Tuesday, December 15, 2015

‹‹ለሃሜት አሳልፈው ሰጡን›› (ክፍል 1)

© በመልካሙ በየነ
ታህሳስ 1/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ትምህርታችንን በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 24 እንጀምራለን፡፡ “ወይእተ ዕለተ እንተ የሐውሩ ፪ቱ እምውስቴቶሙ ሀገረ እንተ ትርኅቅ እምኢየሩሳሌም  መጠነ ፷ ምዕራፍ እንተ ስማ ኤማሑስ”   በዚያን ቀን ከርሳቸው ሁለቱ ከኢየሩሳሌም ስሳ ምዕራፍ ያህል የሚርቅ ኤማሑስ ወደምትባል አገር ሲሄዱ (ሁለቱ የተባሉት ሉቃስና ቀለዮጳ ናቸው ሉቃስን ዘውእቱ  ቀለዮጳ ይለዋል ብሎ ሉቃስና  ኒቆዲሞስ ናቸው ይላል) “ወይትናገሩ በበይናቲሆሙ በእንተ ኩሉ ዘኮነ”  ስለተደረገው ነገር ሁሉ ሲጫወቱ “ወእንዘ እሙንቱ ይትናገሩ ወይትኃሠሥዎ ለዝንቱ” ይህን ሲነጋገሩ ሲመራመሩ “ቀርቦሙ እግዚእ ኢየሱስ ወሖረ ምስሌሆሙ” ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቀርቦ ከርሳቸው ጋራ ሄደ፡፡ “ወተእኅዘ አዕይንቲሆሙ ከመ ኢያእምርዎ” እንዳያውቁት ዓይናቸው ከእውቀት ተገታ “ወይቤሎሙ እግዚእነ ምንትኑ ዝንቱ ነገር ዘትትናገሩ በበይናቲክሙ እንዘ ተሐውሩ ትኩዛኒክሙ” እያዘናችሁ ስትሄዱ እርስ በርሳችሁ የምትነጋገሩት ይህ ነገር ምንድን ነው አላቸው፡፡ “ወአውስአ ፩ዱ እምኔሆሙ ዘስሙ ቀለዮጳ” ከርሳቸው አንዱ ቀለዮጳ የሚባለው መለሰ “ወይቤሎ አንተኑ ባሕቲትከ ነግድ ዘኢሀለውከ በኢየሩሳሌም” አንተ ብቻህን በኢየሩሳሌም አልነበርህምን? “ወኢያእመርከኑ ዘኮነ በውስቴታ በዝንቱ መዋእል” በዚህ ወራት በርሷ የተደረገውን አላወቅህምን አለው፡፡ “ወይቤሎሙ እግዚእ ኢየሱስ ምንትኑ ውእቱ” ጌታም ምንድን ነው አለው፡፡ “ወይቤልዎ በእንተ ኢየሱስ ናዝራዊ” የናዝሬቱን የኢየሱስን ነገር ይነግሩት ጀመር፡፡ “ብእሲ ጻድቅ” ደግ ሰው “ወነቢይ” ዐዋቂ የሆነ “ዘኮነ ከሃሌ በቃሉ ወበምግባሩ በቅድመ እግዚአብሔር ወበቅድመ ሰብእ” በተናገረው ነገር በሚሠራው ሥራ በእግዚአብሔር ዘንድ በሰውም ዘንድ ማድረግ የሚቻለው “ወዘከመ አግብእዎ ሊቃነ ካህናት ወመኳንንቲነ” የካህናት አለቆችና አለቆቻችን አሳልፈው እንደሰጡት “ወሰቀልዎ” ሰቀሉት  “ወንሕነሰ ነአምን ቦቱ ከመ ውእቱ ሀለዎ ያድኅኖሙ ለእስራኤል” እኛ ግን እርሱ እስራኤልን ያድናቸው ዘንድ እንዳለው እናምናለን፡፡ /ሉቃ 24 13-21/
የኤማሑስ መንገደኞች ሉቃስና ኒቆዲሞስ እየተነጋገሩ ይሄዱ የነበረው ስለኢየሱስ ክርስቶስ በአይሁድ ያለበደሉ፣ ያለኃጢአቱ ለሰው ፍቅር ሲል ለመስቀል ሞት ተላልፎ መሰጠት ስለነበር ኢየሱስ ክርስቶስ ከእነርሱ ጋር አብሮ መጓዝ ጀመረ፡፡ በጉዞው መካከልም ስለምን እንደሚነጋገሩ ጠየቃቸው ፍቅራቸው እጅግ ብዙ ስለነበር ኢየሱስ ክርስቶስ የሚባለውን አምላክ አይሁድ ተመቅኝተው እንዴት እንደገደሉት ነገሩት፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ፣ ደግ፣ ለድሆች የሚራራ፣ ለበሽተኞች መድኃኒት፣ ለተራቡት እውነተኛ ምግብ ለተጠሙት ደግሞ እውነተኛ መጠጥ እንደሆነ እነርሱ በጣም የሚወዱት አምላክነቱን የማይጠራጠሩ እንደሆኑ አስረዱት፡፡ ከማን ጋር እንደሚነጋገሩ ባወቁ ኖሮ ዝቅ ብለው ወድቀው በሰገዱለት ነበር ነገር ግን ማን እንደሆነ ስላላወቁ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስን እንዲያምን ሊያስተምሩት ነበር የሞከሩ፡፡ ምንም እንኳ በኋላ አምላካቸው ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን የሚያውቁ ቢሆኑም ማለት ነው፡፡ እነዚህ የተቀደሱ የኤማሑስ መንገደኞች አይሁዳውያንን ለማማት ያበቃቸው የክርስቶስ ፍቅር ነው (በእርግጥ ይህ ሐሜት አይደለም ምክንያቱም አይሁድ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የሠሩትን እውነተኛ የግፍ ሥራ ስለነበር የሚነጋገሩ) ስለስሙ በሚነጋገሩት ተጓዦች መካከል አምላክ ተገኝቶ ባረካቸው፡፡ ሰውና ሰው ሲገናኝ የሰውን ጥፋት ያቅዳል፣የሌላውን ውድቀት ይመኛል፣ ሰውን እንዴት ማጥፋት እንደሚቻል ይወያያል፣ ሰውን በሌለበት በተሳለ ምላስ በሐሜት ይበላል እንጅ በእውነት የክርስቶስ ፍቅር፣ የእመብርሃን ፍቅር፣ የመላእክት ክብር፣ የቤተክርስቲያን ጉዳይ አገብሮት አንዳች ነገር የሚተነፍስ የሚነጋገር ሰው ከቶ የለም፡፡ እኔ በመኪናም ይሁን በእግሬ ስጓዝ አብረውኝ የሚጓዙ ሰዎችን ንግግር ማዳመጥ ደስ ይለኛል፡፡ ምክንያቱም ስለምማርበትና ሰውም ስለምመክርበት እኔም ስለምመከርበትና ስለምገሰጽበት ነው፡፡ እናም ስጓዝ የሰማሁትን ላካፍላችሁ ወደድሁ መልካም ንባብ…

ይቀጥላል፡፡

No comments:

Post a Comment