
ማስመሰል ለምን ያገለግላል?
ሰዎች ማስመሰልን ለበርካታ ነገሮች ይጠቀሙበታል፡፡ ለተቀደሰ ዓላማ ማስመሰልን የተጠቀመው ቅዱስ ጳውሎስ ነው፡፡ ያላመኑትን ለማሳመን፣ ያልተጠመቁትን ለማስጠመቅ፣ ያልተማሩትን ለማስተማር ቅዱስ ጳውሎስ ሳይታመም የታመመ መስሎ ከታመሙት ጋር አብሮ ተኝቶ ብዙ ሰዎችን ወደ እግዚአብሔር ቤት መልሷል፡፡ አብዛኞቻችን ግን ማስመሰልን የምንጠቀመው ለኃጢአት ሥራ ብቻ ነው፡፡ ከላይ ከአገሪቱ መሪ እስከታች ተራው ሰው ድረስ ማስመሰልን የምንጠቀመው የምንፈልገውን ነገር ለማግኘት ብቻ ነው፡፡ በቅርበት የማያዩን ሰዎች እውነት እንደሆነ እንዲረዱን ስንሻ ማስመሰልን አማራጭ እናደርጋለን፡፡ ልማትን በማስመሰል፣ ምርጫን በማስመሰል፣ መንገድን በማስመሰል፣ ባቡርን በማስመሰል፣ ግድብን በማስመሰል፣ ትምህርትን በማስመሰል፣ ጤናን በማስመሰል አረ ስንቱን ብቻ ሁሉንም በማስመሰል የውጭ ብድር እና እርዳታ ማግኘትን የሚሻ መንግሥት አለ፡፡ ለምን ማስመሰልን መፍትሄው አደረገ? ካልን መልሱ ግልጽ ነው፡፡ ለታይታ በማስመሰል የውጭ መንግስታትን ድጋፍ ለማግኘት ስለሚፈልግ ነው፡፡ እነዚያ ረጅ ድርጅቶች የሚመለከቱት በወረቀት የሰፈረውን እንጅ መሬት ላይ ያለውን ነባራዊ እውነታ አይደለም፡፡ ጸሎት ምን እንደሆነ የማያውቅ የኔቢጤ የሚፈልገውን ለማግኘት ሲል በማስመሰል ለምድ ተደብቆ ትልቁን የጸሎት መጽሐፍ ይዞ ቤተክርስቲያን ይሄዳል፡፡ የሚፈልገውን በዚህ መልኩ ማግኘት የለመደ ሰው ሁሌም ሲያስመስል እንጅ ሲሆን አናየውም፡፡ በለምድ ውስጥ ተደብቆ የራሱን የተደበቀ ሥራ ብቻ የሚሠራ ሰው ሁሌም አስመሳይ ነው፡፡
ሌላው ማስመሰልን ተከታይ ወይም ደጋፊ ለማፍራት የሚጠቀሙበትም አሉ፡፡ በመንፈሳዊውም ሆነ በዓለማዊው ማስመሰልን ለዚህ ዓላማ የሚጠቀሙ ድርጅቶች አሉ፡፡ ተሐድሶ መናፍቃን የቤተክርስቲያን ልጆች ሳይሆኑ እንደሆኑ አስመስለው የእግር ኳስ ደጋፊ የሚመስል “ክርስቲያን” ያፈራሉ፡፡ ሳይማሩ በማእረግ ስሞች ውስጥ ተደብቀው “ዲያቆን፣ መምህር፣ መጋቢ ሐዲስ …” በሚለው የማጭበርበሪያ ስልት ተጠቅመው ወገኖቻችንን ለመናፍቃን አዳራሽ ያዘጋጁ በርካታዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ነቅተን ራሳችንን፣ አገራችንን፣ ቤተክርስቲያናችንን፣ ወገናችንን ልንጠብቅ ያስፈልጋል፡፡ በማስመሰል ሥራ የተሰማራን ካለንም ከዚህ ድርጊታችን ልንቆጠብ ይገባናል፡፡
መልካሙ በየነ (ወልደ ማርያም)
No comments:
Post a Comment