Monday, September 15, 2014

ተሐድሶ መናፍቃን ክፍል ሁለት

ቤተ ክርስቲያንስ ሄዋን ናት
አንድ የተሐድሶ ሰባኪ “ያረጀችው ቤተ ክርስቲያን አሮጊቷ ሣራ ወለደች፡፡ እኔን ወለደች፣ እገሌን ወለደች፣ እገሊትን ወለደች” እያለ ተሐድሶ የወለደቻቸውን ይዘረዝራል፡፡ ቤተክርስቲያን አሮጌ መባሏ ያበሳጨው የተዋሕዶ ልጅ ወደ “ሰባኪው” ተጠግቶ “መጽሐፍ ማንበብ ይቀርሃል ሣራ በእርጅናዋ ወራት የወለደችው አንድ ልጅ ይስሐቅን ብቻ እንደነበር አላወቅህም እንዴ? አሮጊቷ ሣራ እኔን፣ እገሌን፣ እገሊትን ወለደች እያልህ የምትቀባጥር፡፡ ቤተ ክርስቲያንስ አሮጊት ሣራ ሳትሆን ቀድሞ የነበረች መንታ መንታ የምትወልድ የብዙዎች እናት ሄዋን ናት፡፡፡ የግል ክብርህን ፈልገህ ደግ ይስሐቅን ነኝ ለማለት ክብርት ቤተክርስቲያንን ዝቅ ዝቅ ያደረግህበት ይህ ደፋር አንደበት በደሙ በመሠረታት በክርስቶስ ፍርድ ወንበር ፊት ስትቆም ምን ይናገር ይሆን?” በማለት ብዙ ትምህርት አስተማረው፡፡
ሥርዓቷ ሳይሆን ሕንጻዋ
አንድ መናፍቅ “ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ያረጀች ያፈጀች ናትና በአዲስ ነገር መታደስ ይገባታል፡፡” እያለ በይፋ ይናገራል፡፡ ይህን የሰሙ አንድ የቤተክርስቲያን ሊቅ መናፍቁን አስጠርተው “የምትለው ሁሉ ልክ ነው፡፡ መታደስ ያለበት ግን ሥርዓቷ ሳይሆን ሕንጻዋ ስለሆነ የማሳደሻ ገንዘብ አሰባስብ” ሲሉት ያ መናፍቅ “መታደስ የሚገባው ትምህርቷ ሥርዓቷ ነው እንጅ ሕንጻዋ አይደለም”  ይላቸዋል፡፡ ሊቁም “በል እንግዲያውስ የራስህን አእምሮ በመልካም ትምህርትና ሥርዓት አድስና ከዚያ በኋላ ብንገናኝ ይሻላል” ብለው አባረሩት፡፡
እንዘምራለን ስትናፍቀን
ተሐድሶ መናፍቃን እግዚአብሔርን የሚናፍቁበትና የማይናፍቁበት ቀንና ጊዜ አላቸው፡፡ ምክንያቱም ሲፈልጉ ዘማሪ ክርስቲያን ሲፈልጉም ታዋቂ ዘፋኝ በመሆን በተደበላለቀና በተመሰቃቀለ ሕይወት ውስጥ ስለሚኖሩ ነው፡፡ በዝማሬዎቻው ውስጥ የምንሰማው
ዛሬም የአንተ ነው አዲሱ ቀን
እንዘምራለን ስትናፍቀን
የሚል ነው፡፡ በእውነት እግዚአብሔር የማይናፈቅበት ወቅት አለን? በዚያስ ወቅት መዘመር አስፈላጊ አይደለምን? ዝማሬን የናፍቆት መግለጫ ያደረጉት፡፡ ወገኖቼ ሳናውቅ በተኩላ እየተበላን ስለሆነ መንቃት ያስፈልጋል፡፡
መዶሻ ያልያዘ ሠራዊት
ተሐድሶ መናፍቃን በስብከታቸው እና በመዝሙራቸው ውስጥ “መዶሻ ያልያዘ ሠራዊት” የሚለው መሪ ቃላቸው ሆኗል፡፡ በእውነትም መዶሻ ያልያዘ ከንቱ ሠራዊት ነው፡፡ መዶሻው ቃለ እግዚአብሔር  የሚገኘው ቤተክርስቲያን ውስጥ ስለሆነ በየቦታው ሲዞሩ ይህን ማግኘት ባለመቻላቸው ቃለ እግዚአብሔርን ያልያዘ ሠራዊት ነን ሲሉ “መዶሻ ያልያዘ ሠራዊት” ነን ይላሉ፡፡ ቃለ እግዚአብሔርን ያልያዘ ሠራዊት ደግሞ የአጋንንት ስለሆነ ከተዋሕዶ ልጆች ጋር ምንም ሕብረት የለውም፡፡
ስብከት ጋዜጠኛነት አይደለም
“እገሌ ሲናገር ሲሰብክ ልዩ ተሰጥዎና ግርማ ሞገስ አለው፡፡ስለዚህም ተሐድሶ መናፍቅ ሊባል አይገባውም” የሚሉ ደጋፊዎች በዝተዋል፡፡ እነዚህ ደጋፊዎች ያልገባቸው ነገር የድምፅ ማማር ወይም የንግግር ግርማ ሞገስ መኖር የሰባኪ መመልመያ መስፈርት ማድረጋቸው ነው፡፡ ስብከት የድምፅ ግርማ ሞገስን ብቻ መሠረት ያደረገ የጋዜጠኛነት ሙያ አይደለም፡፡ ስለዚህ የንግግር ግርማ ሞገስ ያላቸው የተሐድሶ መናፍቃን ጋዜጠኛነት መወዳደር ይችላሉ እንጅ በድምጻቸው ማማር ብቻ ተዋሕዶን ሊሰብኩ አይችሉም፡፡ ስብከት በተግባር የሚኖሩት ሕይወት እንጅ እንደ ጋዜጠኛ መናገር ብቻ አይደለምና፡፡
በጣም ይመቸኛል
“እገሌ እና እገሊት ሲዘምሩ ድምጻቸው በጣም ይመቸኛል” የሚሉ በርካታ ደጋፊዎች በዝተዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች በመዝሙሩ ውስጥ ምን መልእክት እንደተላለፈ አልተረዱም፡፡ እነርሱ የተማረኩት በዘማሪዎች የድምጽ ማማር ብቻ ነው፡፡የድምጽ ማማርን የሚደግፉ ሰዎች ደግሞ ዘፋኞችንም የሚደግፉ በመሆናቸው መዝሙርና ዘፈን የተቀላቀለባቸው በመሆናቸው “ድምጻቸው ይመቸኛል” ከማለት የዘለለ ሌላ የሚደግፉበት ቃል የላቸውም፡፡ ስለዚህ መዝሙርን በዘማሪዎች ድምጽ ማማር ብቻ ሳይሆን በውስጡ ባለው መልእክትና በዜማው የቤተክርስቲያናችን መሆን አለመሆኑን ልንገነዘበው ያስፈልጋል፡፡

No comments:

Post a Comment