Monday, December 28, 2015

ሲድራቅ----ሚሳቅ----አብደናጎ

© በመልካሙ በየነ
ታህሳስ 18/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
በዱራ ሜዳ ላይ ናቡከደነፆር አምላኩን አቆመው፣
በስድሳ ክንድ ቁመት በስድት ክንድ ወርድ ከወርቅ አቅልጦ ሠራው፡፡
አምላኩን ሊያስመርቅ ያልተመረቀ አምላክ መርቁልኝ ብሎ፣
መኳንንት፣ ሹማምንት፣ አዛዥ፣ አዛውንቱን፣ መጋቢውን ሁሉ ጠራቸው በቶሎ፡፡
የንጉሥ ትዕዛዝ ነው ከታች ባትን ከላይም አንገትን ሊያስቆርጥ የሚችል፣
ታዲያ ማን ይቀራል? ማንስ ይንቀዋል? ማን ያቃልለዋል?
ሁሉም ለምረቃው ተሰበሰቡና፣
በተሠራው አምላክ ፊት ለፊት ቆሙና፣
ያደንቁት ጀመሩ ንጉሣቸውን አምላክን የሠራ ስለሆነ ጀግና፣
በሚሠራ አምላክ ሁሉም አምኗልና፡፡
ከዚያማ ! አዋጅ ተናጋሪው እየጮኸ መጣ፣
ትእዛዙን ሊናገር ካልፈጸምን ሊቀጣ፡፡
ወገኖችና አህዛብ በልዩ ልዩ ቋንቋም የምትናገሩ፣
መለከት፣ እንቢልታ፣ መሰንቆ፣ በገና፣ ዋሽንት ክራሩ፣
ዘፈን ግርግሩ፣
እንደተሰማችሁ ንጉሡ ላቆመው ለወርቅ ምስሉ ስግደትን ገብሩ፡፡
ይህን ባታደርጉ በሚነድ እሳት ውስጥ ትጨመራላችሁ፣
ከሰል እስክትሆኑም ትቃጠላላችሁ፡፡
እያለ አስፈራራን እጅግ አስጨነቀን፣
ለጣዖት እንድንሰግድ እያስጠነቀቀን፡፡
ከዚያማ! መለከት፣ እንቢልታ፣ መሰንቆ ክራርን፣
በገና ዘፈንን አዋጅ ተናጋሪው ሁሉንም አሰማን፣
ለጣዖት እንድንሰግድ ፊሽካውን ነፋልን፡፡
ይህን እንደሰሙ አህዛብ በሙሉ፣
በልዩ ልዩ ቋንቋ ተናጋሪው ሁሉ፣
ተደፍተው ሰገዱ ለወርቅ ምስሉ፡፡
ከዚያ ከለዳውያን አይሁድን ከሰሱ፣
ንጉሥ ሽህ ዓመት ንገሥ እያሉ ወደቁ ተነሡ፡፡
መለከት፣ እቢልታ፣ መሰንቆ እና ክራር፣
በገና እና ዘፈን ስንሰማ ልንሰግድም አልነበር?
ታዲያ እነዚህ ሰዎች በባቢሎን ግዛት ሥራ የሾምካቸው፣
ላንተ ለወርቅ ምሥል አንሰግድም እንቢ ማለታቸው፣
ንጉሥ ሺህ ዓመት ንገሥ ችግሩ ምንድን ነው?
እያሉ ከሰሱን እኛም እንድንሰግድ፣
ለወርቅ ምስሉ እንድናጎበድድ፡፡
ናቡከደነፆር ይህን እንደሰማ እጅግ ተበሳጭቶ፣
መልእክተኛ ልኮ ወሰደን ጎትቶ፡፡
ከዚያማ ጮኸብን እጅግ ተቆጥቶ፣
አምላኬን አለማምለካችሁ፣
ላቆምኩትም ምስል አለመስገዳችሁ፣
ከቶ እውነት ከሆነ ንገሩኝ ፈጥናችሁ አለን ተበሳጭቶ፡፡
አሁንም መለከት፣ እንቢልታ፣ መሰንቆ፣ ክራርን፣
በገና ዋሽንትን ዘፈን እንጉርጉሮን፣
በሰማችሁ ጊዜ ድፍት ብላችሁ ገብሩ ስግደትን፣
ይህን ባታደርጉ ተመልከቱ ያንን፣
በዚያ ተጥላችሁ ትቃጠላላችሁ፣
እያለ ጠቆመን የሚነደውን የእሳት እቶንን፡፡
እኛም ተመለከትን ይነዳል እሳቱ፣
ነገር ግን… ከንቱ እንደሆነ የንጉሥ ትምክህቱ
ማሳየት ማስተማር በመፈለጋችን ዝም አልነው በብርቱ፡፡
እርሱም ጀመረ ገባ ያስፈራራን፣
ከእጄ የሚያድናችሁ አምላክ የለም አለን፣
አምላኩ ወርቅ ሆኖ ለወርቅ ሊያሰግደን፡፡
እኛ ግን! እኛስ አምላክ አለን የሚያድን ከምንም፣
ከእጅህ የሚያስመልጥ የሚበልጥ ከሁሉም፡፡
ምንም ንጉሥ ብትሆን ብናከብርህ ቅሉ፣
አንተ ለሠራኸው ለወርቅ ምስሉ፡፡
አንሰግድም በፍጹም እግዚአብሔር እያለን፣
ሰማይና ምድርን አንተንም እኛንም የፈጠረን አምላክ ከላይ ሆኖ እያየን፡፡
የአምላክ ፈቃድ ሆኖ እንኳ ብንቃጠል፣
አንሰግድም በፍጹም ላንተ ለወርቅ ምስል፡፡
ብለን ስንናገር ፊቱ ተለወጠ ናቡከደነፆር፣
የእርሱ የወርቅ ምስል በልጦበት ከእግዚአብሔር፡፡
ቀድሞ ከሚነደው ሰባት እጥፍ ያህል ይቀጣጠል አለ፣
ነበልባል ሲጨምር ይፈራሉ ብሎ ንጉሥ ተታለለ፡፡
እኛ ግን! ከቶ ምንም ቢሆን ምንም ቢመጣብን፣
አንክድም በፍጹም እግዚአብሔር አምላክን፣
መከራ ስቃዩን ችግሩን ካላለፍን፣
መውረስ እንደማንችል መንግሥተ ሰማይን፣
እኛ እናውቀዋለን ከድሮ ጀምረን፣
ነንና ክርስቲያን፣
ስለዚህ በእቶኑ አቃጥሉን አንድዱን፣
አምላክን ከመካድ ሞት እንመርጣለን አልን፣
የንጉሥ ቃል ሆኖ ሁሉም አሽከሮቹ ተጣድፈው መጡና፣
አርባ ዘጠኝ ክንድ ከፍ ከፍ እስከሚል አቀጣጠሉና፡፡
እጃችንን አስረው በዚያ ላይ ጨመሩን፣
ከሰል እስከምንሆን በእሳት ሊያቃጥሉን፡፡
እኛ እኮ አምላክ አለን አምላክ እንደሌለው፣
አናዝንም አናፍርም ከቶም አንቃጠል እግዚአብሔር ከኛ ነው፡፡
ስቡህኒ ውእቱ ወልዑልኒ ውእቱ እንላለን ገና፣
አምላከ አብርሃም ከኛ ጋር ነው፣
እያልን አጨበጨብን እጃችን ተፈታ፣
ምስጋና ይድረሰው ለፈጠረን ጌታ፡፡
እኛ እሳት ውስጥ ወድቀን ምንም ሳንነካ፣
በዳር የነበሩት እኛን የጣሉን ግን ተቃጥለዋል ለካ፡፡
ናቡከደነፆር አሁንስ ደነቀመው፣
አማካሪዎቹን እንደዚህ አላቸው፡፡
ሦስት ሰው አስረን በእሳቱ ውስጥ ጥለን አልነበረምን?
እጃቸው ተፈትቶ አራት ሰዎች ሆነው የሚመላለሱ ይታዩኛል እኔን፣
ማመን አቅቶኛል ዛሬስ ይህን ዓይኔን፡፡
ይህ እንዴት ይሆናል?
 እንዴት ይደረጋል?
አራተኛው ሰው ግን የአማልክት ልጅን በእጅጉ ይመስላል፡፡
እያለ ሲደነቅ ሲገረም ቆየና፣
የልዑል ባሪያዎች ኑ ውጡ! ወደዚህ ቅዱስ ናችሁና፡፡
እሳት ውኃ ሆኖስ ካላቃጠላችሁ፣
እኔም አመልካለሁ እኔም እሰግዳለሁ፣
ከእቶን እሳት ውስጥ ከእጄም ላዳናችሁ፡፡
ከዛሬ ጀምሮ ለሲድራቅ ለሚሳቅ ለአብደናጎ አምላክ፣
እኔም ልወድቅ ልሰግድ ፊቱ ልንበረከክ፣
አምላኬ ጌታዬ ብዬ በእርሱ ብቻ ላመልክ፡፡
ራሴን ሰጠኹኝ እስከመጨረሻ፣
እግዚአብሔር ነውና መነሻ መድረሻ፡፡
ከዛሬ በኋላ በእነዚህ ቅዱሳን ክፉ የሚናገር፣
በአምላካቸውም ላይ የስድብን ነገር ከቶ የሚናገር፡፡
ይቆረጣል  ባቱ፣
ከላይም አንገቱ፡፡
****************************************
እንዲህ ነው እንግዲህ አምላክ የታደገን፣
ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ ከመንደድ ያስጣለን፣
በአህዛብ መካከል ከፍ ከፍ ያረገን፡፡
የአማልክት አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡

(ትንቢተ ዳንኤል ምእራፍ ሦስት በሙሉ ያንብቡ)

No comments:

Post a Comment