Wednesday, April 13, 2016

መናፍቃንን እንደ ገባዖን ፀሐይ--ክፍል ሦስት

© መልካሙ በየነ
ሚያዝያ 5/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

ባለፉት ክፍሎች ትምህርታችን ላይ መናፍቃንን እንደገባዖን ፀሐይ የሚያቆሙ 12 ያህል የሚሆኑ ነጥቦችን ከመጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎች ጋር ተመልክተናል። በዚህ ክፍል ደግሞ ሌሎች ርእሶችን እንመለከታለን። መልካም ንባብ!!!
v  13ኛ ነጥብ፡- ጾምን በተመለከተ፡፡
·         ጾም አያስፈልግም (አይጠቅምም) ለሚሉ፡- ኢዩ 2÷12 “አሁንስ ይላል እግዚአብሔር በፍጹም ልባችሁ በጾምም በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ” ይላልሳ ጾም ካላስፈለገ ታዲያ እግዚአብሔር ለምን እንዲህ ሊለን ቻለ በሏቸው፡፡
·         በክፉ በሽታ የሚሰቃይ አንድን ህጻን ወደ ደቀመዛሙርቱ አመጡ ነገር ግን ሊፈውሱት አልቻሉም፡፡ ከዛም ኢየሱስ ወደ እኔ አምጡት አላቸውና እርሱ ገሰጸው ጋኔኑም ከብላቴናው ላይ ወጣ፡፡ ከዚያን ሰዓት ጀምሮ ብላቴናው ተፈወሰ ይላል፡፡ ከዚያም ደቀመዛሙርቱ ወደ ኢየሱስ ተጠግተው እኛ ልናወጣው ያልቻልን ስለምን ነው? ብለው ጠየቁት ኢየሱስም ስለእምነታችሁ ማነስ ነው እውነት እላችኋለሁ የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ (ፍጹም እምነት ቢኖራችሁ ማለት ነው) ይህን ተራራ ከዚህ ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል የሚሳናችሁ ነገር የለም ካላቸው በኋላ የጸሎትንና የጾምን ጥቅም ሲያስረዳ በማቴ 17÷21 ላይ “ይህ ዓይነት ግን ከጸሎትና ከጾም በቀር አይወጣም አላቸው” ይላል፡፡ ታዲያ ጾም የማይጠቅም ቢሆን ኖሮ  ለምን እንዲህ ሊላቸው ይችላል በሏቸው፡፡ ይህን ሁሉ የማይሰሙ ከሆኑ ግን በቅዱስ ጳውሎስ ጥቅስ እንገስጻቸውና እንሰነባበታቸው፡፡
·          ጥቅሱ ይህ ነው ፊሊ 3÷19-20 “መጨረሻቸው ጥፋት ነው ሆዳቸው አምላካቸው ነው ክብራቸውም በነውራቸው ነው ዐሳባቸውም ምድራዊ ነው እኛ አገራችን በሰማይ ነውና…” እንበላቸው፡፡
·         ኢየሱስ ጾሞልኛል ለሚሉ፡-ማቴ 26÷20 “በመሸ ጊዜ ከአሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት ጋር በማዕድ ተቀመጠ” ይላልና ኢየሱስ ስለበላልኝ አልበላም ማለት አለባችሁ በሏቸው፡፡
·         ጾም በአዋጅ መሆን የለበትም ለሚሉ፡- በመጀመሪያ ይህንን ጥያቄ ለማቅረብ መጾም ያስፈልጋል፡፡ የማይጾም ሰው በአዋጅ ሆነም፤ ሰው በተመቸው ጊዜ ሆነም ጾም አይመለከተውምና ምንም ጥያቄ ሊያነሣ አይችልም፡፡ ግን ምን ይላሉ መሰላችሁ “እኛም እኮ እንጾማለን! ግን በአዋጅ ከዚህ እስከዚህ ጾም ነው በዚህን ቀን ደግሞ አይጾምም ተብሎ ጾም መታወጅ የለበትም!” ይላሉ፡፡ እሽ ኢዩ 2÷15 ላይ “በጸዮን መለከትን ንፉ ጾምንም ቀድሱ ጉባኤውንም ዐውጁ” ይላልሳ በሏቸው፡፡
v  14ኛ ነጥብ፡- ኢየሱስ ክርስቶስን በተመለከተ፡፡
·         ኢየሱስ አልተሰበከም ለሚሉ፡- ኢየሱስ ማን እንደሆነ ጠንቅቃ የምታስተምር በኢትዮጵያ ብቸኛዋ ቤተክርስቲያን  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ናት፡፡ ይህች ቤተ ክርስቲያን በቅዳሴዋ፣ በማኅሌቷ፣ በሰዓታቷ፣ በምልክእ፣በድርሳኗ፣ በተአምራት መጻሕፍቷ በአጠቃላይ ከጉልላቷ እስከ ታች መሠረቷ ድረስ ኢየሱስን ስትሰብክ የኖረች እየሰበከች ያለች ወደፊትም የምትሰብክ እመቤት ናት፡፡ ተሐድሶ መናፍቃኑም እዚህ ላይ ያነሣሉ “በቤተ ክርስቲያን ኢየሱስን መስበክ መናፍቅ ያስብላል” ይላሉ፡፡ ይህን የሚያስብለው “ኢየሱስ አማላጅ ነው” ብሎ የሰበከ ሰው ከሆነ ብቻ ነው፡፡ ብርጭቆ በተሰበረብን ቁጥር “በኢየሱስ ሥም!” ብሎ መጮኽ ኢየሱስን መስበክ ከመሰላቸው እኛ “በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ሥም” ነው የምንል ልጅ ኢየሱስን ስንጠራ አባቱ አብን እና ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስንም ጨምረን ነው በሏቸው፡፡ እውነተኛውን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስበክ አንደኛዋ፤ የመጀመሪያዋ፤ ግንባር ቀደሟ ቤተ ክርስቲያን የእኛዋ ናት፡፡ ተአምረ ኢየሱስ፤ መልክአ ኢየሱስ፣ መልክአ መድኃኔ ዓለም ስንል የማይቀበሉን ሰዎች ናቸው እኮ ኢየሱስ አልተሰበከም ብለው የሚጮኹት አይገርምም!!!!! መልክአ መድኃኔ ዓለም መጨረሻው ላይ “የቅዱስ አብ አካላዊ ቃል ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ኢየሱስ ሆይ ለአንተ ክብር ምስጋና ይገባል ለዘላለሙ አሜን” ይላል፡፡ እኛስ ጸሎታችንም ስብከታችንም ትምህርታችንም መሠረታችንም ጉልላታችንም ኢየሱስ ነው በሏቸው፡፡
v  15ኛ ነጥብ፡- ስግደትን በተመለከተ፡፡
·         ለእመቤታችን ስግደት አይገባም ለሚሉ፡- እመቤታችን መልእልተ ፍጡራን መትሕተ ፈጣሪ ናት፡፡ እመቤታችን አምላክን በድንግልና ጸንሶ በድንግልና የመውለድ ለማንም ያልተደረገ ልዩ ጸጋ የተሰጣት ናትና የጸጋ ስግደት እንሰግድላታለን፡፡ የምንሰግድላት ግን አምላካችን ብለን ሳይሆን የአምላክ እናት እናታችን ብለን ነው፡፡ መዝ 131÷7 ላይ “ወደ ማደሪያዎቹ እንገባለን እግሮቹ በሚቆሙበት ሥፍራ እንሰግዳለን” ይላል ዳዊት፡፡ እመቤታችን ደግሞ እግሮቹ ከቆሙበት ሥፍራ በላይ በማኅጸኗ ተሸክማዋለችና እንሰግድላታለን በሏቸው፡፡
·         ለመላእክት ስግደት አይገባም ለሚሉ፡- ለቅዱሳን መላእክት የሚሰገደው ስግደት የአክብሮት ስግደት ነው፡፡ ዘፍ 19÷1 ላይ “ሁለቱም መላእክት በመሸ ጊዜ ወደ ሰዶም ገቡ ሎጥም በሰዶም በር ተቀምጦ ነበር፡፡ ሎጥም ባያቸው ጊዜ ሊቀበላቸው ተነሣ ፊቱንም ደፍቶ ወደ ምድር ሰገደ” ይላል ታዲያ እናንተ ከሎጥ ትበልጣላችሁን በሏቸው፡፡
·         ለቅዱሳን ስግደት አይገባም ለሚሉ፡- ለቅዱሳን የሚሰገደው ስግደት የአክብሮት ስግደት ነው፡፡ ዳን 2÷46 ላይ “የዚያን ጊዜም ንጉሡ ናቡከደነጾር በግንባሩ ተደፍቶ ለዳንኤል ሰገደለት” ይላል፡፡ ታዲያ ለቅዱሳን ስግደት ባይገባ ኖሮ ያውም ትእቢተኛ የነበረው ንጉሥ ናቡከደነጾር ለነቢዩ ዳንኤል እንዴት ሊሰግድለት ቻለ በሏቸው፡፡
ሎሎችን በርካታ ነገሮችን ማንሣት ይቻል ነበር ነገር ግን ለዛሬው ለዚህ ክፍል እዚህ ላይ ልፈጽም በቀጣይ ክፍል ሌሎችን በርካታ ነገሮችን በዚሁ አይነት አቀራረብ ይዤላችሁ እመጣለሁ። አምላክ እንዲረዳኝ በጸሎታችሁ አስቡኝ “ወልደ ማርያም” ነኝ፡፡
ይቀጥላል...

No comments:

Post a Comment