Saturday, June 13, 2015

የሞተውን ለመቅበር ያልሞተውን መግደል

አንድ ቀን ሂድ ሂድ የሚል መንፈስ ያዘኝና መጓዝ በለመደው እግሬ እከንፍ ጀመር፡፡ በእርግጥ ክንፍ እንደሌለኝ አምናለሁ ነገር ግን በላይ በሰማይ ከሚበርሩት አእዋፋት እኩል የምበር ይመስለኛል፡፡ ዳሩ ግን አርሱ ፈጣሪ ቢያውቀው እንጅ ማን ሊያውቅ ይችላል? እኔም በመንፈሴ አይደለሁምና፡፡ ነገር ግን ከሰውነቴ አልወጣሁም፡፡ ለዚያም ነው አንድ ሽማግሌ በምሬት ሲናገሩት የነበረውን ምርር የሚል ንግግር የሰማሁ፡፡ ምሬቱ ለእሳቸው ብቻ ሳይሆን ለእኔም ነበር፡፡
ሽማግሌው ሌሊት የሰሙት የእድር ጥሩንባ የቀሰቀሳቸው ይመስላሉ፡፡ “እንቅልፍ አጣን እኮ እናንተ! ቀን ከሌሊት ጥሩንባ ብቻ፡፡ የእድር ጥሩንባ ነፊዎች እገሌ ሞተ ለማለት ጥሩንባ፣የቀበሌ ልማት ቡድኖች  እርከን ሥራ ውጡ ለማለት ጥሩንባ፤ ቀበሌ ስብሰባ አለ ለማለት ጥሩንባ፤ ምርጫ ለመምረጥ ጥሩንባ፤ ሰላማዊ ሰልፍ ውጡ ለማለት ጥሩንባ፣ መኪናዎች መንገድ ልቀቁልኝ ለማለት ጥሩንባ፣አምቡላንሶች  በሽተኛ ይዣለሁ ለማለት ጥሩንባ፣ ጋዜጠኞች ልማቱን ለማብሠር ጥሩንባ ብቻ ሁሉም ጥሩንባ ሆነብን እኮ፡፡ አረ መቼ ነው ከዚህ ድምጽ ጆሮዬ ነጻ የሚሆነው? እስከመቼ ድረስ ነው እንድንሰማቸው ብቻ የሚፈልጉትን ሁሉ የምንሰማቸው?” አሉ፡፡ ሽማግሌው  በሁሉ ነገር በጣም የተበሳጩ ይመስላሉ፡፡ እሳቸው ሲናገሩ ስሰማ እኔም  ውስጤ ትንሽ ተሰማው፡፡ እርግጥ ነው መናገረን ይናገሩ ግን ግድ ስሙኝ የሚሉ ሰዎች ሊኖሩ አይገባም አልኩ በውስጤ፡፡ እሳቸው ግን በነጩ እንደያዘው የሃምሌ ዝናብ በቀላሉ ከምሬታቸው የሚያባሩ አይመስሉም፡፡ ቀጠሉ “የትናንትናን ታሪክ ደፍጣጭ ምኑ ይደመጣል? የበሬ ወለደን ንግግር ማን ይሰማል? ዜና እና የጉዞ ማስታወሻ የተቀላቀለበትን ጋዜጠኛ ማን ይሰማል? አሉባልታ አይሉት ምክር፣ ማስጠንቀቂያ አይሉት ማስፈራሪያ፣ መግለጫ አይሉት ማላገጫ የመሰለውን ትርኪምርኪ ማን ያዳምጣል? ያለፈውን ታሪክ ለመቅበር የዛሬውን ታሪክ የሚገለውን ማን ይከተላል? በሽተኛውን ለማዳን ሲል ያልታመመውን የሚያሳምም ሃኪምን ማን ይቀርበዋል? ዘንዶ የሚወጣበትን ጉድጓድ ዓሣ ይኖርበታል ብሎ ማን እጁን ይሰዳል?” አሉ ሽማግሌው፡፡ ውስጤ ነደደ ተንቦገቦገ፡፡ ግን የትኛው እስር ቤት ሊገቡ ፈልገው ነው እንዲህ ዘራፍ የሚሉት? ስል አሰብኩ፡፡ እስር ቤቶች እንደ አሸን በዝተው እንደተራበ አንበሳ አፋቸውን ከፍተው ሊውጡ በተዘጋጁበት ወቅት እንዲህ አይነት ንግግር  የምሬታቸው ደረጃ ራሳቸውን እንዳሳታቸው ማሳያ መሰለኝ፡፡

ሽማግሌው በዚህ አላበቁም “በዚያ በቀደምለት ማናቸው አያ! እኒያ ትልቁ ባለሥልጣን የሞቱ ጊዜ ትልልቅ የተባሉት የጦር መሪዎች አስከሬናቸውን ይዘው ወደ መቃብር ሊያውርዷቸው ሲሉ የአገራችን ሰው በሕይወት ሳሉ በቴሌቪዥን እንጅ በአካል አይተዋቸው ስለማያውቁ ቢያንስ ሬሳቸው ያለበትን ሳጥን እንመልከት ብለው ሲጠጉ በፖሊሶች ዱላ እንደ እባብ ራስ ራሳቸውን ተቀጠቀጡ፡፡ በሕይወት ሳሉስ ጠባቂ የተመደበላቸው ለህዝብ ቅን ስለማያስቡ ሰው ይገለኛል ብለው ፈርተው ወይም ሰግተው ሊሆን ይችላል፡፡ ለህዝብ የሚያስቡ ከሆነ ማንን ፈርተው ነው ታዲያ ጠባቂ የሚያቆሙት? እሽ እሱስ ይቅር ከሞቱ በኋላ ሬሳቸውን የሚሰርቅ ሰው አለ እንዴ ያን ያህል በግድ ሃዘን እንዲወጣ የተቀሰቀሰውን ሰው በዱላ የሚቀጠቅጡት? የሞተውን ለመቅበር ያልሞቱትን መግደል ምን አይነት ግፍ ነው? የሞተው እኮ ከዚህ በኋላ አገሪቱን ላይመራ አንዴ የተሰናበተ ነው? ሊቀብሩ የመጡት ግን እድል አላቸው እድሉን ማን ይሰጣቸዋል እንጅ? ታዲያ በቁሙ ባናየው ቢያንስ ከሞተ በኋላ አስከሬኑን እንመልከት ያለውን ህዝብ በዱላ! የሞተውን ማን ይገለዋልና ነው ግን እንዲህ የተደረገው?” አሉ፡፡  እኔ አሁን ዋና መልእክታቸው ገባኝ እውነታቸውን ነው የተናገሩት፡፡ ገንዘብ ሞልቶት ሁሉ ኖሮት የዓለም ቁጥር አንድ ባለሃብት ለመባል ሲል የስንቱን ምስኪን ኪስ ይዳስሳል መሰላችሁ፡፡ ሰው የሚበላው ሞልቶት ሁሉ ተርፎት የዳቦ ሽራፊ የቀረችውን ደሃ ተካፍሎ ሊበላበት ሲጠጋ አይገርምም ትላላችሁ? የድሮ ታሪክን ለማጥፋት ሲባል ስንት የዛሬ ታሪክ ተጨፈለቀ መሰላችሁ? በሽተኛውን ለማዳን ሲሉ ስንቱን ጤነኞች በሽተኞች አደረጉ መሰላችሁ? የምትለውን ሳይሆን የሚሉትን ብቻ እንድትሰማቸው በየቀኑ ስብሰባ የሚጠሩህ ስንት ናቸው? አረ ተውት ስንቱ ስንቱ ስንቱ ጉድ ይነገራል?????? ናርምም አለ ሊቁ ነገሩ ቢረቅበት፡፡

No comments:

Post a Comment