Tuesday, March 1, 2016

የዮናስ ቸልተኝነት

© በመልካሙ በየነ
የካቲት 22/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ዮናስ ማለት የዋህ ማለት ነው፡፡ የሰራፕታዋ መበለት ልጅ ነው፡፡ ረሀብ በነበረ ጊዜ ነቢዩ ኤልያስ ቤቷን በበረከት የሞላላት ናት፡፡በዚያም ወቅት ልጇ ዮናስ ሞተ ነቢዩ ኤልያስም ከሞት አስነሣው፡፡ ይህ ልጅ ሲያድግ እግዚአብሔር ወደ ታላቂቷ ከተማ ነነዌ በነቢይነት ሄዶ እንዲያስተምር አዘዘው፡፡ ዮናስ ግን ወደ ነነዌ መሄድን ቸል አለ፡፡ ነነዌ ሄጄ ኃጢአታችሁ ወደ እግዚአብሔር ደርሷልና እግዚአብሔር ከተማዋን ሊያጠፋ ነው እያልኩ ብሰብክና ከኃጢአታቸው ቢመለሱ እግዚአብሔር ምሕረቱ የበዛ ነው በዚያ ላይ እኔ ሐሰተኛ ነቢይ ልባል አይደለምን? ብሎ አሰበ አስቦም አልቀረ የነነዌን ጉዞ ቸል አለና ወደ ተርሴስ ይሄድ ዘንድ ዋጋ ከፍሎ መርከብ ውስጥ ገባ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር በባሕሩ ላይ ታላቅ ነፋስን አመጣና ታላቅ ማዕበል ሆነ መርከቢቱም ልትሰበር ቀረበች፡፡ መርከበኞቹም ፈሩ እያንዳንዱም ወደ አምላኩ ጮኸ መርከቢቱም እንድትቀልላቸው በውስጧ የነበረውን ዕቃ ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ በመርከቢቱ የነበረውን ሀብት ንብረታቸውን ሁሉ ወደ ባሕር ሲወረውሩ ያን ያህል የሚያስጨንቅ ፍርሐት ሲመጣባቸው ዮናስ ግን በመርከቢቱ ውስጠኛ ክፍል ተኝቶ ነበር፡፡ የመርከቡ አለቃ ዮናስን ተነሥተህ አምላክህን ጥራ ክፉ ማዕበል አስጨንቆናልና አለው፡፡ ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት እንደመጣባቸው ለማወቅ ዕጣ ተጣጣሉ ዕጣውም ለዮናስ ወጣ፡፡ ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት እንዳገኘን እባክህን ንገረን? ሥራህ ምንድን ነው? ከወዴትስ መጣህ? አገርህስ ወዴት ነው? ወይስ ከማን ወገን ነሀ? ብለው በዮናስ ላይ የጥያቄ መዓት አወረዱበት፡፡ ዮናስም ሰማይንና ምድርን በፈጠረ እግዚአብሔር የሚያመልክ ዕብራዊ እንደሆነ ነገራቸው፡፡ ሞገዱ የተፈጠረውም በእርሱ ምክንያት እንደሆነና እንዲቆምላቸውም እርሱን ወደ ባሕር እንዲጥሉት ፈቀደላቸው፡፡ እነርሱም ስለዚህ ሰው ነፍስ እንዳንጠፋ ንጹሕም ደም በእጃችን ላይ እንዳታደርግ እንለምንሃለን አሉና ዮናስን ወደ ባሕር ውስጥ ጣሉት ባሕሩም ከመናወጥ ጸጥ አለ፡፡ሰዎቹም እግዚአብሔርን እጅግ ፈሩ መሥዋዕትንም አቀረቡ ስእለትንም ተሳሉ፡፡ እግዚአብሔር ግን ለዮናስ በባሕሩ ውስጥ ሦስት ቀንና ሶስት ሌሊት ውጦ የሚያቆየውን ዓሣ አንበሪ አዘጋጅቶ ነበርና በዚያ ውስጥ አስገባው፡፡ከሦስት ቀን በኋላ ዓሣ አንበሪው ዮናስን የብስ ላይ ተፋው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል አሁንም ድጋሜ ወደ ዮናስ እንዲህ ሲል መጣ “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ የምነግርህንም ስብከት ስበክላቸው” አለው፡፡ ዮናስም ተነሥቶ እንደእግዚአብሔር ቃል ወደ ነነዌ ሄደ ቸልተኝነቱን ተወ፡፡/ትንቢተ ዮናስን በሙሉ ተመለከት/ ዮናስ የየዋህነት ቸልተኝነት ነበረበት ያ ቸልተኝነቱ ደግሞ ወዳልታዘዘው አገር እንዲሄድ አድርጎታል፡፡ የትም ቢሄዱ ከእግዚአብሔር መሠወር አይቻልምና ዮናስን እግዚአብሔር በጥበቡ መጀመሪያ እንዲሄድ ወዳዘዘው ቦታ ወሰደው፡፡ ነነዌንም አስተማረ እግዚአብሔርም ሊያመጣ የነበረውን መከራ መለሰላቸው፡፡ የሰዎች መዳን ሊያስደስተው ሲገባ ነቢዩ ዮናስ የራሱን ክብር ማለትም ሐሰተኛ ነቢይ እንዳይባል ብቻ ከእግዚአብሔር ሊርቅ መወሰኑ ጥሩ እንዳልነበር እንማራለን፡፡

No comments:

Post a Comment