፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
ዛሬ ገጽ ፱ እና ፲ ላይ ያሉ ስህተቶችን በማስረጃ እንመለከታለን፡፡ በፎቶ ከስር ስለማያይዝላችሁ ሙሉውን
ማንበብ ትችላላችሁ እኔ ግን ዋና ዋና ነጥቦች ላይ ብቻ ነው ትኩረት የማደርገው፡፡


እዚሁ ገጽ ላይ ይቀጥልና “የቃል ገንዘብ ምንምን ነው ቢሉ ሳድስ ቀለም ንጉስ ባዕል ረቂቅ ምሉዕ ስፉሕ
ህያው ልዑል ክቡር አምላክ ነው፡፡ የሥጋ ገንዘብ ግዕዝ ቀለም ሐየሰ ወረሰ ተለአለ ነግሠ ከብረ ነው” ይላል፡፡ ምሥጢረ ተዋሕዶን
ስንነጋገር ሦስት ነገሮች ላይ ትኩረት መስጠት ይኖርብናል፡፡ በነገራችን ላይ ጌታ የተዋሐደው ሥጋ ተፈጥሮ የቆየን ሥጋ አይደለም፡፡ እዚህ ላይ በሦስት ክፍሎች ስንከፋፍለው ስለ ሥጋ እና ስለመለኮት ባህርይ
ለመነጋገር ያህል እንጅ ሥጋ ተፈጥሮለት ቆይቶ ያንን የተዋሐደ አይደለም፡፡ የቃላት አጠቃቀማችንን ለማብራራት ሲባል ብቻ ነው ለሦስት ክፍሎች ከፋፍየ የማሳያችሁ፡፡
፩ኛ. ቅድመ ተዋሕዶ፡፡ ይህ ጊዜ ሥጋ በሥጋነቱ መለኮትም በመለኮትነቱ ያለበት ጊዜ ነው፡፡
ከተዋሕዶ አስቀድሞ ያለው ጊዜ ነው፡፡ መለኮት ረቂቅ ነው ስፉሕ ነው ምሉዕ ነው ንጉሥ ነው ህያው ነው ባዕለ ጸጋ ነው አምላክ ነው
ወዘተ እንላለን ይህ ሁሉ ገንዘቡ ነውና፡፡ ይህ ችግር የለውም፡፡ ሥጋንም እንዲሁ ነዳይ (ደሃ) ነው ተወካፊ (ተቀባይ) ነው ግዙፍ
ነው ውሱን ነው ጠባብ ነው ፍጡር ነው ወዘተ እንላለን ይህ ሁሉ ገንዘቡ
ነውና፡፡ ይህ ምንም ህጸጽ የለበትም፡፡ እዚህ ጊዜ ላይ የሥጋ ገንዘብ ለቃል፤ የቃልም ገንዘብ ለሥጋ ስላልሆነ ሥጋ በሥጋነት ገንዘቡ
መለኮትም በመለኮትነት ገንዘቡ ቢጠራ ምንም ችግር የለውም፡፡ እንዲያውም “ነው” ተብሎ ነው የሚገለጸውም፡፡ ሥጋም (ሰውም) ሥጋ
(ሰው) ነው ይባላል፡፡ አምላክም አምላክ ነው ይባላል፡፡ ልብ በሉ አሁንም ሥጋ ቀድሞ ተፈጥሮ ያንን ተዋሐደው ማለት አይደለም፡፡
፪ኛ. ጊዜ ተዋሕዶ ነው፡፡ ይህ መለኮት እና ሥጋ የተዋሐዱበት ድንቅ ምሥጢር የተፈጸመበት ጊዜ
ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ነው የሥጋ ገንዘብ ለቃል፤ የቃልም ገንዘብ ለሥጋ የሆነው፡፡ የቃል ገንዘብ ለሥጋ የሥጋ ገንዘብም ለቃል ሲሆን
በተዓቅቦ (በመጠባበቅ) ነው፡፡ የሥጋ ገንዘቦች በሙሉ (ከኃጢአት በቀር) ለቃል ሆኑ የቃልም ገንዘቦች በሙሉ ለሥጋ ሆኑ እንጅ የሥጋ ገንዘቦች
ጠፍተው ለቃል፤ የቃል ገንዘቦችም ጠፍተው ለሥጋ አልተሰጡም አልተለወጡም፡፡ በዚህም መሠረት ዘመን የማይቆጠርለት መለኮት የሥጋን ገንዘብ ገንዘቡ
አድርጎ ዘመን ተቆጠረለት፡፡ ረቂቅ ስፉህ ምሉዕ የነበረው መለኮት የሥጋን ገንዘብ ገንዘቡ አድርጎ ግዙፍ እና ጠባብ ሆነ በሦስት
ክንድ ከስንዝር ተወሰነ፡፡ ረሃብ እና ጥም የማይስማማው መለኮት የሥጋን ገንዘብ ገንዘቡ አድርጎ ተራበ ተጠማ በላ ጠጣ ተባለ፡፡ ዘመን የሚቆጠርለት ሥጋ የመለኮትን ገንዘብ
ገንዘቡ አድርጎ ቀዳማዊ አምላክ ዘመን የማይቆጠርለት ሆነ፡፡ የሚሞት የሚበሰብስ ሥጋ የመለኮትን ገንዘብ ገንዘቡ አድርጎ ህያው አምላክ
ዘላለማዊ ገዥ ሆነ፡፡ ፍጡር የሆነው ሥጋ የመለኮትን ገንዘብ ገንዘቡ አድርጎ ፈጣሪ አምላክ ሆነ፡፡ ይህ ሁሉ የተፈጸመው በተዋሕዶ ምስጢር ነው፡፡ ለዚህም ነው ሰው አምላክ ሆነ
አምላክ ሰው ሆነ ማለታችን፡፡ ሰው አምላክ
ከመሆን በላይ ምን መክበር አለና ነው “በተዋሕዶ ከበረ” ማለት ኑፋቄ ሊሆን የሚችለው? በተዋሕዶ ይህ ሁሉ አልተደረገም ካላችሁ
ምንፍቅናችሁ ያኔ ይገለጣል፡፡
እዚህ ላይ ተዋሕዶው ያለመለየት፣ ያለመቀላቀል፣ ያለመለወጥ፣ ያለመደመር፣ ያለማደር፣ ያለመጎራበት በፍጹም ተዋሕዶ በተዓቅቦ
(በመጠባበቅ) ነው፡፡ እዚህ ላይ “ነው”
ተብሎ መነገር ይቀርና “ሆነ” በሚል ቃል ይነገራል፡፡ በዚህም መሠረት “ሰው ነው አምላክ ነው” መባል ቀርቶ “አምላክ ሆነ ሰው
ሆነ” ይባላል ማለት ነው፡፡
፫ኛ. ድኅረ ተዋሕዶ፡፡ ይህ ከተዋሕዶ በኋላ ያለ ጊዜ ነው፡፡ አምላክ ሰው ሆኗል ሰውም አምላክ
ሆኗል፡፡ ከዚህ በኋላ መለኮቱ እንዲህ አደረገ ሥጋው እንዲህ አደረገ ብሎ መለያየት መከፋፈል ክህደት ነው፡፡ እሳትና ብረት ተዋሕደው
የጋለ ብረት ይሆናል፡፡ በዚህ የጋለ ብረት ላይ ይህ ብረት ነው ይህ እሳት ነው እንደማንል ሁሉ ክርስቶስን (ሥግው ቃል) ንም እንዲሁ
ሥጋው ይህ ነው መለኮቱ ይህ ነው አንልም ምክንያቱም ሥጋና መለኮት አንድ አካል አንድ ባሕርይ ሆኗልና ነው፡፡ “በ” የምትል ፊደል
ጨምረን “በመለኮቱ”፣ “በሥጋው” እያልን እንገልጻለን እንጅ “በ” ን አጥፍተን “መለኮቱ”፤ “ሥጋው” ማለት ግን ክህደት ነው፡፡
እነዚህ ሁለቱ የሰማይ እና የምድርን ያህል የምሥጢር ልዩነት አላቸው፡፡ “ሥጋው ተራበ” ማለት እና “በሥጋው ተራበ” ማለት በጣም
ይለያያል፡፡ “ሥጋው ተራበ” ስንል ሥጋ ና መለኮት መዋሐዳቸውን አያመለክትም አያሳይም፡፡ ለምሳሌ እኔ ሥጋየ ተራበ እንደምለው ዓይነት
ነው የሚሆነው፡፡ “በሥጋው ተራበ” ስንል ግን መለኮት እና ሥጋ አንድ አካል አንድ ባሕርይ ሆነዋል ማታችን ነው፡፡ ይህ አንድ አካል
አንድ ባሕርይ የሆነ አምላክ በሥጋው ተራበ እንላለን፡፡ ይህም ማለት በአጭር ቃል “በሥጋው ተራበ” ማለት “መለኮት የተዋሐደው ሥጋ
ተራበ” ማለታችን ነው፡፡
ስለዚህ የቃል ገንዘብ በሳድስ የሥጋ ገንዘብ በግዕዝ ፊደላት ይገለጻሉ የሚለው አነጋገር መጀመሪያ በዚህ
መልኩ ተዋሕዶን መዘርዘር ሳያስፈልግ አይነገርም፡፡ ከተዋሕዶ በኋላ ሳድስ ቀለም ለቃል ግዕዝ ቀለም ለሥጋ ማለት አይቻልም፡፡ “ከበረ”
የሚለው ቃል እኮ ሰው አምላክ ሆነ አምላክ ሰው ሆነ የሚለውን ድንቅ ምሥጢር ለማሳየት ካልሆነ በቀር ለቃል የሚቀጸል ቃል አይደለም፡፡
ሰው አምላክ ከመሆን በላይ ምን መክበር አለና ነው “በተዋሕዶ ከበረ” ቢባል ስህተት የሚሆነው? የቻላችሁ መልሱልኝ ያልቻላችሁ ደግሞ
ሊቅ የምትሏቸውን ወገኖቻችሁን ጠይቁ፡፡

፩. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን
በእርሱ አጋዥነት ድንቅ ተአምራትን ያደርግ ዘንድ በመንፈስ ቅዱስ ከበረ የሚለው ቢኖር ውጉዝ ይሁን፡፡
፪. ርኩሳን አጋንንትን
በማውጣት ጊዜም ኃይልን ተአምራትን ከመንፈስ ቅዱስ ይቀበላል የሚለው ቢኖር ውጉዝ ይሁን፡፡
፫. በሰውም የአምላክነትን ሥራ ይሠራል የሚለው ቢኖር ውጉዝ ይሁን፡፡
፬. መንፈስ
ቅዱስ የባሕርዩ ነው የማይል ቢኖር ውጉዝ ይሁን፡፡ የሚሉ ናቸው፡፡
ስለዚህ “ወልደ አብ ወልደ ማርያም በመንፈስ ቅዱስ ከበረ” የሚለው ኑፋቄ የተወገዘ ትምህርት ነው፡፡ ስለዚህ
“ወልደ አብ ወልደ ማርያም በመንፈስ ቅዱስ ከበረ ይህቺ ናት ሐይማኖት” ማለት ሀሰት ነው፡፡ ትክክለኛዋ የአባቶቻችን ጥንታዊቷ ቀጥተኛ
ሃይማኖት “ወልደ አብ ወልደ ማርያም በተዋሕዶ ከበረ ነው ሃይማኖቲቱም ይህቺ ናት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ”
ይቀጥላል፡፡
፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍
© መልካሙ በየነ
ኅዳር ፯
/ ፳፻፲ ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣
ኢትዮጵያ
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍
No comments:
Post a Comment