Sunday, December 31, 2017

ደብረ ምሕረት የረቦ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን



፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
የረቦ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት በደጀን ወረዳ ቤተክህነት ሥር የሚገኝ ቤተክርስቲያን ነው፡፡ ቤተክርስቲያኑ ከደጀን ከተማ በምሥራቅ አቅጣጫ ሃያ ሰባት ኪሎሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ ወደቦታው ለመሄድ ለሚፈልጉ ሰዎች ከደጀን ከተማ ተነሥተው ጉባያ በሚለው መኪና ገብተው ቦታውን ያለምንም ችግር ማግኘት ይችላሉ፡፡ እንደአሁኑ መኪና ሳይኖር ግን ከሦስት ሰዓት እልህ አስጨራሽ የእግር ጉዞ በኋላ ነበር ቦታው የሚገኘው፡፡ ቦታው ጥንታዊ ቦታ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ሆኖም ግን መዛግብትን ማገላበጥ አባቶችንም መጠየቅ የሚያስፈልገው ጉዳይ ስለሆነ የተመሰረተበትን ቀን እንዴት እንደተመሠረተ ሙሉ ታሪኩን መናገር አልችልም፡፡ እኔም በቦታው ተወልጀ ያደግሁ መሆኑን እንጅ ጥንታዊነቱን ጠይቄም ሆነ መዛግብትን አገላብጨ አላውቅም፡፡ ሆኖም ግን መዛግብትን ማገላበጥ አባቶችን መጠየቅ እንደሚኖርብኝ አውቃለሁ፡፡ ከቤተክርስቲያኑ በታች የሚገኘው ዋሻ ጥንታዊ የቤተክርስቲያኑ መገኛ እንደነበር ይነገራል ሆኖም ግን በመዛግብት እና በአባቶች ማረጋገጫነት መታገዝ ስለሚኖርበት ወደፊት እገልጥላችኋለሁ፡፡



ትናንት ታህሳስ ፲፱ ወደቦታው ሄጀ ከቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል ላይ ተገኝቼ ከበረከቱ ለመሳተፍ ችያለሁ፡፡ በተለያዩ የጉዞ ላይ ችግሮች የእኔም ስንፍና ተጨምሮበት ታቦቱ ወደ ማደሪያው ሲመለስ ነበር የደረስሁት፡፡ በሊቃውንቱ ወረብ በሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች መዝሙር በእናቶች እልልታ በወጣቶች ሆታ በድምቀት ነበር ወደማደሪያው ሲመለስ የደረስን፡፡ ቦታው ንጹህ የተዋሕዶ ክርስቲያኖች የሚኖሩበት ልዩ ቦታ ነው፡፡ በሃይማኖት ድርድር አያውቁም፡፡ ብዙ ሊቃውንት አሉበት ብዙ አባቶች አሉበት፡፡ በተለይም የቀበሌዋ ስያሜ “ሐገረ ሰላም” የሚለው ስም ታሪካዊ አመጣጡ በብዙ ድርሳናት የተገለጠ ነው፡፡ በዚሁ ቦታ በጣም ጥንታዊ እንደሆነ የሚነገርለት “ሀገረ ሰላም ጊዮርጊስ” ቤተክርስቲያን የሚገኝ መሆኑ ከዚህ ትንሽ ራቅ ብሎ “ተዝካረ ማርያም” ቤተክርስቲያን የምትገኝ መሆኑ ከዚሁ አካባቢም አንድ ቅዱስ አባት ዲማ ገዳምን ያስተዳድሩ እንደነበርና ዲማ በሚገኘው የብራና ስንክሳር ላይ በስማቸው አርኬ ተደርሶላቸው ስንክሳሩ ላይ ስማቸው እንደተጻፈ ይታወቃል፡፡ አስቀድሜ እንደተናገርሁት ወደፊት ሙሉ ታሪኩን በመጠየቅ እና መዛግብትን በማገላበጥ እንደምጽፍ ቃል እገባለሁ፡፡

ወደ ቀደመ ነገሬ ልመለስና በጉባያ አካባቢ ከሚገኙ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዱ ደብረ ምሕረት የረቦ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ በየወሩ በቅዱስ ገብርኤል በዓል ላይ ቦታውን ተሳልሞ ቅዳሴውን አስቀድሶ የሚሄደው ሰው ቦታውን የትልቅ ከተማ ቤተክርስቲያን ማስመሰሉ ብዙዎችን ያስገርማል፡፡ ትናንት በተከበረው ክብረ በዓል ላይ በዚህ ቦታ የተገኘው የምእመን ቁጥር በጣም በርካታ ነበር፡፡ ልብ በሉ! እንደካህናት ድካም (አለማስተማር አለመምከር አለመገሰጽ) ይህን አድርጉ ይህን አታድርጉ ብሎ የሚያስተምር ሰው እንደመጥፋቱ መጠን በራሱ ከመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከብረ በዓል ላይ ተገኝቼ በረከቱን እሳተፋለሁ ብሎ የተገኘው ሰው ቁጥር እጅጉን ያስገርማል፡፡

ይህ ቦታ አሁን አዲስ ህንጻ ቤተክርስቲያን በሚያምር ዲዛይን በማሠራት ላይ ይገኛል፡፡ የህንጻውን ዲዛይን የተመለከተ ሁሉ “የየት ከተማ ቤተክርስቲያን ነው” ብሎ መጠየቁ ብዙዎችን ያስገርማቸዋል፡፡ ቦታው ገጠር ቢሆንም አሁን በመሠራት ላይ ያለው ህንጻ ቤተክርስቲያን ግን የአንድ ትልቅ ከተማ ካቴድራል የሚመስል በመሆኑ ለደጀን ከተማ ጌጥ ሆኗል፡፡ የህብረተሰቡ ትጋት ይህን ህንጻ ለመሥራት ያለው ቁርጠኝነት ጉልበቱን ገንዘቡን እውቀቱን ሳይሰስት መለገሱ ሲታይ ለደጀን ብቻ ሳይሆን ለመላው ዓለም አርአያ የሚሆን ተግባር ነው፡፡ ህንጻው ከተጀመረ ሁለት ዓመት አልሞላውም ሆኖም ግን የህንጻው ግማሽ ክፍል ያህል የተጠናቀቀ ይመስላል፡፡ በባለሙያዎች ምልከታ መሠረት ከዐርባ በመቶ በላይ ተሠርቷል ብለዋል፡፡ ትናንትና ለዚህ ህንጻ ማሰሪያ በተደረገው ግንዛቤ ፈጠራ ሥራ ከአስራ ዘጠኝ ሺህ ብር በላይ ተሰብስቧል፡፡ ገጠር ቤተክርስቲያን ላይ በአንድ ሰዓት ቅስቀሳ ይህን ያህል ገንዘብ ሲሰበሰብ ለእኔ የመጀመሪያ ጊዜየ ነው፡፡

ይህ ቦታ ገጠር መሆኑን እና ብዙ ገቢ እንደማያገኝ በዚያ ላይ አዲስ ህንጻ ቤተክርስቲያን እያሠራ መሆኑን የዘነጉት የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች ግን ከአሥር ሺህ ብር በላይ እንዲከፍላቸው ጠይቀዋል፡፡
 
ይህን አዲስ ጅምር ህንጻ ቤተክርስቲያን ሠርቶ ለማጠናቀቅ የሁሉም ክርስቲያኖች ድጋፍ ያስፈልጋል፡፡ በጸሎት፣ በጉልበት፣ በገንዘብ፣ በእውቀት ሁሉም ሊረዳ ይገባዋል፡፡ ከመልአኩ በረከት ለመሳተፍ የሚፈልግ ሁሉ እግዚአብሔር እንዲባርከው የሚፈልግ ሁሉ ሊሳተፍ ይገባዋል፡፡ በተለይ ደግሞ #የደጀን_ተወላጆች ይህ ጉዳይ ይመለከታችኋል፡፡ ከደጀንም በተለይ #የጉባያ_ልጆች የግድ ይመለከታችኋል፡፡ ጉባያ በመንፈሳዊውም ሆነ በሥጋዊው በኩል ብዙ ሊቃውንት አሏት ስለዚህ የዚህ ህንጻ ጉዳይ ይመለከታችኋል፡፡ ቦታው ላይ ከህንጻ ቤተክርስቲያኑ በተጨማሪ በርካታ ሥራዎችን መሥራት የሚገባን ሆኖ ነው ያገኘሁት፡፡ ስለዚህ ሌሎች ተጨማሪ ሥራዎችንም መሥራት ስለሚኖርብን ድምጻችሁን ልታሰሙ ይገባል፡፡ በሚቀጥለው ዓመት ይህ ህንጻ ቤተክርስቲያን ሙሉ በሙሉ ባይጠናቀቅ እንኳ ሥርዓተ ማኅሌቱ በዚሁ ቦታ እንዲደረግ በርካታ ሥራዎችን እንሠራለን፡፡ 
ለህንጻ ማሠሪያው የተዘጋጀ ሥዕለ ቅዱስ ገብርኤል አለ እርሱን በመግዛት በገንዘብ ደግፉ፡፡ ሌላ ተጨማሪ ሥራ መንፈሳዊ መርሐ ግብሮችን ማዘጋጀትም እንደሚገባ ተረድቻለሁ እርሱንም እንሰራለን፡፡ ይህን ሁሉ ለማድረግ ገንዘብ ያስፈልጋልና እባካችሁ እንነጋገርበት በተለይ በቦታው የተወለዳችሁ የግድ ስለሚመለከታችሁ እንነጋገርበት፡፡በዚሁ አጋጣሚ የዓቢይ ኮሚቴዎችን ስልክ ከታች ካለው ስዕለ ጊዮርጊስ ላይ ስላለ እየደወላችሁ ድጋፋችሁን ግለጡልን፡፡ ስልኬን የምታውቁ የአካባቢው ልጆችም እባካችሁ ደውሉልኝ እናውራበት እንወያይበት፡፡ ይህ ጉዳይ ከእኛ አያልፍም፡፡ ብዙ መሠራት ያለበት ቦታ ነው፡፡ ተኩላው ለምድ ለብሶ ዓለምን እየዞራት ነውና ቀድሞ መዘጋጀቱ ተገቢ ነው፡፡
፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍
© መልካሙ በየነ
ታህሳስ ፳ / ፳፻፲ ዓ.ም
የረቦ ደጀን፣ ኢትዮጵያ
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍

No comments:

Post a Comment