Friday, July 17, 2015

ምጽዋት


©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

ምጽዋት ማለት ስጦታ፣ ችሮታ፣ ልግስና ማለት ነው፡፡ ጠላት በዚህ አገልግሎት እጅግ ይቀናብሃል ከዚህም ለመለየት ቀን ከሌሊት የጥፋት ስትራቴጅ ሲነድፍ ይውላል ያድራልም፡፡ “አንተ የምትበላው የምትጠጣው የምትለብሰው ሳይኖርህ ገነረዘብህን ለምን ለድሆች ትበትናለህ?” ይልሃል፡፡ ይህን የጠላት ክፉ ምክር ከተቀበልክ በስግብግብነትና በፍቅረ ንዋይ አስሮ ከምጽዋት አገልግሎት ያርቅሃል፡፡ ምጽዋት በተለያየ ማድረግ እንደምትችል መረዳት አለብህ ሁልጊዜ ከገንዘብ ጋር ብቻ አታያዘው፡፡ በእውቀት፣ በጉልበት፣ በገንዘብ፣ በምክር ወዘተ ምጽዋት ልታደርግ ትችላለህ፡፡ በጉልበትን ደካሞችን በገንዘብህ ድሆችን በእውቀትህ አገርህን ቤተክርስቲያንህን ወዘተ ከረዳህ ምጽዋት ይህ ነው፡፡ ሰይጣን ግን እዚህ ላይ ቆሞ እውቀትህን የጋን መብራት አድርጎ እንዳትጠቀምበት ያደርግሃል፡፡ እውቀትን በነጻ የሰጠህን አምላክ ከማመስገን ይልቅ በራስህ እንድትመካ ያደርግሃል፡፡ ገንዘብህንም በኑሮ ውድነት እያሳበበ አሥራት በኩራቱን እንዳታወጣ ድሆችን እንዳትረዳ አንተ ምን ልትበላ ምንስ ልትጠጣ እያለ እያሸማቀቀ ከምጽዋት አገልግሎት እንድትሸሽ ያደርግሃል፡፡ ጉልበትህንም የወጣት ልፍስፍስ አድርጎ የደካማ ልብስ እንዳታጥብ፣ ለቤተክርስቲያን ሥራ ድንጋይ እንዳትሸከም ወዘተ ያደርግሃል፡፡ ባለኝ ነገር መሥራት አለብኝ ብለህ ወስነህ ስትመጣ ደግሞ በሌሎች አድሮ እንዳትሠራ ያደርግሃል፡፡ አንተ የምትጠየቀው ትልቅ ነገርን አይደለም ባለህ ነገር እንድታገለግል ነው እንጅ፡፡ ጥንተ ጠላት ግን አሁንም ያሸማቅቅሃል እገሌ ያን ያህል ገንዘብ እየሰጠ አንተ ይችን ትንሽ ነገር ሰጠው ብለህ ነውን ከዚህስ ብትተወው ይሻልሃል ይልሃል፡፡ አንተ ግን ዛሬ ያለኝን ነገር እሰጣለሁ ነገ ሳገኝ ደግሞ እጨምርበታለሁ በለውና ያለህን ነገር ጣል፡፡ ማስረጃ የሚፈልግ ከሆነ /ሉቃ21፥1-4/ ያለውን ቃል አስነብበው፡፡ “ዓይኑንም አንሥቶ መባቸውን በመዝገብ የሚጥሉ ባለጠጎችን አየ፡፡ አንዲትም ድሃ መበለት ሁለት ሳንቲም በዚያ ስትጥል አየና እውነት እላችኋለሁ ይህች ድሃ መበለት ከሁሉ ይልቅ አብልጣ ጣለች እነዚህ ሁሉ ከትርፋቸው ወደ እግዚአብሔር መዝገብ ጥለዋልና ይህች ግን ከጉድለቷ የነበራትን ትዳሯን ሁሉ ጣለች አለ፡፡” ከባለጠጎች ምጽዋት ይልቅ ያለቻትን 2 ሳንቲም የጣለችው መበለት የበለጠ ዋጋ እንዳገኘች አስረዳው፡፡ “ድሆች ከምድሪቱ ላይ አይታጡምና በአገርህ ውስጥ ላለው ድሃ ለተቸገረውም ወንድምህ እጅህን ትከፍታለህ ብየ አዝዝሃለሁ” /ዘዳ15፥11/ ስለዚህም ድሆችን በምጽዋት ላስባቸው ትእዛዜን አከብራለሁ ብለህ ጠላትን አሳፍረው፡፡ ይህን ሁሉ እያስረዳኸው አሁንም የሚፈትንህ ከሆነ ግን “ምን ይዤ ወደ እግዚአብሔር ፊት ልምጣና በልዑል አምላኬ ፊት ልስገድ?”  /ሚክ6፥6/ ብለህ ባዶ እጅህን ወደ እግዚአብሔር ቤት እንደማትገባ ምጽዋትን እንደምታደርግ ቁርጥ ውሳኔህን በሚገባ አስረዳወ፡፡ እርሱ ግን አይተውህም ከምጽዋት ርቀህ እንድትቆም ይበረታብሃል፡፡ አንተ ግን መጽሐፍ ቅዱስን እያነበብክ ለሌሎች በመራራት ያለህን እያካፈልክ በጎ ሥራ እየሠራህ ኑር፡፡ ትልቅ ዋጋ የምታገኝበት እንዲሆንልህ ይህን አንብብ፡፡ “እንግዲህ ምጽዋት ስታደርግ ግብዞች በሰው ዘንድ ሊከብሩ በምኩራብ በመንገድም እንዲያደርጉ በፊትህ መለከት አታስነፋ እውነት እላችኋለሁ ዋጋቸውን ተቀብለዋል፡፡ አንተ ግን ምጽዋት ስታደርግ ምጽዋትህ በሥውር እንዲሆን ቀኝህ የምትሠራውን ግራህ አትወቅ በሥውር የሚያይ አባትህ በግልጥ ይከፍልሃል” /ማቴ6፥1-6/ ስለዚህ ዋጋ የሚያስገኝ ምጽዋትን  በሥውር አድርግ፡፡ ለተጠማ ቀዝቃዛ ውኃ ለተራበ ቁራሽ እንጀራ ስጥ በሰማይ ቤት ምስክር እንድታገኝ፡፡ በፍርድ ቀን ተርቤአብልታችሁኛል? ተጠምቼአጠጥታችሁኛል? እንግዳሆኜተቀብላችሁኛል? ታርዤአልብሳችሁኛል? ታምሜጠይቃችሁኛል? ታስሬወደእኔመጥታችኋል? ነውና የምትባለው ምጽዋትን ከማድረግ አትቆጠብ፡፡ እነዚህ ጥያቄዎች ያለህን በመመጽወት የምትመልሳቸው ናቸው፡፡ የሌለህን አምጣ ብሎ የሚጠይቅህ ማንም የለም ካለህ አካፍል የሚል እንጅ፡፡ ስለዚህ ከምጽዋት አገልግሎት ርቀህ እንዳትቆም ሁልጊዜም ልትጠነቀቅ ያስፈልጋል፡፡

No comments:

Post a Comment