Tuesday, March 1, 2016

የሔዋን ቸልተኝነት

© በመልካሙ በየነ
የካቲት 9/2008 ዓ.ም
ደብረማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
ሔዋንን ብዙ ጊዜ በተለያዩ ርእሶች ላይ አንሥተናታል፡፡ እዚህ ላይ ለማየት የምንሞክረው ቸልተኝነቷንና በቸልተኝነቷ የመጣባትን ርግማን ነው፡፡ ሔዋን በቸልተኝነት ለሌላ ሊነገር የማይገባውን እግዚአብሔር የሰጣቸውን ሕግ ክፉ ባልንጀርነትን ከእባብ ጋር መሠረተችና ምሥጢራቸውን ለእባብ አወጣች፡፡ እባብ ምሥጢራቸውን ከተረዳ በኋላ ዕፀ በለስን ወደ ሔዋን አፍ የሚጨምርበትን ጥበብ መፈለግ ቀጠለ፡፡ ይህ የሔዋን የመጀመሪያው ቸልተኝነት እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ የተባሉትን ዕፅ ለመብላት ሌላ ቸልተኝነትን አመጣባት፡፡ እግዚአብሔር እንዳዘዛቸው ያችን ዕፅ በበሉ ጊዜ የሞት ሞትን እንደሚሞቱ ሔዋን በሚገባ ታውቃለች፡፡ነገር ግን “ያችን ዕፅ በበላችሁ ጊዜእግዚአብሔር መልካምና ክፉውን የምታውቁ ያደርጋችኋል ጥበብንም ይገልጽላችኋል፤ አምላክም ትሆናላችሁ” የሚለውን የእባብ ክፉ ምክር በቸልተኝነት ተቀበለች፡፡ ያ ቀስ በቀስ የጎለበተው የሔዋን ቸልተኝነት አትብሉ የተባሉትን ዕፅ እንዲበሉ አድርጓቸዋል፡፡ የሔዋን ቸልተኝነት የወለደው ክፉ መዘዝከአምላክ ፊት በገነት ዛፎች መካከል ለመሸሸግ አበቃቸው፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ማምለጥ አልተቻላቸውም፡፡ ሁሉም ተጠየቁ አዳም በሔዋን ሔዋንም በእባብ አሳበቡ፡፡ ይሁን እንጅ ያ ቸልተኝነት ርግማን ማምጣትን አልተወም፡፡ ሁሉም እንደየድርሻቸው ርግመታቸውን ተቀበሉ፡፡ ርግማኑ ከእባብ ጀመረ“ከእንስሳት ከምድር አራዊትም ሁሉ ተለይተህ አንተ የተረገምህ ትሆናለህ፡፡ በሆድህም ትሄዳለህ አፈርንም ሕይወትህ ዘመን ሁሉ ትበላለህ፡፡ በአንተና በሴቲቱ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ እርሱ ራስን ይቀጠቅጣል አንተም ሰኮናውን ትቀጠቅጣለህ” የሚለውን ርግማን እባብ ተቀበለ፡፡ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንደሚያስተምሩት እባብ መልከ መልካም በአራት እግሩ የሚሄድ ጊደር የሚያህል እንስሳ ነበር ከተረገመ በኋላ ግን በልቡ የሚሳብ ሆኗል፡፡ የእግዚአብሔር ቁጣ ሲመጣ እንዲህ ነውበአራት እግሩ የሄደውን በሆዱ እየተሳበ እንዲመለስ ያደርጋል፡፡ ቀጣይ የርግማን ሰለባ ሔዋን ናት፡፡ “በፀነስሽ ጊዜ ጭንቅሽን እጅግ አበዛለሁ በጭንቅ ትወልጃለሽ ፈቃድሽም ወደ ባልሽ ይሆናል፡፡ እርሱም ገዥሽ ይሆናል” የሚል ርግማን ለሔዋን ደረሳት፡፡ለዚህ ነው ሴቶች ሲወልዱ በምጥ በልብ ጋር የሚወልዱት ከወለዱም በኋላ ፈቃዳቸው ወደ ባላቸው ይመለሳል፡፡ የመጨረሻው ርግማን ለአዳም እንዲህ ሲል መጣ “የሚስትህን ቃል ሰምተሃልና ከእርሱ እንዳትበላ ካዘዝኩህ ዛፍም በልተሃልና ምድር ከአንተ የተነሣ የተረገመች ትሁን በሕይወት ዘመንህም ሁሉ በድካም ከእርሷ ትበላለህ እሾህና አሜከላን ታበቅልብሃለች የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፡፡ ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ አፈር ነህና ወደ አፈርም ትመለሳለህና” /ዘፍ3÷1-ፍጻ/እንግዲህ የሔዋን ቸልተኝነት ያመጣው ርግማን በጣም ከባድ መሆኑን ልብ ልንል ያስፈልጋል፡፡ ይህ ቸልተኝነት የሞት ሞትን ወደ ሰው ልጅ ሁሉ ያመጣ ነው፡፡ሰነፎችንም ቸልተኛ መሆን ያጠፋቸዋልና እንዳለ ጠቢቡ ሰሎሞን አዳምና ሔዋን በቸልተኝነታቸው ጠፉ፡፡ /ምሳ1÷32/ በገነት ሦስት ዕፅዋት ነበሩ እንዳይበሉት የታዘዙት፣ እንዲበሉት የታዘዙትና ብሉም አትብሉም ያልተባሉት ማለት ነው፡፡ ብሉም አትብሉም ያልተባሉት ዕፅ ዕፀ ሕይወት ይባላል፡፡ አትብሉ የተባሉትን ዕፅ ሳይበሉ ቢጠብቁት ኖሮ ከአንድ ሽህ ዘመን በኋላ ይህን ዕፀ ሕይወት በልተው ታድሰው ወደ መንግሥተ ሰማያት ይሸጋገሩ ነበር፡፡ ነገር ግን ዕፀ በለስን ከበሉ በኋላ ያን ዕፀ ሕይወት በልተው መንግሥተ ሰማያት እንዳይገቡ እግዚአብሔር ከገነት አባረራቸው፡፡ ወደ ሕይወት የሚወስደውንም መንገድ ለመጠበቅ ኪሩቤልንና የምትገለባበጥ የነበልባል ሰይፍን በዔድን ገነት ምሥራቅ አስቀመጠ፡፡ አዳምና ሔዋን ተድላና ደስታ ከነበረባት ገነት ወጥተው ኀዘንና መከራ ወደበዛባት ምድር ወረዱ፡፡ ከእንስሳት ከአራዊት ጋር ከአጋንንትም ጋር ስትዋጋ ኑር ተብሎ ተፈረደበት፡፡ በገነት ሳለ ያከብሩት ይገዙለትም የነበሩ እንስሳት ሰባን አርደህ ብላን አልበህ ጠጣን ይሉት የነበሩት ሁሉ እንበላሃለን፣ እንወጋሃለን እያሉ ያስጨንቁት ጀመር፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር መጣላት እንዲህ ነው እንስሳት አራዊቱን ሁሉ በጠላትነት ያስነሣል፡፡ አዳምም በዚህ የተነሣ እጅግ አለቀሰ ከዋሻ ዋሻ ከዱር ዱር ተንከራተተ፡፡ ይህን የተመለከተ የእግዚአብሔር መልአክ ደብር ቅዱስ ወደሚባል ተራራ ወስዶ በዚያ አኖረው፡፡ በዚህ ቦታ ተቀምጠው እጅግ እያለቀሱ እግዚአብሔርን ለመኑ ነገር ግን ልመናቸው ቅድመ እግዚአብሔር አልደርስ አላቸውና ከእህል ከውኃ ተለይተው ለየብቻ ሁነው ባሕር ውስጥ ገብተው ለ40 ቀን ያህል ሱባኤ ገቡ፡፡ ጠላት አሁንም 35ኛውን ቀን ጨርሰው 36ኛውን ሊጀምሩ ሲሉ የእግዚአብሔርን መልአክ መስሎ መጥቶ ጸሎታችሁ ተሰምቷልና ከባሕር ውጡ አላቸው፡፡ ሔዋን አሁንም ሌላ ቸልተኝነት ተፈጠረባት፡፡ አዳም ድሮ የፍጡር ቃል ሰምቼ ተጎድቻለሁና እግዚአብሔር ውጣ ካላለኝ በቀር አልወጣም ብሎ የመጣውን ጠላት ሲያባርር እርሷ ግን እግዚአብሔር እንኳንን ይህን ያህል ቀን ቆይተን ይቅርና በ1 ቀንስ ይቅር ይለን የለምን ብላ የጠላትን ምክር አሁንም ተቀበለች፡፡ በዚህም ምክንያት ሱባኤውን አቋርጠው ወጡከገነት ያስወጣቸውን ያን የቀደመውን ጠላታቸውን ባለማዎቅ ተከተሉት፡፡ ከእግረ ገነት ሲደርሱ ገብርኤል ነኝ ያላቸው እነርሱም መስሏቸው የተከተሉት ዲያብሎስ ከእንግዲህ ወዲያ ተስፋ የላችሁም ብሎ መጥፎ ሽታውን አሸተታቸው ክፉ መልኩንም አሳያቸው፡፡ አዳምም ደንግጦ ወደቀየምይራራ ጠላት ዲያብሎስም ቤት የሚያህል ድንጋይ አንሥቶ ጫነበት፡፡አዳም በሦስተኛው ቀን ቢነሣ ሥጋው ተቆርሶ፣ ደሙ ፈስሶ፣ አጥንቱ ተከስክሶ አገኘው ፍሬ ዕፅም አምጥቶ በደሙ ለውሶ መሥዋዕት አሳረገ፡፡ እግዚአብሔርም ተስፋ ሰጠው “ከሰማየ ሰማያት ወርጄ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ በመስቀል ተሰቅዬ ሥጋዬን ቆርሴ ደሜን አፍስሼ ሞቼ ተነሥቼ ከሲዖል አወጣሃለሁ ከዲያብሎስም መከራ አድንሃለሁ” አለው፡፡እነርሱም ይህንን ተስፋ ሲጠብቁ ኖሩ፡፡ ከዚህ የምንረዳው የሔዋን ቸልተኝነት የከፋ ርግማንን በሰው ዘር ሁሉ ማምጣቱን ነው፡፡

No comments:

Post a Comment