Thursday, December 31, 2015

“እመ አምላክ ድንግል ማርያም”

© በመልካሙ በየነ
ታህሳስ 21/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ይህ ቃል ለአፍ ስንጠራው ሊቀለን ይችል ይሆናል እንጅ የእምነታችን ትልቁ ምሥጢር የእምነታችን መሠረት የተመሠረተበት እምነታችን የታነጸበት ዋና ቃል ነው፡፡ ስለ ድንግል ማርያም የሚከራከሩን ሰዎች  ይህን ቃል ብትነግሯቸው ቀላል ተራ ቃል ሊመስላቸው ይችላል ከምንም ሳይቆጥሩም ቃሉን ሊጠሩት ይችላሉ ግን አይደለም፡፡ በእውነት ይህንን ቃል እየጠሩ ምን የሚሉት ክህደት ነው? እስኪ ሰው ሆነን እናስበውማ በጣም የረቀቀ ምሥጢርን ያዘለ ቃል እኮ ነው፡፡ በእውነት በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ላይ የሚሸፍት ልብ ምን አይነት ልብ ነው? ስለ እናታችን አማላጅነት ለመከራከር እኮ ይህን ቃል ግዴታ መጥራት አለብን፡፡ ይህን ቃል ከጠራነው ደግሞ ትርጉሙን መገንዘብ ያስፈልገናል፡፡ እስኪ በእውነት አስቡትማ ቢያንስ አሁን  ለደቂቃዎች ሰው እንሁንና አስተውለን እንረዳ “እመ አምላክ ወላዲተ አምላክ” ይህ ቃል ስለእውነት ገብቶን የምንጠራው ስንቶቻችን ነን? የሁለት ተቃራኒ ቃላት ጥምርታ እኮ ነው፡፡ “እመ አምላክ” የአምላክ እናት ማለት ነው “ድንግል ማርያም” ማለት ደግሞ ምንም ወንድ የማታውቅ ሴት ማለት ነው፡፡ “እመ አምላክ ድንግል ማርያም” ስንል ወንድን የማታውቅ በድንግልና በንጽሕና አምላክን ለመውለድ የበቃች አምላክን የወለደች እናት ማለት ነው፡፡ እንግዲህ እስኪ ሴቶች አስቡት እናት ተብሎ ድንግል ይባላልን? ድንግል ሆኖ ባለልጅ መሆንስ ይቻላልን? አይቻልም፡፡ ምንም ይሁን ምን ድንግል የሆነች ሴት ልጅ ልትወልድ አትችልም፤ በተመሳሳይ ልጅ የወለደች ሴትም ድንግል ልትባል አትችልም፡፡ ድንግል ማርያም ግን ድንግል ወእም ስትባል ለዘለዓለም ትኖራለች፡፡ በእውነት ግን ምን ቃል ይገልጻታል እናታችንን ምን ቃል እንፈጥርላታለን ምን ምሳሌስ እንመስልላታለን፡፡ የማይቻለውን ቻለች የማይወሰነውን ወሰነች ዘመን የማይቆጠርለት መለኮትን ዘመን እንዲቆጠርለት አደረገች፡፡ ሰሎሜ ልታዋልድ ስትቀርብ በቅጽበት እጇ ተቃጠለ ቶማስ የተወጋ ጎኑን እዳስሳለሁ ብሎ እጁን ሲያስጠጋው እጁ እርር ኩምትር አለ እመቤታችን ግን በድንግልና ጸንሳ በድንግላ ስትወልደው እሳተ መለኮቱ አላቃጠላትም ከቶ ለምን ይሆን? እነዚያ ደቂቃ ላልሞላ ጊዜ እጃቸውን ማስጠጋት ያልተቻላቸውን እሷ ግን ታቀፈችው አዘለችው አይገርምም፡፡ አረ ቅዱሳኑም ሊቃውንቱም እመቤታችንን የሚገልጹበት ቃል የላቸውም “በመኑ በአምሳለ መኑ ናስተማስለኪ” ያላት ምስጋና የበዛለት አባ ሕርያቆስ አይደል እንዴ? ታዲያ ምሳሌ ሲያጣላት ቃል ባይገልጽለት ምን ያድርግ? ግርምት ድንግል ማርያም ያልገረመች ማን ይግረም፡፡ በዚያ በኃጢአት ዘመን የቀደመው የአዳም በደል በእናቷና በአባቷ ሳለ እርሷ ግን ያ በደል ሳያገኛት ለድህነታችን የተወለደች የተፈጠረች ንጽሕት ዘር  ናት እናታችን እመብርሃን፡፡ በዚህ እንኳ በሰው ሚዛን በሰው ፍርድ እየነዘንና እየለካን ልንከራከር እንፈልጋለን፡፡ ጥንተ አብሶ አባትና እናቷ ስለነበረባቸው እርሷም አለባት ይላሉ ምስጋና ይግባትና፡፡ በዚህ ዘመን አባትና እናት በሽተኛ ሆነው ልጁም በሽተኛ ሆኖ ይወለዳል ብሎ መከራከር እንዴት ያለ ጭንቅላት ነው?
በእውነት ስሟን ጠርቶ የሚሰለች ማነው? እኔ እኮ እመብርሃንን የማከብራት እመ ብርሃንን የማመሰግናት እመ ብርሃንን የምሰግድላት ከመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ስለማልበልጥ ነው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችንን ሲያበስር ሰግዶ ደስታ ይገባሻል ደስ ይበልሽ ብሎ እኮ ነው፡፡ ታዲያ እርሱ እንዲህ ከሰገደላት እንዲህ ካከበራት እኔ ማን ሆኜ ነው እናቴን ላቃልል የስድብ አፍ የምከፍተው? ስሟን መጥራትስ ይቻለኛል እንዴ እንኳን በእናቴ ላይ ስድብን ልሰነዝር የምደፍረው? እናስተውል ወገኖቼ መናፍቃኑ በሚጠሯት አጠራር አንጠራትም እኛ፡፡ ለእኛ እናታችን ናት ለእኛ መድኃኒታችን ናት ለእኛ ተስፋችን ናት ለእኛ ገነት መግቢያችን ናት ለእኛ መመኪያችን ናት ለእኛ ስንቃችን ናት ለእኛ እረፍታችን ናት ለእኛ መሰላላችን ናት ለእኛ የደስታችን መፍሰሻ የደስታችን መፍለቂያ የደስታችን ምንጭ ናት ለእኛ ብርሃናችን ናት ለእኛ አምላክን የወለደችልን ናት ለእኛ አማላጃችን ናት ለእኛ ሁለመናችን ናት ለእኛ በደማችን ውስጥ ያለች በልባችን ውስጥ የታተመች ናት ለእኛ ፍቅሯ በሁለመናችን የመላች እናታችን ናት፡፡ ይህን የምንለው መናፍቃኑን ለመከራከር መናፍቃኑን ለመቃወም አይደለም እናታችን ከዚህም በላይ ስለሆነችልን  ነው፡፡ እኛ ፍቅሯን ቀምሰነዋል እናትነቷን አውቀነዋል መሸሸጊያነቷን አይተነዋል አማላጅነቷን አምነነዋል ሁሉንም እንደሆነችን ተገንዝበናል ለዚህ ሁሉ ክብር ያበቃንም እመ ብርሃንን ለእናትነት የመረጣት ከሴቶች ሁሉ መርጦ ያከበራት አምላካችን ነው፡፡

በእውነት እስኪ አስቡት ማን ነው ኃጢአት መሥራትን የማያውቅ? ከሰው ወገን ሆኖ በገቢር ባይፈጽም በነቢብ፣ በነቢብም ባይፈጽም በሀልዮ ኃጢአትን የማያደርግ ማነው? በእውነት ማነው ይህን ማድረግ የሚቻለው? ንጽሕናን እንደጠበቁ ምንም ኃጢአትን ሳያደርጉ እስከ ዘለዓለም መጽናት ለማን ተሰጠው? ለማንም አልተሰጠውም እኮ መላእክት እንኳ እንደ እርሷ ንጹሕ አይደሉም፡፡ እመቤታችን ግን ምንም አይነት ኃጢአት ርኩሰት የለባትም በሃሳብሽ ድንግል ነሽ በስጋሽም ድንግል ነሽ የምንላት ለምን መሰላችሁ ሃሳቧ ኃጢአትን ለማሳብ ጊዜ የሌለው ስለነበር እኮ ነው፡፡ እናታችን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እናቴ የማይላት ከቶ ማነው? እርሱ እኮ መዳኑን የማይወድ ተስፋውን የማይሻ መጠጊያውን የማይፈልግ ከለላውን የማያውቅ መከታውን የዘነጋ ምርኩዙን መደገፊያውን የማይወድ ምግብ ስንቁን የሚጠላ ውሉደ አጋንንት ነው፡፡ እንዲያው ሌላውን እንተወውና አምላክን በድንግልና ለመውለድ መመረጧ እንዴት አያስደንቀንም? በድንግልና የሴቶች ልማድ ሳያገኛት በመንፈስ ቅዱስ ጸንሳ መገኘቷ እንዴት አያስደምመንም? ሰው ሆና ሳለች ከኃጢአትና ርኩሰት በሃሳብም በሥጋም ድንግል መሆኗ እንዴት አይገርመንም? መላእክት እንኳ ንጹሕ ባልሆኑበት ዓለም ለብቻዋ ንጽሕት ዘር መሆኗ እንዴት አይደንቀንም? በእውነት ስለእውነት ለስሟ መግለጫ ቃላት እኮ የለንም፡፡ እኛን የሚደንቀን እኮ እንደኛው ሰው ስትሆን እንዲህ ያለውን ንጽሕና ይዛ በመገኘቷ ነው፡፡ እኔ ሰው ነኝ አንተም ሰው ነህ አንችም ሰው ነሽ ማንነታችንን አናውቀውም እንዴ? ለትንሽ ጊዜ እንኳ እስኪ ሰው ሁኑ ያልኳችሁ ለዚህ ነው፡፡ በቅጽበት ውስጥ ምን ያህል ኃጢአትን ነው ስናነሣ ስንጥል የምንውለው? እኛ እንኳን ቆመን ተኝተንስ ኃጢአትን አይደል እንዴ ስንቃዥ የምናድረው እርሷ እንዲህ የሚባል ነገር የለባትም፡፡ ታዲያ እመቤታችን ያልገረመችን ማን ይግረምን? ከመላእክት ወገን ብትሆን እኮ እንዲህም ባልተገረምን ነበር ባልተደነቅንም ነበር ምክንያቱም ባሕርያቸውን ባሕርያችን ስላላደረግን እነርሱ እኮ ከእንደዚህ ባሕርይ ስለተፈጠሩ ነው እንል ነበር እመቤታችን ግን ሰው ናት ለዚያም ነው የደነቀችን የገረመችን፡፡ በእውነት “እመ አምላክ ድንግል ማርያም” የሚለውን ቃል ሳየው ሁልጊዜ አዲስ ነገር አዲስ ትምህርት አዲስ ቃል አዲስ ስብከት ነው ለእኔ፡፡ ዛሬም አዲሴ ነው ነገም እንደዚያው፡፡ ዝም ብሎም እናትና ድንግል ቢል ላይደንቀኝ ይችል ነበር “እመ አምላክ ሲባል ግን እንዴት አይደንቀኝም፡፡ ለሁሉም ነገር ግን አበው ተናግረውት ጽፈውት ያልጨረሱትን የክብሯን ነገር ስጨልፍ ብውል አልጨርሰውምና ዝም ልበል፡፡

No comments:

Post a Comment