Monday, September 26, 2016

“ደርሰናል!”

© መልካሙ በየነ

መስከረም 16/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
=============================================

==============================================
እንኳን ለአዲሱ ዓመት በሰላም እና በአንድነት አደረሳችሁ! ይህን የምለው ግን ለ2009 ዓ.ም ማለቴ ለአዲሱ ዓመት የመጀመሪያየ ጽሑፍ ስለሆነ ነው እንጅ አዲሱ ዓመት ከገባ በጣም ቆይቷል እናም እንኳን አደረሳችሁ ለማለት በጣም ዘግይቻለሁ፡፡ የሆነው ሆኖ ግን አምላክ በወደደው እና በፈቀደው መጠን ደርሰናል፡፡ ለነገሩ ችግሩ ያለ ከእኔ ጋር ነው፡፡ እንኳን አደረሳችሁ የምንባባለው በዓላትን ጠብቀን ብቻ ነው እንዴ? አረ አይደለም፡፡ ብቻ ግን ልማድ የሆነብን ይመስለኛል፡፡ እንኳን አደረሳችሁ የምንባባለው በዓላትን ጠብቀን ብቻ ነው፡፡ በእርግጥ በርካታ ትውስታዎች  ያሉ በበዓላት ወቅት ስለሆነ እንኳን አደረሳችሁ መባባል ልማድ ቢሆንብንም አይገርምም፡፡ ግን እንጅ በዓል ባልሆኑባቸው ቀናትስ ለምን እንኳን አደረሳችሁ አንባባልም፡፡ በበዓላት ቀን ለመድረስ እኮ በዓላት ያልሆኑ ቀናትን ማለፍ ግድ ነው፡፡ ስለዚህ እንደእኔ በእነዚያ ቀናትም እንኳን አደረሳችሁ ብንባባል መልካም ነው እላለሁ፡፡ ለዚያም ነው አንኳን አደረሳችሁ የምላችሁ፡፡ ዛሬ ላይ መድረስ ቀላል አይደለም ምክንያቱም ለዚህ የደረስነው በራሳችን ፈቃድ ስላልሆነ ነው፡፡
የሆነው ሆኖ ግን ደርሰናል፡፡ ለዛሬም ደርሰናል ነገም እንደርስ ይሆናል የአምላክ ፈቃድ ነው፡፡ ግን የመድረሳችን ትርጉሙ ምን እንደሆነ መረዳት ያስፈልገናል፡፡ አምላክ ለዚህ ቀን ሲያደርሰን ምክንያት አለው እኛ ለዚህ ቀን ስንደርስ ግን ምክንያት የለንም፡፡ ስለዚህ ትልቁ ነገር መድረሱ ሳይሆን የደረስንበትን ምክንያት ማወቅ ነው፡፡ ባለፈው ኃጢአትን አደረግን፣ ባለፈው ሰውን ገደልን፣ ባለፈው ሰውን አማን፣ ባለፈው የሰው ንብረት ሰረቅን፣ ባለፈው በዝሙት ወደቅን ግን ዘንድሮ ደረስን ለምን? ትልቁ ጥያቄ ይኼ ነው፡፡ መድረስማ ደረስን እኮ ግን ምን ቀሪ ሥራ ቢኖረን ነው ለዚህ ቀን የደረስነው የሚለውን መመለስ ተገቢ ነው፡፡ መድረሳችንን ለመልካም ምኞት መግለጫ ብቻ አድርገነው ከቀረን ዋጋ የለንም፡፡ ቸርነቱ ለዚህ ካደረሰን ቸርነቱን ለኃጢአት ሳይሆን ለጽድቅ፣ ለክፉ ሳይሆን ለበጎ ልንጠቀምበት ይገባል፡፡ አምና በነበርንበት ኃጢአት ሳለን እንኳን አደረሳችሁ መባባላችን እንኳን ለኃጢአት አደረሳችሁ ማለታችን እንደሆነ መረሳት የለበትም፡፡ ስለዚህ ለዚህ ቀን መድረሳችንን ለምን እንጠቀመው የሚለውን መመለስ ትልቅነት ነው፡፡ ይህ በሁሉም ዘንድ ይስተዋላል አዲስ ዘመን ሲመጣ አዲስ እቅድ ይዘጋጃል፡፡ አንዳንዱ ለጽድቁ አንዳንዱም ለኃጢአቱ ፤ አንዳንዱ ለሕይወቱ አንዳንዱም ለሞቱ ያቅዳል፡፡ ግን የዚህ ዕቅድ ተግባራዊነት መመዘኛ የለውም፡፡ ደስ ሲለን ለሚቀጥለው ዓመት ልናሸጋግረው መብቱ የራሳችን ስለሆነ ቸል ማለት እናበዛለን፡፡
በቃ አሁን ምንም ጥርጥር የለውም 2009 ዓ.ም ላይ ደርሰናል፡፡ ስለዚህ ነገን ስለመኖራችን ባናውቅም በዚህ ዓመት ምን ልናደርግ አቅደናል? ለሕይወታችን ወይስ ለሞታችን? ለጽድቃችን ወይስ ለኃጢአታችን? ለመጾም ወይስ ለመብላት? ለመዘመር ወይስ ለመዝፈን? ለመቀደስ ወይስ ለመርከስ? ለመነሣት ወይስ ለመውደቅ? ለንስሐ ወይስ ለበደል? ብቻ የራሳችን እቅድ ስለሆነ ራሳችን ብቻ ነን መፈተሸ የምንችለው፡፡ ሁላችሁም እቅዳችሁን ፈትሹት እስኪ ለሕይወት ይጠቅማል? ከጠቀመ ቀጥሉበት ካልጠቀመ ደግሞ ሰርዙት፡፡ ምክንያቱም ለሞት ማቀድ ሳያስፈልግ መሞት ስለሚቻል፡፡ ንስሐ መግባት እንጅ ኃጢአት መሥራት እኮ አይከብድም፡፡ በሕይወት መኖር እንጅ መሞት እኮ ቀላል ነው፡፡ ስለዚህ በጎ እቅድ አቅደን ራሳችንን በሕይወት ማኖር ይገባናል፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ፈቃደ እግዚአብሔርን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡
አምላከ ቅዱሳን በሕይወት እንድንኖር ይርዳን!!!

No comments:

Post a Comment