Wednesday, July 30, 2014

ግልጥ ሥውር

“ኧረ የእንደሻው ነገር እንዴት ነው?” አለ አንድ የእንደሻው ጓደኛ፡፡ “የሰፈሩ ሰው ሁሉ ሥሙን ቀይሮታል እኮ” አለ ሌላኛው፡፡ “ማን አሉት?” አለ ለመስማት ጆሮውን እየኮረኮረ፡፡ “እንዴ! አልሰማህም ማለት ነው ግልጥ ሥውር እያሉ ነው የሚጠሩት” አለ፡፡ ሥሙን ከምን አንጻር እንደሰጡት የተረዳ ይመስላል፡፡ ራሱን ነቀነቀና “ልክ ነው ይህ ሥም ይገባዋል፡፡ እኛ በግልጥ ብናየው፣ አብሮን ቢውል፣ አብሮን ቢያወራ እርሱ ግን ሥውር ነው፡፡ የሚገርም ሥም! የተቃራኒ ቃላት ጥምርታ ግ-ል-ጥ-- ሥ-ው-ር” አለ ፊደላቱን አንድ በአንድ በቀስታ ረገጥ እያደረገ፡፡ ሌላኛው ተቀበለ “የሰፈሩ ሰዎች ሁሉ የሚጠሩት በዚህ ሥም ነው፡፡ እኔም እንደሰፈር አባልነቴ በዚሁ ነው የምጠራው፡፡ እንደሻውም አምኖበታል መሰለኝ አቤት ይለናል፡፡ ደግሞም እኮ ማንነቱን የሚገልጽ ትክክለኛና ተገቢ ሥም ነው፡፡ ይህን ሥም ያወጣለትን ሰው ባጣም አድንቄያለሁ፡፡ እንደሻው ማለት እኮ እንደፈለገው፣ እርሱ እንዳለ፣ እንደፍላጎቱ በፈለገው አቅጣጫ የሚሄድ፣ የፈለገውን ሁሉ የሚያደርግ እንደማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከሥራው ጋር በፍጹም የሚገናኝ ሥም አይደለም፡፡ ግልጥ ሥውር ያሉትም ሥራውን አይተው ይመስለኛል፡፡ እኔም ብሆን የተቃራኒ ቃላትን ጥምርታ የያዘ ሥም አይሁን እንጅ ሥም ባወጣለት ደስ ይለኝ ነበር፡፡ እንደሻው ብዬ ለመጥራት እሰቀቅ ነበር፡፡ ሥራው ሌላ ሥሙ ሌላ ነው የነበረው፡፡ ይህ አዲስ ሥም ግን የሚገባው ነው” አለ፡፡ ራሱን ነቀነቀና ጣቱን አፋተጋቸው “በጣም ይገባዋል እንጅ፡፡ ጫማ ቢሰፋ፣ ጸጉሩ ቢንጨፈረር፣ ሱሪው ቢተለተልም በልቡ ያለው ንጹህ እምነት ሥውር አድርጎታል፡፡ ይገርምሃል ጫማ ሲሰፋ ውሎ ያገኘውን ገንዘብ ትንሽ ሳያስቀር ለነዳያን እና ለቤተክርስቲያን ይሰጣል፡፡ ይህን ሥራውን ለማንም አይነግርም፡፡ እኔ ራሱ አንድ ቀን ነው ይህን ያረጋገጥኩ፡፡ ያገኘውን ገንዘብ ሁሉ መጽውቶ ሆቴል ለምኖ ትርፍራፊ ተመግቦ ያድራል፡፡ ይህ ብቻ በራሱ ሥውር አያሰኘውም እንዴ ሌላው የጽድቅ ሥራው እንኳ ቀርቶ፡፡” አለ፡፡ በንግግሩ የተስማማ ሌላኛው ቀጠለ “ልክ ነህ፡፡ እኔስ ይህም ያንሰዋል ባይ ነኝ፡፡ ሰው ሁሉ የሚያየው ጫማ ሰፍቶ ገንዘብ ተቀብሎ በኪሱ ሲያስገባ ነው እንጅ ገንዘቡን ሲመጸውት አይደለም፡፡ ይህን ተግባሩን በሥውር ነው የሚያደርገው፡፡ በጸጉሩ መንጨፍረር ስንቱ ከሰው በታች ይቆጥረዋል መሰለህ፡፡ ጫማ የሰፋለት ቀለም የቀባለት ሰው ሁሉ የጸጉርህ መስተካከያ ይሁንህ እያለ ገንዘብ ትቶለት ይሄዳል፡፡ እርሱ ግን ያው ነው አይስተካከለውም፡፡ አሁን ሲገባኝ ነው እኔም ጸጉርህን ተስተካከለው ማለቴን ያቆምኩ፡፡ በዚህ ሁሉ ያገኘውን ገንዘብ ለድሆች ይመጸውተዋል፡፡ አየኸው ሥውርነቱን፡፡ ይህን ሥውርነቱን የምናውቅ እኔና አንተ ብቻ ነን፡፡ የሰፈሩ ሰው ይህን ሥም የሰጠው በቤቱ ውስጥ ባለው አልጋ ነው፡፡” ሌላኛው ንግግሩን አቋረጠውና “ይቅርታ በማቋረጤ እንጅ አልጋው ደግሞ ምን ተአምር ሠራ ነው የምትል?” አለው፡፡ ንግግሩን ካቆመበት ቀጠለ “አንድ የሰፈሩ ሕጻን በቤቱ በር ቀዳዳ አጮልቆ እንደሻው ወደ አልጋው ሄዶ አልጋዬ በይ ደህና ሁኝ አንች ላይ በምቾት ማደርን አልፈልግም፡፡ የሚያድርብሽን ሰው ስትራቢ ትኖሪያለሽ እንጅ በፍጹም አላድርብሽም፡፡ አንች ለሥጋዬ እንጅ ለነፍሴ ምንም ጥቅም የለሽም፡፡ ብሎ አልጋውን ተሰናብቶ ወደ ሳሎን ተመልሶ ከወለሉ ላይ በሰላም አሳድረኝ ብሎ ሲተኛ በተደጋጋሚ እንደተመለከተው ለሰፈሩ ሰዎች ያወራል፡፡ እርሱ ግን ይህን ሁሉ አልሰማም፡፡ ወዲያውም ግልጥ ሥውር የሚለውን ሥም ሰጡት፡፡ ያ የሚያምር አልጋው እኮ ለማንም የሚታይ ግልጥ ነው፡፡ እንደእኛ አስተሳሰብም አልጋ ለመኝታ የተሠራ ስለሆነ ተኝቶ እንደሚያድርበት ነበር የምንረዳው፡፡ ነገር ግን ግልጥ የሆነውን እርሱ ሠውሮታል፡፡ አይተኛበትማ!!!” አለ፡፡ ሌላኛው ንግግሩን ቀጠለ “እርሱ እኮ በጣም የተለየ ፍጡር ነው፡፡ ከእኛ መካከል ማንም የማያደርገውን የቅድስና ሥራ ነው እኮ የሚሠራ፡፡ ጾሙ፣ ጸሎቱ፣ ስግደቱ፣ ምጽዋቱ ቀላል መሰለህ እንዴ? እርሱ ግን እንደማይጾም፣ እንደማይጸልይ፣ እንደማይሰግድና እንደማይመጸውት ነው የሚናገረው፡፡ ባለፈው እንዲያውም ጸሎት ማለት ምን ማለት ነው ብሎ ጠይቆኛል፡፡ በጣም ይገርምሃል እኮ! የቅድስናሥራውን ሁሉ ሠውሮ ነው የሚኖረው፡፡ ታዲያ ይህን ግልጥ ሥውር ቢሉት ያንሰዋል እንጅ ይበዛበታል እንዴ? ባለፈው ደግሞ በአጋጣሚ ልብሱን ነፋስ ሲገረባው ጉድ አየሁ፡፡ ወገቡን በሰንሰለት አስሮ ነው ለካ ጫማ የሚቀባና የሚሰፋ፡፡ በጣም ተደንቄ እርሱንም ምንድን ነው ብዬ አልጠየቅሁትም፡፡ ሁሉም ነገር ሲገባኝ ገና ዛሬ ማውራቴ ነው፡፡” ሌላኛው ቀጠለ “እኛ ከእንደሻው ብዙ ነገር መማር አለብን፡፡ ነጠላ ለብሰን ቤተክርስቲያን ስለተመላለስን ብቻ ራሳችንን እንደጻድቅ እየቆጠርን አይደል እንዴ ያለነው? የእርሱን ሥራ ያህል መሥራት ባንችል እንኳ ብዙ የጽድቅ ሥራ ማንም ሳያውቅብን በሥውር ልንሠራ እንችላለን፡፡ እንደሻውን እኮ እንኳን ይህን ያህል የጽድቅ ሥራ ይሠራል ለማለት ቀርቶ በሥም ያውቃቸዋል ብሎ የሚገምተው ሰው የለም፡፡ ሰው የሚያየው በግልጥ ያለውን አለባበሱን ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ከእርሱ ልንማር ያስፈልጋል፡፡ በከንቱ ውዳሴ ስንቱ ያልሠራውን የቅድስና ሥራ እንደሠራ አስመስሎ ይናገራል መሰለህ፡፡” አለ፡፡ ሌላኛው ቀጠለ “ልክ ነህ፡፡ እኛም ቢሆን ከከንቱ ውዳሴ ርቀን የቅድስና ሥራዎችን በሥውር ልንሠራ ይገባናል፡፡” አለ፡፡ በዚህ ሃሳብ ተስማሙ፡፡ የቅድስና ሥራዎችንም በሥውር ሊሠሩ ለየግላቸው ቃል ገቡ፡፡ ከንቱ ውዳሴ ተገቢ እንዳልሆነ ተነጋግረው የጽድቅን ሥራ በሥውር ሠርተው ግልጥ የሆነውን በረከት ለመቀበል እና “ግልጥ ሥውር” ተብለው እንዲጠሩ የሚያደርገውን የጽድቅ ሥራ ለመሥራት ወስነው ተለያዩ፡፡

No comments:

Post a Comment