Monday, June 5, 2017

ፍኖተ እግዚአብሔር--- ክፍል ፲፪


© መልካሙ በየነ
ግንቦት 28/2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ተጽሕፈ እም አሐዱ ሊቅ ኢትዮጵያዊ ኅሩይ ወመፈክራዊ
ጌታው አለቃ ኅሩይ
ክፍል ፪
ዳግመኛ:- ጌታችን በዕለተ ዓርብ በመስቀል ተሰቅሎ ሙቶ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር አድሮ በተነሣ ጊዜ፣ በማናቸው ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን ተነሣ ይባላል ይሆን? በወልድ አካል ብቻ ባለ ኃይልና ክሂል ሥልጣን ተነሣ እንዳይባል፤ እግዚአብሔር ከሙታን ለይቶ እንዳስነሣው፤ በእግዚአብሔር ኃይልና መንፈስ እንደተነሣ፤ መጻሕፍት ይመሰክራሉ:: /ማስረጃ/ ብፁዕ ጳውሎስ፤ ንባብ፦ “ወአርአየ ከመ ወልደ እግዚአብሔር ውእቱ በኃይሉ ወበመንፈሱ ቅዱስ ከመ ተንሥአ እሙታን ኢየሱስ ክርስቶስ” ትርጉም፦ “በኃይሉ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አሳየ፤ በቅዱስ መንፈሱም ከሙታን ተለይቶ እንደተነሣ ኢየሱስ ክርስቶስ” ብሏል:: ሮሜ ፩÷፬ ዳግመኛም:- ንባብ፦ “በከመ ውእቱ ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን በስብሐተ አቡሁ፤ ከማሁ ንሕነኒ ናንሶሱ ውስተ ሐዳስ ሕይወት” ትርጉም፦ “ክርስቶስ በአባቱ ጌትነት ከሙታን ተለይቶ እንደተነሣ እኛም እንደሱ ተነሥተን በአዲስ ሕይወት እንኖራለን” ብሏል:: ሮሜ ፯÷፬ ዳግመኛም ንባብ፦ “እመሰ መንፈሱ ለዘአንሥኦ ለኢየሱስ እሙታን ዘኅዱር ላዕሌክሙ፤ ውእቱ ዘአንሥኦ እሙታን ለኢየሱስ ያሐይዋ ለነፍስትክሙኒ በውእቱ መንፈሱ ዘየኀድር ላዕሌክሙ” ትርጉም፦ “ኢየሱስን ከሙታን ለይቶ ያስነሣው የእግዚአብሔር መንፈስ በእናንተ ካደረባችሁ ኢየሱስን ከሙታን ለይቶ ያስነሣው እሱ መንፈስ ቅዱስ አድሮባችሁ ባለ በሕይወትነቱ ሥጋችሁን ሕያው ያደርጋታል” ብሏል:: ሮሜ ፰÷፲፩ ንባብ፦ “እመ ከመ ተአምን በአፉከ ከመ ክርስቶስ ውእቱ እግዚእ፤ ወተአምን በልብከ ከመ አንሥኦ እግዚአብሔር እሙታን ተሐዩ” ትርጉም፦ “በአፍህ ብትናገር ኢየሱስ ጌታ እንደሆነ፤ በልብህም ብታምን እግዚአብሔር ከሙታን ለይቶ እንዳስነሣው ትድናለህ” ብሏል:: ሮሜ ፲÷፱ ይህን የመሰለ በየአንቀጹ የተነገረው ብዙ ነውና፣ ከዚህ ቀጥሎ በተመለከተው ምዕራፍና ቁጥር እየገቡ መመልከት ነው:: ፩ኛ ቆሮ ፯÷፲፬፣ ኤፌ ፩÷፳፣ ፩ኛ ጴጥ ፩÷፳፩፣ የሐዋ ፪÷፳፬፣ የሐዋ ፬÷፲፣ የሐዋ ፭÷፫፣ የሐዋ ፲፫÷፴፬-፴፮፣ የእስክንድርያ ሊቀ ዻዻሳት ቄርሎስም:- ንባብ፦ “ተብህለ በእንቲአሁ ከመ አንሥኦ አብ እሙታን” ትርጉም፦ “አብ ከሙታን ለይቶ እንዳስነሣው ስለ እርሱ ተነገረ” ብሏል:: ዮሐንስ አፈወርቅም ንባብ፦ “ዘከመ ገብረ እዘዘ ኃይሉ ዘገብሮ በክርስቶስ ዘአንሥኦ እሙታን” ትርጉም፦ “ከሙታን ለይቶ ባስነሣው በክርስቶስ እንዳደረገው ተአምራቱ ብዛት” ያለውን ኤፌ ፩÷፲፱-፳:: ሲተረጉም ንባብ፦ “ትርጓሜሁ ለዝ እስመ በኃይል ዘቦቱ አንሥኦ ለክርስቶስ ይስሕበነ ኀቤሁ” ትርጉም፦ “የዚህ ትርጓሜው ክርስቶስን በአስነሣበት ኃይል አስነሥቶ ወደ እርሱ አቅረቦናል ማለት ነው” ብሏል:: /ድርሳን ፫/  ዳግመኛ:- ንባብ፦ “ዘንተ ንብል በእንተ ዘውእቱ እምኔነ፣ ዝንቱ ዘአንሥኦ እግዚአብሔር እምነ ሙታን” ትርጉም፦ “ከእኛ ባሕርይ ስለተገኘ ሥጋ ይህን እንናገራለን፤ ይኸውም እግዚአብሔር ከሙታን ለይቶ ያስነሣው ነው” ብሏል:: /ድርሳን ፫/ ዳግመኛም:- ንባብ፦ “ወሶበ ትሰምዑ ቃለ ዘይብል ከመ እግዚአብሔር አንሥኦ ለክርስቶስ፤ ኢተሐልዩ ከመ ውእቱ ይብል ዘንተ በእንተ ቃል አላ ይቤ በእንተ ሥጋ እግዚእነ” ትርጉም፦ “እግዚአብሔር ክርስቶስን እንዳስነሣው የሚናገር ቃል ብትሰሙ፤ እርሱ ይህንን ስለ ቃል እንደተናገረ አታስቡ የተናገረ አይምሰላችሁ፤ ከእኛ ባሕርይ ስለነሳው ሥጋ ተናገረ እንጅ” ብሏል:: /ድርሳን ፬/ ከዚህ በላይ የተጠቀሰውን ሁሉ ተመልክተው በአብ አካል ብቻ ወይም በመንፈስ ቅዱስ አካል ብቻ ባለ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን ተነሣ እንዳይሉ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገዛ ሥልጣኑ እንደ ተነሣ ሲመሰክር ቤተ አይሁድን:- ንባብ፦ “ንሥትዎ ለዝንቱ ቤተ መቅደስ ወበሥሉስ ዕለት አነሥኦ” ትርጉም፦ “ይህን መቅደስ አፍርሱት እኔ በሦስተኛው ቀን አስነሣዋለሁ” ብሏል ዮሐ ፪÷፲፱:: ይህንም ወንጌላዊ:- ንባብ፦ “ውእቱሰ በእንተ ቤተ ሥጋሁ ይቤሎሙ” ትርጉም፦ “እርሱ ግን መቅደስ ስለሚባል ሥጋው ነገራቸው” ብሎ ተርጉሞታል:: ዮሐ ፪÷፳፩ ዳግመኛም:- ንባብ፦ “ወበእንተ ዝንቱ ያፈቅረኒ አብ እስመ አነ እሜጡ ነፍሰየ ከመ ካዕበ አነሥአ፤ ወአልቦ ዘየሀይደንያ ለልየ እሜጥዋ በፈቃድየ፤ እስመ ብውህ ሊተ አንብራሂ ወብውህ ሊተ ካዕበ አንሥአ” ትርጉም፦ “ስለዚህ አብ ይወደኛል እኔ ነፍሴን እሰጣለሁና፣ ደግሞ አስነሳት ዘንድ ማንም ከኔ የሚወስዳትም የለም፤ እኔ በፈቃዴ እሰጣታለሁ እንጅ:: ለእኔ ችሎት አለኝ እሰጣት ዘንድ፣ ዳግመኛም ችሎት አለኝ አሥነሣት ዘንድ” ብሏል:: ዮሐ ፲÷፲፯-፲፰ ዳግመኛ:- ንባብ፦ “አነ ውእቱ ትንሣኤ ወሕይወት” ትርጉም፦ “እኔ ነኝ ትንሣኤ ሕይወትም” ብሏል ዮሐ ፲፩÷፳፭:: በመጻሐፈ ኪዳንም ንባብ፦ “ወተንሣእኩ በሥልጣነ ባሕቲትየ” ትርጉም፦ “በኔ ብቻ ሥልጣን ተነሣሁ” ብሏል:: እኛም ይህን ሁሉ ተመልክተን ወልድ በአካሉ ባለች በገንዘቡ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን ተነሣ ብለን አምነን፤ በወልድ አካል ያለች ኃይል፣ ክሂል፣ሥልጣን በአብና በመንፈስ ቅዱስ አካል ያለች አንዲት ናትና፣ መጻሕፍት አንድነታቸውንና ሕልውናቸውን ለመንገር አብ አንሥኦ፣ መንፈስ ቅዱስ አንሥኦ እያሉ ስለመሰከሩ፣ “ወተንሣእኩ በሥልጣነ ባሕቲትየ” አለ ብለው ስለአስረዱ ኃይል፣ ክሂል፣ ሥልጣን ከሦስት የማይከፈል አንድ እንደሆነ እምነታችንን እንገልጻለን፤ በዚያውም ላይ የአብ ኃይሉ ጥበቡ የሚባል እርሱ ክርስቶስ እንደሆነ የሚያስረዳ ቅዱስ ዻውሎስ:- ንባብ፦ “ክርስቶስ ኃይለ እግዚአብሔር ውእቱ ወጥበበ እግዚአብሔር ውእቱ” ትርጉም፦ “ክርስቶስ የእግዚአብሔር ኃይል ነው፤ የእግዚአብሔር ጥበብም ነው” ብሎ ነግሮናል:: ፩ኛ ቆሮ ፩÷፳፬
ክፍል ፫
በኃይል፣ በክሂል፣ በሥልጣንም በሚሠራ በባሕርይ ሥራ በሦስቱ አካላት መለያየት እንደሌለ የሚያስረዳ ነገር፤ ከሙታን ተለይቶ መነሣት የክርቶስ አካል ብቻ ግብር ሲሆን፣ ማስነሣት የሦስቱ አካላት የባሕርይ ግብር ነው:: ስለዚህ ከሦስቱ አካላት ለሰው ሁሉ የሚሰጥ ሕይወት በአንድነት በሚሠራ በባሕርይ ግብር እንደሆነ መጻሕፍት ያስረዳሉና:: ቄርሎስ:- ንባብ፦ “ ፩ ሕላዌ ዘሥሉስ ቅዱስ ኲሉ ዕበይ ወኲሉ ክብር ይደሉ ለባሕቲቶሙ፣ ወኲሉ ዘኮነ በአምላክነ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ፣ ወለእመኒ ተብህለ በእንተ አብ ከመ ውእቱ ማሕየዊ፤ ዘእንበለ ኑፋቄ፤ እስመ ለዝንቱ ግብር ወልድኒ ይገብር፤ ወዓዲ ይገብሮ መንፈስ ቅዱስ፤ ወለእመኒ ወልድ ሕይወት በእለ ይፈቅድዎ ለሕይወት፣ እስመ ኢይገብር ዘንተ ዘእንበለ ፈቃደ አቡሁ፣ ዘይትዔረዮ፤ እስመ ቦቱ ለርእሱ ዘአብ ወላዲሁ፣ ወለሊሁኒ ይቤ ክሡተ ኢይገብር ግብረ ምንተኒ ዘእምኀቤየ አላ እገብር ግብሮ ለአቡየ ዘሀሎ ብዬ፤ ወለእመ ተብህለ በእንተ መንፈስ ቅዱስ ከመ ውእቱ ማሕየዊ ዘእንበለ ኑፋቄ ይገብር ዘንተ እስመ መንፈሰ ሕይወት ውእቱ፤ ንሕነሰ ንብል እስመ ሕይወት ውእቱ በህላዌሁ እግዚአብሔር አብ:: ወወልድ ዋሕድ ዘተወልደ እምኔሁ፤ በዝንቱ አምሳል ሶበ ይትበሀል ከመ አብ አንሥኦ ለክርስቶስ፣ ንሕነሰ ንረክብ ከመ ለሊሁ አንሥአ ርእሶ፣ ወይቤሎሙ ለአይሁድ ንሥትዎ ለዝንቱ ቤተ መቅደስ ወአነ አነሥኦ በሠሉስ መዋዕል” ትርጉም፦ “በአካል ልዩ የሚሆን የሥላሴ ባሕርይ አንድ ነው፣ ፍጹም ጌትነት ፍጹም ክብርም ለሦስቱ ብቻ ይገባል፤ ፍጥረት ሁሉ በአምላካችን በአብና በወልድ በመንፈስ ቅዱስም ተፈጠረ:: አብ ያለ ጥርጥር ያለ መለየት ማሕየዊ እንደሆነ ምንም ቢነገር ይህን ሥራ /ማዳኑን/ ያለመለየት ወልድ ይሠራዋልና፣ ወልድም ሕይወትን በሚሹ ሰዎች የሕይወትን ሥራ ቢሠራ በማስነሣት ሕይወት በሚተካከለው መተካከል በአካል ነው በአባቱ ፈቃድ ነው እንጅ ያለ አባቱ ፈቃድ ይህን አይሠራምና:: የወለደው የአብ ገንዘብ የእርሱ ገንዘብ ስለሆነ፤ እርሱም እራሱ በሕልውናየ ያለ አባቴ የሚሠራውን እሠራለሁ እንጅ እኔ ከራሴ ብቻ አንቅቼ ምንም አልሠራም ብሎ ገልጾ ተናግሯልና፣ መንፈስ ቅዱስም ማሕየዊ እንደሆነ ቢነገር ያለ መለየት ይህን ይሠራል የሕይወት መንፈስ ነውና፣ እኛ ግን እግዚአብሕር አብ በባሕርዩ ሕይወት እንደሆነ እንናገራለን:: ከእርሱ የተወለደ አንድ ልጁም በዚህ አምሳል/ማሕየዊ/ በመባሉ አብ ክርስቶስን አስነሣው ቢባል እኛ እርሱ ራሱ ራሱን እንዳስነሣ ከመጻሕፍት እናገኛለን:: አይሁድን “ይህን መቅደስ አፍርሱት እኔ በሦስተኛው ቀን አስነሣዋለሁ ብሏቸዋልና” እንዳለ:: /ክፍል ፶ ለኀበ ነገሥት ሄራን/ ዳግመኛ:- ንባብ፦ “እግዚእነ ክርስቶስ ያነሥአነ ለኩልነ እስመ ሕያው ውእቱ በእንተ አቡሁ እስመ ዘተወልደ እምአብ ሕያው ዘለዓለም ወበእንተዝ ደለዎ ሎቱኒ ዓዲ ይኩን ሕይወተ፤ እስመ ዘተወልደ እምሕይወት ማሕየዊ” ትርጉም፦ “ጌታችን ክርስቶስ ሁላችንን ያስነሣናል አባቱ ሕያው ስለሆነ እርሱም ሕያው ነው፤ ለዘለዓለም ሕያው ከሚሆን ከአብ ስለተወለደ ስለዚህም ሕይወት ይሆን ዘንድ ዳግመኛም ለእርሱ ተገባው፤ ሕይወት ማሕየዊ ከሚሆን ከአብ ተወልዷልና” ብሏል:: /ክፍል ፶/ ኪራኮስም ፴፮ኛ ንባብ፦ “ንሕነሰ ፅኑዐን በጽድቅ ወንሰብክ እንዘ ንትአመን በሥሉስ ቅዱስ እለ ሕልዋን ቅድመ፣ ወይሄልው ለዓለም፣ ንጹሐን ፫ አካላት ፍፁማን፣ ዘውእቶሙ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ ሕላዌሆሙ ወ፩ መለኮቶሙ ወ ፩ ግብሮሙ ወአሐቲ ሥምረቶሙ ወአሐቲ ክሂሎቶሙ ሕልዋን በዘዚአሆሙ:: ወአኮ አብ በርእሱ ባሕቲቱ ዘይገብር ዓዲ አኮ ወልድ ዘይገብር በርእሱ ባሕቲቱ ወአኮ መንፈስ ቅዱስኒ በርእሱ ባሕቲቱ ዘይገብር፣ አላ ዳዕሙ ለዘፈቀደ አብ ይፈጽምዎ ወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ወምግባሮሙኒ ፩ እስመ ፩ ውእቱ መለኮቶሙኒ፤ አካላት ዕሩያን በአርአያ ወአምሳል ወመልክዕ” ትርጉም፦ “በእውነት የፀናን እኛ ቅድመ ዓለም በነበሩ ለዘለዓለም በሚኖሩ በልዩ ሦስት አካላት አምነን፣ ፍጹማን የሆኑ ሦስቱ አካላት፣ ከመለየት ከመለወጥ ንጹሐን እንደሆኑ እናስተምራለን:: እኒሁም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ናቸው:: በሕልውና አንድ፣ በባሕርይም አንድ፣ በግብርም (አምላካዊ ግብር) አንድ፣ በፈቃድም አንድ፣ ሁሉን ማድረግ በመቻልም አንድ እንደሆኑ እናስተምራለን:: /በዘዚአሆሙ/ በሚገናዘቡበት በልብነት፣ በቃልነት፣ በእስትንፋስነት በየራሳቸው፣ በወላዲነት በተወላዲነት በሠራጺነት የሚኖሩ ናቸው:: አብ በተለየ አካሉ ብቻውን ሥራ የሚሠራ አይደለም፣ ወልድም በተለየ አካሉ ብቻውን ሥራ የሚሠራ አይደለም፤ አብ ያሰበውን ወልድና መንፈስ ቅዱስ ይሠሩታል እንጅ፣ ግብራቸውም አንድ ነውና፤ ሦስቱ አካላት በግብርና በመመሳሰል በቅርጽም የተካከሉ ናቸው” ብሏል:: /ክፍል ፩/ ከዚህ በላይ እንደተነገረ ከሦስቱ አካላት ለዓለሙ ሁሉ የሚሰጥ የዘለዓለም ሕይወት በአንድነት በሚሠራ ግብር ከሆነ፣ ይህን የሚያደርጉበት ኃይል ክሂል ሥልጣን ከሦስት የተከፈለ ነው ማለት አይገባምና፣ ይህን በአስተዋይ ልቡና መመልከት ያሻል:: አንዳንድ ሰዎች በሚናገሩት በሦስቱ አካላት ላይ የሚገኝ ዕሪና ብቻ ነው እንጅ ሕልውናም ዋሕድና /መገናዘብም አንድነትም/ አይገኝበትም ይላሉ:: እንዲህም ማለታቸው መጻሕፍት ስለ ዕሪና እና ስለ ሕልውና ስለዋሕድናም የተናገሩትን ምሥጢር አስተውሎ ባለመመልከት ነው:: ዕሪና የሚነገር በአካል ላይ በሚወድቅ ምሥጢር ነው:: ሕልውናም የሚነገር በከዊን ላይ በሚነገር ምሥጢር ነው:: ዋሕድናም የሚነገር ስለ ባሕርይ ነው:: ወይም ስለ ጠባይዕ በሚነገር ምሥጢር ነው:: ስለዚህ ከዚህ በላይ ዘርዝረን ያሳየናቸውን ነገሮች ማሳሳትን የሚያመጣ ስልት ስልታቸውን ለይቶ ሳያውቁ የሃይማኖትን ነገር ማስተማር፣ መጻሕፍትንም መጻፍ ምሥጢረ ሥላሴን ያፋልሳል:: መጻሕፍትንም ያጣላል:: ሰሚንና ተመልካቹንም ገደል ይሰዳል:: ማቴ ፲፭÷፲፬ ስለዚህ ጠንቅቆ ማስተዋል ይገባል:: የዚህን ነገር በሰፊው ልናስረዳ በቻልን ነበር:: ነገር ግን በብዙ ዘመን አንፈጽመውም:: ባስልዮስ ዘቂሣርያ:- ንባብ፦ “ወይእዜኒ ናሕፅር ነገረ ወንፈጽም ዘንተ ክፍለ ወንኅድግ ኩሎ አእምሮ ለእግዚአብሔር ዘይመውዕ ኩሎ ግብራተ” ትርጉም፦ “ነገርን በማሳጠር ይህን ምሥጢር ፍጹም ዕውቀትንም ሥራን ሁሉ፣ ድል መንሣት ለሚቻለው ለእግዚአብሔር እንተው” ብሎ እንደተነገረን /ሃይማኖተ አበው ክፍል ፩/ ነገራችንን በማሳጠር እንወሰን::
ይቀጥላል፡፡
ይቆየን፡፡

No comments:

Post a Comment