©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

ተራሮችን በአበቦች የሚያስጌጥ አምላክ አኔንም አበባ አደረገኝ፡፡ እንዲያውም ሰው የሆኑ ሰዎችን
ለማስተማር ጌታችን ተጠቅሞብኛል፡፡ “ስለ ልብስስ ስለምን ትጨነቃላችሁ የሜዳ አበቦች እንዴት እንዲያድጉ ልብ አድርጋችሁ ተመልከቱ፡፡
አይደክሙም አይፈትሉም ነገር ግን እላችኋለሁ ሰሎሞንስ እንኳ በክብሩ ሁሉ ከእነዚህ እንደ አንዱ አልለበሰም” ማቴ 6÷28-29፡፡
ዛሬ እኔ አበባ ነኝ ለጌጥነት ማንም ሊጠቀምብኝ የሚችል፡፡ በጌጥነቴ እና ውብ በመሆኔ ግን የምማርከው ንቦችን እና ቢራቢሮዎችን
ብቻ አይደለም፤ ማንም ተራ የሚባለውንም ሰው ብቻ አይደለም እኔ የምማርከው ንጉሡንም ጭምር ነው፡፡ ሰሎሞን ንጉሥ ነው ነገር ግን
እኔ ባጌጥኩበት መጠን አላጌጠም እኔም በከበርኩበት መክበር አልከበረም፡፡ ለዛም ነው ሁሉንም ወደ እኔ የመሳብ ችሎታ ያለኝ፡፡ ነገር
ግን አበባ መሆኔ ብቻ አይደለም ለዚህ ክብር ያበቃኝ መልኬ ደም ግባቴ እና ሽታየ ጭምር ነው እንጅ፡፡ ብዙ አበቦች አሉ በተለያየ
ኅብረ መልክ የሚታዩ፤ ብዙ አበቦች አሉ በተለያየ መልኩ ለአፍንጫ የሚሸቱ፡፡ ታዲያ እንደ መልካችንና ሽታችን እንለያያለን፡፡ ሰው
የሚመለከተን አበባ መሆናችንን ብቻ ሊሆን ይችላል ግን የማንሸት አበቦችም እንዳለን ልብ ልትሉ ያስፈልጋል፡፡
“በማለዳም ወደ ከተማ ሲመለስ ተራበ፡፡ በመንገድም አጠገብ በለስ አይቶ ወደ እርሷ መጣ ከቅጠልም
ብቻ በቀር ምንም አላገኘባትም” ማቴ21÷ 18-19 ይች ዛፍ ከእኔ ጋር ተመሳሳይ ታሪክ አላት፡፡ እርሷ ለእይታ በጣም ማራኪ ናት
ለተራበ ሰው ደግሞ እጅግ በጣም ሲበዛ ማራኪ ናት፡፡ ነገር ግን ለጥላነት
ካለሆነ በቀር ለምግብነት የሚሆን ነገር የላትም፡፡ በሩቅ ለሚመለከታት ቀርቦ ላልፈተሸት ግን ፍሬ ያላት ለርኁባን ጥጋብን የምታድል
ትመስላለች፡፡ እኔም ብሆን አበባ መሆኔ እንጅ እንደ እርሷ ነኝ፡፡ ሰው ዛፏን የሚቀርባት የሚበላ ነገር ለመፈለግ ነው እኔን ግን
የሚጠጋኝ በመልኬ አልያም በሽታየ ተማርኮ ነው፡፡ ነገር ግን አልሸትም አለመሽተቴ የሚታወቀው ግን ለቀረበኝ ብቻ ነው፡፡ ብዙ ሰዎችን
አስመርቄያለሁ፣ ብዙ ሰዎችን አጋብቻለሁ፣ የብዙዎችን ቤት አጊጫለሁ ነገር ግን አልሸትም፡፡ ሰዎች ለምረቃ ገዝተው ለስጦታነት ያበረክቱኛል፣
ለቤታቸው ጌጥነት ይጠቀሙብኛል፣ በጋብቻቸው መካከል የፍቅር ማሞቂያነት ይጠቀሙብኛ፡፡ ነገር ግን ለራሴ አበባ አይደለሁም ለሰዎች
ግን ስላላስተዋሉኝ አበባ ነኝ፡፡ አበባ ለመባል ቀለሜ ብቻውን በቂ አልነበረም ሽታየም ተገቢ ነበር ግን ሰዎች አላስተዋሉም፡፡
የእኔ ህይወትም እንደዚህ አበባ ነው ሽታ የሌለው አበባ፡፡ ሰዎች እንደ ትልቅ ሰው የሚቆጥሩኝ፣
የበለሷን ዛፍ የመሰልኩ አለባበሴ ከሩቅ የሚማርክ፣ አነጋገሬ በቅርብ የሚያሳምን፣ ለእይታ ማራኪ፣ ለሚዳስሰኝ እጅግ በጣም ለስላሳ
ቅጠል ያለኝ ነገር ግን ፍሬ አልባ ዛፍ፡፡ ነገር ግን ሽታ አልባ አበባ፡፡ አበባው እኔ ነኝ ሽታው ደግሞ ምግባሬ ነው፡፡ ከጌጥነት
ከቁጥር የዘለለ ጥቅም የማልሰጥ ከንቱ ሽታ አልባ አበባ፡፡ በተፈጥሮ ከሚገኘው መልክና ሽታው ማራኪ ከሆነው አበባ ጋር ተመሳስየ
በሰው እጅ በፋብሪካ የተሰራሁና የተመረትሁ አበባ፡፡ በቃ እኔ ሰው ሰራሽ ሽታ አልባ አበባ ነኝ፡፡
No comments:
Post a Comment