Tuesday, December 15, 2015

‹‹ለሃሜት አሳልፈው ሰጡን›› (ክፍል 2)

© በመልካሙ በየነ
ታህሳስ 5/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
…እኔ በመኪናም ይሁን በእግሬ ስጓዝ አብረውኝ የሚጓዙ ሰዎችን ንግግር ማዳመጥ ደስ ይለኛል፡፡ ምክንያቱም ስለምማርበትና ሰውም ስለምመክርበት እኔም ስለምመከርበትና ስለምገሰጽበት ነው፡፡ እናም ስጓዝ የሰማሁትን ላካፍላችሁ ወደድሁ መልካም ንባብ!
በክፍል 1 (http://melkamubeyene.blogspot.com/2015/12/1.html) እንደተመለከትነው የኤማሑስ መንገደኞች አርስ በርሳቸው የሚነጋገሩት ነገር የተቀደሰ በመሆኑ የጉዞ ጉባኤ ብንለው ደስ ይለኛል፡፡ በስሜ ሁለት እና ከዛ በላይ ሆናችሁ ብትሰበሰቡ በዚያ መካከል እኔ እገኛለሁ ያለን አምላክ በእነዚህ በሁለቱ መንገደኞችም መካከል ተገኘ፡፡ የዚያን ጊዜ ወቅታዊው ጉዳይ የክርስቶስ በአይሁድ መገረፍ፣ መደብደብ፣ መሰቀል፣ መሞት፣ መነሣት ነበር እነዚህም የሚነጋገሩበት ጉዳይ ወቅታዊ ስለነበረው ነገር ነበር፡፡ እኔም የሰማኋቸው ሰዎች እንዲሁ በወቅታዊ ጉዳይ ላይ ያነጣጠሩ ናቸው፡፡ አንድ የታወቀ ገዳም አስተዳዳሪ ናቸው ከሆነ ሰው ጋር ሲሄዱ “በ5 ሚሊዮን ብር ዕዳ የተከሰሰ የሃገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ እንዴት ሌላ ሹመት ይሰጠዋል?” ይላሉ፡፡ ያ እሳቸው የሚሉት ሰው ያሉትን ያህል እዳ ይኑርበት አይኑርበት ማን ያውቃል? ሊኖርበት እንደሚችል ሁሉ ላይኖርበትም ይችላል፡፡ ነገር ግን ተበርዘናል የአሁኑ ወቅታዊ ጉዳይ የሆነው ተሐድሶ ከገንዘብ ጋር ንክኪ እየፈጠረ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሰላም እንዳይኖር እየፈጠረ ያለው ችግር ለሃሜት አሳልፎ እንደሰጠን እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ ዝም እንዳንል ዝም የሚያስብል ጉዳይ የለንም እንዳንናገርም ተናጋሪዎች ተሳዳቢዎች ሃሜተኞች ተንኮለኞች ምቀኞች ወዘተ እንባላለን፡፡ ታዲያ ወዴት ልናዘነብል እንችላለን?
ተሐድሶዎቹ ዓላማቸው ብዙ ዕቅዳቸው ረዥም ነው፡፡ በቤተክርስቲያን ውስጥ በቀላሉ ሰርጎ መግባት አይቻልም መጀመሪያ ክፍተታችንን ማዎቅ አለባቸው ያንን ያወቁትንና ያጠኑትን ክፍተት ደግሞ ውሻ በቀደደው.. እንዲሉ ይገቡበታል ምክንያቱም ጅቦች ናቸውና፡፡ ቤተክርስቲያንን ለመቆጣጠር የሰበካ ጉባኤ አባልና ስራ አስፈጻሚ፣ ዲያቆን፣ ሰባኪ፣ ቄስ፣ ዘማሪ፣ ከፍ ብሎም ቆሞስ፣ ኤጲስ ቆጶስ፣ ጳጳስ፣ ሊቀ ጳጳስ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ ለዚህም ነው ዛሬ ላይ በየቦታው በየአጥቢው ብጥብጥ ሲፈጠር የምንመለከተው፡፡ ሁሉም የሰበካ ጉባኤ ጸሐፊ፣ ሰብሳቢ፣ ገ/ያዥ መሆን ይፈልጋል ሁሉም የቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ መሆን ሂሳብ ሹም መሆንን ይሻል፡፡ ሁሉም የአንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያን መሪ አስተዳዳሪ መሆን ይፈልጋል ድሮ አባቶቻችን ይሸሹት የነበረውን ሥልጣንና ሹመት የዛሬዎቹ ደግሞ አብዝተው ይፈልጉታል፡፡ ድሮ ጳጳስ ለመሆን የተመረጠ አባት “አይገባኝም” ብሎ ይሸሽ ነበር የዛሬዎቹ ግን ስለሚገባኝ “ጵጵስና እንድትሾሙኝ” የሚል ማመልከቻም ሳያስገቡ አይቀሩም፡፡ ታዲየ ይሄው  እኛም እኮ ለሃሜት ተላልፈን ተሰጠን አማናቸው አይደል፡፡ ሳይገባቸው እንደተገባቸው አድርገው የሚቀርቡ ሰዎች ለብዙ መከራና ስቃይ እየዳረጉን ነው፡፡ ግዴለሽነትን፣ ምን አገባኝነትን፣ ማን አለብኝነትን አስተማሩን፡፡ በመናፍቁ ዘንድ ያለውን ሥርዓት አልባነት እኛ ውስጥም ጨመሩት፡፡ አሥራትና በኩራቱን ታወጣለህ የሆነ አስተዳዳሪ ነኝ ባይ አልያም ሂሳብ ሹም ነኝ ባዩ የራሱን ፎቅ ይሠራበታል፡፡ አንተም አሥራት ማውጣትህን ታቆማለህ ምክንያቱም ግለሰቦች ናቸዋ እየበለጸጉበት ያለው፡፡ ግን ትክክል ሥራ ሠርቻለሁ ትክክለኛ እርምጃ ወስጃለሁ ብለህ ታምናለህ? በፍጹም አያሳምንም፡፡ አሥራት በኩራት አውጣ ያለህ ፈጣሪ ነው ያወጣኸውን ገንዘብ የወሰደው ደግሞ ሰው ነው ላንተ ዋጋህን የሚከፍልህ ፈጣሪ እንጅ ሰው አይደለም ስለዚህ በሁለት መንታ ሃሳቦች መካከል ይጥሉሃል ማለት ነው፡፡ ከዚያስ ግዴለሽ ትሆናለህ “አሥራት ባወጣ የሚበላው እገሌ” እያልክ ትሸሻለህ፡፡ ታዲያ አንተ ለሃሜት ተላልፈህ አልተሰጠህም?

ሳንወድ በግድ ለሃሜት ተላልፈን እየተሰጠን ነው፡፡ ቤተክርስቲያናችን የምትፈልገው እንደ ኤማሑስ መንገደኞች ያሉ ሰዎችን ነው፡፡ ስለዚህ እንደነርሱ ልንሆን ይገባል፡፡ እነርሱ አይሁድ እንዲህ አድርገው ሰቀሉት እንዲህ አድርገው ገደሉት ካሉ በኋላ መጨረሻ ላይ “ወንሕነሰ ነአምን ቦቱ ከመ ውእቱ ሀለዎ ያድኅኖሙ ለእስራኤል” እኛ ግን እርሱ እስራኤልን ያድናቸው ዘንድ እንዳለው እናምናለን ብለው ነው የራሳቸውን አቋም የገለጹ፡፡ ዛሬ ግን እገሌ እንዲህ አደረገ፣ እገሊት እንዲህ አደረገች ከማለት ባለፈ እኔ ብሆን እንዲህ አደርግ ነበር የሚል የቀና መንፈስ የለንም፡፡ ይልቁንም እነርሱ በሳቱበት እንስታለን በወደቁበትም እንወድቃለን እንጅ፡፡ ስለዚህ ከሁለቱ የኤማሑስ መንገደኞች ከሉቃስና ኒቆዲሞስ ልንማር ያስፈልገናል ማለት ነው፡፡

No comments:

Post a Comment