Wednesday, September 7, 2016

“የወላጅ ቁንጥጫ ረሃብን አያጠፋም”

ጳጉሜን 2/ 2008 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

=======================
በመጀመሪያ ይህንን ገጽ ላይክ ያድርጉ facebook.com/beyenemlkm 
=======================

አንድ ነገር አሰብኩ፤ ያሰብኩትንም እንዲህ ጻፍኩት፡፡ ልጆች ሲርባቸው፣ ሲበርዳቸው፣ ሲታመሙ ወዘተ ያለቅሳሉ፡፡ የሚያለቅሱበትን ምክንያት በአግባቡ መለየት የወላጆች ድርሻ ነው፡፡ የሕጻንኛን ቋንቋ በሚገባ ያልተረዳ ወላጅ በማይመክርና በማያስተምር እንዲሁም በማይገስጽ መልኩ ልጆቹን ይቀጣል፡፡ ልጆቹም ለጥቂት ጊዜ ከማልቀሳቸው ዝም ይላሉ፡፡ ከማልቀሳቸው ዝም ስላሉለት ብቻ ግን ለልጆቹና ለራሱ ሰላም የፈጠረ የመሰለው ወላጅ ጅል ነው፡፡ ምክንያቱም ልጆቹ ከማልቀሳቸው ዝም ያሉ ችግራቸው ስለተፈታላቸው ወይም ጥያቄያቸው ስለተመለሰላቸው ሳይሆን ስለቆነጠጣቸው እና ስላስፈራራቸው እንደሆነ አልተረዳም ማለት ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ወላጅ የወላጅነት ድርሻው ለስሙ አባት ወይም እናት ለመባል ብቻ ነው፡፡
ራበኝ አብላኝ ጠማኝ አጠጣኝ እያለ ረሃብ ጎድቶት የሚያለቅስብንን ህጻን እንደወላጅነታችን ማብላትና ማጠጣት ካልቻልን ያልቻልንበትን ምክንያት ማስረዳት ይጠበቅብናል እንጅ ቆንጥጠን ዝም ማስባል አይገባንም፡፡ ልጆቹ እኮ ያለቀሱብን ስለራባቸው እና ስለጠማቸው ነው፤ ታዲያ የእኛ ቁንጥጫ እና ኩርኩም ረሃብን የሚያስታግስ ይመስል ለምን ቁንጥጫና ኩርኩሙ አስፈለገ? በተገቢው መልኩ ልጆቻችን ያለቀሱበትን መረዳትና ተገቢውን መልስ መስጠት የወላጅነት ድርሻችን ነው፡፡ እንደወላጅነታችን ተገቢውን መልስ መስጠት ከእኛ የሚጠበቅ ነው፡፡ ለምን አለቀሱብን አትበሉ ሲርባቸው ያለቅሳሉ፣ ሲጠማቸው ያለቅሳሉ፣ ሲበርዳቸው ያለቅሳሉ፣ ግፍ ሲበዛባቸው ያለቅሳሉ፡፡ የወላጅ ቁንጥጫ ደግሞ ረሃብን አያስታግስምና ልጆች ለጊዜው ከማልቀሳቸው ቢቆጠቡም ቆይተው ግን ለቅሷቸውን በአዲስ መልኩ ይጀምሩታል፡፡ ስለዚህ ሁነኛው መፍትሔ የወላጅነትን ምግባር ተላብሶ የልጆችን እንባ ማበስ  ነው፡፡ ምክንያቱም የልጆች ጥያቄ ረሃብና ጥማት በዛብን የሚል እንጅ ማልቀስ አይደለም፡፡ ወላጆችም እንዳያለቅሱባቸው ከመደብደብ ባለፈ ለምን እንዳለቀሱባቸው መረዳት አይፈልጉም፡፡ ይህ ደግሞ ዘላቂ መፍትሔ የሚሆንበት አንዳች ነገር የለውም፡፡
በርካቶቻችን መፍትሔ የምንሰጠው ለችግሩ ሳይሆን ችግሩ ለወለደው ሌላ ችግር ነው፡፡ ጎርፍ ቤታችን ውስጥ ሲገባ የገባውን ውኃ ወደ ውጭ እየረጨን መጨረስ መፍትሔ እናደርጋለን፡፡ ከዚያም በጎርፉ የተበላሹ ዕቃዎቻችንን ፀሐይ ላይ በማስጣት ማድረቅ እንጀምራለን፡፡  ነገር ግን ይህ ሁሉ መፍትሔ ሊሆን አይችልም፡፡ ምክንያቱም ነገ ጎርፉ ቤታችን ላለመግባቱ ምንም ዋስትና የለንምና፡፡ ስለዚህ ዘላቂ የሚሆነው መፍትሔ የጎርፉን አቅጣጫ ማስቀየር አልያም ቤትን ማስተካከል ብቻ ነው፡፡
በሀገራችን እየሆነ ያለውም እንደዚሁ ያለ ነው፡፡ ሰልፍ እንዳይወጡ በማስፈራራት ወይም የወጡትን በመደብደብ የህግ የበላይነትን አስከብረናል ሰላምንም አስፍነናል ማለት ያስቸግራል፡፡ ህዝቡ ሰልፍ እንዳይወጣ ማድረግ ወይም የተሰለፈውን መበተን በምንም መልኩ ዘላቂ መፍትሔ ሊሆን አይችልም፡፡ ችግሩ እኮ ሰልፍ መውጣታቸው አይደለም ሰልፍ እንዲወጡ ያደረጋቸው ጉዳይ እንጅ፡፡ ሰልፍ እንዲወጡ ያደረጋቸው ምክንያት ሰልፉ ቢበተንም አብሮ አይበተንም፡፡ የተሰለፈውን ሰው ብናስፈራራው እና ብንገድለውም ሰልፉን ሊበትነው የሰውን ቁጥር ሊቀንሰው ይችላል እንጅ ችግሩን ሊፈታው አይችልም፡፡ ስለዚህ መፍትሔ ሊሆን የሚችለውን ነገር እንደተማረ፣ ለሀገር እንደሚያስብ፣ ለወገን እንደሚቆረቆር ሰው ሆነን በጋራ ልንፈታው ያስፈልጋል፡፡ ህጻናት ተርበው ሲያለቅሱ በወላጅ ቁንጥጫ ለጊዜው ዝም ቢሉም ረሃቡ ሲጸናባቸው ቁንጥጫውን ከምንም ሳይቆጥሩ አብልጠው እንደሚያለቅሱ ሁሉ ችግሩ ካልተፈታለት ይህ ህዝብም ሞትን ሳይሰቀቅ ወደፊት ማለቱ አይቀርም፡፡ ስለዚህ የወገኖቻችን ደም ሳይፈስ ዘላቂ መፍትሔ የሚፈለግበትን መንገድ መፈለግ ይገባናል፡፡

No comments:

Post a Comment