Friday, December 25, 2015

ዘጠኙስ ወዴት አሉ? (ሉቃ 17÷17)------ክፍል 2

© በመልካሙ በየነ
ታህሳስ 14/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
…እስኪ ወደ መከራው ሰዓት እንሂድ፡፡ ማቴ 26÷20 ላይ እንዲህ ይላል “በመሸም ጊዜ ከዐሥራ ሁለቱ ደቀመዛሙርት ጋር በማእድ ተቀመጠ ይላል፡፡ እንግዲህ አሁን 5 ሺህ ሕዝብ የለም 4 ሽህ ሕዝብም የለም አሁን የቀሩት ከዋለበት የሚውሉት ካደረበት የሚያድሩት ደቀመዛሙርቱ ብቻ ናቸው፡፡ ከእነዚህ 12 ቱ መካከልስ እስከ መጨረሻው የሚጸና እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ የሚሄድ ማነው? አሁን እዚህ ላይ እራት እየበሉ ሁለት ነገሮች ተከውነዋል፡፡ የመጀመሪያው ነገር ይሁዳ አይሁድ የመዘኑለትን ሰላሣ ብር በከረጢቱ ይዞ አብሯቸው መቀመጡ ነው፡፡ ሌላኛው ነገር ደግሞ የጴጥሮስ “ሁሉም ባንተ ቢሰናከሉ እኔ ከቶ አልሰናከልም” ያለው መልስ ነው፡፡ እንግዲህ እዚህ ላይ ይሁዳ የሚስቱ ወንድም የሆነውን ቀማኛ እና ሽፍታ በርባንን እንዲፈቱለትና ኢየሱስ ክርስቶስን ደግሞ እንዲይዙት ከአይሁድ ጋር ምክሩን ጨርሶ የሚያሲዝበትን ምቹ ጊዜ ይፈልግና ያመቻች ነበር፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም ይህን ያውቅ ስለነበር እንዲህ አለ “እውነት እላችኋለሁ ከእናንተ አንዱ እኔን አሳልፎ ይሰጣል” በዚህ ሰዓት ደቀመዛሙርቱ ሁሉ እጅግ አዝነው “ጌታ ሆይ እኔ እሆንን” እያሉ ይጠይቁት ነበር፡፡ እርሱም መልሶ እንዲህ አላቸው “ከእኔ ጋራ እጁን በወጭቱ ያጠለቀ እኔን አሳልፎ የሚሰጥ እርሱ ነው” ሲል ይሁዳ ራሱን ያውቅ ነበርና “ መምህር ሆይ አኔ እሆንን አለ ኢየሱስም መልሶ አንተ አልህ” አለው፡፡ ጌታ በልማዱ ስድስቱን አቁሞ ስድስቱን አስቀምጦ ይዞ ይበላሉ ይመገባሉ፡፡ ዛሬ የቆሙ ነገ ይቀመጣሉ ወጥ የሚያወጣው በተራ ነው፡፡ ጌታ እያወጣ ይበላል አውጡልኝ አይልም ስድስተኛው ለአምስቱ ለራሱም እያወጣ ይበላል፡፡ በዚህ ቀን ከተቀመጡት አንዱ ይሁዳ ነበር  ወጥ ማውጣትም ተራው ነበርና ከእኔ ጋር እጁን በወጭቱ ያጠለቀ እኔን አሳልፎ ይሰጠኛል” ሲል ይሁዳ እርሱ እንደሆነ አልጠፋውም ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ እንጀራውንና ጽዋውን በየተራ አንሥቶ ባርኮ መግቧቸዋል፡፡ የሐዲስ ኪዳንን የቁርባን ሥርዓት አስተምሯቸዋል፡፡ እንግዲህ የይሁዳ ልብ እንደሸፈተ ነውና ከደቀመዛሙርቱም መካከል አንዱ ቀነሰ ማለት ነው፡፡ ይሁዳ ውሎውና አዳሩ ከአይሁድ ጋር ሆነ የአባቱን ቤት የጌታውን ጋጣ ዘነጋ፡፡ የይሁዳ ዓይን በሰላሣ ብር ተሸፈነ ፈጣሪውን ለወጠው፡፡ ከ12ቱ ደቀመዛሙርት መካከል 11ዱ ቀሩ ማለት ነው፡፡
ሌላው የሚገርመው ነገር የጴጥሮስ መልስ ነው፡፡ ጴጥሮስ እንዲህ አለ “ሁሉም ባንተ ቢሰናከሉ እኔ ከቶ አልሰናከልም” እንግዲህ ጴጥሮስ በራሱ ተመክቶ ነገ የሚሆነውን የሚደረገውን ነገር ስላላወቀ ከሁሉም ይልቅ ጌታውን አብልጦ እንደሚወደውና ከእርሱም እንደማይሸሽ ፈጥኖ ተናገረ፡፡ ኢየሱስም እንዲህ አለው “እውነት እልሃለሁ በዚች ሌሊት ዶሮ ሳይጮኽ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ” ጴጥሮስ ግን አሁንም በራሱ እንደተመካ ነበር “ከአንተ ጋራ መሞት እንኳ የሚስፈልገኝ ቢሆን ከቶ አልክድህም አለ” አምላኩ የሚነግረውን እንኳ ማመን አቃተው፡፡ እስከሞት ድረስም እንደሚታመን በራሱ አንደበት ተናገረ፡፡ በእውነት ግን ጴጥሮስ በዚያች ሌሊት እስከሞት ድረስ ይታመን ይሆን? እናንተ ማቴ 26ን በሙሉ እያነበባችሁ ተከተሉኝ አሁን ይሁዳ መምህር ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን ብሎ ስሞ ለአይሁድ አሳልፎ ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም ወደሊቀ ካህናቱ ቀያፋ ወሰዱት፡፡ በዚህ ጊዜ ያ ማንም ቢክድህ አልክድህም እስከሞት ድረስ እከተልሃለሁ ያለው ጴጥሮስ እስከዚህ ግቢ ድረስ በሩቅ ሆኖ ነበር የሚከተለው፡፡ የአይሁድ ጭፍሮችን ፈራ ነገር ግን ደግሞ አልክድህም ያለው ቃል አሰረው ስለዚህ በሩቅ ሆኖ መከተሉን መረጠ፡፡ ቁጥር 69 ላይ ቅዱስ ጴጥሮስ ከቤቱ ውጭ በዐጥሩ ግቢ ተቀምጦ ነበር አንዲት ገረድም ቀርባ አንተ ደግሞ ከገሊላው ከኢየሱስ ጋር ነበርህ አለችው፡፡ እርሱ ግን የምትዪውን አላውቀውም ብሎ በሁሉ ፊት ካደ፡፡ በተድላና ደስታ ዘመን ምንም መከራ ሳይኖር እስከሞት ድረስ እታመናለሁ ብሎ በአፍ መናገር እስከሞት ድረስ መታመን ማለት አይደለም፡፡ አሁንም ደግሞ ሌላኛዪቱ እንዲህ ጠየቀቸው አሁንም አላውቀውም ብሎ ካደ፡፡ አሁንም ለሦስተኛ ጊዜ አነጋገርህ ይገልጥብሃልና በእውነት አንተ ከእርሱ ወገን ነህ አሉት ሰውየውን አላውቀውም ብሎ ለሦስተኛ ጊዜ ካደ፡፡ ከዚህ በኋላ ዶሮ ጮኸ የዚያን ጊዜ ያ ኢየሱስ ክርቶስ የነገረው ቃል ትዝ አለውና መራራ ልቅሶን አለቀሰ፡፡ አሁን በዚህ በመከራው ሰዓት የ5 ገበያ ሕዝብ የለም ቢኖር እንኳ ለመስቀል እንጅ እንዳይሰቀል ለመከልከል አይደለም፡፡ ሌሎችም ደቀመዛሙርት እንዲሁ በየፊናቸው ልብሳቸውን ጥለው ሁሉ የሸሹ አሉ፡፡ (ማር 14÷51-52) ታዲያ እስከመጨረሻ የጸናው ማነው?

ይቀጥላል…

No comments:

Post a Comment