Tuesday, July 5, 2016

“ሰውን ሳይሆን መጽሐፍን!”

© መልካሙ በየነ
ሰኔ 28/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

ሰው መጻሕፍትን ሳያነብ በራሱ መንገድ የሚተረጉማቸውና የሚያስተምራቸው ትምህርቶች አሉ፡፡ በተለይ ደግሞ በቤተክርስቲያናችን የማዕረግ እርከኖች ላይ በአንዱ የተቀመጠ ሰው ለእንደዚህ ያለው ችግር ይጋለጣል፡፡ አንድ ጥያቄ ሲመጣ አላውቀውም መጻሕፍትን ልመልከት መምህራንን ልጠይቅ በማለት ፋንታ በድፍረትና በማን አለብኝነት ስሜት እንዲህ ነው እያልን እንመልሳለን፡፡ አላውቀውም እንዳንል የማዕረጋችን ሥም ትልቅ ነው፡፡ ታዲያ ዲያቆን ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ፣ ታዲያ ቀሲስ ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ፣ ታዲያ መምህር ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ፣ ታዲያ ቆሞስ ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ፣ ታዲያ መልአከ ሰላም ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ፣ ታዲያ መልአከ ፀሐይ ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ፣ ታዲያ ቆሞስ ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ፣ ታዲያ ኤጲስ ቆጶስ ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ፣ ታዲያ ጳጳስ ተብየ ይህን ካልመለስኩማ ምን ዋጋ አለኝ ወዘተ እያሉ ስማቸው ከእውቀታቸው ቀድሞ እየመጣ የሚቸገሩ እኔን መሰሎች አሉ፡፡ አለማወቅን ማወቅና አላውቀውም ማለት ትልቅነት ነው፡፡ የሚጠይቀን ሰውም በጠየቀን ጉዳይ ላይ አመኔታ የሚኖረው መጻሕፍትን ጠቅሰን መምህራንን አብነት አድርገን ስንመልስላቸው ነው እንጅ በመሰለኝ የሚመለስ መልስ ጠቀሜታ የለውም፡፡ እኛም መጻሕፍትን የሚጠቁሙን ሰዎችን እንጅ መልስ የሚመልሱልንን ሰዎች አንጠይቅ፡፡ አመኔታ ካለን ብቻ ነው እንዲመልሱልን መጠየቅ ያለብን፡፡ ብዙዎች አሉ መጻሕፍትን ሳይሆን ሰዎችን አብነት አድርገው በድፍረት የሚመሰክሩ፡፡ የሆነ ሰው ሲናገር ከሰሙት ለእነርሱ እውነት ማለት ያ ብቻ ነው፡፡ ያ መሆኑንም እውነትነቱን እና ሐሰትነቱን እንኳ ከመጻሕፍት አናረጋግም፡፡ እዚህ መጽሐፍ ላይ እንዲህ የሚል አለ ሲሉን ዝም ብለን እንቀበላቸዋለን ለምን የጠቀሱልንን መጽሐፍ አንመለከተውም፡፡ ባለፈው ስለ ቅብአት ምንፍቅና በጻፍኳቸው ጽሑፎች ያስተዋልኩት ይህንን ነውው፡ አንዳንድ የቅብአት ምንፍቅና አራማጆች አክሲማሮስ ላይ እንዲህ ይላል መዝገበ ቃላት ላይ እንዲህ ይላል ይላሉ፡፡  ነገር ግን ያ የሚሉት ነገር በጠቀሱት መጽሐፍ ላይ አይገኝም፡፡ አንዳንዴ ይገርመኛል ቢያንስ ስለምንጠቅሰው ጥቅስ እውቅና ሊኖረን ይገባል፡፡ ከዚያ ውጭ በጣም ያስተቻል፡፡ በተለይ በተለይ ጥቅሶች ላይ ጥንቃቄ ልናደርግ ይገባናል፡፡ መጻሕፍትን ሄደን ማየት እና የተጻፈው ነገር እውነት ስለመሆን አለመሆኑ ማረጋገጥ አለብን፡፡ ከዛ ውጭ ከሆነ ግን ሰውን እንጅ መጻሕፍትን አልተከተልንምና ያስነቅፈናል፡፡

No comments:

Post a Comment