Wednesday, July 30, 2014

ራስን አለማዎቅ

ራስን አለማዎቅ ትልቅ በሽታ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ራሳቸውን አለማዎቃቸው የሚገባቸው እጅግ በጣም ዘግይቶ ነው፡፡በከፋ ችግር ውስጥ ሲዘፈቁ ወይም ደግሞ አቻዎቻቸው ከእነርሱ ቀድመው ትልቅ ደረጃ ሲደርሱ ያን ጊዜ ራሳቸውን እንዳላዎቁ ይገባቸዋል፡፡ አንድ ሰው ብዙ ገንዘብ በሚያስገኝ ትልቅ ውድድር ላይ ይሣተፋል፡፡ ውድድሩ እንዲህ ነው ውኃ እና ሌሎች መጠጦችን ሳይጠጡ ለ4 ተከታታይ ቀናት ያህል በየቀኑ አንድ አንድ ኪሎ ጨው በመመገብ ለፈጸመ 10 ሚሊዮን ብር ሽልማት የሚያገኝ ሲሆን ውድድሩ ከተጀመረ በኋላ ከ4ኛው ቀን በፊት ውኃ ወይም ሌላ መጠጥ የቀመሰ ግን አውራ ጣቱን ሊቆረጥ የሚል ነው፡፡ ታዲያ ራሳቸውን ያላዎቁ ብዙዎች የ 10 ሚሊዮን ብር ተሸላሚ ለመሆን ተስማተው ለውድድሩ ተራ ይዘዋል፡፡ እነዚህ ተወዳዳሪዎች ሳይንስን ከራሳቸው በላይ ያውቁታል፡፡ ሳይንስ እንደሚለው የሰው ልጅ ያለውኃ 7 ቀናት መቆየት ይችላል፡፡ ይህን የሳይንሱን ሃሳብ የሚጋሩና በሚገባ የሸመደዱ ተወዳዳሪዎች ከውድድሩ አዳራሽ ውስጥ ተሰልፈዋል፡፡ የውድድሩ የመጀመሪያ ቀን ደረሰ እና ለተወዳዳሪዎች በየስማቸው አንድ አንድ ኪሎ ጨው ከአንድ አንድ ሊትር ውኃ ጋር ተሰጣቸው፡፡ ሁሉም አንድ ብለው ጀመሩ፡፡ 1 ኪሎ ጨው ለ 1 ቀን የሚለውን የውድድሩ መርኅ አክብረው ለ2ኛው ቀን ደረሱ፡፡ አሁንም እንደተለመደው ጨውና ውኃ ተሰጣቸው፡፡ አንዳንዶች ግን ውድድሩ በጣም እየከበዳቸው መጥቷል፡፡ አሁን ሳይንሱን ረስተው ራሳቸውን አስታወሱ፡፡ የወደቀ የተረሳ የወደቀ ማንነታቸውን ማንሣት ጀመሩ፡፡ የተሰጣቸውን ውኃ ማሽተት የጀመሩም አሉ፡፡ እንዳይጠጡ የአውራ ጣታቸው ጉዳይ አስቸገራቸው፡፡ ስለአውራ ጣታቸው ይህን ቀን እንደምንም ታገሱ፡፡ የ 3ኛው ቀን ውድድር ተጀመረ፡፡ አብዛኞቹ የመጣው ይምጣ ብለው የተሰጣቸውን ውኃ መጠጣት ግዴታ ሆነባቸው፡፡ በገቡት ውል መሠረት አውራ ጣታቸውን እተቆረጡ ከውድድሩ ተሰናበቱ፡፡ ጥቂቶች ግን የአውራ ጣታቸውን ጉዳይ በማምሰልሰል በጨው ብዛት አንጀታቸው ተቃጠለ፡፡ 3ኛውን ቀን ታገሰው ወደ ፈጻሜው 4ኛ ቀን ሊሸጋገሩ ባለመቻላቸው ሆዳቸው ተቃጥሎ ነፍሳቸው አለፈች፡፡ አሁን ይህ ከባድና የከፋ ችግር ሲደርስባቸው ራሳቸው እነማን እንደሆኑ ተረዱ፡፡ ለእነዚህ ሰዎች ጣት መቆረጥና ነፍስ መጥፋት ምክንያት የሆናቸው ራሳቸውን አለማዎቃቸው ነው፡፡ ታዲያ ጣታቸውን ከተቆረጡት ሰዎች መካከል አንዱ እንዲህ አለ ይባላል፡፡ “ወይኔ ወይኔ ተቆረጠ ጣቴ ወይኔ እያየ ዓይኔ” ሌላኛው ደግሞ እንዲህ አለ “ለእነ እገሌ መሞት ለእኔ ጣት መቆረጥ ራስን አለማዎቅ መሆኑን አዎቅሁት” አያችሁ ወገኖቼ! እነዚህ ተወዳዳሪዎች የተመለከቱት ከውድድሩ በኋላ የሚያገኙትን ሽልማት ነው፡፡ ነገር ግን ያን ሽልማት ለማግኘት እኔ ብቁ ነኝ ወይ? የሚለውን ጥያቄ መመለስ አልቻሉም፡፡ ወደ ራሳቸው መልሰው ያለውኃ አራት ቀን መቆየት መቻል አለመቻላቸውን ማዎቅ የማንም ድርሻ አይደለም የራሳቸው ድርሻ ነው፡፡ ስለራሴ ማዎቅ የሚገባኝን ነገር ማዎቅ ያለብኝ እኔ እንጅ ሌላው አይደለም፡፡ አንዳንዶች ሲመክሯቸው ራሳቸውን ያዎቁ እየመሰላቸው “ከራሴ በላይ ለእኔ የለም” እያሉ በዝሙት አልጋ እንደወደቁ በአስከፊ በሽታ ሲማቅቁ ሰው ሁሉ ሲያገልላቸው፣ መሳቂያ መሳለቂያ ሲያደርጋቸው ያን ጊዜ “ወይኔ ይህን ባላደርግ ኖሮ” ይላሉ፡፡ በሽታው ከያዘህ በኋላ ራስህን ብታውቅ ምን ዋጋ አለው በፊት ነበር እንጅ፡፡ በእርግጥ አሁን ላይ ሆነህም ቢሆን ራስህን ማዎቅህ ጥሩ ነው፡፡ በፊት ራስህን ሳታውቅ የሠራኸው ሥራ ትልቅ ዋጋ እንድትከፍል አድርጎሃል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሁሉን አውቀናል ብለን ሳለ የሚመጡብንን ጥያቄዎች መመለስ ከማንችልበት ደረጃ ላይ ስንደርስ ቆም ብለን “ለካ ይህን አላውቅም ነበር” እንላለን፡፡ አያችሁ ገና አሁን ነው ራሳችንን ያወቅነው፡፡ አብሮን እየኖረ እኛም አብረነው እየኖርን ራሳችንን ራሳችን ማዎቅ ካልቻለ በጣም አደጋ ነው፡፡ አንድ ከጓደኛው እየኮረጀ ጥሩ ውጤት የሚያመጣ ተማሪ ያ ውጤት የራሱ አለመሆኑን የሚረዳው ብቻውን ተፈትኖ ብቻውን ተወዳድሮ ማለፍ አልችል ሲል ነው፡፡ አንድ አስተማሪ ራሱን አለማዎቁ የሚገባው ተማሪዎቹ የሚጠይቁትን ጥያቄ በአግባቡ መመለስ አልችል ሲል ነው፡፡ አንድ እስከ 6 እና 7 ሰዓት ድረስ በመጾሙ ራሱን የበቃ አድርጎ የሚቆጥር ሰው ራሱን አለማዎቁ የሚገባው ጓደኞቹ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረት እስከ ዘጠኝም እስከ አሥራ አንድ ሰዓትም ከዚያም በላይ እንደ ጾሙ ሁኔታ ሲጾሙ ሲመለከት ነው፡፡ አንድ ራሱን ምሉእ አድርጎ የሚቆጥር ሰው ምሉእ አለመሆኑን የሚረዳው መናፍቃን ሲነሡ መርታት አላውያን ሲነሡ መጽናት ሲያቅተው ነው፡፡ አንድ እንደምንም ቁጭ ብድግ እያለ ለ 10 ደቂቃ ያህል የነግህ ጸሎት ብቻ በማድረጉ ራሱን እንደ ጻድቅ የቆጠረ ሰው ሰባት የጸሎት ጊዜያት እንዳሉ የተረዳ ቀን ወይም ቅዳሴ ያስቀደሰ ቀን ራሱን ማዎቅ ይጀምራል፡፡ አንድ አርብ ረቡዕን ብቻ በመጾሙ ራሱን ከብቃት ደረጃ ላይ ያስቀመጠ ሰው ራሱን ማዎቅ የሚጀምረው ሰባቱን አጽዋማት መማር ከቻለ ነው፡፡ አንድ መጽሐፍ ቅዱስን አንብቤ ተረድቼዋለሁ በማለት ራሱን እንደ ትልቅ የሚቆጥር ሰው ራሱን አለማዎቁ የሚገባው ቃሉን በተግባር መቀየር አልችል ብሎ “እርሱን ብሎ ክርስቲያን” ብለው ሰዎች ሲመጻደቁበት ነው፡፡ አዳምና ሔዋን ምክረ ከይሲን ሰምተው አምላክ ለመሆን ሽተው እፀ በለስን በበሉ ጊዜ የጸጋ ልብሳቸው በተገፈፈና እርስ በርሳቸው ተፋፍረው በተሸሸጉ ጊዜ ለማንነታቸው ጥያቄ መልስ አግኝተዋል፡፡ ራሳቸውን በሚገባ ባለማዎቃቸው ራሳቸውን መሆን ያቃታቸው አዳምና ሔዋን የሠሩት ስህተት ገነትን ያህል ቦታ እግዚአብሔርን ያህል ጌታ አሳጥቷቸዋል፡፡ ለ5500 ዘመናትም በእግረ አጋንንት እንዲጠቀጠቁ አድርጓቸዋል፡፡ ራሳቸውን ያዎቁት ከዚህ ሁሉ ውድቀትና መከራ በኋላ ነው፡፡ የማንነትን ጥያቄ በሚገባ መመለስ ትልቅነት ነው፡፡ በዚህ ዘመንም የተሻለ ሰው ሆኖ ለመገኘት ራስን ማዎቅ ትልቅ ቦታ አለው፡፡ እኔ ማነኝ ብለን ራሳችንን ብንፈትሸው እንደ ሳጥናኤል ሐሰተኛ፣ እንደ ፈርዖን ትዕቢተኛ፣ እንደ አዳምና ሔዋን ትዕዛዝ የምናፈርስ፣ አምላክ መሆንን የምንሻ፣ እንደ ቃየን ወንድማችንን የምንገድል፣ እንደ ጎልያድ ትምክህተኛ፣ እንደ ይሁዳ አምላካችንን በገንዘብ የምንለውጥ ገንዘብ አምላኪዎች፣ እንደ ሎጥ ሚስት ወደ ኃጢአት ከተማ ፊታችንን የምናዞር፣ እንደ አይሁዳውያን አምላካችንን የምንሰቅል ሰዎች ነን፡፡ ነገር ግን ራሳችንን ለማዎቅ ትኩረት ባለመስጠታችን ብዙ ጉዳቶችን በማስተናገድ ላይ እንገኛለን፡፡ የዘመኑ ሰማእትነት ራስን ማዎቅ ይመስለኛል፡፡ ለማንኛውም ሥራ መሠረቱ ራስን ማዎቅ ነው፡፡ ስለዚህ አሁን እኛ ማድረግ የሚገባን ነገር ቢኖር ራስን መፈለግና ማዎቅ ከዚያም ራስን መሆን ነው፡፡ ይህንን ለማድረግም አምላከ ቅዱሳን ወደ ማንነታችን መልሶ ራሳችንን አውቀን በትሕትናና በመታዘዝ እንድንኖር ይርዳን፡

No comments:

Post a Comment