Thursday, July 31, 2014

ድንግል ማርያምና መናፍቃን /የመጀመሪያ ክፍል/


እመብርሃን ድንግል ማርያም
የበኩር ልጇን እስክትወልድ ድረስ ዮሴፍ አላወቃትም/ማቴ1:25/
ይህን ቃለ ንባብ በራሱ ምንገድ ተርጉሞ ኑፋቄውን የጀመረው ሔልቪዲስ ሲሆን የኑፋቄው አስተሳሰብ “ድንግል ማርያም የበኩር ልጇን ኢየሱስ ክርስቶስን ከወለደች በኋላ በግብር አወቃት ልጆችንም /የጌታ ወንድሞች የሚባሉትን ማለት ነው/ ከዮሴፍ ወልዳለች” የሚል ነው፡፡ ሊቃውንቱ “አወቀ” የሚለውን ቃል በሁለት መልኩ ይፈቱታል፡፡
1.      አወቀ----› በግብር ማወቅን/ሩካቤን/ ያሳያል
ለምሳሌ፡- “አዳምም ሚስቱ ሔዋንን አወቀ ጸነሰችም ቃንንም ወለደች” ዘፍ4፡1
“ሕልቃና ሚስቱን ሐናን አወቃት፣ እግዚአብሔርም አሰባት የመጽነሷም ወራት ካለፈ በኋላ ሐና ወንድ ልጅ ወለደች” 1ኛ ሳሙ1፡19-20
ከእነዚህ ጥቅሶች እንደምንረዳው “ማወቅ” ማለት በሩካቤ ሥጋ መተዋወቅን የሚያሳይ ነው፡፡
2.     አወቀ-----› ተገነዘበ፣ተረዳ፣አስተዋለ የሚለውን ትርጉም ይይዛል
ለምሳሌ፡- “የሁለቱም ዓይኖች ተከፈቱ እነርሱም እራቁታቸውን እደሆኑ አወቁ የበለስንም ቅጠሎች ሰፍተው ለራሳቸው ግልድም አደረጉ” ዘፍ3፡7
“ዳሩ ግን በዚያ ስፍራ  ሕዝብ ስለነበሩ ኢየሱስ ፈቀቅ ብሎ ነበርና የተፈወሰው ሰው ማን እንደሆነ አላወቀም” ዮሐ5፡14
በእነዚህ ሁለት ጥቅሶች ደግሞ “ማወቅ” የሚለው ቃል መረዳት፣ ማስተዋል፣ መገንዘብ የሚለውን ትርጉም ይሰጣል፡፡
ለሁለቱም የአተረጓጎም ስልቶች በርካታ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎችን መስጠት የሚቻለ፤ ቢሆንም የቃሉን ትርጉም ለመረዳት ያህል እነዚህ በቂዎች ናቸው፡፡
መናፍቃን “የበኩር ልጇን እስክትወልድ ድረስ ዮሴፍ አላወቃትም” የሚለውን ቃል በመጀመሪያው አፈታት /ማለትም ሩካቤ በሚለው/ ይተረጉሙታል፡፡ በማቴ 13፡53-55 ያለውን ምንባ በመጥቀስም እመቤታችን ከዮሴፍ ልጆች ወልዳለች ይላሉ፡፡ ምንባቡ እንዲህ የሚል ነው “ይህን ጥበብና ተአምራት ከወዴት አገኘው? ይህ የጸራቢ ልጅ አይደለምን? እናቱስ ማርያም ትባል የለምን? ወንድሞቹስ ያዕቆብና ዮሳ ስምዖንም፣ ይሁዳም አይደሉምን? እህቶቹስ በእኛ ዘንድ ያሉ አይደሉምን?” ማቴ 13፡53-55
በመጀመሪያ ይህን የተናገሩት እነማን ናቸው? ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን አይደሉምን? ታዲያ እነርሱ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት ያልተረዱ የተናገሩት ተራ ወሬ እንደ ማስረጃ ሊጠቀስ እንዴት ይቻላል? ሊቃውንቱ “አላወቃትም” የሚለውን ሲተረጉሙ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክርስቶስን በጸነሰች ጊዜ ኅብረ መልኳ ለዮሴፍ ይቀያየርበት ነበር የበኩር ልጇን ከወለደች በኋላ ግን በአንድ ኅብረ ምልክ ሆና መልኳን ማወቅ መቻሉን ያስረዳሉ” ሊቁ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው “ኦ ድንግል አኮ ለዮሴፍ ዘተፍኅርኪ ለተቃርቦ አላ ይዕቀብኪ ንጹሐ”---› ‹‹ ድንግል ሆይ ለዮሴፍ የታጨሽ ለመገናኘት አይደለም በንጽሕና ሊጠብቅሽ ነው እንጅ›› ይላል፡፡ ዮሴፍ ዕድሜው ከ 50 የተረፈ ከ 60 ያለፈ ነበር፡፡ ስለዚህ እርሱ በዚያ ዕድሜው በንጽሕና ሊጠብቃት እንጅ ለጋብቻ አይደለም እጮኛ የሚለው፡፡ መታጨት ለጋብቻ ብቻ አይደለም ለሹመት፣ ለምርጫም ያገለግላል፡፡ ለምሳሌ እጩ ወታደር፣ እጩ መኮንን፣ እጩ ምልምል፣ እጩ ተወዳዳሪ ወዘተ እንደማለት ያለ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ሲገልጽ “ለእግዚአብሔር ቅንነት አቀናችኋለሁና እንደ ንጽሕት ድንግል እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁና” 2ኘ ቆሮ 11፡2 በዚህ አገባብ  “አጭቻችኋለሁና” የሚለው ቃል ጋብቻን የሚያሳይ አይደለም፡፡ ስለዚህ ዮሴፍ “አላወቃትም” የሚለው በግብር ማወቅን የሚተረጉም አይደለም፡፡ “የጌታ ወንድሞች” የሚላቸውና “በኩር” የሚለውን ቃል ትርጉም በሚቀጥለው ክፍል እናያለን፡፡
ይቆየን
አሜን፡፡

No comments:

Post a Comment