Friday, July 31, 2015

ቅዱሳን ስዕላት

©መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ክፍል ሦስት
የቅዱሳን ሥዕላት አሣሣል
4.   የእመቤታችን ሥዕል፡-  የእመቤታችን ሥዕል ሲሳል እመቤታችን በቀኝ ጌታችንን በግራ እጇ ታቅፋ ነው፡፡ ይህ ያለምክንያት አይደለም የሆነው መዝ 44÷ 9 “የንጉሦች ልጆች ለክብርህ ናቸው፡፡ በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” የሚለውን ቃል መነሻ በማድረግ ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል በቀኝ ሰይፍ ይዞ ቅዱስ ገብርኤል በግራ መስቀል ይዞ ይሣላሉ፡፡ ዘላለማዊ ድንግል ናትና ጸጉሯ ሙሉ በሙሉ በአጽፍ ተሸፍኖ መሣል አለበት፡፡ የልብሷቀለም አቀባብም ከላይ ሰማያዊ ከውስጥ ደግሞ ቀይ ሆኖ ይሣላል፡፡ ቀይ ከውስጥ መሆኑ እሳተ መለኮትን በማኅጸኗ መሸከሟን ለማስረዳት ነው፡፡ ሰማያዊት ናትና ከላይ ያለው ሰማያዊ ቀለም ይደረጋል፡፡ አንድም ከላይ ሰማያዊ ከውስጥ ቀይ መሆኑ ክብሯ ሰማያዊ ያውም መልዕልተ ፍጡራን መትሕተ ፈጣሪ ከፍጡራን ሁሉ በላይ ከፈጣሪ በታች የሆነ ቢሆንም በመከራና በስደት እንጅ በተድላና በደስታ እንዳልኖረች ያስረዳል፡፡ እዚህ ላይ ጌታ አውራ ጣቷን የሚይዛት ሆኖ የሚሣልበትም አለ፡፡ ጣጦች ሁሉ ካለ አውራጣት ምንም ሊሠሩ አይችሉም፡፡ ያለ አውራጣት ይዞ ማስቀረጥ አስሮ ማጥበቅ አይቻልም፡፡ እርሷም እንዲሁ ከሁሉ በላይ ናት ካለእርሷ ምልጃ ዓለም ድኅነትን አያገኝምና፡፡ መናፍቃን ግን በብዙ መንገድ ሥዕሏን ይሥላሉ፡፡ አንደኛ ጸጉሯን በአጽፍ አይሸፍኑም ምክንያቱም ጸጉር ማሳየት ድንግልና የሌላት ሴት የምታደርገው ነውና ዘላለማዊ ድንግልናዋን ለመካድ፡፡ ሁለተኛም ቀዩን ከላይ ሰማያዊውን ከውስጥ አድርገው የሚሥሉም አሉ እሳተ መለኮት በውስጧ አላደረም ለማለት፡፡ የእመቤታችን ሥዕል ከዚህ በተጨማሪም እመቤታችን በቤተ መቅደስ ሐርና ወርቅን እያስማማች ስትፈትል በቅዱስ ገብርኤል ስትበሰር፣ ጌታን ይዛ በአሕያ ተቀምጣ ከቅዱስ ዮሴፍና ሰሎሜ ጋር ስትሰደድ ትሣላለች
5.   የቅዱሳን መላእክት ሥዕል፡- ቅዱሳን መላእክት በሁለት መልኩ ይሣላሉ፡፡ ሊቃነ መላእክት ብቻቸውን ከሆነ በሰው ሙሉ አካል መልክ መስቀልና ሰይፍ እንደያዙ ልብሰ ተክህኖ ለብሰው ይሣላሉ፡፡ መስቀልና ሰይፍ መያዛቸው ለምሕረትም ለመቅሰፍትም እንደሚላኩ ለማስረዳት ነው፡፡ ዘፍ48ን ይመልከቱ፡፡ ልብሰ ተክህኖ መልበቸው ደግሞ ዕጣን በማጠን የሰውን ጸሎት ቅድመ እግዚአብሔር የሚያደርሱ ናቸውና ነው፡፡ ራዕ 8÷4-5 “የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋራ ከመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ፡፡ መልአኩም ጥናውን ይዞ የመሰዊያውን እሳት ሞላበት ወደ ምድርም ጣለው ነጎድጓድና ድንጽም መብረቅም መናወጥም ሆነ” እንዲል፡፡ሠራዊተ መላእክት የሆኑ እንደሆነ ግን ከአንገት በላይ እና በክንፍ በክንፎቻቸውም ላይ ብዙ ነጠብጣቦች ይሣሉባቸዋል ዓይናቸው ብዙ መሆኑን ለማሣየት፡፡ አንድም ያለፈውንና የሚመጣውንና ያውቃሉና፡፡
6.   የቅዱሳን፣ የጻድቃን፣ የሰማዕታት ሥዕላት፡- መስቀልና መጻሕፍት ይዘው ልብሰ ተክህኖ ለብሰው ዓይናቸው ጎላ ጎላ ብሎ በጸሎት የተጋደሉ፣ ወንጌልን ዞረው ያስተማሩ፣ በክህነታቸው እግዚአብሔርንና ሰውን ያገለገሉ፣ በተሰጣቸው ልዩ ልዩ ጸጋ መሠረት ሁሉን የሚያውቁ መሆናቸውን የሚገልጽ ሆኖ ይሣላል፡፡ በተጨማሪም በምድር እያሉ የተጋደሉትን ተጋድሎ ዓይነትና የደረሰባቸውን ስቃይና መከራ በዚህም ትእግስታቸው ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን አክሊል እንዲያሳይ ሆኖ ይሣላል፡፡
7.   የመምህራን የሊቃውንንት ሥዕል፡- መምህራንና ሊቃውንንት ካባ ለብሰው ወንጌል ይዘው ይሣላሉ፡፡ ይህም ክብራቸውን ለማሳየት ነው፡፡ በዚህ ዓለም ዞረው ወንጌልን ለማስተማራቸው መናፍቃንን ተከራክረው ስለመርታታቸው እውነተኛዋን እምነት ስለማስተማራቸው ነው፡፡
8.   የርኩሳን መናፍስትና የአፅራረ ቤተክርስቲያን ሥዕል፡- ሌላው በቤተክርስቲያናችን የአሣሣል ዘዴ ልዩ የሆነው የርኩሳን መናፍስት አሣሣል ነው፡፡ እነዚህ ሲሣሉ የብዙ ቀለሞች ድብልቅ ሆነው፣ በዓይን በማይታይ መልኩ የሰውም የአውሬም ቅርጽ ይዘው፣ በግማሽ ፊት አንድ ዓይናቸው ብቻ እየታየ ይሣላሉ፡፡ ምክንያቱም የሃይማኖት ሕጸጽ አለባቸውና፣ ሁሉንም መርምረው አያቁምና ነው፡፡

ይቀጥላል…

1 comment:

  1. ሰላም ላንተ ይሁን።
    አንዳንድ ትምህርታዊ መልክቶችን በፌስ ቡክ ለሚከታተሉን ሼር እናደርጋለን። ነገር ግን ፌስ ቡክ ወደ ገጽህ የሚመሩትን ሊንኮች በጣም በጥርጣሬ ነው የሚያያቸው። ከዚህ በታች የምታየው መልክት ከብዙ ትንሹ ነው ...
    ... It looks like a link that you're sharing might be unsafe.
    Please remove this link:
    http://melkamubeyene.blogspot.com/2015/07/blog-post_23.html
    http://3.bp.blogspot.com/-gvbfc1ukxse

    If you're sure you want to share this link, please complete the security check below.

    ... ብሎ ይቀጥላል። ካንተ በኩል ማስተካከል የምትችለውን እባክህ አስተካክል።

    እግዚአብሔር ስራህን ይባርክ።

    ReplyDelete