Thursday, May 11, 2017

ፍኖተ እግዚአብሔር--- ክፍል ፪



© መልካሙ በየነ

ግንቦት 4/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ተጽሕፈ እም አሐዱ ሊቅ ኢትዮጵያዊ ኅሩይ ወመፈክራዊ
ጌታው አለቃ ኅሩይ


መቅድም
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሕዱ አምላክ ዘለዓለም ሥላሴ::
ንባብ :- ንጽሕፍ መቅድመ አሠሩ ወፍኖቱ ለእግዚአብሔር በረድኤት አምላካዊት ከሃሊተ ኩሉ፣ ክሂሎታኒ አኮ ባሕቲቱ በአበው ለባውያን ወማእምራን፣ አላ ዓዲ በሕፃናትኒ የዋሃን፣ በከመ ቃሉ ለእግዚእነ “አእኩተከ አባ እግዚአ ሰማይ ወምድር፣ እስመ ኀባእኮ ለዝንቱ እማእምራን ወእምጠቢባን፣ ወከሠትኮ ለሕፃናት እስመ ከማሁ ኮነ ሥምረትከ በቅድሜከ”
ትርጉም :- ከአምላክ በምትገኝ፣ ሁሉን ማድረግ በሚቻላት ረድኤት የእግዚአብሔርን የጎዳናውንና የፍለጋውን መቅድም እንጽፋለን:: ችሎታዋም በዐዋቆችና በልበኞች ብቻ አድራ አይደለም፣ አላዋቆች በሆኑ ሕፃናትም አድራ ነው እንጂ:: ጌታችን እንዲህ ብሎ እንደተናገረ “አመሰግንሃለሁ አባት ሆይ የሰማይና የምድር ጌታ፣ ይህን ከዐዋቆችና ከልበኞች ሰውረህ ለሕፃናት ገልጠኸዋልና፣ እንዲህ በፊትህ ፈቃድህ ስለሆነ” ማቴ ፲፩÷፳፭-፳፮
ንባብ :- በእንተ ዝንቱ ፈቀድነ ንጽሐፍ ኀዳጠ እምነ ብዙኅ፣ በእንተ እማሬሃ ለይእቲ ፍኖት ሠናይት:: ፍኖትሂ ሠናይት ሃይማኖት ይእቲ ብሂለ አሐዱ መለኮት ወሠለስቱ አካላት፣ ባቲ ያጽንዐነ እግዚአብሔር ሎቱ ስብሐት እስከ እስትንፋስ ደሃሪት ለዓለመ ዓለም አሜን::

ትርጓሜ:- ለሕፃናተ አእምሮ ምሥጢርን የሚገልጽ ስለሆነ የዚችን ቅን ጎዳና ነገር ለማስረዳት፣ ከብዙ በጥቂቱ ልንጽፍ ወደድነ:: መልካም ጎዳና የተባለችም ሃይማኖት ናት:: ይህችውም በአንድ መለኮት፣ ሦስት አካላት ብሎ ማመን ናት:: እስከ ጊዜ ሞት ድረስ በርስዋ ያጽናን እግዚአብሔር ምስጋና ይግባውና ለዘለዓለም አሜን:: ከጌታችን ከኢየሱስ የተገኘች ሃይማኖት አንዲት ነበረች:: ለዚኸውም ማስረጃ ሐዋርያው ዻውሎስ “ሃይማኖት አንዲት ናት” ብሎ ተናግሮአል:: ኤፌሶን ፬÷፭ ነገር ግን የሰው ጥንተ ጠላቱ ሰይጣን በአንዳንድ ሰዎች እያደረ በዓላማው ስሕተት የሃይማኖት መለያየት መጣ:: ማስረጃ ጌታችን በወንጌል
ንባብ :- “ወእንዘ ይነውሙ ሰብኡ መጽአ ጸላኢ ወዘርዐ ክርዳደ ማዕከለ ሥርናይ ወኀለፈ”
ትርጉም :- “ሰዎች በተኙ ጊዜ ጠላት መጥቶ በስንዴው መካከል እንክርዳድ ዘርቶበት ሄደ” እንዳለ ማቴ ፲፫÷፳፭
ንባብ :- “ፀጋሰ ኢትትወሀብ ዘእንበለ ለትሑታን ወፈድፋደሰ ለምኑናን ወለየዋሃን”
ትርጉም:- “የዕውቀት ሀብት ለተዋረዱ፣ ይልቁንም ለተናቁና፣ ቅንነት ላላቸው ነው እንጂ፣ ለትዕቢተኞች አትሰጥም” ዮሐንስ አፈወርቅ ድርሳን 3 ያለውን በመዘንጋቱ በፍቅርና በትሕትና ፀንቶ ወንድም ከወንድም ጋራ ሐሳብ ለሐሳብ እየተግባባ፣ በስምምነት ሃይማኖትን ወደጥንተ ቦታዋ፣ ወደ አንድነት በመመለስ ፈንታ፣ እኔ ያልሁት ይሁን ማለትን ስለወደደና፣ መለያየት ስለተስፋፋ፣ መነቃቀፍ ያመጣው የወገን ስም መለያየት ተፈጠረ:: ይልቁንም ወላዲ መለኮት ተወላዲ መለኮት ሠራፂ መለኮት የማለትና፣ መለኮትንም መንግሥትንም በአካል ሦስት የማለት እንግዳ ትምህርት ስለመጣ፣ ይህንም አንዳንድ ሰዎች አክብረው ስለተቀበሉት፣ አንዲት የኢትዮጵያውያን ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከብዙ ከፋፈላት:: የመጣበትም ምክንያት እንዲህ ነው የኢትዮጵያ ሊቃውንት ወንጌላዊ “ቃል ሥጋ ኮነ” ዮሐንስ ፩÷፲፬ ያለውን ንባብ ከምሥጢር ተመልክተው፣ መለኮትና ትስብእት ተዋሕደው አንድ አካልና አንድ ባሕርይ በመሆናቸው፣ ክርስቶስ የአምላክነትንም የሰውነትንም ሥራ በአንድ ፈቃድ ይሠራል ብለው፣ እምነታቸውን ስለገለጡና ስላስተማሩ፣ በካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያሉ ሰዎች:- “ባሕርይ ተዋሐደ ከተባለ፣ ባሕርየ ሥላሴ አንድ ነውና፣ ሦስቱ አካላት ሰው ሆኑ” ያሰኛል ብለው ሲከራከሩ፣ ምሥጢሩን ያላስተዋሉ ሰዎች “መለኮት በአካል ሦስት” በማለትና “ወላዲ መለኮት፣ ተወላዲ መለኮት፣ ሰራጺ መለኮት” በማለት፣ የሐዲስ ትምህርት መንገድን አውጥተዋል:: ነገር ግን ይህ የሐዲስ ትምህርት መንገድ ዮሐንስ ተዐቃቢ የሔደበት ያልቀና መንገድ ነው:: ስለዚህ አስተዋዮች በቅን አስተያየት ተመልክተው በዚህ ባልቀና መንገድ ከመሄድ እንዲጠበቁበትና፣ “አንድ መለኮት በሦስት አካላት አለ” ወደ ማለት  ቅን ጎዳና እግረ ልቦናቸውን እንዲያቃኑበት ይችን ትንሽ መጽሐፍ እንጽፋለን:: የዚችም መጽሐፍ ጥርጊያ ጎዳና “በአካል ሦስት በመለኮት አንድ አሰኝቶ፣ መለኮት አንድ ከሆነ፣ ሦስቱ ሰው ሆኑ ያሰኛል ብሎ ከመፍራት ጠብቆ “ከሦስት አካላት አንድ አካል ወልድ ብቻ ሰው ሆነ” ወደ ማለት ያለችግር በቀጥታ የሚያደርስ ስለሆነ ስሟ “ፍኖተ
እግዚአብሔር” ተባለ::
አሠረ ፍኖት
ንባብ :- “ኩሉ ማዕመቅ የምላዕ፣ ወኩሉ ደብር ወአውግር ይተሐት ወይኩን መብዕስ መጽያህተ ርቱዐ፣ ወይዕሪ ፍኖት መብዕስ፣ ወይርአይ ኲሉ ዘነፍስ አድኅኖቶ ለእግዚአብሔር”
ትርጓሜ :- “ዝቅ ያለው ሁሉ ከፍ ይበል፣ ተራራው ኮረብታው ሁሉ ዝቅ ይበል:: ጠማማውም ይቅና:: አቀበቱም ሜዳ ይሁን:: ሥጋን የለበሰ ሁሉም የእግዚአብሔርን ትድግናውን ይይ” ኢሳ ፵÷፴፭ “ማዕምቅ እንደ ሰባልዮስ አንድ ገጽ የሚል አንድ ገጽ ማለቱን ትቶ ባሕርየ መለኮት
አንድ በሚያደርጋቸው በሦስቱ አካላትና በሦስቱ ገጻት ይመን”
ማስረጃ :- ዮሐንስ ዘአንጾኪያ “ንትአመን በሠለስቱ አካላት ወበሠለስቱ ገጻት፣ እንተ አሐዱ ባሕርየ መለኮት” ፍቹ “በሦስት አካላት በሦስት ገጾች አንድ ባሕርይ መለኮት ባለው እንታመናለን” ማለት ነው፡፡ ብሏልና::
ደብር (ተራራ)
እንደ ዮሐንስ ተዐቃቢ ዘጠኝ መለኮት ወይም ሦስት አማልክት ዘጠኝ አካላት ከማለት የሚያደርስ መለኮትና መንግሥት በአካል ሦስት የማለት እምነትን የያዘ ይህን አርቆ ሥላሴ በአካል ሦስት በመለኮት አንድ፣ መንግሥታቸውም በአካል ከሦስት የማትከፈል አንዲት ብቻ እንደሆነች ይመን::
ማስረጃ:- የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ዲዮናስዮስ “ወኢንበውእ ውስተ ከፊለ መለኮት ወመንግሥት አላ ንብል አሐዱ መለኮት ወአሐዱ መንግሥት ይትወሐዱ በመለኮት ወይሤለሱ በአካላት” መለኮትን ወደ መክፈል አንገባም:: መንግሥትንም አንከፍልም አንድ መለኮት አንድ መንግሥት እንላለን እንጅ በመለኮት አንድ ናቸው በአካል ሦስት ናቸው ማለት ነው::(ሃይማኖተ አበው) እንዳለ::
ሠለስቱ ምዕትም:- “ሥሉስ ፍጹም በአሐዱ መለኮት እስከ ለዓለም አሐዱ እግዚእ ወአሐቲ መንግሥት እንተ ኢትትከፈል ወኢትትፋለስ” “ፍጹም ሦስትነትን በአንድ መለኮት፣ እስከ ዘለዓለም አንድ ጌታ፣ አንዲት መንግሥት የማትከፈል እና የማትፋለስ  ማለት ነው። (ሃይማኖተ አበው)  ብለዋል::
ፍኖት መብዕስ (ያልቀና መንገድ)
ወላዲ መለኮት ተወላዲ መለኮት ሠራጺ መለኮት የማለት ትምህርትም አንድ መለኮት በሦስት አካላት ሕልው ሆኖ ሦስቱን አካላት ያገናዝባል በማለት የቀና ይሁን የተካከለም::
ማስረጃ ንባብ :- ዮሐንስ ዘአንጾኪያ “ወበሠለስቲሆሙ ሀሎ ፩ መለኮት” በሦስቱ አንድ መለኮት አለ ማለት ነው::(ሃይማኖተ አበው) ብሎአል:: “ይርአይ ኩሉ ዘነፍስ” በነፍስ ዕውቀት ዐዋቂ ሆኖ የሚኖር ሁሉ ወንጌላዊት ሃይማኖትን ለመግለጽ እግዚአብሔር በቅዱሳት መጻሕፍት በሊቃውንት በየአንቀጹ ያናገረው የአካላትን ሦስትነት፣ የመለኮትንና የመንግሥትንም አንድነት የሚያስረዳውን ኃይለ ቃል “ፍኖተ እግዚአብሔር” በተባለች በዚች ትንሽ መጽሐፍ ለተመልካች በቅርብ እንዲገኝለት በመደረጉ፣ በቅን ኅሊና የሚመለከታት ከብዙ ስሕተት መዳኑን ይወቅ:: ተመልካችዋም ቃሏን ተመልክቶ ተቀብሎ ከስሕተት የሚድንበትንና የዘለዓለም ድኅነት የሚያገኝበት ጊዜ እነሆ ከሞት በፊት ዛሬ ነው::
ማስረጃ :- ቅዱስ ዻውሎስ “በዕለት ኅሪት ሰማዕኩከ ወበዕለተ መድኀኒት ረዳዕኩከ” በተመረጠች ቃል ሰማሁህ በዕለተ ድኅነት እረዳሁህ ማለት ነው:: ያለውን የኢሳይያስን ትንቢት ከጠቀሰበት:: ኢሳ ፵፱÷፰ ንባብ :- “ወናሁ ይእዜ ዕለት ኅሪት፣ ወናሁ ዮም ዕለተ አድኅኖት” ትርጓሜ :- “የተመረጠች ቀን ድኅነት የሚገኝባትም ጊዜ ዛሬ ናት'' እንዳለ:: ፪ኛ ቆሮ ፯÷፪ የዘለዓለም ድኅነት የተባለችም፣ ዕሪናቸው በአካል፣ መመሳሰላቸው በኅብረ መልክዕ፣ ህልውናቸው በእኩልነት፣ ተዋሕዶዋቸው በመለኮት የሚነገር ሥላሴ፣ በአብ ልብነት ለባውያን፣ በወልድ ቃልነት ነባብያን፣ በመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስነት ሕያዋን መሆናቸውን አውቆ ተረድቶ አንድ የባሕርይ አምለክ ብሎ ማመን ናት::
ማስረጃ :- ባለቤቱ ጌታችን ንባብ :- “አባ በጽሐ ጊዜሁ ከመ ትሰብሆ ለወልድከ፣ ወከመ ወልድከኒ ይሰብሕከ፣ በከመ አኮነንኮ ላዕለ ኩሉ ዘሥጋ ወነፍስ ከመ የሀቦሙ ሕይወተ ዘለዓለም ለኩሎሙ እለ ወሀብካሁ ወዛቲ ይእቲ ሕይወት ዘለዓለም ከመ ያእምሩከ ለከ ለአሐዱ ዘበአማን አምላክ ወለዘፈነውኮ ኢየሱስ ክርስቶስ” ብሎአል:: ትርጓሜ :- “አባት ሆይ ልጅህን ትገልጸው ዘንድ፣ ልጅህም አንተን ይገልጽህ ዘንድ፣ የምትገልጽበት ጊዜውም ደረሰ፣ ለሰጠኸው ሁሉ ዘለዓለም ሕይወትን ይሰጣቸው ዘንድ፣ በሥጋዊና በነፍሳዊ ሁሉ ላይ እንዳሠለጠንኸው መጠን፣ የዘለዓለም ሕይወት ይች ናት:: ያውቁህ ዘንድ አንተ ብቻህ /እውነተኛ/ የባሕርይ አምላክ እንደሆንህ የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን'' ብሏልና:: ዮሐ ፲፯÷፩-፫ የባሕርይ አምላክ እንደሆነም የሚያውቁበትን ዕውቀት የሚገልጽ መንፈስ ቅዱስ መሆኑን ለደቀ መዛሙርቱ ሲያስረዳ:- ንባብ:- “ጰራቅሊጦስ መንፈሰ ጽድቅ ዘይፌኑ አብ በስምየ፣ ውእቱ ይሜረክሙ ኩሎ፣ ወያዜክረክሙ ኩሎ ዘነገርኩክሙ አነ” ትርጓሜ:- “አብ በእኔ ስም የሚሰድላችሁ የሚያፀና መንፈስ ቅዱስ ሁሉን ያስተምራችኋል ይገልጽላችኋል/ እኔ የነገርኋችሁንም ሁሉ ያሳስባችኋል'' ብሏል:: ዮሐ ፲፬÷፮ በማቴዎስ ወንጌልም:- ንባብ:- “እስመ ኢኮንክሙ አንትሙ እለ ትትናገሩ አላ መንፈሱ ለአቡክሙ ውእቱ ይትናገር በላዕሌክሙ” ትርጓሜ:- “እናንተ የምትናገሩ አይደላችሁም ያባታችሁ መንፈስ በእናንተ አድሮ ይናገራል እንጂ'' ብሏል:: ማቴ ፲÷፳ ጳውሎስም:- ንባብ ፦ “ወአልቦ ዘይክል ብሂለ እግዚእ ኢየሱስ ዘእንበለ ዘመንፈስ ቅዱስ ላዕሌሁ” ትርጓሜ:- “መንፈስ ቅዱስ ካደረበት ሰው በቀር ኢየሱስ የባሕርይ አምላክ ነው የሚል የለም” ብሏል:: ፩ኛ ቆሮ ፲፪÷፫ ነገር ግን የበጎ ሃይማኖት የምሥጢሩን ፍለጋ ለሚከታተል ሰው በቅዱሳት መጻሕፍትና በሊቃውንት የተጻፈውን በጎ ትምህርት ይዞ ምሥጢሩን እንዲገልጽለት የአምላክ መሆን ይገባዋል እንጂ የመጻሕፍት ንባባቸውንና ምሥጢራቸውን አፍርሶ ስህተትን ሲያንጽ፣ አስተዋይ ልቦና ለሌላቸው ሰዎች የቀና መስሎ ወደሚታይ ክፉ ጠማማ ሃይማኖት በመሳብ መንፈስ ቅዱስን ማሳዘን አይገባም:: ማስረጃ:- ሐዋርያው ጳውሎስ:- ንባብ፦ “ወኢታምዕዎ ለመንፈስ ቅዱስ ዘቦቱ ዐተቡክሙ አመ ድኅንክሙ'' ትርጓሜ:- “ከክህደት በዳናችሁ ጊዜ የታተማችሁበትን መንፈስ ቅዱስን አታሳዝኑት” እንዳለ:: ኤፌ ፬÷፴ የሰው ኅሊናው ወደ በጎ ሃይማኖት ሳያስብ የሃይማኖት ምሥጢርን በመግለጽ የእግዚአብሔር ፀጋ ሰውን አትረዳውምና:: ማስረጃ:- ፊልክስዩስ “እምቅድመ ትጽንን ኅሊናሁ ለስብእ ለኂሩት ወለእከይ፣ ኢትረድኦ ወኢትርሕቅ እምኔሁ'' እንዳለ:: /ክፍል ፪ ተስእሎ ፲፬/ ትርጉም:- “ወደ በጎና ወደ ክፉ ሳይጸን በመካከል ሳለ /ፈዞ ማለት ነው/ አትረዳውም አትርቀውም” ብሎአል:: ስለዚህ አምላካዊ የሆነ የሃይማኖትን ምሥጢር ለመረዳት አምላካችን ወደ በጎ ሃይማኖት የሚሳብ በጎ ኅሊናን ይስጠን አሜን::
ይቆየን፡፡
ይቀጥላል፡፡

No comments:

Post a Comment