Wednesday, July 29, 2015

ቅዱሳን ስዕላት

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ክፍል አንድ
መግቢያ
“ቅዱሳን ስዕላት” የሚለው ከሁለት ቃላት ማለትም “ቅዱሳን” እና “ስዕላት” ከሚሉት የተሰናሰለ ነው፡፡ “ቅዱስ” ማለት ልዩ ማለት ሲሆን “ስዕል” ማለት ደግሞ የዓይን ትኩረትን የልብ ተመስጦን የሚሹ ለሚመለከታቸው ሁሉ የመግባቢያ ቋንቋ የሆኑ ማለት ነው፡፡ “ቅዱሳን ስዕላት” ማለትም ከዓለም ሁሉ  ልዩ የሆኑ የዓይንን ትኩረት የልብን ተመስጦ የሚሹ ከተሳለው ቅዱስ ጋር የምንግባባበት ቋንቋ ማለት ነው፡፡ ከዓለም ስዕላት ሁሉ ልዩ የሚያደርጋቸው ነገር እግዚአብሔር በስዕላቱ አድሮ የሚያነጋግርበት ድምጹንም የሚያሰማበት በመሆኑ ነው፡፡ ቅዱሳን ስዕላትን መሳል ዝም ብሎ በአንድ ሰው ፍላጎት ላይ ተመሥርቶ የተጀመረ አይደለም፡፡ ስዕላት መሳልን ያዘዘ አምላካችን እግዚአብሔር ነው፡፡ የታቦትን አሰራር ለሙሴ እግዚአብሔር በነገረው ጊዜ ስዕል እንዲስልበትም አስታውቆታል፡፡ ዘጸ 25÷ 18-22 “ሁለት ኪሩቤል ከተቀመጠ ወርቅ ሥራ በስርየት መክደኛውም ላይ በሁለት ወገን ታደርጋቸዋለህ፡፡ ከስርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን ሁለተኛውን ኪሩብ በሌላው ወገን አድርገህ በአንድ ላይ ትሰራቸዋለህ…” እንዲህ እያለ የመጀመሪያውን ስዕል እንዴት ሊስል እንደሚገባው ይገልጻል፡፡ በታቦቱ ላይ የኪሩቤልን ስዕል መሳሉ ምን ጥቅም እንዳለው ሲናገርም “በዚያም ካንተ ጋር እገናኛለሁ፡፡ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለት ኪሩቤል መካከል በስርየት መክደኛው ላይ ሆኜ እነጋገርሃለሁ” ዘጸ 25÷22 በዚህ መልኩ የተጀመረው ስዕል ለሙሴ በቤተመቅደስ መጋረጃዎች ላይ፣ ለጠቢቡ ሰሎሞንም በቤተ መቅደሱ ግንብ ዙሪያ በውስጥ እና በውጭ እንዲሰሩ በታዘዙት መሠረት በመሥራታቸው እግዚአብሔር ወድዶና ፈቅዶ ተቀብሎላቸዋል፡፡ ዘጸ 26÷1 “ደግሞም ከተፈተለ በፍታ ከሰማያዊ ከሐምራዊ ግምጃ የተሰሩ ዐሥር መጋረጃዎች ያሉበትን ማደሪያ ሥራ ብልህ ሰራተኛ እንደሚሰራ ኪሩቤል በእነርሱ ላይ ይሁኑ” የሰሎሞንን ቤተ መቅደስ አሰራርም ሲናገር “… ቤቱንም ሰረገላዎቹንም መድረኮቹንም ግንቦቹንም ደጆቹንም በወርቅ ለበጠ በግንቦቹም ላይ ኪሩቤልን ቀረጸ…” እያለ ስለ ኪሩቤል አሳሰል በዝርዝር እያተተ ይቀጥላል፡፡ 2ኛ ዜና.መዋ 3÷ 7-መጨ፡፡ ከዚህ እንደምንረዳው ስዕላት እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ ሳይሆኑ በአምላክ ትዕዛዝ የተጀመሩ ናቸው፡፡ ይህንን የአምላክ ትዕዛዝም መሠረት በማድረግ በሐዲስ ኪዳንም ስዕላት ተስለዋል እየተሳሉም ናቸው ወደፊትም ይሳላሉ፡፡ በአዲስ ኪዳንም ጢባርዮስ ቄሳር የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ፍቅር እንዲያስብ ለሰው ልጆች ሲል በመልዕልተ መስቀል መሰቀሉን ዓለምን በደሙ መፍሰስ እንደቀደሳት እንዳይዘነጋው በቀራንዮ እንደተሰቀለ ሆኖ በሐዋርያው ዮሐንስ ተስሎለታል፡፡ የዑር ንጉሥ አብጋር ኡካማ በታመመ ጊዜ መጥቶ እንዲያድነው ወደ ጌታችን የላከው ባሪያው በጌታችን መልክ ተመስጦ ስዕሉን ነድፎ ያስቀረውና ወደ ንጉሡ መስዶ ከበሽታው ያዳነው ስዕል እንዲሁም 12 ዓመት ያህል ደም ይፈሳት የነበረችው ማርያም ለውለታዋ ያሰራችው የጌታችን ስዕል ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስም የእመቤታችንን ስዕል ስሏል፡፡ እንዚህ ማስረጃዎች የሐዲስ ኪዳን የስዕል ማስረጃዎቻችን ናቸው፡፡ ሌሎችም እንዲሁ ብዙ ማስረጃዎች እንዳሉ ታሪክ ይነግረናል የሳይንስ ባለሙያዎችን ያስረዱናል፡፡ በተጨማሪም የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች በሮማ ነገሥታት አዋጅ ምክንያት በተሰደዱ ወቅት በ68 ዓ.ም በዋሻና በፍርክታ ውስጥ ሃይማኖታቸውን በስዕል ለመታሰቢያነት ይቀርጹ ነበር፡፡ ይህም የተረጋገጠና እስከ እስከ 8ኛው መ/ክ/ዘ ድረስ ጸንቶ የኖረ ሲሆን በነዚያ ሥዕሎችም የእግዚአብሔር ኃይል በተአምራት ይገለጽ ስለነበር እጅግ ይከብሩ ነበር፡፡ በ8ኛው መ/ክ/ዘ ግን ሥዕልን ከመውደዳቸው የተነሣ አማልክት የሚሉ ኢኮኖስትሪያ በአንጻሩም ፀረ ሥዕል አቋም በመያዝ የተነሡ ኢኮኖሚኺያ ተነሥተው ጠባቸው ተካረረ በ784 ዓ.ም ይህንን ጠብ አስታረቀ ክብርና ስግደት እንደሚገባቸው ቀኖና የሰራው ጉባኤ በመደረጉ በዘመኑ ተከራካሪዎች መፍትሔ ለእኛም ሥርዓት ሆኗል፡፡ ስዕላት ሲሳሉም በእጅ የማይዳሰሱ ሆነው ነው፡፡ ያ ማለት ቅርጻ ቅርጽ ሥዕላት  ፈጽመው ተከልክለዋል ማለት ነው፡፡ ሌላው ከብሉይ ኪዳን ጀምሮ ሲሰራ የነበረው ሐረግ የሚባል የተለያዩ ቅርጾች ተሰናስለው በነጠላ ወይም ተዋሕደው በቋሚ ወይም በአግዳሚ የሚሳለው ነው፡፡ እነዚህ ሥዕላት የሚሳሉት የመስቀል፣ የአበባ፣ የሮማን፣ የሐረግ ዛፍ፣ የቅዱሳን መላእክት፣ የነጥቦች፣ የዘንባባ ቅጠል ወዘተ ሆነው በግልጽ ወይም በስውር በውሕደት የሚሠሩ ናቸው፡፡ ሐረግን ለመጀመሪያ ጊዜ መጠቀሙ የሚነገርለት ጠቢቡ ሰሎሞን ነው፡፡ /2ኛ ዜና. መዋ÷3 በሙሉ ተመልከት/፡፡ እነዚህ ሥዕላት አንዱን ሥዕል ከሌላው ለመክፈል፣ የሥዕላቱን ክብር ለማጉላት፣በመጽሐፍ በቀን፣ በዕለት፣ በሰዓት እንዲሁም በምእራፍ፣ በአርእስት ወዘተ ለመክፈል ያገለግላሉ፡፡ በብራና መጻሕፍት ላይ በብዛት እንመለከታል፡፡

 ይቀጥላል…

No comments:

Post a Comment