Thursday, July 23, 2015

ለልመና ዕድል የፈጠረው ሰልፍ

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

ዛሬ በጠዋቱ አስቸኳይ ጉዳይ ገጥሞኝ በታክሲ ልሔድ አሰብኩና ወደ ታክሲ ቦታ አቀናሁ፡፡ የተሰለፈውን ሰው አሞራ ዞሮ አይጨርሰውም፡፡ ለማጋነን እንዳይመስላችሁ አንድ ጥቁር አሞራ ከላይ ሆኖ ዞሮ ሊጨርስ ፈልጎ ይሁን አይሁን ባላውቅም ሲበር ሲበር ሰልፉን ሳይጨርስ በጣም ስለደከመው ከአንድ ዛፍ ጫፍ አረፈ፡፡ በእርግጥ ሰልፍ መሰለፍ አዲስ ነገር አይደለም እጅግ በጣም የተለመደ ነው፡፡ ለስኳር፣ ለዘይት፣ ለታክሲ ወዘተ ብቻ ለሁሉም ነገር ትሰለፋለህ፡፡ ሳትሰለፍ ጉዳይ ማስፈጸም ሳታሰልፍ ጉዳይ መፈጸም የሚባል ነገር የለም፡፡ እኔም አሞራ ዞሮ ከማይጨርሰው ሰልፍ መጨረሻ ላይ መሰለፍን አልተሰቀቅሁም፡፡ ምክንያቱም ሳይሰለፉ ታክሲ የለማ! አንድ ባጃጅ የምትይዘው 3 ሰዎችን ብቻ ነው፡፡ ከፊት ያሉትን የተሰለፉትን ልቆጥራቸው ሞከርሁ ግን ሰልፉ ከመርዘሙ የተነሣ ምን ያህል ሊሆኑ እንደሚችሉ በትክክል አላወቅሁም፡፡ በግምት ግን ከ 30ኛው ባጃጅ በኋላ ሊደርሰኝ እንደሚችል ተረድቻለሁ፡፡ “አይ ይሁን ይደርሰናል ችግር የለውም” አለ አንድ ቋሚ ተሰላፊ ሰው፡፡ “ገና 30 ባጃጅ ከመጣ በኋላ እኮ ነው የሚደርሰን” አለ ከጎኑ ያለው ሌላ ተሰላፊ፡፡ እኔ ድምጼን አጥፍቼ የተሰላፊዎቹን ጨዋታ መከሽከስን ተያያዝኩት፡፡ “ችግር ያለብን እኛ ነን እኮ ሙሉ ችግረኛ!” አለ ተሰላፊው፡፡ “ትክክል ነህ እሱስ እኛው ነን ችግረኞች፡፡ ለ30 ደቂቃ ጉዞ ከ 1 ሰዓት በላይ እኮ ነው የምንሰለፈው፡፡ ሰነፎች ሆነናል ነገሩስ በእግር መሄድ የጠላን እስኪመስል ድረስ” አለ ሌላኛው፡፡ “ምን አንተ ደግሞ ድሮ እኮ ታክሲ የሚያዘው ቶሎ ለመድረስ ነበር ዛሬ ግን ለመዝናናት ነው የሚመስለው፡፡ እንዳንዴም በእግሩ መራመድ የጠላ ሰው የሚጓዝበት ሌላ አማራጭ ሆኖ የቀረበም ይመስለኛል” አለ፡፡ “ልክ ነህ አሳቅኸኝ እኮ! መራመድ የጠላ ሰው ነው ያልከው ተወው እስኪ ይሁን” አለ ሌላኛው፡፡ ይህን እየተነጋገሩ እያለ ስመ እግዚአብሔርን እየጠራች የምትለምን አንድ ሴትዮ ከእኛ አጠገብ ደረሰች፡፡ “ስለ ወላዲተ አምላክ ስለ እምብርሃን ብላችሁ አሥር አምስት ጣሉልኝ” አለች፡፡ “ትሰማታለህ ይችን ለማኝ ስለ እመብርሃን እያለች ስትለምን ትንሽ አታፍርም፡፡ እኛ ለራሳችን ዓላማ የተሰለፍነውን ሰልፍ እሷ ለግል ዓላማዋ ትጠቀምበታለች፡፡ አታይም እንዴ አሰልፋ ስትለምነን፡፡ እሱስ ይሁን ተወው የምንሰጠውን ገንዘብ ራሱ እኮ ወሰነችው፡፡ አሥር አምስት እኮ ነው የምትለው፡፡ ለግልህ ዓላማ ትሰለፋለህ ሌላው የግሉን ጉዳይ ያስፈጽምብሃል፡፡ አይ አንች ምድር!” አለ በመገረም አይነት ንግግር፡፡ “ተው እንጅ ወዳጄ! ለማኝ ትለለህ እንዴ? አነጋገርህን አስተካክል የኔ ቢጤ ነው የሚባል” አለ ሌላኛው፡፡ “ ተው እባክህ! እሷ የኔ ቢጤ የምትባለው ለምንድን ነው? አንተ እኮ በደንብ አታውቃትም፡፡ የኔ ቢጤ የምላት እኮ እንደ እኔ ቤት የሌላት፣ መኪና የሌላት፣ ሃብት ንብረት የሌላት ምስኪን ብትሆን ነበር ወይም ከእኔ ያነሰች ብትሆን ነበር እሱም ለትህትና ያህል፡፡ ይች እኮ ቤት አላት፣ ወፍጮ አላት፣ አረ መኪናም አላት ይባላል” አለ፡፡ “እንዴ የምትለኝ ነገር እውነት ነው? ታዲያ ለምን ትለምናለች?” አለ ሌላኛው፡፡ “ተወው አንተ! ሱስ እኮ ለመያዝ እንጅ ለመልቀቅ ያስቸግራል፡፡ ሲጋራ አጫሾችን ተመልከት በሲጋራ ጢስ ሲታጠኑ የሚውሉት ሆዳቸውን ስለሚሞላላቸው መሰለህ እንዴ? ጫት ቃሚዎችስ ቢሆኑ ምን ጠብ የሚል ጥቅም ያገኙበት መሰለህ? ምንም ረብ የለውም እኮ፡፡ ኳስን አየር እንደሚሞላት ሁሉ እነሱም በሲጋራ ጢስ እና በጫት ቅንጣቢ ሆዳቸውን የሞሉ ይመስላቸዋል፡፡ ለምን እንዲህ ታደርጋላችሁ በላቸው እስኪ፡ ምን እንደሚመልሱልህ ታውቃለህ? ሱስ ስለሆነብን ነው ብለው ነው የሚመልሱልህ፡፡ ሱስን ለመልቀቅ በጣም ይከብዳል፡፡ ይች ሴትዮም እንደዛው ናት ልመና ሱስ ሆኖባታል፡፡ ልመናን ተዪ ከምትላት ምግብ መመገብሽን አቁሚ ብትላት ይቀላታል፡፡ አገራችንስ ብትሆን እንደዚች ሴትዮ ልመና ሱስ ሆኖባት የለም እንዴ? እሽ ከኢትዮጵያ የሚበልጥ ሃብታም በዓለም አለ? የለም እኮ፡፡ ግን ሃብቷን በአግባቡ መጠቀም ስላልቻለች የሃብታም ደሃ ሆና እጇን ለልመና እንደዘረጋች ናት፡፡ ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች አልነበረም እንዴ የሚለው መጽሐፉ፡፡ አሁን ግን ለልመና ሆኗል የአገራችን እጅ የሚዘረጋው” አለ፡፡ “እውነት አድናቂህ ነኝ እንዴ! እንዲህ አይነቱን አስተሳሰብ እስከዛሬ የት ደብቀኸው ነው የኖርኸው? በእውነት ነው የምልህ እንዲህ ገንዘብ እያላት የምትለምን ከሆነ  ልትወገዝ ይገባታል” አለ ሌላኛው፡፡ “ተወው እባክህ የልመና ሱሰኛ ያደረግናቸው እኛው ነን፡፡ ለለመነ ሁሉ እጅ ስንዘረጋ እየዋልን፡፡ ለደካማ፣ ምንም ለሌለው ሰው እኮ መመጽወት በሰማይ ቤትም ዋጋ ያስገኛል፡፡ ለእንደዚህ አይነቷ መስጠት ግን ምንም አይነት ዋጋ አያስገኝም፡፡ ስለዚህ የምንመጸውተውን ሰው ማወቅ አለብን” አለ፡፡ ሴትዮዋ የእኛን ሰልፍ ለግል ጥቅሟ እንደቀየረችሁ ገባኝ፡፡ ያው ሰልፉን አሰልፋ ትለምናለች ተራችን ደረሰ “ስለእመብርሃን አምስትም አሥርም ጣሉልኝ” አለች፡፡ “ምነው ሴትዮ! ቤትዎን፣ ወፍጮዎን የት ጥለው ነው እዚህ በኪራይ ቤት የምንጨማደድ ድሆችን የሚለምኑ? ሃብታም ብንሆን ኖሮ ገንዘብ ቢኖረን ኖሮ እኮ እዚህ ተሰልፈን አያገኙንም ነበር፡፡ የራሳችንን መኪና ገዝተን በዚያ እንጓዝ ነበር፡፡ እማማ በጣም ካላስቸገርንዎ እኛን ቢያልፉን ደስ ይለናል፡፡ ልመናን ሱሱ ካደረገ ሰው ጋር መነጋገር ያስጠላኛል” አላቸው፡፡ ይህን እንደሰሙ “ለካ ቤት እንዳለኝ፣ ወፍጮም እንዳለኝ ታውቆብኛል? ብለው ሌላውን ሰልፈኛ ሳይጠይቁ “እግዚአብሔር ይስጥልኝ” ብለው ዘወር አሉ፡፡ ለካ ከመመጽወታችን በፊት ስለምንመጸውተው ሰው ማወቅ ያስፈልጋል ማለት ነው ብየ ለራሴ ትምህርት ተማርኩ፡፡ አሁን ከብዙ ቁመት በኋላ ተራችን ደርሶ ታክሲ ውስጥ ገባን፡፡

No comments:

Post a Comment