነው በድንግል ማርያም ነው:: ድንግል ባትኖር ኖሮ ኢየሱስን ሥጋ ለብሶ ማየት አንችልም ነበር :: ለዓለም መዳን ምክንያት እመብርሃን ናት:: ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጥሬ ቃል አሳዩን የምትሉ መናፍቃን በእርግጠኝነት ቃሉን አላጣችሁትም እውርነት ጎድቷችሁ ካልሆነ በቀር:: የጻድቅ መታሰቢያ ለዘላለም ይኖራል:: መዝ111÷6 እንግዲህ ለዘላለም ማለት እስከ መቼ እንደሆነ አስቡት:: እስከ ዓለም ፍጻሜ አይደለም ከዚያም በኋላ ጭምር እንጅ:: ድንግልንም ለዘላለም እናከብራታለን አማልጅን እንላታለን:: ምክንያቱም ቅድስት ናትና መታሰቢያዋም ለዘላለም ነውና አምላክ ለእናትነት አክብሯታልና፡፡ አንድን ነገር ስታከብሩ የራሳችሁ መስፈርት ይኖራችኋል ድንግል ማርያምን ስናከብር ግን የአምላክ እናት የዓለም መዳኛ ብለን ነው:: አማላጅ ጌታ ሳይሆን ተማላጅ አምላክን አስገኝታለችና እናመሰግናታለን ከፍ ከፍም እናደርጋታለን:: ክብር ምስጋና ይግባውና ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ማርያም ቢገለጥ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ አላነሰም አልበለጠምም እኩል ነው እንጅ:: በሥጋዌው ወራት ሕዝቡን ከራሱ ጋር አስታርቋል አማለደ የምንለውም ከራሱ ጋር እንታረቅ ዘንድ ያደረገውን የቤዛነት ሥራ ነው፡፡ ያን የቤዛነት ሥራውን ያደረገልን ወድዶ ፈቅዶ ነውና እኛን ለማዳን  ወደደ ፈቀደ ብለን እንተረጉመዋለን:: አሁን ግንይማልዳል” ማለት ፍጹም ስህተት ነው:: መናፍቃን እንደ ጥያቄ የሚጠይቁ እንደመልስም የሚመልሱት እንደመከራከሪያም የሚከራከሩበት ብቸኛ ጥቅስ ሮሜ 8÷34 “ስለእኛ የሚማልደው” የሚለው ነው፡፡ በዚህ ጥቅስ መነሻነት ኢየሱስ ክርስቶስ አሁንም ይማልዳል ይላሉ:: ቃሉስለእኛ የሚፈርደው” የሚል ነው ቅርብ ጊዜ በታተሙት ላይ ግንስለእኛ የሚማልደው” ተብሎ ተቀይሮ ተጽፏል:: ለመቀየሩ ማረጋገጫ ቁጥር 33 ላይ ስንመለከት “የሚያጸድቅ እግዚአብሔር ነው የሚኮንንስ ማን ነው?” ይላል፡፡ ይህ ማለት አንተ ገነት ግባ ብሎ የሚያጸድቅ፤አንተ ሲዖል ግባ ብሎ የሚኮንን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ይህን የመጨረሻ ፍርድ የሚሰጠው ደግሞ አምላክ ወይም ፈጣሪ እንጅ ፍጡር /አማላጅ/ አይደለም፡፡ ይህ አያሳምንም የሚል ካለ ደግሞ ለምን ወልድ ብቻ አማላጃችን ነው እንለዋለን አብና መንፈስ ቅዱስስ አያማልዱንምን? እስኪ ጥሬ ቃላትን እንመልከት?
v  ሮሜ 8÷26 ነገር ግን መንፈስ ራሱ በማይነገር መቃተት ይማልድልናልይላል፡፡ ስለዚህ በዚህ ጥቅስ መሠረት መንፈስ ቅዱስም ይማልዳል ማለት ነው::
ኤር 7÷25 አባቶቻችሁ ከግብጽ ምድር ከወጡበት ቀን ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ በየዕለቱ እየማለድሁ ባሪያዎቼን ነቢያትን ልኬባቸችሁ ነበርይላል፡፡ እዚህ ጥቅስ ላይ እግዚአብሔር የሚለው እግዚአብሔር አብን ነው፡፡ በኦሪት እንዲህ እንደአሁኑ በግልጥ ሦስትነታቸው አይታወቅም ነበርና፡፡ ሦስትነትና አንድነት በሚገባ የታወቀው ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ከተወለደ በኋላ ነውና፡፡ በዚህ ጥቅስም መሠረት እግዚአብሔር አብ ይማልዳል ማለት ነው፡፡ ታዲያ አብ አማላጅ፣ ወልድም አማላጅ፣መንፈስ ቅዱስም እንዲሁ አማላጅ ከተባሉ አምላካችን ማን ሊሆን ነው? የሚማለደው ማን ነው ልንል ነው? መናፍቃን ሆይ ልብ በሉ አስተውሉ ዝም ብላችሁ ቀንጭባችሁ አትከራከሩ፡፡ በርግጥ አንዴ ልባችሁ ስለጨለመባችሁ አሁንም ትከራከሩ ይሆናል:: ነገር ግን ትክክለኛና አሳማኝ የሆነ ማስረጃ ማቅረብ የምትችሉበት ወኔ ያላችሁ አይመስለኝም፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ ፈራጅ አምላክ እንጅ አማላጅ አይደለም:: ማስረጃ ካስፈለገ ሮሜ 9÷5 “ክርስቶስ በሥጋ መጣ እርሱም ከሁሉ በላይ ሆኖ ለዘላለም የተባረከ አምላክ ነውእንዲሁም ሮሜ14÷10 ላይ  “ሁላችን በክርስቶስ ፍርድ ወንበር ፊት እንቆማለንና” ይላል ፈራጅነቱን ሲገልጥ፡፡

2 comments:

  1. betam teru new wendemachen berta get yebarkeh amen yohannes neg

    ReplyDelete