Thursday, July 31, 2014

፩ አንድ

“፩ ማለት ሁለት መሆን አይቻልም ማለት ነው እንዴ?” አለ ዮናስ፡፡ ዳዊት ቀጠለ “ምን ለማለት ነው አልገባኝም?” አለው፡፡ “አልሰማህም እንዴ? የኢትዮጵያ  ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አንዲት አገር አንዲት እምነት እያለች የእምነት ነጻነትን ተጋፍታለች ተብላ ተከሰሰች እኮ” አለ ዮናስ፡፡ ዳዊት ቀጠለ “መጀመሪያ ከሳሹ ያልተባለውን ነው ያለው፡፡ አንድ ጌታ፣ አንዲት ጥምቀት፣ አንዲት እምነት የሚል መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል ነው፡፡ እዚህ ክፍል ላይ አንዲት አገር የሚል የለውም ቢል እራሱ ኢትዮጵያ ስንት አገር ናት ፩ አይደለችም እንዴ? ለማንኛውም ኤፌ4፥4 ን ያንብቡና ክሳቸውን ያስተካክሉ” አለ ዳዊት፡፡ ዮናስ ቀጠለ “የእኔም ጥያቄ ይህ ነበር እኮ አንድ ሰው አንድ እምነት አንድ አገር ነው የሚኖረው ይህ ተፈጥሯዊ ግዴታ ነው፡፡ በአንድ ጊዜ እስላምም ክርስቲያንም መሆን አይችልም አንዱን መምረጥ አለበት፡፡ አንድ ጊዜ ኢትዮጵያዊም ኤርትራዊም መሆን አይችልም አንዱን መምረጥ አለበት፡፡ አንድ እምነት ማለት ሌላ ሁለተኛ እምነት ሊኖር አይገባውም ማለት አይደለም፡፡ ከሳሾች ያልገባቸው ይህ እውነታ ብቻ ነው እንጅ ቢገባቸው ኖሮ እኛ ያልነውን እነርሱም ይሉት ነበር” አለ፡፡ ዳዊት ማብራራት ጀመረ “አንተ እንዳልከው ፩ እምነት ማለት ሁለተኛ እምነት ሊኖር አይገባውም ማለት አይደለም፡፡ ምን ይመለከተናል እኛ ድንጋይ፣ ዕፅዋትን፣ ፀሐይ፣ ጨረቃን ቢያመልክ? ማንም ሰው የመሰለውን ማምለክ ይችላል መብቱ ነው፡፡ ነገር ግን የሚያመልከው አንድ ነገር ነው፡፡ ስለዚህ አንድ እምነት ቢል ማንም አይቃወመውም አንድ እምነት ነዋ ያለው፡፡ አንድ እምነት አለኝ ሲል ግን ብዙ ቁጥር ያለው እምነት በል ተብሎ ሊገደድ አይገባውም፡፡ እርሱ አንድ ነዋ! አንድ ወንድ አንድ ሚስት አለችኝ ቢል የግድ ሁለት ሚስት በል ይባላል እንዴ? አንድ ወንድ ለአንድ ሴት ማለትስ ወንጀል ነውን? የፈለገው ቁጥር ወንድ ለፈለገው ቁጥር ሴት በል ተብሎ ሊከሰስ ነውን?” አለ፡፡ ዮናስ በዳዊት ንግግር ላይ ቀጠለ “ልክ ነህ ዳዊት ወንዶች ተሰብስበው አንድ ወንድ አንድ ሚስት ቢሉ ሊከሰሱ ነው ማለት ነው? እና አንድ ወንድ ስንት ሚስት እንዲኖረው ነው የሚፈለገው ፩ አይደለም እንዴ? ነው ወይስ የፈለገው ቁጥር ያላቸው ሚስቶች ይፈቀዱለታል ማለት ነው? ከሳሾች ያልገባቸው ብዙ ነገር አለ፡፡ ሲገባቸው ግን እነርሱም እንደእኛ ማለታቸው አይቀርም፡፡” አለ፡፡ “ቆይ እንጅ ግን አንድ ጌታ፣ አንዲት ጥምቀት፣ አንዲት እምነት አትበሉ የሚባለው መጽሐፍ ቅዱሳችንን ሰርዘን ነው ወይስ አቃጥለን፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ነው እኮ! ማንም ስላለ የምንፍቀው አይደለም፡፡ እግዚአብሔርን ስናመልክ አብሮ የተሰጠን የፈጣሪ ቃል ነው፡፡ ይህን መስማት የማይፈልግ ፈጣሪን ይክሰስ እንጅ እኛ በሕይወት እስካለን ድረስ ለዚህ ቃል እንገዛለን፡፡” አለ ዳዊት፡፡ ዮናስ ቀጠለ “እነርሱ የፈሩት ፩ ማለት ሁለት መሆንን ይቃወማል ብለው መሰለኝ፡፡ ይህ እኮ ቀላል አማርኛ ነው እንዴት አልተረዱትም ግን? የሰው ልጅ ሁለት ጾታዎች ነው ያሉት ሴት ወይም ወንድ፡፡ ወንዱ አንድ ጾታ ነው ያለው ሴቲቱም እንዲሁ፡፡ የሰው ልጅ ሁሉ አንድ ጾታ እያለ ሰላማዊ ሰልፍ ቢወጣ ማነው የሚከሰው? ሁለት ጾታ እና ከዚያ በላይ ያላቸው ሰዎች ወይስ ጾታ የሌላቸው ሰዎች? ማንም አይከስም፡፡ ምክንያቱም አንድ ሰው አንድ ጾታ ብቻ ነውና ያለው፡፡ እምነትም እንዲሁ ነው፣ አገርም እንዲሁ ነው፡፡ አንድ ሰው ፩ እምነት ፩ አገር ብቻ ነውና ያለው” አለ፡፡ “ምኑ እንደተሰወረባቸው አልገባኝም፡፡ ከሳሾች ስንት እምነትና ስንት አገር እንዳላቸው ግራ ገባን እኮ፡፡ ኢትዮጵያ አንድ መሆኗን አጠራጠሩን፡፡ ኢትዮጵያ ለእኛ አንድ አገር ነበር የምትመስለን ለካ ብዙ አገር አድርገዋታል?” አለ ዳዊት፡፡ “፩ አምነት በአንድ አገር ውስጥ የሚል አቋም ቢኖረን ኖሮ ኢትዮጵያ አንድ እምነት ብቻ በነበራት ወቅት የመጡትን የእስልምና እምነት ተከታዮች በእንግድነት ማን ይቀበላቸው ነበር? በእንግድነት ከተቀበልን በኋላስ ግድ የእኛን እምነት ካልተከተላችሁ ብለናቸዋል እንዴ? በፍጹም እንዲህ ያላቸው የለም፤ ብለውናል ያለ ካለም ይመስክር፡፡ እንድ ጌታ፣ አንዲት ጥምቀት፣ አንዲት እምነት የሚለው ቃል ያን ጊዜም ነበር እኮ ነገር ግን ትርጉሙ እንደከሳሾች ያለ ስላልሆነ ነው ዝም ብለን ከእነእምነታቸው የተቀበልናቸው” አለ ዮናስ፡፡ “ልክ ነሀ ዮናስ! አሁንም ቢሆን ፩ እምነት ፩ አገር የምንለው አንድ ሰው አንድ እምነት አንድ አገርም ብቻ ይኑረው ማለት ነው፡፡ ያች አንዲት እምነት ማናት? አንዲት አገርስ ማናት? ላለ መልሱ ለየግሉ ነው፡፡ ለእኔ ፩ እምነት የምለው ኦርቶዶክስ ተዋሕዶን ነው፤ ፩ አገርም የምለው ኢትዮጵያን ነው፡፡ ለሌላው ደግሞ ፩ እምነት ፩ አገር የሚለው ሌላ ነው፡፡ ስለዚህ ይህን መረዳት ያስፈልጋቸዋል” አለ ዳዊት፡፡ በዳዊት ሃሳብ ተስማምተው ተሰነባበቱ፡፡
፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠

No comments:

Post a Comment