Monday, April 3, 2017

የቅብዓት ምንፍቅና ምንጭ---ክፍል ፲፮


© መልካሙ በየነ
መጋቢት 26/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ


1.  ኢሳ 61÷1 “መንፈሰ እግዚአብሔር ላዕሌየ ዘቀብአኒ ዘበእንቲአሁ አስተፍሥሆሙ ለነዳያን ፈነወኒ”
“መንፈሰ እግዚአብሔር ላዕሌየ ዘቀብአኒ ዘበእንቲአሁ ወአስተፍስሆሙ ለነዳያን ፈነወኒ”
ስለሱ ነዳያን ትሩፋንን ደስ አሰኛቸው ዘንድ በኔ ያደረ መንፈሰ ረድኤት ላከኝ ይላል ኢሳይያስ ወእፈውሶሙ ለቁስላነ ልብ፣ በቁስለ መከራ የተያዙትን አድናቸው ዘንድ፤ ወእስብክ ሎሙ ግዕዛነ ለፂውዋን፣ ለተማረኩት ነጻነትን አስተምራቸው ዘንድ ማለት ሚጠትን አስተምራቸው ዘንድ ላከኝ፡፡ ወይርአዩ እውራን፤ እውራነ ልቡና እስራኤል ያዩ ዘንድ ላከኝ፡፡ ወእስምዮ ለዓመተ እግዚአብሔር ኅሩየ፤ ዕለተ ሚጠትን የተመረጠ እለው ዘንድ ወለዕለተ ፍዳ ኅሪተ፤ ዕለተ ፍዳም ያላት ዕለተ ሚጠት ናት የባቢሎን ሰዎች ፍዳን ስለተቀበሉባት ዕለተ ፍዳ አላት፡፡ ወአስተፍሥሆሙ ለልህዋን፤ ሰባ ዘመን ያዘኑትን ደስ አሰኛቸው ዘንድ፡፡ ወአሀቦሙ ክብረ ለእለ ይላህውዋ ለጽዮን፣ ኢየሩሳሌምን አጥተው ላዘኑ ሰዎች ክብረ ሥጋን እሰጣቸው ዘንድ፡፡
ወህየንተ ሐመድ እፍረተ ትፍሥሕት ለእለ ይላህው፣ ትቢያ ይበንባቸው ስለነበረ ፈንታ ላዘኑ ሰዎች ደስ የሚያሰኝ ሽቱን እሰጣቸው ዘንድ፤ ወልብሰ ክብር ህየንተ መንፈስ ትኩዝ፣ ሰባ ዘመን ስለአዘነ ልብ ፈንታ ደስ አሰኘው ዘንድ ፈነወኒ፣ ላከኝ፣ አንድም መንፈሰ እግዚአብሔር ላዕሌየ ዘቀብአኒ ዘበእንቲአሁ አስተፍሥሆሙ ለነዳያን ፈነወኒ፣ ያዋሐደኝ በህልውናዬ ያለ የእግዚአብሔር የባሕርይ ህይወቱ መንፈስ ቅዱስ፣ አንድም ሳይናበብ መንፈሰ እግዚአብሔር ላዕሌየ፤ በእኔ ህልውና ባለ መንፈስ ቅዱስ ያዋሀደኝ እግዚአብሔር አብ ምእመናንን አስተምር ዘንድ ላከኝ፣ አንድም መንፈስ ዘዚአየ በህላዌ ለሊሁ ኀደረ ላእሌየ ብሎ ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ ተረጉሞታልና ብሎ የእግዚአብሔር አብ የባህርይ ህይወቱ መንፈስ ቅዱስ ላዕሌየ በእኔ ህልው ነው፣ ወዘበእንቲአሁ ቀብዐኒ፣ ስለማስተማርም ያዋሐደኝ መንፈስ ቅዱስ ምእመናንን አስተምራቸው ዘንድ ላከኝ፡፡
2.  ዳን 9÷24
“ወይትቀባዕ ቅዱሰ ቅዱሳን፣ ቅዱሰ ቅዱሳን ጌታ ይከብራል፣ የባህርይ ክብሩን ገንዘብ ያደርጋል፤ አእምር ወለቡ እምፀአተ ቃሉ ዘታወሥእ፣ ንገረው የሚለኝ ቃሉ ከመውጣቱ የተነሳ የምትመልሰውን እወቅ፤ አንድም እምጸአተ ቃል ዘአወስአከ ንገረው የሚለኝ ቃል ከመውጣቱ የተነሳ የምመልስልህን እወቅ፡፡ አንድም እምፀአተ ቃሉ ዘታወሥእ ንገረው የሚለኝ አካላዊ ቃሉ ከመምጣቱ የተነሳ የምትመልሰውን እወቅ፤ አንድም እምጸአተ ቃል ዘአወሥአከ አካላዊ ቃል ከመምጣቱ የተነሣ የምመልስልህን እወቅ ወትትሐነፅ ኢየሩሳሌም እስከ ክርስቶስ ንጉሥ፣ ኢየሩሳሌም ጌታ እስቲወለድ ድረስ በመፍረስ በመታነፅ ቤተ መቅደስ በመሆን ቆይታ ቤተክርስቲያን በመሆን ትታነፃለች ሰብአተ ሰንበታተ ስሳ ወክልዔተ ሰንበታተ ሰባት ሱባኤ ስድሳ ሁለት ሱባኤ ቆይታ፡፡
3.  ሐዋ 10÷38 “ዘቀብኦ እግዚአብሔር መንፈሰ ቅዱሰ ወኃይለ”
“ዘቀብኦ እግዚአብሔር መንፈሰ ቅዱሰ ወኃይለ”
እግዚአብሔርነቱ ኃይሉ ሕይወቱ በሚሆን በመንፈስ ቅዱስ የመረጠው የሾመው፡፡ ውእቱ መጽአ ከገሊላ ወደ ይሁዳ በመምህርነት መጥቶ ወረድኦሙ ለእለ ይተዔገሎሙ ሰይጣን፤ ሰይጣን ድል አድርጓቸው የነበሩትን እንዳዳነ ታውቃላችሁ እስመ በዘአመከርዎ ክህለ ረድኤቶሙ ለሕሙማን ወረድነ በከመ ምክረ ፈቃዱ እንዲል፡፡ እስመ እግዚአብሔር ምስሌሁ እግዚአብሔር በህልውናው ነውና፡፡

4.    ሮሜ 1÷2-4 “በእንተ ወልዱ ዘተወልደ ወመጽአ እም ዘርአ ዳዊት በሥጋ ሰብእ ወአርአየ ከመ ወልደ እግዚአብሔር ውእቱ በኃይሉ ወበመንፈሱ ቅዱስ”
“ዘአቅደመ ነጊረ በአፈ ነቢያቲሁ ወበመጻሕፍቲሁ ቅዱሳት በእንተ ወልዱ ዘተወልደ”
አካል ዘእም አካል፣ ባሕርይ ዘእምባሕርይ የተወለደ የልጁን ነገር ፤ ስለ ተወለደ ስለ ልጁ፤ በዳዊት “ወልድየ አንተ ወአነ ዮም ወለድኩከ” መዝ 2÷7፤ በነገሥት “አነ እከውኖ አባሁ ወውእቱ ይከውነኒ ወልድየ” 2ኛ ነገ 7÷14፤ በሰሎሞን “እምቅድመ አድባር ወአውግር ወለደኒ” ምሳሌ 8÷25፤ በነቢያት በመጻሕፍት  ያናገረ የአብን ነገር ከማስተምር ከእኔ ከጳውሎስ የተገኘች ክታብ (መልእክት)  ሐተታ  መጻሕፍት፣ ነቢያት የሚላቸው ልዩ ናቸውን ቢሉ ነቢያት ያላቸው ሳሉ የተናገሩት፡፡ መጻሕፍት የሚላቸው ከሞቱ በኋላ የተጻፉት ናቸው፡፡ ይህማ ሳሉ የተናገሩት ከሞቱ በኋላ ቢጻፍ ልዩ ነውን ብሎ ነቢያት የሚላቸው አድሮ ያናገራቸው፡፡ መጻሕፍት የሚላቸው በዘፈቀደ ታይቶ ያጻፋቸው ናቸው፡፡ ቅዱሳት ንጹሐት ክቡራት ሲል ነው፡፡ ርኩሳት መጻሕፍተ ጥንቆላ አሉና ከዚያ ሲለይ ንጹሐት አለ፡፡ ምኑናት መጻሕፍተ ደብዳቤ አሉና ከዚያ ሲለይ ክቡራት አለ፡፡
“ወመጽአ እም ዘርዐ ዳዊት በሥጋ ሰብእ”
በሥጋ ከዘርዐ ዳዊት ስለተወለደ ስለ ልጁ፤ የተወለደ የልጁን ነገር በኢሳይያስ “ትወጽእ በትር እምሥርዎ እሴይ  ወየዐርግ  ጽጌ እምጉንዱ” “ወይቀውም ሥርዎ እሴይ ወዘተወልደ እምኔሁ ይከውን ንጉሠ ለአሕዛብ“ ኢሳ 11÷1 እና 10፤ በዳዊት “ እስመ እምፍሬ ከርስከ አነብር ዲበ መንበርከ” መዝ 132÷1 ብሎ በነቢያት በመጻሕፍት ያናገረ የአብን ህግ ከማስተምር ከእኔ ከጳውሎስ  ሐተታ ሥጋ እንስሳ አለና ከዚያ ሲለይ ሥጋ ሰብእ አለ፡፡ ምነው ዘርዐ ዳዊት ያለው አይበቃምን ቢሉ ነፍስን እንደነሣ ለማጠየቅ ፤ ያውስ ቢሆን “ዘርዐ አብርሐም አልዐለ” እንዲል (ዮሐንስ አፈወርቅ) ዘርዐ ዳዊት ያለው አይበቃምን ቢሉ  በከዊን ሲል ነው፡፡

“ወአርአየ ከመ ወልደ እግዚአብሔር በኃይሉ ወበመንፈሱ ቅዱስ”
“ዘተወልደ ወዘአርአየ” ብሎ ለወልድ ይቀጽላል፡፡ ኃይሉ ሕይወቱ በሚሆን በመንፈስ ቅዱስ ከዘርዐ ዳዊት በመወለዱ ወልደ እግዚአብሔር እንደሆነ ስላሳየ ፣ ስለ ልጁ ያሳየ፣ የልጁን ሕግ ወንጌልን ከማስተምር ከእኔ ከጳውሎስ ሐተታ፡፡ አምስት ሽህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከእመቤታችን ያለ አባት መወለዱ ቅድመ ዓለም ከአብ ያለ እናት መወለዱን ያስረዳልና፡፡ “ልደት ቀዳማዊ ተዐውቀ በደኃራዊ ልደት”  እንዲል (ሃይማኖተ አበው ዘሱኑትዩ)  አንድም በኃይሉ በኅቱም ድንግልና ተጸንሶ በኅቱም ድንግልና በመወለዱ ፡፡
“ወበመንፈሱ ቅዱስ” 
መንፈስ ቅዱስን በዮርዳኖስ በርግብ አምሳል በእራሱ ላይ በማኖሩ፡፡ “አሜሃ ስምዐ ኮነ መንፈስ በዮርዳኖስ ከመ ወልድ ዘበአማን ወአምላክ ዘበአማን” እንዲል ቄርሎስ አንድም በኃይሉ ሦስት አመት ሦስት ወር ባደረገው ተአምራት፡፡

ወበመንፈሱ ቅዱስ መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት በጽርሐ ጽዮን በመስደዱ፡፡ አንድም፡ “ዘአቅደመ ወዘአርአየ” ብሎ ለአብ ይቀጽላል፡፡ “በኃይሉ ከመ ወልደ እግዚአብሔር አርአየ በመንፈስ ቅዱስ”  በባሕርዩ ወልደ እግዚአብሔር እንደሆነ መንፈስ ቅዱስን በእራሱ ላይ በማኖሩ ያሳየ የልጁን ነገር፡፡ አንድም “በመንፈስ ቅዱስ ከመ ወልደ እግዚአብሔር አርአየ በኃይሉ” በግብረ መንፈስ ቅዱስ በመወለዱ ወልደ እግዚአብሔር እንደሆነ በግብሩ፣ በነገሩ አሳየ አለ፡፡  በነገሩ “ዝንቱ ውእቱ ወልድየ” ብሎ፡፡ በግብሩ መንፈስ ቅዱስን በርግብ አምሳል በእራሱ ላይ በማኖሩ ያሳየ የልጁን ነገር በኢሳይያስ “ቁልዔየ ፍቁርየ ዘሰምረቶ ነፍስየ ወአነብር መንፈስየ ላዕሌሁ ወየአርር መንፈሰ እግዚአብሔር ዘላዕሌየ ዘበእንቲሁ ቀብዓኒ” ብሎ ያናገረ የአብን ሕግ ከማስተምር ከእኔ ከጳውሎስ የተላከች ክታብ፡፡
5.  1ኛ ዮሐ 2÷22
“ወመኑ ውእቱ ሐሳዊ ዘእንበለ ዘይክህድ ወይብል እስመ ኢየሱስ ኢኮነ መሢሐ” ኢየሱስ መሢሕ አይደለም ከሚል ሰው በቀር የሚል ሰው ነው እንጅ ያለሱ ሐሰተኛ ማን ነው፡፡ አንድም ኅድረት ከሚል ከንስጥሮስ በቀር ሐሰተኛ ማነው የለም፡፡ ሐተታ ምነው ሥጋ አምላክ አይደለም ብሏል እንጅ፡፡ ቃል መሲሕ አይደለም ብሏልና እንዲህ አለ ቢሉ ቃልንስ መሢሕ ቢሆን ሥጋን አምላክ ባለ ነበር ቀንጃ ተዋሕዶን አለ፡፡
6.  1ኛ ዮሐ 5÷1
“ኩሉ ዘየአምን ከመ ኢየሱስ ውእቱ መሢሕ እምነ እግዚአብሔር ተወልደ” ኢየሱስ መሢሕ እንደሆነ አለ ሥጋን እንደ ተዋሐደ የሚያምን ሁሉ ከእግዚአብሔር የተማረ፡፡ አንድም የተወለደ ነው፡፡ “ወኩሉ ዘያፈቅሮ ለወላዲ ያፈቅር ዘኒ ተወልደ እምኔሁ” ወላዲውን አብን የሚወደው ተወላዲውን ወልድን ይወደዋል፡፡ አንድም ወላዲውን ወልድን የሚወድ ተወላዲውን ምእመንን ይወዳል፡፡
ይቆየን፡፡
ይቀጥላል፡፡

No comments:

Post a Comment