Monday, June 29, 2015

መሞት ብርቅ አይደለም (ክፍል አራት)

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ስለ ሞት አይነቶች በተከታታይ ክፍሎች ተመልክተናል በዚህ ክፍል ደግሞ መሞት ብርቅ እንዳልሆነ እናያለን።

ብዙዎቻችን ኑሮ አልሰምርልን ሲል፣ ገንዘብ ሲጠፋብን፣ የምንወደው ሰው ሲከዳን፣ የምንወደው ሰው ሲሞትብን፣ የፈተና ውጤት አልመጣ ሲለን፣ ከስራ ስንባረር፣ ከሰው ስንጣላ ወዘተ ተስፋ እንቆርጣለን። ተስፋ መቁረጥም ብቻ አይደለም ለመሞት እንመኛለን። ሰይጣን ይህንን ክፍተት ተጠቅሞ ራሳችንን በምን ልናጠፋ እንደምንችል የሞት መንገዶችን ያማርጠናል። ራስህን በመርዝ አጥፋ የሚል መንፈስ ሹክ ይልሃል። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ለምን ታንቀህ አትሞትም ይልሃል። ትምሽ ቆይቶ ደግሞ ለምን ኤሌክትሪክ ገመድ ጨብጠህ አንዴ አትገላገልም ይልሃል። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ሌላ መንፈስ ለምን ራስህን ወደ ገደል ወርውረህ አትገላገልም ይልሃል። ሌላው መንፈስ ደግሞ ይመጣል ለምን ራስህን ውኃ ውስጥ አጥልቀህ አትገድልም ይልሃል። ብቻ ተስፋ መቁረጥህን ያየ መንፈስ ሁሉ የምትሞትበትን ምርጫ በገፍ ያቀርብልሃል። ብልጥ መሆንን የሚጠይቀው ያን ጊዜ ነው። ሞኞች የሚሞቱት ሞት መነሻው ይህ ተስፋ የመቁረጥ ተስፋ የማጣት ሂደት ነው። ሰይጣን መንግሥተ ሰማያት ስትገባ ማየት አይወድም። ለዚህም ነው የሞት አማራጭ የሚያቀርብልህ። ተስፋ በማስቆረጥ በቁምህ እንድትሞት ካግባባህ በኋላ ራስህን እንድታጠፋ ይጋብዝሃል። ጫቱን በገፍ፣ሲጋራውን በገፍ፣ ዝሙቱን በገፍ ያቀርብልሃል። አንተ እጅህን ወደዚያ ከጨመርህ ያንጊዜ ወደ ሞት መስመር መግባትህን ልትዘነጋ አይገባውም። ሰይጣን የሞት አማራጭ ሲያቀርብልህ መሞት ብርቅ አይደለም መርዝ አልጠጣም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ራሴን አላንቅም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ራሴን ወደ ገደል አልወረውርም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ኤሌክትሪክ አልጨብጥም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ጫት አልቅምም፣ ሲጋራ አላጨስም፣ ዝሙት አልፈጽምም በለው፡፡ መሞት ብርቅ አይደለም ራሴን ውኃ ውስጥ አልገድልም በለው፡፡ ለእኔ ብርቄ መሞት አይደለም ለኔ ብርቄ በህይወት መኖር ነው በለው። ሞት ብርቅ አይደለም እኔ የምፈልገው ብርቅ የሆነውን እንጅ የረከሰውን አይደለም በለው። ወንድሜ ሆይ መሞት ብርቅ አይደለም። ዛሬ ራስህን ልትገድል እድሉ አለህ ነገር ግን ብርቅ አይደለም። ብርቁ ነገር ንስሐ መግባት ነው። ብርቁ ነገር ሥጋ ወደሙን መቀበል ነው። ብርቁ ነገር ከኃጢአት መራቅ ነው። ብርቁ ነገር በእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ መሄድ ነው። ብርቁ ነገር ራስን መግደል ሳይሆን ራስን ማዳን ነው። ስለዚህ ሰይጣንን መሞት ብርቅ አይደለምና ለአንተ አንገዛም እንበለው። በቤተ ክርስቲያን ፊት ቆመን እንካደው። ርኩስ መንፈስ ሲገፋፋህ ቆም ብለን አስብ። 

2 comments:

  1. መሞት የምንጀምረው መቼ ነው?

    ReplyDelete
  2. መሞት የምንጀምረው መቼ ነው?

    ReplyDelete