Tuesday, March 1, 2016

የተከሰሰ ሁሉ ወንጀለኛ ነውን?

© በመልካሙ በየነ
የካቲት 20/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
አንድ ወንድሜ ስለክስና ወንጀል እንዲሁም ስለወንጀለኛና ስለ ፍርድ ውሳኔ አሰጣጥ ያጫወተኝ ጫወታ ዛሬ በጣም ትዝ አለኝ፡፡ እርሱ ጥፋት ሠራም አልሠራም ብቻ በመከሰስ ይታወቃል በዚህም የተነሣ ብዙ ፍርድ ቤቶችን እና ብዙ ዳኞችን የማየት ዕድል አጋጥሞታል፡፡ እኔ ግን ፍርድ ቤት የሚባለውን ነገር እንዳያሳየኝ ነው ፈጣሪየን የምለምነው፡፡ ለምን መሰላችሁ እንዲህ የምለው ተከስሼ ለፍርድ ከቀረብኩ አጠፋሁም አላጠፋሁም የሚቀጣኝ እንጅ በነጻ የሚለቀኝ ዳኛ ያለ ስለማይመስለኝ ነው ግን ይቅርታ!
እኔ የሚመጣብኝ በማቴዎስ ወንጌል ምእራፍ 27 ላይ ያለው ኢየሱስ ክርስቶስ የተከሰሰበት ወንጀልና የነሔሮድስና የነጲላጦስ ፍርድ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእውነት ከጲላጦስ ወደ ሔሮድስ ከሔሮድስ ወደ ጲላጦስ እርጥብ መስቀልን ተሸክሞ የተንገላታውና በመጨረሻም ለመስቀል ሞት ተላልፎ የተሰጠው ወንጅል ሰርቶ በደል ኖሮበት አልነበረም ዓለም ለቀማኞች፣ ለሐሰተኞች፣ ለወንጀለኞች፣ ስለሆነች እንጅ፡፡ ለዛም ነው ዓለም እውነትን ለመስቀል እውነትን ለመግደል እውነትን ለማሰቃየት ፍቅርን ለመስቀል ጠማማ ፍርዷን ለመፍረድ የተቻኮለች፡፡ የተከሰሰ ሁሉ በደለኛ የተከሰሰ ሁሉ ወንጀለኛ ነው ብላ ይሙት በቃ የምትፈርደዋ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስንም ስቀሉት ስቀሉት ስቀሉት በሚሉ አፎች ተሞልታ ያችን የመከራ ዕለተ አርብን አሳለፈች፡፡ ፍርድን የሚሹ አይሁዳውያን ለፍርድ ወደ ጲላጦስ አደባባይ አቀረቡት ይህ ባልከፋም ነበር፡፡ ንጉሡ በቅንአት ተነሣሥተው ወደ ፍርድ አደባባዩ እንዳመጡት በሚገባ ያውቅ ስለነበር በርባንን ልፍታላችሁ ወይስ ኢየሱስን አላቸው ሕዝቡ ግን የቀማኞችን አለቃ በርባንን እንዲፈታላቸው አጥብቀው ጮኹበት፡፡ ኢየሱስን ምን ላድርገው ብሎ ንጉሡ ዳግም ጠየቃቸው ለፍርድ ያቀረቡት ሰዎች ራሳቸው ፈራጅ ሆኑና ይሰቀል ብለው በአንድ ድምጽ ተናገሩ፡፡ ንጉሡም ምን ጥፋት አግኝታችሁበት ነው አላቸው እነርሱ ግን አሁንም መልሳቸው ይሰቀል የሚል ብቻ ነው፡፡ ተመልከቱ የዓለምን ጉድ ጥፋቱ ምንድን ነው ለሚል ንጉሥ መልሷ ይሰቀል የሚል ነው ለስቅላት የሚያበቃውን ወንጀል መናገር አልቻለችም ምክንያቱም እውነትን ነውና ልትሰቅል የያዘችው ሐሰትን ከአፉ ማግኘት እንኳ አልቻለችም፡፡ ንጉሡ የኢየሱስ ክርስቶስን በመስቀል ተሰቅሎ መሞት አልፈለገም ምክንያም የተከሰሰበት ነገር ለስቅላት ለሞት ሳይሆን ለሹመት ለሽልማት የሚያበቃ ነውና፡፡ ለዚህም ነው ንጉሡ እጁን ታጥቦ ከዚህ ሰው ደም በእውነት ንጹሕ ነኝ ብሎ የመሰከረው፡፡ ነገር ግን ከሳሾቹ ራሳቸው ፈራጆች ሆኑና ደሙ በእኛ ብቻ ሳይሆን ልጆቻችን ላይም ይደር ብለው ንጹሕ ክርስቶስን ለመስቀል ሞት አበቁት፡፡ አይሁድን የምጠይቃቸው ነገር ቢኖር ይኼው ነው፡፡ እናንተው ፈራጆች ከሆናችሁ ለምን መክሰስና በጲላጦስ አደባባይ ማቆም አስፈለጋችሁ? የንጉሡን ውሳኔስ መፈጸም ካለባችሁ ለምን ንጹሕ ክርስቶስን በነጻ አልለቀቃችሁትም? ወይስ ወደ ንጉሡ አቅርባችሁ ክስ መሳይ ነገር ያቀረባችሁት ለይስሙላና እንዲህ አደረጉ ለመባል ብቻ ነበር? እናንተው ከሳሽ እናንተው ወሳኝ እናንተው ገዳይ እናንተው ሁሉን ሰሪ ያደረጋችሁስ ማነው? በእውነት አይሁዳውያን እነዚህን ጥያቄዎችን በመለሱልኝ ኖሮ ምንኛ ደስ ባለኝ ነበር፡፡
የወንድሜ ክስና ውሳኔም ከአይሁዳውያኑ የተቀዳ ነው፡፡ ወንድሜ አሁን የተከሰሰው ከሳሹና ወሳኙ ራሱ በሆነ አካል ነው፡፡ በማን አለብኝነት ተከሰሰ በማን አለብኝነት ተፈረደበት በማን አለብኝነት ተቀጣ፡፡ ለነገሩ የአገሬ ሰው ጨርሶታል እኮ “አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ” ብሎታል፡፡ የቀማኞች ስብስብ ንጹሐንን ወደ ወኅኒ ይወረውራል፡፡ ቆይ ግን ለምን? እኛ ሰዎች እኮ ከእንስሳት የምንለየው በማሰባችን መሰለኝ ታዲያ ማሰቢያችን የት ሔደ? በገንዘብና በማንአለብኝነት ለወጥነው እንዴ? ወይስ የትም አይሔዱም ምንም አያመጡም ተብለን ይሆን? እንጃ አምላከ ሰማይ አምላከ ፀሐይ እያለልን የምንሔድበት የምናጣ ምንም የማናመጣ እንዳይመስላቸው፡፡ ዳኞቹ በከሳሾች ተጽእኖ ይደረግባቸዋል፡፡ ከሳሹ በፈለገው መልኩ ውሳኔ ካልሰጡ ዳግም ጉዳዩ እንዲታይ ያደርጉታል፡፡ ምን ዓይነት ፍርድ ነው ግን? ይህ የሚሆነው ግን አንተ ከሳሽ ስትሆን ሳይሆን ተከሳሽ ስትሆን ብቻ ነው፡፡ አንተማ ምን አቅም አለህና ነውና እንዲህ ብላችሁ ወስኑ ብለህ የምትከሰው፡፡ “ግን እኮ ያለማስተዋል ጉዳይ እንጅ እኔም እኮ የበላይ ሐላፊ ነኝ እነርሱ የሆኑትን ሁሉ መሆን የምችል ነበርኩ ግን ዕድሉን ለእነርሱ አሳልፌ የሰጠኋቸው ራሴው ነኝ፡፡ በታማኝነት በእውነትና በቅንነት ያለምንም አድልዎ ይሠራሉ ብየ ወንበር ላይ ያከበርኳቸው እኮ እኔው ራሴ ነኝ፡፡ አላስተውል ብለው እንጅ እኮ እኔ የምቀጣላቸው ሕግን ለማክበር እንጅ ትክክለኛ ውሳኔን ስለወሰኑብኝ አይደለም፡፡ ሕግ ከሌለ እኮ እሱም ወንበሯን ይለቅቃል እኔም የማደርገውን አደርጋለሁ፡፡” ይለኝ ነበር በፍርድ አሰጣጥ ሂደቱ የተማረረው ወንድሜ እውነት ነው፡፡ ቀበሌ ላይ ከተከሰስክ ወረዳው ቀድሞ እንዲሰማው ይደረጋል፡፡ ወረዳ ላይ አቤቱታ ብታቀርብ ማንም አይሰማህም አጠፋህም አላጠፋህም ጥፋተኛ ነው ተብለህ ወረዳ ድረስ ተናፍሶልሃላ፡፡
የተከሰሰ ሁሉ ወንጀለኛ ነው? አይደለም!!! 100% እርግጠኛ ነኝ አይደለም!!! ግን ይፈረድብሃል፡፡ ያሳዝናል!!! ታዲያ መቼ ይሆን ከከሳሹ ተጽእኖ ነጻ የሆነ ዳኛ ተፈጥሮ የምናየው፡፡ ከሳሹ አቅርቦህ ውሳኔው እንደ ከሳሹ ፍላጎት ካልሆነ ሥነ ምግባር የጎደላቸው ዳኞች ተብለው ገለል ይደረጋሉ፡፡ ከሳሹ ማን ሲሆን መሰላችሁ ይህ የሚሆነው መ…..
(በሐሰት ተከሶ ከሳሹ ራሱ ለወሰነበት ወንድሜ!!!)

No comments:

Post a Comment