Friday, September 9, 2016

“ዘመን ለዘመናት”

ጳጉሜን 4/ 2008 ዓ.ም

ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ 
=============================================
በመጀመሪያ ይህንን ገጽ ላይክ ያድርጉ facebook.com/beyenemlkm
==============================================

ዓለም ከተፈጠረችበት ዕለት ጀምሮ ያለውን ያለፈና የሚመጣ ዘመን በተለያዩ የቀን አቆጣጠሮች እንቆጥራለን። ከእነዚህ የዘመንና የቀን አቆጣጠር ስልቶች መካከል አንዱ ያልተበረዘውና ያልተከለሰው የእኛው የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ነው። የእኛ ዘመን አቆጣጠር ዓመትን በ ፲፫ ወር ይከፍላል። ፲፫ ኛዋ ወር ጳጉሜን ትባላለች። ይህች ወር የወርን ቀመር አታከብርም። ፩ ወር ፴ ቀናትን ይይዛል ይህች ጳጉሜን ግን ስትፈልግ ፭ ሲያሻት ደግሞ ፮ ትሆናለች።
ደስ የሚለው ነገር የቤት ኪራይ አይታሰብባትም በእርግጥ ደመወዝም አንቀበልባትም። ባትሰራ ደመወዝህ የሚቆረጥባት ብትሰራ ደግሞ ክፍያ የማታገኝባት ወር ...... ጳጉሜን። የውኃ፣ የመብራት፣ የስልክ ወጭ ግን ከምንጊዜውም በላይ የሚልቅባት ጭማሪ ወይም ትርፍ ወር ናት ……. ጳጉሜን። ይህች ወር መሸጋገሪያ ድልድይ ናት። አሮጌውን ዓመት ሽኝተን አዲሱን ዘመን የምንቀበልባት መሸጋገሪያ ናት። አሮጌው ዘመን ለሚመጣው አዲስ ዘመን ቦታውን ሲለቅ የመልቀቂያ ውሉ  መፈጸሚያና መፈራረሚያ ጳጉሜን ናት።
በባህላችን ዘመን ሲተካ እንኳን አደረሳችሁ እንባባላለን፡፡ እንቁጣጣሽ እየተባባልን መልካም ምኞት እናቀርባለን። አዲስ ዘመን ላይ ብዙ ተስፋ እንጥላለን አዲስ እቅድ እናቅዳለን፣ አዲስ መሠረት እንመሠርታለን። በመንፈሳዊውም ሆነ በሥጋዊው መንገድ እቅድ እናቅዳለን። ዘመኑን መኖር ስንጀምር የተወሰነውን እቅድ እንሰራዋለን፤ የተወሰነውን እንረሳዋለን፤ የተወሰነውንም ለሚቀጥለው ዓመት እናዞረዋለን። ዘመን ወደፊት አሻግሮ ሲያዩት የሚያልቅ አይመስልም፤ ነገር ግን ባላወቅነውና ባላሰብነው ሰዓት ፀሐይ ይጠልቅብናል ዘመን ያልቅብናል። ዘመን ማለት እንዲህ ነው፡፡ በጣም የሚገርመው ግን ላንተ የተሰጠ ዘመን ለእኔ አልተሰጠኝም ምናልባት ግን የሆነ ዘመን የጋራችን ሊሆን ይችላል። 
እንቁጣጣሽ የሚለውን ቃል እንደመልካም ምኞት መግለጫ የምንጠቀመው ዘመኑን በሚገባ ስለምናውቅና ስለምንረዳ ነው። እንቁጣጣሽ የሚለው ቃል የሁለት ቃላት ጥምርታ ነው የ "እንቊ" እና የ "ጣጣሽ" ማለት ነው። የዘመን መለወጫ ወር መስከረም በእኛ አገር ልዩ ወር ነው። ገደሉ፣ ሜዳው፣ ጋራው፤ ሸንተረሩ ሁሉ በተፈጥሮ አበባ የሚያምርበት የሚያጌጥበት የሚፈካበት ወር ነው። የአበቦች መዓዛ እንኳንስ ንቦችን ዝንቦችንም የሚስብበት ወቅት ነው። ስለዚህ ነው እንግዲህ እንቁ የሚያስብለው። ውኃው የሚጠራበት ጋራው የሚያሸበርቅበት እንቁ የሚሆንበት ነው። በሌላ ጎን ደግሞ መስከረም ማለት የተዘራው የማይደርስበት፣ የጎተራው የሚያልቅበት ወቅት ነው። በዓሉን ደግሞ ለማክበር በጉን ዶሮውን ማረድ ለምደናል። ጎተራችን አልቆ በግ እና ዶሮው  በሌለበት ሁኔታ አዲስ ዘመን ስንቀበል ደግሞ ቅር ያሰኘን ይሆናል። ነገር ግን ካልቻልን ምን ማድረግ እንችላላን? ምንም። በተለይ በዚህ ወቅት ደግሞ ከባድ ፈተና ነው። በጉን ከጓሮ ጎትተን አናቀርበው ነገር የለንም። ስለዚህ ምርጫችን መግዛት ብቻ ነው። ያንን ማድረግ ደግሞ አንችልም። ከዚህ በተጨማሪም ልጆች አዲሱን ዘመን ምክንያት አድርገው ልብስ ጫማ እንዲገዛላቸው ይጠይቃሉ፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ ትምህርት ቤቶች የሚከፈቱበት ወር በመሆኑ ደብተር እስክብሪቶ እርሳስ ይፈልጋሉ። አቤት የዘመን መለወጭ ጣጣ! እውነትም ጣጣሽ ብንላት ሲያሳት እንጅ አይበዛባትም። ለዚህ ነው እንግዲህ " እንቁጣጣሽ " የምንባባለው። 
ዘንድሮ ደግሞ ማለቴ አዲሱ ዓመት 2009 ዓ.ም ለሀገራችን የደስታ የዘመን መለወጫ አልሆነልንም የሀዘን ሆነብን እንጅ፡፡ ወገኖቻችን በግፍ ደማቸው ፈስሷል፣ ወንድሞቻችን፣ እህቶቻችን ያለርኅራኄ በጭቃኔ ተገድለዋል፡፡ በዚህም አንገታችንን ደፍተናል፡፡ እንደእኔ ከሆናችሁ የዘንድሮው የዘመን መለወጫ በዓል ምንም አልመስልህ ብሎኛል፡፡ በዓል በዓልም አልሸተተኝም ውስጤ በዓሉን ለመቀበል ደስተኛ አይደለም፡፡ ብቻ ግን ዘመናትን የሚያቀዳጅ ፈጣሪ ይህንን ዘመን አሳልፎ መጭውን ዘመን እንድቀበል በሕይወት ስላኖረኝ አመሰግነዋለሁ፡፡
አዲሱን ዓመት የንስሐ፣ የፍቅር፣ የአንድነት፣ የመልካም ነገር፤ የሰላም፣ የመረጋጋት፣ የመደማመጥ፣ የመተሳሰብ፣ ያድርግልን። ከዘመነ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ማቴዎስ በሰላም ያሸጋግረን።
አሜን፡፡

No comments:

Post a Comment