Friday, December 25, 2015

ዘጠኙስ ወዴት አሉ? (ሉቃ 17÷17)------ክፍል 3

© በመልካሙ በየነ
ታህሳስ 15/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
እስከመጨረሻው የጸናውን ለማወቅ ወደ ራስቅል ኮረብታ ወደ ቀራንዮ እንውጣ፡፡ ዮሐ19÷25 ጀምራችሁ ተከተሉኝ፡፡ ነገር ግን በኢየሱስ መስቀል አጠገብ እናቱ (እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም) የእናቱም እህት (ሰሎሜ የእናቱ የእመቤታችን እኅት ናት፡፡ ሃና ከሞተች በኋላ የቀለዮጳን ሚስት አግብቶ ወልዷታል)፣ የቀለዮጳም ሚስት ማርያም (ማርያም ባውፍሊያ) መግደላዊትም ማርያም ቆመው ነበር፡፡ ኢየሱስም እናቱን ይወደው የነበረውንም ደቀመዝሙር በአጠገቡ ቆሞ ባየ ጊዜ እናቱን አንች ሴት እነሆ ልጅሽ አላት፡፡ ከዚህ በኋላ ደቀመዝሙሩን እናትህ እነኋት አለው፡፡ ከዚህም ሰዓት ጀምሮ ደቀመዝሙሩ ወደ ቤቱ ወሰዳት ይላል፡፡ እንግዲህ ከ12 ቱ ደቀመዛሙርት መካከል መስቀሉ ስር የተገኘው ዮሐንስ ወንጌላዊ ብቻ ነው፡፡ መከራ ላይ እንዲህ ነው ሁሉም ይሸሻል ሁሉም ይርቃል፡፡ አበርክቶ ሲመግብ የተመገበው ሁሉ ዛሬ ላይ የለም፡፡ 5 ገበያ ሕዝብ 4 ገበያ ሕዝብ ከበረከቱ የተመገበው ዛሬ የለም፡፡ ያ መልኩን ለማየት፣ ፈውሱን ለመቀበል፣ከበረከቱ ለመሳተፍ ይከተለው የነበረው ሁሉ ዛሬ ሸሽቷል፡፡ ከዋለበት የዋሉት ካደረበት ያደሩት ሃብት ንብረታቸውን ቤት ልጆቻቸውን ሥራቸውን ሁሉ ትተው የተከተሉት ደቀመዛሙርቱም ራሳቸው በፍርሐት ተይዘው ሸሹት፡፡
እነዚህ 10 ለምጻሞችም እንዲሁ ናቸው፡፡ በዘመናቸው ለምጽ የወጣበት ሰው ኃጢአተኛ ነውና ከከተማ ርቆ ይጣላል፡፡ እንግዲህ እነዚህም እንዲሁ ናቸው፡፡ ዓለም ንቋቸው ሰው ጠልቷቸው የሰው ፍቅር ርቋቸው ከዓለም ሁሉ ተገልለው ለብቻቸው ከከተማ ዳር አውጥተው የጣሏቸው ሰዎች ናቸው፡፡ ነገር ግን አምላካችን ክብር ምስጋና ይድረሰውና ኃጢአተኛን የማይጠላ እውነተኛ አምላክ ስለሰው ፍቅር ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከንጽሕተ ንጹሐን ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ ሕሙመ ሥጋን በተአምራት ሕሙመ ነፍስን በትምህርት እየፈወሰ ሲመጣ እነዚህንም ተገናኛቸው፡፡ ዓለም የናቃቸውን ሰው የጠላቸውን እርሱ ቀረባቸው፡፡ እነርሱም ተገቢ የሆነውን ልመና አቀረቡ፡፡ “እየጮኹ ኢየሱስ ሆይ አቤቱ ማረን” አሉ፡፡ እርሱም የኃጥአንን ለመና ሰማ ከዚያም “ኺዱ ራሳችሁን ለካህናት አሳዩ” አላቸው፡፡ ካሕናት እንዲህ ያለ ትልቅ ክብርና ጸጋ አላቸው፡፡ አምላክ ሲሆን እዚያው ላይ ማንጻት ሲቻለው እንዴት ራሳችሁን ለካህናት አሳዩ ይላቸዋል? ንስሐ ግቡ ራሳችሁን ለካሕናት አሳዩ የማሰር እና የመፍታት ሥልጣንን የሰጠኋቸው ናቸውና፡፡ እነርሱም የአምላክን ቃል አክብረው ራሳቸውን ለካህናት ሊያሳዩ ሄዱ  እነሆም ሲሄዱ ነጹ፡፡ ይህን ከለምጽ መንጻታቸውን ግን ለየግል ጥቅማቸው ተጠቀሙበት፡፡ ዛሬም እንዲሁ ነው ንስሐ እንገባለን ከደዌ ዳኛ ከአልጋ ቁራኛ እንፈወሳለን ሥጋውን እንበላለን ደሙን እንጠጣለን ነገር ግን ይህን ሁሉ ቸርነት ለኃጢአት እንጠቀምበታለን፡፡ ዲቁና፣ ቅስና፣ ቁምስና፣ ጵጵስናን አምላክ ያድለናል እኛ ግን ላልሆነ ነገር እንጠቀምበታል፡፡ መንጻታቸው ከሰው ጋር እንደሰው የሚያስቆጥራቸው ስለሆነ በዚያው እንደነጹ ያነጻቸውን አምላክ ተመስገን ሳይሉ እንደወጡ ቀሩ፡፡ ነገር ግን ከእነርሱም አንዱ እንደ ተፈወሰ ባየ ጊዜ በታላቅ ድምጽ እግዚአብሔርን እያከበረ ተመለሰ፡፡ እያመሰገነውም በእግሩ ፊት በግንባሩ ወደቀ እርሱም ሳምራዊ ነበር፡፡ ኢየሱስም መልሶ ዐሥሩ አልነጹምን ዘጠኙስ ወዴት አሉ? ከዚህ ከልዩ ወገን በቀር እግዚአብሔርን ሊያከብሩ የተመለሱ አልተገኙም አለ፡፡ እርሡም ተነሣና ሂድ እምነትህ አድኖሃል አለው፡፡ እንግዲህ የነጹት ዐሥር ነበሩ መንጻቱን አምኖ ያነጻውን ለማመስገን የመጣ ግን አንድ ቅዱስ ብቻ ነው፡፡ ቅድስናው አምላክ መስክሮለታል “ከዚህ ከልዩ ወገን በቀር” ብሎ ቅዱስ ማለት ልዩ ማለት ነው፡፡ ከሌሎች አስተሳሰብና አመለካከት ተለይቶ ተገኝቷል፡፡ አንድ ሲሆን በዘጠኙ ሃሳብና ምክር ሳይታለል ያዳነኝ ከለምጽም ያነጻኝ አምላኬን ሳላመሰግነው የትም አልሄድም ብሎ ተመልሶ ስለተደረገለት ምስጋና አቅርቧል፡፡
የቀሩቱ ዘጠኞቹ ግን የተደረገላቸውን ድንቅ ነገር ተጠቅመው ተመለሰው ወደ ዓለም ገብተዋል፡፡ ታጥቦ ጭቃ የሚባለው እንዲህ አይነቱ ተግባር ነው፡፡ ስለዚህ አምላካችን ያደረገልንን ውለታ ዘንግተን ዘጠኙስ ወዴት አሉ? ከመባል ይሰውረን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን፡፡

No comments:

Post a Comment