Friday, October 20, 2017

✍✝“ሥልጣን እለቃለሁ”--ቅዱስ ፓትርያርኩ✝✍



፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
ይኼ ፌስቡክ ደግሞ ዛሬ ሰበር ዜና አድርጎ በጠዋቱ የነገረኝ  አቡነ ማትያስ “ሥልጣን እለቃለሁ” አሉ የሚለውን ነው፡፡ በእውነት ቅዱስነታቸው አቡነ ማትያስ ይህንን ተናግረውት ይሆን? ብየ ራሴን ስጠይቅ ብዙ ቆይቻለሁ፡፡ ቅዱስነታቸው “ሥልጣን እለቃለሁ” የሚሉ የሆነ አካልን አስገድደው የሆነ ሥራ ለማሠራት ፈልገው እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ በዚህ ጥቅምት ፮/ ፳፻፲ ዓ.ም ትናንት ጥቅምት ፱/ ፳፻፲ ዓ.ም በተጠናቀቀው ፴፮ኛ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባዔ ላይ በሁለት ጎራ የተከፈሉ ሀሳቦች ተስተውለዋል፡፡ ሃሳቦቹም በዋናነት ያተኮሩት ከማኅበረ ቅዱሳን የሥራ እንቅስቃሴ ላይ ነበር፡፡ የሥራ ፍሬው በጉባዔው መቅረብ አለበት እና መቅረብ የለበትም የሚሉ ጎራዎች ነበሩ፡፡ ሆኖም ግን እውነት ምንጊዜም እውነት ስለሆነች እውነቱ በጉባዔው መካከል ቀርቧል፡፡





ቅዱስነታቸው አቡነ ማትያስ ለምን እንደሆነ በማይታወቅ መልኩ የማኅበረ ቅዱሳንን መኖር አይፈልጉትም፡፡ ማኅበሩ በአሌፍ ቴሌቪዥን የጀመረውን መርኃ ግብር እንዲዘጋም በጣም ብዙ ጥረቶችን አድርገዋል፡፡ በዚህ ላይ ቀኝ እጅ ሆነው የሚሠሩት የምሥራቅ ጎጃሙ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማርቆስ እና የአዊው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቶማስ እንደሆኑም ታውቋል፡፡ በተለይ ብጹእነታቸው አቡነ ማርቆስ “የማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን እንዲዘጋ ከመንግሥት ደብዳቤ አስጽፌያለሁ” በማለት ያስፈራሩ እንደነበረ ለማንም የተገለጠ እውነት ነው፡፡ ሆኖም ግን ቤተክርስቲያኒቱ የምትመራው በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እንጅ በአንድ ፓትርያርክ ወይም በአንድ ሊቀ ጳጳስ ውሳኔ እንዳልሆነ አበው ሊቃነ ጳጳሳት በከፍተኛ ሁኔታ ተሟግተዋል፡፡ በተለይ በዚህ በተጠናቀቀው ጉባዔ ላይ “የማኅበረ ቅዱሳን ግብዓተ መሬት ይፈጸማል” ብለው ራሳቸውን አሳምነው በጉባዔው ላይ የተገኙት አንዳንድ በሙስና የተጨማለቁ አስተዳዳሪዎች እና በእምነት እና በምግባር ህጸጽ የሚጠረጠሩት በሙሉ ያለሙት ህልም ሳይሳካላቸው እንደቀረ ታውቋል፡፡ በዚያም ብለው በዚህ በሁሉም አማራጭ መንገዶች ተጠቅመው አልዘጋላቸው ያለው ማኅበረ ቅዱሳን በምእመናን ዘንድ ይበልጥ እንዲታወቅ አድርገውታል፡፡

ቅዱስነታቸው አቡነ ማትያስ “ሥልጣን እለቃለሁ” አሉ ሲባል የተረዳሁት ነገር አለ፡፡ እውነት ይህን ተናግረውት ከሆነ ስለሚከተሉት ነገሮች ይህን እንደተናገሩ ተረድቻለሁ፡፡
፩. በሙስና እና በልዩ ልዩ የምግባር እና የእምነት ችግሮች ውስጥ የተዘፈቁትን የአንዳንድ ሥራ አስኪያጆችን እና አስተዳዳሪዎችን ሙሉ ድጋፍ ለማግኘት ሲሉ ነው፡፡
፪. የራሳቸውን ጉዳይ ለማስፈጸም ሲሉ የእርሳቸውን በፓትርያርክነት መቀጠል የሚፈልጉትን የአንዳንድ ሊቃነ ጳጳሳት ድጋፍ ለማግኘት ነው፡፡
፫. ፕትርክናው አቡነ ማትያስ ተወልደው ካደጉበት ብሔር እንዳይወጣ በእግዚአብሔር አሠራር ላይ ገብተው የሚፈተፍቱትን የብሔርተኞችን ድጋፍ ለማግኘት ነው፡፡
፬. በመጨረሻም እርሳቸው እንዲቀጥሉ የሚፈልግ ከሆነ የመንግሥትን ድጋፍ ለማግኘት ነው፡፡
በዚህ መልኩ ድጋፋቸውን ካሰባሰቡ በኋላ “ማኅበረ ቅዱሳንን የማጥፋቱ ሥራ” የጋራ ይሆናል ማለት ነው፡፡ “ሥልጣኔን እለቃለሁ” በሚል ብሒል ብቻቸውን ይታገሉት የነበረውን ማኅበር በርካታ ታጋዮችን የማሰባሰብ ሥራ ይሠራሉ ማለት ነው፡፡ በነገራችን ላይ ማኅበረ ቅዱሳን እኛ ፍረስ ስላልነው አይፈርስም አትፍረስ ስላልነውም ሳይፈርስ አይቀርም በቃ ይህ እውነት ነው፡፡ እግዚአብሔር ለሥራ ያስነሣው የዘመናችን ሙሴ ነው ማኅበረ ቅዱሳን ማለት፡፡ ስለዚህም ሙሴ በእግዚአብሔር መወሰዱ አይቀርም አምላክ ሙሴን ከመውሰዱ በፊት ግን ሙሴ ከአምላክ የተሰጠውን ተልእኮ መፈጸሙ አይቀርም ግድ ነው፡፡ ባሕረ ኤርትራን በበትሩ ከፍሎ እስራኤላውያንን አሻግሮ ሙሴ ይወሰዳል ተልእኮውን ፈጽሟልና የሙሴ መኖርም ሆነ አለመኖር ለእስራኤላውያን ምንም ለውጥ እንደማያመጣ እግዚአብሔር ሁሉን ያውቃል፡፡  ይህ ማኅበርም መኖሩ ካልጠቀመ አይኖርም መኖሩ ከጠቀመ ደግሞ ሽህ ዘመናትን ይኖራል፡፡

በነገራችን ላይ “ፕትርክና” እለቀዋለሁ እያሉ የሚያንገራግሩበት ሥልጣን ሳይሆን አደራ ነው፡፡ በርግጥ “ይደልዎ! ይደልዎ! ይደልዎ!” ሳይባል ዕጣ ሳይጣጣል የተሰጠን አደራ ከሥጣን እኩል ቆጥረውት “ሥላጣኔን እለቃለሁ” ቢሉ አይገርመንም፡፡ ይህ አደራ እስከሞት ድረስ ስለእውነት የሚሠሩበት እንጅ “አልቀዋለሁ” እያሉ የሚያንገራግሩበት እና የሚያስፈራሩበት እንዳልሆነ ነው እኔ የሚገባኝ፡፡ “ለመጀመሪያ ጊዜ ሥልጣናቸውን በራሳቸው ፈቃድ የለቀቁ ፓትርያርክ” መባልን ሽተው ከሆነ እናዝናለን፡፡ “አደራቸውን የተወጡት ፓትርያርክ” መባል በተሻለ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ ከራሷ ልጆች መሾም ከጀመረችበት ጊዜ ጀምሮ በተከታታይ የተሾሙት ሁለቱ ፓትርያርኮች አቡነ ባስልዮስ እና አቡነ ቴዎፍሎስ ናቸው በህጉ እና በሥርዓቱ መሠረት የተሾሙት ከዚያ በኋላ ያለው ግን የህግ እና የሥርዓ ጥሰት የተፈጸመበት ነው፡፡ ደጉ መናኝ መነኩሴ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሦስተኛ ፓትርያርክ ሆነው ሲሾሙ እኮ አቡነ ቴዎፍሎስ እስር ቤት ነበሩ፡፡ “ፓትርያርክ ሳይሞት ሌላ ፓትርያርክ አይተካ” የሚለው ህግ የተጣሰ ያንጊዜ ነበር፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የፕትርክናቸውን ተልእኮ እና አደራ በአግባቡ የተወጡ ቅዱስ አባት ቢሆኑም በወቅቱ በነበረው አገዛዝ ተጽእኖ ህጉን ሽረው ነው ወደ ፕትርክናው ያመጧቸው፡፡ ዐራተኛ የተሾሙት አቡነ መርቆርዮስ እስካሁን ድረስ በሕይወት እያሉ በአገራችን ሁለት ፓትርያርኮች ተሸመዋል (አቡነ ጳውሎስ እና አቡነ ማትያስ)፡፡ አንድ ፓትርያርክ በሕይወት እያለ ሌላ ፓትርያርክ ሲሾም እየተመለከትን ባለንበት በዚህ ከባድ ዘመን “ሥልጣኔን እለቃለሁ” ብሎ ሌላ አዲስ ነገር በሀገራችን ላይ ማምጣቱ ለእኔ በጣም ያሳዝነኛል፡፡ እሁድ በጸሎት የሚጀመረው የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ሁሉን ነገር በጥንቃቄ ዓይቶ የራሱን ውሳኔ እንደሚያሳርፍ ተስፋ እናደርጋለን፡፡ “ሥልጣኔን እለቃለሁ” ብለው ለቅዱስ ሲኖዶስ ካቀረቡ እንኳ በሥርዓቱ መሠረት ተወግዘው ተለይተው ሌላ አባት “ይደልዎ፣ ይደልዎ፣ ይደልዎ” ብለው በመንበሩ ላይ ይተካሉ፡፡ ቅድሚያ የሚሰጠው ለቤተክርስቲያኒቱ እንጅ ለግለሰቦች ምቾት አይደለም፡፡ እውነታቸውን ሆኖ “እለቃለሁ” በሚለው ሃሳባቸው ከጸኑ ግን ለቤተክርስቲያናችን ደህንነት ሲባል ቢለቁ በእኔ በኩል ደስታየ ወሰን የለውም፡፡

የዘንድሮው የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ከባድ ውሳኔዎችን እንደሚያሳርፍ ይጠበቃል፡፡ አሁን ላይ በቤተክርስቲያኒቱ ላይ እየተፈጸመ ስላለው ጉዳይ በጥልቀት ይመረምራል ብለንም ተስፋ እናደርጋለን፡፡
፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍
© መልካሙ በየነ
ጥቅምት ፲ / ፳፻፲ ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍

No comments:

Post a Comment